” ስንቃችንን በአህያ፣ አመላችንን በጉያ” ይላል የአገሬ ምሳሌያዊ አነጋገር ፤ አዎ ይህ መሰሉ ምሳሌያዊ አነጋገር ብዙ መልዕክቶችን በአንድ ጊዜ ለማስተላለፍ አቅም ያለው ነው። በተለይም አሁን አገራችን እንዲህ ባለው “በልቶ ካጅ” የእናት ጡት ነካሽ” በሆነ እብሪተኛ ስትፈተን ልኩን አሳይቶ ወደመጣበት ለመመለስ ብሎም ዳግም አንገቱን ቀና አድርጎ ጦርነት ማሰብ አይደለም ፤ የበደላቸውን ህዝቦች ማየት እንዳይችል አድርጎ ለመቅጣት ሁለም በአንድ ልብ አሳቢ በአንድ መካሪ ይሆን ዘንድ አመሉን በጉያ ስንቁን በአህያ መጫኑ ግድ ይለዋል።
ቀደምት አባቶቻችንም በውጭ ጠላት ሲፈተኑ ያን ጊዜ ምንም እንኳን በመካከላቸው ብዙ የሚያለያዩዋቸው ጉዳዮች የነበሩ ቢሆንም፤ ህብረታቸውን ለማሳየት ግን አመላቸውን ወይም የውስጥ ችግራቸውን በጉያቸው ይዘው ምንም እንዳልተፈጠረ በመካከላቸው ምንም ልዩነት እንደሌለ ሆነው በአንድነት በመነሳት እስክ አፍንጫው ዘመናዊ የጦር መሳሪያን ታጥቆ የመጣን ጠላት ድባቅ መተው ነጻነታቸውን ያረጋገጡት።
ዛሬስ አገራችን ቀና ልትል ለልጆቿ ዋልታ መከታ ልትሆን፤ በቀን አንድ ጊዜ መብላት ያቃተውን ዜጋዋን በቀን ሁለት እና ሶስት ጊዜ ከዛ በላይ እንዲበላ ልታደርግ ጫፍ ስትደርስ የውስጥ ባንዳ የእናት ጡት ነካሾች ውጪ ካሉ ምቀኛ የኢትዮጵያ ጠላት ጋር እጅና ጓንት ሆነው ሊያጠፏት ሊያፈራርሷት ዳር ዳር እያሉ ነው። በዚህ ጊዜ ኢትዮጵያ ከእኛ ከልጆቿ ምን ትጠብቃለች? ከተባለ እኔ በበኩሌ አገራችን ከእኛ የምትጠብቀው አመላችንን ወይም ችግራችንን በጉያችን ይዘን አንድ ሆነን አለምን ጉድ ማሰኘትን ነው። የጠገበን ጥጋቡን ማብረድ እኩይ ተግባሩን አምክኖ እንደገና አገራችን ቀና ብላ የምስራቅ አፍሪካ ተምሳሌት እንድትሆን ማስቻል ነው።
አገር እንዲህ በጭንቅ ወቅት ህልውናዋን ለመፈታተን ከውስጥም ከውጭም ተደራጅቶ እኩይ ኃይል ሲነሳባት፣ የሚያሻግራት ጥበበኛ አርበኛን ትፈልጋለች። አባቶቻችን ለዘመናት ከውስጥም ከውጭም ጠላት ሲነሳባቸው አንድ ሆነው በመመከት፣ ይህችን የመሰለች ታላቅ አገር አስረክበውናል። እኛ ደግሞ በብዙ መስዋትነት የተረከብናትን አገራችንን ለማስቀጠል አንድ ሆነን ጠላት ላይ መዝመት አለብን። አባቶቻችን አገራቸውን አስከብረው ለመቆየት ከርስታቸው ተፈናቅለዋል፤ ቤተሰባቸውን በትነዋል ፤ ተርበዋል፣ ተጠምተዋል፣ ከምንም በላይ ትልቁን ውድ ሕይወታቸውን ገብረዋል። ዛሬ እኛም የአባት የእናቶቻችንን ውለታ ሳንረሳ የአገርን አንድነት ጠብቆ ለቀጣይ ትውልድ ለማሻገር የህሊና ቃል ኪዳን መግባት ብሎም ልዩነትን ወደጎን ጥሎ በአንድ ልብ መነሳት ያስፈልጋል።
ምናልባት ይህ አንድነት ሁሉም ወደጦር ግንባር ስለሄደ ብቻ የሚገለጽ ወይም አገራችንን የምናድንበት መንገድ አይደለም፤ ወደጦር ግንባር ለመሄድ አቅም፤ ጤንነት እንዲሁም እድሜው የሚፈቅድለት ሄዶ ለአገሩ ደጀን ዋልታ እና ማገር ይሆናል፤ መሆንም አለበት ። ሌላው ደግሞ እኔ ከዚህ ነኝ እናንተ ከዛ የሚለውን ትተን አንድ ሆኖ በተሰማራበት መስክ ቀን ከሌሊት ሰርቶ ደክሞ ኢኮኖሚዋን በመደገፍ ይለምኑናል፤ ሲርባቸው ለትዛዛችን ይንበረከካሉ፤ ብለው ዳር ቆመው የረሃብ የችግር ጊዜያችንን በጉጉት የሚጠባበቁትን ምዕራባውያን ማሳፈርም እኛ እንዲህ ነን ሰርተን ለፍተን ጥረን ግረን ችግርን እናልፋለን አንራብም አንጠማም ማለት መቻል በራሱ ትልቅ አርበኝነት ነው።
” አገሬን ለማዳን መቼም߹ የትም߹ በምንም እዘምታለሁ” የተባለውም ከዚህ አንጻር ነው። መቼም የትም በምንም ሁኔታ ብንሆን ለአገራችን ቅድሚያ ሰጥተን በተሰማራንበት መስክ ሁሉ ታማኝ ሆነን ቀድሞ ከምንሰራበት ጊዜ ጨምረን ሰርተን ይህንን የጭንቅ ጊዜ አመላችንን በጉያችን አድርገን በአንድነት ልናልፈው የግድ ነው። ይህ ካልሆነ ግን የተመኙልንን መቸገር፣ ማዘን፣ መራብና መሞት እንዲሁም መበታተን አይቀሬው እጣ ፋንታችን ይሆናል።
ሕወሓት አገር የማስተዳደር ዕድሉን ባገኘባቸው 27 ዓመታት አገርንና ህዝብ የተለያዩ እንዲሆኑ߹ አንዱ የአንዱ ጠላት እንጂ ወንድም መሆኑን እንዲረሳ ከፍተኛ ስራን ሰርቷል። እውነት ለመናገር ይህ እኩይ ተግባሩ ከፍተኛ የሆነ ውጤት አምጥቶለት ነበር። ብሔር ብሔረሰቦች ኢትዮጵያ የምትባለውን አገር ረስተውና በብሔራቸው ውስጥ ተወትፈው እሱኑ ሲያስቡ ከእነሱ ብሔር ውጪ ያለው ህዝብ በሙሉ ጠላታቸው ሲመስላቸው ኖረዋል።
የፈጣሪ ጥበቃ ታክሎበት ግን አገራችን ጁንታው ባሰበው ልክ ሳትፈራርስ እኛም እርስ በእርሳችን ሳንበላላ እዚህ ደርሰን ነበር ነገር ግን ” ያዳቆነ ሰይጣን…..” እንዲሉ ይህ በዛ ሁሉ አመት ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን ላይ የተሰራ ደባ በሚፈልጉት ልክ አልመጣ ሲላቸው ክህደታቸውን በአደባባይ ለማሳየት ተገደዱ ። ክህደታቸው ደግሞ አገር ወደማትፈልገውና እቅዷም ወዳልሆነ ጦርነት ውስጥ እንድትገባ አስገደዳት።
እንግዲህ እውነቱ ይህ ነው፤ ታዲያ ወገን እነዚህን መሰሪዎች ውሸታምና የአገር ጠላቶች ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ከህይወታችን ለማስወጣት አንድ ሆነን መንቀሳቀስ አይበጅም ትላላችሁ? እንደ ሕወሓት ዓይነት የእናት ጡት ነካሽ በሥልጣን ዘመኑ አገር ላይ እንዳሻው ፎልሏል። ዴሞክራሲን ጢባጥቤ ተጫውቶበታል። አገሪቱን የንግድና የፖለቲካ ሥርዓት በኔትወርክ ተቆጣጥሮ ነግዶበታል። ከዚህ ሁሉ ድራማ በኋላም ስልጣኔን ተቀማሁ በሚል ሰበብ መቀሌ መሽጎ ከሁለት ዓመት በላይ ተሰብስቦ ይህችን ቀን ለማምጣት እናት አገሩን ጭንቅ ውስጥ ለማስገባት ዶልቷል። ግን በለኮሰው እሳት ተለብልቦ አይሆኑ መሆንን የሆነ ያለው ወደፊትም የሚሆነው እራሱ ሆነ።
ከሰላም ይልቅ ጦርነትን ምርጫው ያደረገው የጁንታ ስብስብ እስካሁን የፈጸመው በደል አልበቃ ብሎት በትግራይና በትግራይ አጎራባች በሆኑ በአማራ፣ በአፋርና በኤርትራ ሕዝቦች ላይም ጦርነት አውጇል። ምንም የማያውቁ ዕድሜያቸው ለጦርነት ያልደረሱ ሕፃናትን እየወሰደ እየማገደና እያስፈጃቸው ይገኛል። ይህንን ዓለም አቀፍ ወንጀል እንኳን እየፈጸመ ዓለም ዝም ማለቱ ሲታይ፣ ኢትዮጵያን ለማፍረስ የሴራው ማጠንጠኛ ክር ሕወሓት መሆኑን ያመላክታል።
የሕወሓት የሽብር ቡድን በሰው ደምና ሥቃይ ካልኖርኩ የሚል የክፋት ጥግ ማሳያ የአውሬ ስብስብ ነው። በትግራይና በአጎራባች በሚኖረው ማኅበረሰብ ላይ ያደረሰው ሥቃይ እንዲህ በቀላሉ የሚነገር አለመሆኑን በርካታ መረጃዎች እያመላከቱም ነው። በዘር እየለየ በአሰቃቂ ሁኔታ ረሽኗል። እየረሸነም ይገኛል። በርካቶችን የጦርነት ሰለባ አድርጓቸዋል። ረሃቡና ሰብዓዊ ቀውሱም በተለይ በትግራይ ህዝብ ላይ ተባብሶ እንዲቀጥል ሆኗል።
አሁን ላይ የእናት ጡት ነካሹን ጁንታ ጨምሮ እኛ በእሳት ስንለበለብ ቁጭ ብለው ለመሞቅ እየቋመጡ ያሉ ምዕራባውያንን አፍ ለማስያዝ ብሎም እቅዳቸው መቼም ቢሆን ግቡን እንደማይመታ ለማሳየት ከምን ጊዜውም በላይ አንድ እንሁን እንደተባለው እንደ አባት እናቶቻችን “ስንቃችንን በአህያ አመላችንን በጉያችን” አድርገን ለአገራችን ታሪክ የማይረሳን አርበኞች ሆነን እንለፍ። ሰላም!
በእምነት
አዲስ ዘመን ነሐሴ 9 ቀን 2013 ዓ.ም