ከአዲስ አበባ ጎዳናዎች ተጠቃሽ በመሆን በርካታ ዓመታትን አስቆጥሯል:: ዛሬ በርካታ ውብ ጎዳናዎች በከተማዋ ሞልተዋል:: እሱ ግን ተጠቃሽ ጎዳና ሆኖ ቆይቷል:: ከከተማዋ እምብርት አዲስ አበባ ማዘጋጃ ቤት ለገሀር ድረስ ቀጥ ብሎ ሲታይ ረጅም ምን ቢሉት እንደሚሻል እንጃ:: በከተማዋ ውብ ጎዳናዎች በብዛት ባልነበሩበት ወቅት በምርጥ ጎዳናነት የሚደርስበት አልነበረም ማለት ይቻላል:: ቸርችል ጎዳና::
ቦሌ፣ ሀይሌ ገብረስላሴ፣ ወዘተ…ጎዳናዎች ግራና ቀኝ ግዙፍ የሆኑ ህንጻዎች ተገጥግጠውባቸው በውበት ላይ ውበት ቢጎናፀፉም፣ አንጋፋው ቸርችል ጎዳና ግን ይህን ወግ ሣያይ ዓመታትን ተሸጋግሯል:: ይህ ገጽታው ከቅርብ ጊዜ ወዲህ መቀየር በመጀመሩ ከፒያሳ እስከ ቴዎድሮስ አደባባይ ባለው የመንገዱ ግራና ቀኝ ግዙፍና ውብ ህንጻዎች መታየት ጀምረዋል::
ጎዳናው ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ ባለሰፊ የእግረኛ መንገድ እንዲሆን የሚያስችል ግዙፍ ፕሮጀክት ከመስቀል አደባባይ እስከ ፒያሣ እየተካሄደበት ይገኛል:: የእግረኛ መንገዱ ግንባታ በተለይ ቸርችልን ድምቀት በሚያላብስ መልኩ እየተሰራ ነው:: የተንጣለለ ተደርጎ እየተገነባ ያለው ይህ የእግረኛ መንገድ፤ ማየት ለተሳናቸውም፣ ብስክሌት ለሚጋልቡም እንዲመቺ ተደርጎ ነው ግንባታው እየተካሄደ ያለው::
በዚህ አካባቢ ለተሸከርካሪ ማቆሚያ የሚሆን ሥፍራ ግንባታ የሚኖር አይመስለኝም:: ባለህንጻዎቹ በየምድር ቤቶቻቸው መኪናዎችን እንዲያቆሙ ሳይታሰብ አልቀረም ወይም ሌላ የፓርኪንግ ቦታ ይዘጋጅ ይሆናል:: በቀጣይ በቦሌ መንገድ እንደሚሰራበት በዚህ ጎዳና ግራና ቀኝ መኪና አቁሞ መሄድ የሚቻል አይመስለኝም:: ከመኪና መንገድ ውጪ ያለው ቦታ በሙሉ ለእግረኞች መንገድ፣ ለዛፎችና አበቦች ምቹ እንዲሆን ተደርጎ ግንባታ እየተካሄደበት ነው:: ለብስክሌት ጋላቢዎችም የሆነ ነገር ያለ ይመስለኛል፡፡ ወደ ጥቁር አንበሣ በሚወስደው መንገድ ፒያሳ ጫፍ ላይ ብቻ ለታክሲ ተራ የሚሆን ስፍራ የተተወ መሰለኝ::
መንገዱ እግረኛንም ታሳቢ ያደረገ አዲስ የመንገድ መብራት እየተዘረጋለት ነው:: ለአበቦች በተዘጋጀው ስፍራ ላይ በሙሉ አበቦች እየተተከሉ ይገኛሉ:: ለዛፎች በተዘጋጁ ቦታዎች ላይም እንዲሁ ዛፎች እየተተከሉ ናቸው:: የዛፍ ችግኝ እየተተከለ ነው የሚያሰኝ ሁኔታ ስላልተመለከትኩ ነው ዛፎች እየተተከሉ ነው ማለቴ:: በወዳጅነት አደባባይ እንደተደረገው ሁሉ በዚህ መንገድ ዳርቻም የወይራ ዛፎች ከሌላ ቦታ ተነቅለው ተተክለዋል:: በቤተክርስቲያን አጽድ ብቻ የሚታየው የወይራ ዛፍ በዚህ ስፍራ መተከሉ ለሀገር በቀል የዛፍ ዝርያ የተሰጠውን ትኩረትም ያሳያል:: በቀጣይም ሌሎች ሀገር በቀል የዛፍ ዝርያዎችን በመትከል የሀገር በቀል ዛፎች ማሳያ ማድረግ የሚቻል ይመስለኛል::
ሌሎች የውጪ ዝርያ ያላቸው ውብ ዛፎችም እንዲሁ ተተክለዋል:: እነዚህ ዛፎች ፈጣን በመሆናቸውም ጎዳናውን በአረንጓዴ ለማጀብ የሚደርስባቸው የሚኖር አይመስለኝም:: በቅርብ ጊዜም አረንጓዴ የእግረኛ መንገድ ባለቤት ያደርገናል:: የእነዚህ ዛፎች ዝርያዎችም እንዲሁ ፋይዳቸው ብዙ ስለሆነ በስፋት ቢተከሉ መልካም ነው:: በፕሮጀክቱ በአንዳንድ አካባቢዎች የፍራፍሬ ችግኞች ተተከለውም ተመልክቻለሁ::
መንገዱ ሲሰራ በወሰን ማስከበር በኩል የታየው አሰራር ለሌሎችም በምሳሌት ሊወሰድ ይገባል:: በከተማዋ ካለው የወሰን ማስከበር ችግር አኳያ ሲታይ በቀላሉ አጥራቸውን ያነሳሉ ተብለው የማይጠበቁት መንግስታዊ ተቋማት አጥራቸውን አፍርሰው ከግቢያቸው የተወሰነውን መልቀቃቸው ለፕሮጀክቱ ያላቸውን ትልቅ ግምት ያመለክታል:: ድርጊታቸው ሊያስመሰግናቸውም ይገባል:: መከላከያ፣ ኢቲቪ፣ ኢትዮ ቴሌኮም፣ ጥቁር አንበሣ ትምህርት ቤትና ሌሎችም ለእዚህ የልማት ሥራ ላሳዩት ፈጣን ትብብር በርግጥም መመስገን ይኖርባቸዋል:: ርምጃቸው በአርአያነት ሊወሰድም የሚገባው ነው::
ከእነዚህ ተቋማት አንዳንዶቹ ከፍተኛ ጥበቃ የሚደረግላቸው መሆናቸው ይታወቃል:: ግንብ አጥር፣ የሴኩሪቲ አጥር በሽቦ፣ ትላልቅ ኮንክሪቶች፣ ጭምር ያላቸው ነበሩ:: አጥራቸውን ያፈረሱበት ፍጥነት ግን በጣሙን ይገርማል:: ጊዜያዊ አጥር 0አደረጉ፤ አፈረሱ:: አንዳንዶቹ ወዲያው አዲስ አጥረዋል፤ አንዳንዶቹ አጥር የሌላቸው መሆናቸው አላሳሰባቸውም፤ ልክ ናቸው፤ ቤትንም ግቢንም የሚጠብቀው ህግና ህግ ነዋ::
የፈረንሳዮቹ ሊሴ ገብረማርያም ትምህርት ቤት ወሰን ማስከበር ላይ ትንሽ የዘገየ መሰለኝ፤ እሱም ቢሆን ኤምባሲዎችና የመሳሰሉት የፈለገውን ያህል የልማት ነገር ቢመጣ እንዲህ ያለውን ጥያቄ ሲያብላሉት ስለሚቆዩ አይፈረድበትም:: ጊዜ ወስደው ከመንግስታቸው ጋር ጭምር ይመክሩበታል:: ዘግይቶም ቢሆን ለልማቱ ሲል አጥሩን አፍርሶ ወደ ውስጥ ገብቷል::
ከወሰን ማስከበር ጋር ተያይዞ ፕሮጀክቶች በእጅጉ በሚጓተቱባት ሀገራችን በቸርችል ጎዳና የእግረኛ መንገድ ግንባታ እውን ለማድረግ የከተማ አስተዳደሩ የታየበት ቁርጠኝነትና በተቋማት በኩል የታየው ትብብር በተሞክሮነት ተቀምሮ ሊቀመጥና ሌሎች ፕሮጀክቶችም ሊማሩበት የሚገባ ነው::
የመንገድ ግንባታው የአንዳንድ ህንጻዎችን የመጀመሪያ ወለል ጭምር የወሰደ አዲስ አሰራር ሆኖም አግኝቼዋለሁ:: ጥቁር አንበሳ ትምህርት ቤት ፊት ለፊት ያሉት ነባር ህንጻዎች የተወሰነ አካላቸው የእግረኛ መንገድ በሚገነባበት ስፍራ ላይ ያለ ነው:: ለዚህ ስራ ህንጻ ማፍረስ አላስፈለገም:: ለሚገነባው የእግረኛ መንገድ አዲስ ዘዴ ተቀይሷል:: በህንጻው መጀመሪያ ወለል ያሉ ሱቆች የተወሰነ ሜትር የሚሆን ወደ ውስጥ እንዲገቡ ነው የተደረገው:: እግረኛው በጥላ ስር ይጓዛል ማለት ነው:: በቀደመው አካሄድ እነዚህ ህንጻዎች ወይ ይፈርሳሉ፤ አሊያም የእግረኛው መንገድ እስካሁን ባለው መልኩ ይቀጥል ነበር:: ግሩም ልምድ ነው የተገኘው::
እነዚህ ህንጻዎች ብቻ አይደሉም የታችኛውን ወለላቸውን የተወሰነ ክፍል ለእግረኛ መንገድ የለቀቁት:: ዋናው ፓስታ ቤት አጠገብ ያለው ትልቁ የትራንስፓርት ሚኒስቴር ህንጻም የታችኛውን ወለሉን አብዛኛውን ክፍል ለዚሁ ስራ እንዲለቅ ተደርጓል:: የእግረኛ መንገዱም ከህንጻው ወለል ጋር ተገናኝቶ እግረኞች እየተጓዙበት ይገኛል::
ትልቅ የአሰራር ለውጥ ነው የታየው:: ጎበዝ ይኼኔ ነው የእግር ጉዞ ማድረግ:: የተንጣለለ የእግረኛ መንገድ ካለ ስፖርትስ ቢሰራ::
አንድ ሁለት አስተያየት ግን አለኝ:: የእግረኛ መንገድ ግንባታው ከበጣም ጥሩም በላይ ጥሩ ነው:: በዋናው መንገድ ላይ ግን አንድ ነገር እንዲሰራ እጠቁማለሁ:: ከፒያሳ አንስቶ እስከ ጥቁር አንበሣ ትምህርት ቤት ድረስ ያለው መንገድ /ወደ ታች የሚወርደው/ የፍጥነት መቆጣጠሪያ ቢደረግበት መልካም ነው:: እስከ ዛሬም አለመኖሩ የሚገርም ነው:: ቴዎድሮስ አደባባይ እና አጠገቡ ካለው ገደለማ ስፍራ ውስጥ ብዙ ጊዜ መኪኖች ሲገቡ የሚታየውም ከላይ መቆጣጠሪያ ባለመኖሩ ይመስለኛል:: የፍጥነት መከላከያ ይህን ችግር በተወሰነ መልኩም ቢሆን ሊያስቀረው ይችላል የሚል እምነት አለኝ:: አሁን ደግሞ በጎዳናው እግረኞች በብዛት እንዲያዘወትሩት የሚፈለግ እንደመሆኑ ለእግረኞች ደህንነት ሲባል ይህን ማድረግ ጊዜ ሊሰጠው የሚገባ ጉዳይ አይደለም::
ሌላ አንድ ነገር ደግሞ እንደሚደረግ እጠብቃለሁ:: ለሁሉም ተጓዦች የሚመቹ ሌሎች አገልግሎቶች ሊኖሩት እንደሚችሉም ከወዲሁ መገመት ይቻላል:: ለደከማቸው አረፍ የሚሉባቸው ውብ መቀመጫዎች፣ ለጠማው ምግብ ለሚያስፈልገውም ፋስት ፉድ ሊኖሩት የሚችሉት ውብ ግንባታ እጠብቃለሁ::
በአጠቃላይ ጎዳናውን ለመቀየር የተሄደበት ርቀት የከተማ አስተዳደሩን በእጅጉ ሊያስመሰግነው ይገባል ሳልል አላልፍም:: በዚህ መንገድ ሁሌም የምመላለስበት በመሆኑ አጠቃላይ የስራው ሂደትም አድናቆት ሊቸረው ይገባል:: ለምረቃው ደግሞ ያብቃን::
ኃይሉ ሣህለድንግል
አዲስ ዘመን ሚያዚያ 30/2013