ወታደራዊው አገዛዝ ወድቆ «ለሠፊው ሕዝብ ጥቅም» ሥልጣኑን ተቆጣጠርኩ ያለው ኢህአዴግ ሥልጣኑን እንደያዘ በአዲስ አበባ አንዳንድ ርምጃ መውሰድ ሲጀመር የደርግ ዋንኛ መሣሪያ ያለውን ቀበሌዎችን ተቆጣጠረ።
በዚህ ሳያበቃም መልካም ስምና ዝና የነበራቸውን ለኅብረተሰቡ የፍጆታ ዕቃ ያቀርቡ የነበሩትን ነዋሪዎች በዝቀተኛ ክፍያ የመዝናኛና የመሳሰሉትን አገልግሎቶች ያገኙባቸው የነበሩትን የቀበሌ የኅብረት ሱቆችን የጎሪጥ ማየት ጀመረ። በዚህም ሳያበቃ ካሉበት ቦታ እያነሳ በየስርቻው ጣላቸው፤ ይዞታቸውን ለባለሀብቶች በሊዝ አዞረው።
በቀበሌ ሱቆች ላይ መጀመሪያ ርምጃ የተወሰደው ነፃ ገበያ ሥርዓት እንከተላለን በሚል ይመስለኛል፤ መንግሥት ከዚያ ደግሞ አቋሙን ቀየረ። አንዴ መዝጋት ሌላ ጊዜ መክፈት የዚያ መንግሥት መለያ ነበር፤ የሆኑ ግለሰቦችና ቡድኖችን ለመጠቅም ሲባል አሠራር ሲዘጋ ሲከፈት ነው የኖረው።
የቀበሌዎች የኅብረት ሱቅ ሲዘጋ የኑሮ ውድነት ተወለደ ብቻ ሳይሆን ተወደደ፤ ለሕዝቡ ወይስ በሕዝቡ ብላችሁ እንዳትጠይቁኝ ብቻ። ቀስ በቀስ እያደገ እየተመነደገ ጣራ ነካ ብቻ ሳይሆን ሰማይ ሊነካ የሚችልበት ወቅት የደረሰ ይመስለኛል።
ኑሮ ውድነቱ ወደ ላይ ተመነጠቀ፤ ነዋሪው ደግሞ ወደ ድህነት አዘቅትና ቁልቁለት ጠለቀ። አገሪቱ ባለሁለት አሀዝ ዕድገት አስመዝገበች ሲባልልን የነበረው ለዚህ ነው እንዴ? እንላለን አንዳንዴ።
የመንግሥትን ጣልቃ ገብነት የሚፈልጉ አቅርቦቶች እንደሚያስፈልጉ ሲታመን መልሶ ያቀናቸው ገባ። ህብረት ሱቆቹን ሌላ የዳቦ ስም ሰጥቶ የሸማቾች ማህበር እያለ ተመልሰው እንዲደራጁ ተደረገ። የቀበሌ ነዋሪዎች አክሲዮን እንዲገዙ ጭምር እየተደረገ ነው እንደገና እንዲደራጁ የተደረገው።
የእኔ ነገር ስለ ተነጣፊ ሱቆች አወራለሁ ብዬ ስዘባርቅ ስለ ኑሮውድነት አወጋዋችሁ፤ በእኔ አመለካከት ሱቆች በሦስት ይከፈላሉ። ይህን ስል ግን ጥቃቅንና አነስተኛ ሱቆችን መሆኑ ይታወቅልኝ። ተለጣፊ ሱቆች፣ ተነጣፊ ሱቆች እና ሱቅ በደረቴዎች ናቸው። በወታደራዊው ዘመን አዲስ ከተማ፣ በአራዳ፣ በልደታ፣ በቂርቆስ በመሳሰሉ አካባቢዎች በየፎቁና ግንብ ሥር ተለጣፊ ሱቆች ነበሩ፤ ልማታዊው ነኝ ይል የነበረው ያ መንግሥት አዲስ አበባን አድሳለሁ፤ አለማለሁ የሚል ቅን ሃሳብ መጣለት፤ አንዳንዶች ግን ቅንቅን ሃሳብ መጣለት እንደሚሉት ሳይዘነጋ ነው ታዲያ። ተለጣፊ ሱቆቹ ሕገወጥ በሚል እንዲፈርሱ ተደረገ።
ሱቆቹ በሌላም በኩል አይገብሩም፤ የከተማውን ፕላንም ያበላሻሉ በሚል ነበር እንዲፈርሱ የተደረገው። ከእነዚህ ሱቆች የተወሰኑት ወደ ኮልፌ አካባቢ እንዲዛወሩ መደረጋቸውን ግን አስታውሳለሁ። ከዓመታት በኋላ ደግሞ ከላይ እንደጠቀስኩት መንግሥት ጥቃቅን እና አነስተኛ አምራቾችና ነጋዴዎችን አበረታታለሁ የሚል ቅን ሀሳብ መጣለት።
በወቅቱ የከተማዋ ከንቲባ አርከበ እቁባይ አስተዳደር በከተማዋ በርካታ ቦታዎች ቀደም ሲል የተነሱት ተለጣፊ ሱቆች ድጋሚ እንዲለጠፉ ተደረገ። እነዚህ ሱቆች ‹‹አርከበ›› በሚል አሁንም ድረስ ይጠራሉ። ሱቆቹ በመላ አዲስ አበባ የተለያዩ ቦታዎች ተገንብተዋል።
ለብዙዎች የዕለት እንጀራ ከፍተዋል፤ በርካታ ነዋሪዎች ወደ ንግዱ ዓለም ገብተዋል፤ አንዳንዶች ደግሞ እያከራዩ ተጠቅመዋል። በሱቆቹ ራሳቸው ነግደው ወይም ተከራይተው ነግደው ትልቅ ቦታ የደረሱ ነዋሪዎችን አውቃለሁ። መጀመሪያ ላይ በዚያች ከሬሳ ሳጥን ብዙም በማትሰፋ ሳጥን ነገር ምን ይሰራል፤ ይሄ መንግሥት ምን እያደረገ ነው ያላለ አልነበረም። ግን ተሰራባቸው፤ ዋናው ግንባር ቦታ ላይ መሆናቸው ሆነ፤ ዋናው ልባምነት ሆነ፤ ዛሬም በሚገባ እየተሰራባቸው ነው። ተመሳሳይ ሱቆቹ በየጊዜው እየተገነቡ ይገኛሉ።
በመጀመሪያ የተሰሩት አርከበዎች በከተማ መሀል ሆነው ጽዳት በሚጎልባቸው፣ የመንግሥት መስሪያ ቤቶችን አጥር ተገን ተደርገው ነበር። እውነት ለመናገር ከሆነ አካባቢው እንዲጸዳም አስችለዋል። ክፋታቸው መንገድ ማጥበባቸው ላይ ብቻ ነው። ሱቋ በጣም ጠባብ ስለሆነች ንግዱ የሚካሄደው መንገዱ ላይ ነው።
አርከበዎች ለብዙዎች የሥራ ዕድል ቢፈጥሩም ሌሎች የሥራ ዕድል የሚፈጠርላቸው መፈጠራቸው ቀጠለ። መርካቶን ጨምሮ በዋና ዋና አደባባዮች፣ በየገበያው ሥፍራ ተባራሪ ነጋዴዎች በረከቱ፤ እነዚህ ነጋዴዎች ሲመቻቸው አስፋልት ዳር እግረኛ መንገድ ላይ ዕቃቸውን በላስቲክ ይዘው አንጥፈው ይሸጣሉ።
ፖሊሶች ሲመጡባቸው ሸቀጣቸውን አንጥፈው የሚሸጡበትን ላስቲክ ጠቅልለው ዞር ይላሉ። የዛሬዎቹ ደንብ አስከባሪዎች ያኔ አልነበሩም። የሆነ ይህን ሕገወጥ ንግድ የሚቀጣጠር አካል ነበር። በእዚህ አካል እንግልት ይደርስባቸው እንደነበር ግን አስታውሳለሁ።
ተነጣፊ ሱቆች መብዛታቸው መንግሥትን ቆም ብሎ እንዲያስብ አደረገው። አንዳንድ የኢኮኖሚ ባለሙያዎች የጎዳና ንግድ የመደበኛ ንግድ መነሻ ነው ይላሉ። መንግሥትም ይህ ታይቶት ይሁን የዜጎች ጉዳይ አሳስቦት ለነዚህ ነጋዴዎች አንድ መላ ይዞ ከተፍ አለ። እንደ መርካቶ በመሳሰሉ አካባቢዎች በሰንበት ብቻ አስፋልት ላይ ዕቃቸውን ዘርግተው የሚሸጡበትን ሁኔታ ፈጠረ።
እኔ በሚገባ በማውቀው ከአመዴ ገበያ ወረድ ብሎ ባለው በርሜል ተራ ከሚባለው እስከ ሸራ ተራ ድረስ ባለው ጎዳና ላይ ዕሁድ ዕለት ዕቃቸውን ዘርግተው መሸጥ እንደጀመሩ አስታውሳለሁ።
ከምዕራብ ሆቴል ጎን ትንሽ ፈቀቅ ብሎ ካለው ምስር ተራ እስከ ምናለሽ ተራ ድረስ ባለው አስፋልትም ዕቃቸውን ዘርግተው ተረጋግተው ይሸጣሉ። ሳምንቱን ሙሉ ሲባረሩ ቆይተው በሰንበት አረፍ ብለው ይሸጣሉ።
በዚያ ለማለፍና አካባቢውን ለመቃኘት ስትሞክሩ ልብስ ቆሞ የሚያየው፣ ለመግዛት ዋጋ የሚጠይቀውና የሚደራደረው ሰው ብዙ ይደንቆታል፤ በወረፋና በግፊያ ውስጥ እስከ ምናለሽ ተራ ለማለፍ ይገደዳሉ። ካለው ግብይት ብዛት መኪና ሊያልፍበት የሚችል ነገር እንደሌለ ይረዳሉ።
በሥፍራው ብዙ ወጣት ሴቶች ልብሶችን ለማየትና ለመግዛት ይሄዳሉ። በዓላት ሲደርሱ ደግሞ ገበያዎቹ የበለጠ ይደራሉ፤ በልብስ መሸጫ መደብሮች አልሸጥ ያሉ ልብሶች በዚህ ስፍራ በብዛት ለገበያ ይቀርባሉ። ነጋዴዎቹ በሚገርም ዋጋ፣ አላየንም፣ አልሰማንም እንዳትሉ እያሉ ሸማቹን ይጠራሉ።
በመርካቶ እሁድ ገበያ አንጥፈው ከሚሸጧቸው ልብሶች ውስጥ የተለበሱ ልብሶች ማለት ሰልባጅ የሚባል፤ አዳዲስና የታሸጉ ልብሶች የተለያዩ ጫማዎች አነስተኛ የቤት ቁሳቁስ ይገኙበታል። ገበያው ሳምንቱን ሙሉ ሥራ ላይ የሚውሉ ሸማቾች የፈለጉትን እንዲገበዩ ምቹ ሁኔታ የፈጠረም ነው ።
እንደ ሜክሲኮና ለገሃር ባሉ አካባቢዎች ግን ከሳምንት እስከ ሳምንት ጥግ ጥግ ይዘው አንጥፈው የሚሸጡ አሉ። የመርካቶው እሁድ ቀን ብቻ አንጥፈው የሚሸጡበት በመሆኑ ይለያል።
የሰንበት ገበያው ከመጀመሩ በፊት እሁድና በበዓላት ቀናት መርካቶን የተመለከተ ራሱን ለማመን ይቸገር ነበር። ያ ከሰኞ እስከ ቅዳሜ ማለፊያ ማግደሚያ የሌለው የመርካቶ ጎዳና ክፍት መሆን ሊያስደነግጠው ይችላል፤ ከተማው የተወረረ እስከሚመስል ድረስ ጭው ይል ነበር። የሰንበት ገበያው ወይም ተነጣፊ ሱቆች (ሰንዴይ ማርኬት) ይህን ሁኔታ በእጅጉ ቀይረውታል። ሁኔታው ባለተነጣፊ ሱቆች ተረጋግተው በመስራት የራሳቸውንም ነፍስ ዘርተው፣ ገበያውንም ነፍስ ዘርተውበታል ያሰኛል።
ኃይለማርያም ወንድሙ
አዲስ ዘመን ሚያዝ ያ 23/2013