ራስወርቅ ሙሉጌታ
በኢትዮጵያ ከፍተኛ እድገት እያስመዘገበ የመጣው የኮንስትራክሽን ዘርፍ ባለፉት ጥቂት አመታት ከግንባታ ግብዓት እቃዎች በተለይም የሲሚንቶና የአርማታ ብረት እጥረትና የዋጋ ንረት ዘርፉን በሚጠበቀው ደረጃ እንዳይንቀሳቀስ አድርጎታል። ይህንንም ተከትሎ በርካታ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ የሚኖሩ ዜጎች ስራ በመፍታታቸው ለተለያዩ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ቀውሶች ተዳርገዋል። ባለ ሀብቶችም የጀመሯቸው ፕሮጀክቶች መጠናቀቅ ካለባቸው ግዜ በላይ እየቆዩባቸው ሲሆን ለተጨማሪ ወጪም ተዳርገዋል። በቅርቡም የንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ለሲሚንቶ ግብይት ዋጋ መጨመርና መጥፋት በመስኩ የተሰማሩ ህገ-ወጥ ደላሎች የሚሰሩት አሻጥር የፈጠረው መሆኑን አስታውቋል።
በመሆኑም እነዚህን ህገወጦች ከገበያ ሰንሰለቱ በማስወጣት እየናረ የመጣውን ዋጋ ለማስተካከል የመሸጫ ዋጋ በመተመን የሚያከፋፍሉ የመንግስት የልማት ድርጅቶችና መመሪያውን አክብረው ለመስራት የተስማሙ የግል ነጋዴዎችን በመምረጥ ወደ ስራ እንዲገቡ መደረጋቸው ይታወሳል፡፡ ችግሩን በዘላቂነት ለመቅረፍ የምርት ብዛትን መጨመር አንዱ አማራጭ በመሆኑም ከሳምንት በፊት የድሬዳዋ ኢንዱስትሪያል ኮምፕሌክስ የሲሚንቶና የአርማታ ብረት ፋብሪካ ግንባታ የመሰረት ድንጋይ ተቀምጧል። ይህው ፕሮጀክት ግንባታው ተጠናቆ ወደስራ ሲገባ ከሀገር ውስጥ ፍጆታ ባለፈ ለአለም አቀፉ ገበያ በማቅረብ የውጪ ምንዛሬ ለማስገኘት እንደሚጠቅም ተገልጿል ።
የንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር አቶ መላኩ አለበል የመሰረት ድንጋዩ በተቀመጠበት ወቅት እንደተናገሩት፤ በኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት ከተጋረጡ ችግሮች መካከል አንዱና ዋነኛው የስራ አጥነት ነው። ከስልሳ በመቶ በላይ የሚሆነው የስራ እድል የሚፈጠረውና ወደፊትም ከፍተኛ ቁጥር ያለው ስራ ይፈጥራል ተብሎ የሚጠበቀው ኮንስትራክሽን ዘርፍ ነው። በመሆኑም ችግሩን ለመቅረፍ ደግሞ መሰረተ ልማትን በማስፋፋት ኢንቨስትመንትን ማሳደግ ይጠበቃል ። ለዚህ ደግሞ ዋነኛው ግብዓት ሲሚንቶና የአርማታ ብረት በመሆኑ የሲሚንቶ ፋብሪካዎች በሀገሪቱ መበራከት ለመሰረተ ልማት እድገትም ሆነ ለስራ እድል ፈጠራው እንዲሁም ለአጠቃለይ ለኮንስትራክሽን ዘርፍ እድገት ቀዳሚውን ሚና ይጫወታሉ።
በአሁኑ ወቅት እንደ ቻይና ያሉ ሀገራት የዜጎቻቸው የሲሚንቶ አጠቃቀም በአመት በእያንዳንዱ ሰው ከአንድ ሺ ኪሎግራም በላይ የደረሰ ሲሆን የአለም አማካይ የሲሚንቶ አጠቃቀም ደግሞ አምስት መቶ ሀያ አንድ ኪሎ ግራም ነው። ከሰሀራ በታች ባሉ ሀገራት ደግሞ ዘጠና አንድ ኪሎግራም አካባቢ ሲሆን በኢትዮጵያ ግን በነፍስ ወከፍ ሰባ ኪሎ ግራም እንኳን መድረስ አልተቻለም ። ይህም በሀገሪቱ ያለው የሲሚንቶ አጠቃቀም ምን ያህል ክፍተት ያለበትና በርካታ ስራዎች የሚጠብቅ መሆኑን አመላካች ነው። ባለፉት አመታት በሀገሪቱ የተገነቡ የሲሚንቶ ፋብሪካዎች በአመት እስከ አስራ አራት ሚሊየን ቶን ያመርታሉ ተበሎ የሚጠበቅ ቢሆንም አሁን ያለው የማምረት አቅማቸው ግን ከዘጠኝ ሚሊየን ቶን በላይ የዘለለ አይደለም። በዚህም የተነሳ በሀገሪቱ ከፍተኛ የምርት አጥረት እየተከሰተ ይገኛል።
በሌላ በኩል ኢትዮጵያ ካላት አምቅ የተፈጥሮ ሀብትና ሌሎች ሁኔታዎች አንጻር የሲሚንቶ አቅርቦት ምርት በአለም ላይ በውጪ ገበያ የምንወዳደርበት እንጂ እኛ በእጥረት ልንፈተንበት የሚገባ አልነበረም። በመሆኑም እንደ ሀገር የህዝብን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥና በሲምንቶ አቅርቦት ረገድ በአለም ያለንን ሚና ለማስተካከል ያሉትን የሲሚንቶ ፋብሪካዎች ማጠናከርና በርካታ አዳዲስ ፋብሪካዎችንም መገንባት የሚጠበቅ ይሆናል።
በዚህ ረገድ የኢስት አፍሪካ ሆልዲንግ ኩባንያ ይህንን የፍላጎትና አቅርቦት አለመመጣጠን ክፍተት ለመሙላት እየሰራቸው ያሉ ተግባራት ለሌሎች በተመሳሳይ ዘርፍ ለተሰማሩትም አርአያ የሚሆን ነው። በተለይም የድሬዳዋ ኢንዱስትሪያል ኮምፕሌክስ የሲሚንቶና የአርማታ ብረት ፋብሪካ ግንባታ ፋብሪካው የሚገኝበት ስትራቴጂካዊ አቀማመጥ በርካታ እድሎች የያዘ ነው። በተጨማሪ ከሰማኒያ አመት በላይ በቆየው የካበተ ልምድ ከሀገር ውስጥ ገበያ አልፎ ለውጪ ገበያም በማቅረብ የውጪ ምንዛሬ እጥረትን ለመቅረፍ የሚያስችል አቅም ያለው ነው። ይህም ለምርት ሂደቱና ምርቱን በሚፈለገው ፍጥነትና ጥራት ተገቢው ቦታ ለማድረስ ስለሚረዳ የምርቱን ተፈላጊነት ለማሳደግና የፋብሪካውን ተወዳዳሪነት ለመጨመር የሚረዳ ይሆናል።
በተጨማሪ ለሲምንቶ ምርት ዋነኛ ግብዓት ተደርገው የሚወሰዱት የማጓጓዣ አገልግሎቶችና የሀይል አቀርቦት በሀገሪቱ እየተገነቡ ባሉት የባቡር መሰመር፤ ፈጣን መንገድና የሀይድሮ ኤሌክትሪክ ማመንጫዎች እየተሟሉ ይገኛል። ከሁሉም በላይ ደግሞ እስከ ቅርብ ግዜ ለወጪ ባለሀበት ክፍት ያልነበሩት እነዚህ ዘርፎች ክፍት መደረጋቸው ዘርፉን ያነቃቃ የፖሊሲ እርምጃ መሆኑን በመጠቆም በቀጣይም በሀገሪቱ በዘርፉ ያለውን እንቅስቃሴ ለማቀላጠፍ መንግስት አስፈላጊውን ሁሉ ድጋፍ እንደሚያደርግ ሚንስትሩ ተናግረዋል። ምንም እንኳን ፋብሪካው ንብረትነቱ የኢስት አፍሪካ ሆልዲንግ ቢሆንም ዋነኛው ባለንብረት የድሬዳዋ ከተማና የአካባቢው ነዋሪ ማህበረሰብ በመሆኑ ህብረተሰቡ ፋብሪካውን እንደራሱ ሀብት እንዲጠብቅና እንዲንከባከብም ጥሪ አቅርበዋል።
የኢስት አፍሪካን ሆልዲንግ አክሲዮን ማህበር ሊቀመንበር አቶ ብዙአየሁ ታደለ በበኩላቸው የድሬዳዋ ኢንዱስትሪያል ኮምፕሌክሰ ከሁለት ቢሊየን ብር በላይ የሚጠይቀው የለሚ ኢንዱስትሪያል ፕሮጀክት አንድ አካል ሲሆን በሀገሪቱ የኮንስትራክሽን ዘርፍ የራሱን አሻራ የሚያስቀም መሆኑን ይናገራሉ። እንደ ሊቀመንበሩ ማብራሪያ የድሬዳዋ ኢንዱስትሪያል ኮምፕሌክስ 350 ሚሊየን ዶላር የሚያወጣውና በአንድ መቶ ሶስት ሄክታር መሬት ላይ የሚገነባ ነው። ይህው ፕሮጀክት በቀን አምስት ሺህ ቶን በማምረት ሙሉ ለሙሉ ለውጪ ገበያ በማቅረብ የውጪ ምንዛሬ ለማስገኘት የሚጠቅም ሲሆን የብረታ ብረት ፋብሪካው ደግሞ በአመት ሶስት መቶ ሺ ቶን በማምረት የሀገር ውስጥ የብረት ፍላጎትን በመሸፈን በውጪ ምንዛሬ ወደ ሐገር ውስጥ የሚገባውን ለመቀነስ ያግዛል። በግንባታ ወቅት ከሁለት ሺ በላይ ወደ ማምረት ሲገባም አስር ሺ ለሚደርሱ ዜጎች በቀጥታና በተዘዋዋሪ የስራ አድል የሚፈጥርም ይሆናል።
አጠቃላይ ፕሮጀክቱ ለሀገር ውስጥ ባለሀብቶች የተለያዩ የኢንቨስትመንት እድሎችን የሚከፍት ሲሆን በማኑፋክቸሪን ዘርፍ ለሚገቡትም ተነሳሽነተን የሚፈጥር ይሆናል። በተጨማሪ የወጪ ንግድ ሚዛንን ከማስተካከል ባለፈ ከጎረቤት ሀገራት ጋር ያለውን የንግድ ልውውጥና የህዝብ ለህዝብ ትስስር ያጠናክራል። ቀደም ሲል የተገነቡትን የባቡር ትራንስፖርትና የፈጣን መንገድ መሰረተ ልማቶችን የሚፈለግባቸውን አገልግሎቶች እንዲሰጡ ያደርጋል። የናሽናል ሲሚንቶ ፋብሪካ የማስፋፊያ ፕሮጀክት አሁን ያለውን በአመት አንድ ነጥብ ሁለት ሚሊዮን ቶን ሲሚንቶ የማምረት አቅም ከአጥፍ በላይ የሚያሳድግም ይሆናል። ይህ አቅም ለጅቡቲ ሱማሌ ላንድና ሶማሊያ የሲሚንቶ ፍላጎት ለማሳካት ይጠቅማል።
ይህም ሆኖ በሀገር ውስጥ የግንባታ እቃዎች አቅርቦት ረገድ ያለውን እጥረት መሰረታዊ በመሆነ መልኩ ለመፍታትና ለዚህ ስኬት የሚያበቃውን የውጪ ምንዛሬ ፍላጎት ለማሟላት አንደኛ ከጎረቤት ሀገራት በተለይም ከግብጽ ከኦማንና ሌሎች ሀገራት በንጽጽር በርካሽ ዋጋ ወደ ጅቡቲና ሱማሌ ላንድ የሚመጣውን የሲሚንቶ ምርት ዋጋ ለመፎካከር የሲሚንቶ መፍጪያና ማሸጊያ ፋብሪካ የመንግስት ድጋፍና ድጎማ ሊታከልበት እንደሚገባም አሳስበዋል። አየር በአየር ከሚሰሩና ዳጎስ ያሉ ትርፎችን ከሚያስገኙ የንግድ እንስቃሴዎች ይልቅ ዘላቂና ህዝብንም ተሳታፊ በሚያደርጉና የሀገር እድገትን የሚያፋጥኑ ስራዎችን መስራት የኩባንያቸው መርህ መሆኑን ይናገራሉ። በሌላ በኩል ከውጪ ሀገር የሚገባውን የድንጋይ ከሰል በሀገር ውስጥ ምርት ለመተካት በሳይንሳዊ ስያሜው ፕሮሶፒስ ጁሊ ፍሎራ የሚባለውን መጤ አረም ለመጠቀም በቅርቡ በተዋቀረው የኢስት አፍሪካን ማይኒንግና ኢነርጂ ኩባንያ በኩል እየተሰራ ነው ።
«መጤ አረሙን ለድንጋይ ከሰልነት መጠቀም መንግስትን ከውጪ ምንዛሬ፤ አርሶ አደሩን ከጭንቀት እንዲሁም የአየር ብክለትን ይከላከላል» የሚሉት ደግሞ የኢስት አፍሪካን ሆልዲንግ ማይኒንግና ኢነርጂ ኩባንያ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ገዛኸኝ ሀምዛ ናቸው። እንደ አቶ ገዛኸኝ ማብራሪያ ኢንዱስትሪን በማስፋፋት ሀብትን ለመፍጠር የትላልቅ የግንባታ እቃዎች ማምረቻ ኩባንያዎች ግንባታ ሲታሰብ ቀዳሚና መሰረታዊው ጥያቄ ሆኖ የሚመጣው የሀይል አቅርቦት ነው። እስካሁን በሀገር ውስጥ የሀይል አቅርቦት ለማሟላት መንግስት እያደረገ ያለው ጥረት በቂ ባለመሆኑ ክፍተቱን ለመሙላት እስካሁን ለሚያስገባው የድንጋይ ከሰል በአመት ከሁለት መቶ ሚሊየን ዶላር በላይ እያወጣ ሲሆን የገንዘቡ መጠን በየግዜው እየጨመረ ይገኛል። አሁን ባለው የሀገሪቱ ነባራዊ ሁኔታ አንድ ኩንታል ሲሚንቶ ለማምረት ከሚያስፈልጉ ግብአቶች ውስጥ እስከ ስልሳ በመቶ የሚደርሰውን ወጪ የሚይዘው የሀይል ግብዓት በመሆኑ አሁን ላለው ከፍተኛ የሲሚንቶ ዋጋ መጨመር የሀይል አስተዋጽኦ ከፍተኛ ነው። በሌላ በኩል ለመላው አለም ከፍተኛ ስጋት የሆነው የካርቦን ዳዮኦክሳይድ ልቀት የሲሚንቶና መሰል ፋብሪካዎች በሚጠቀሙት የድንጋይ ከሰል ግብዓትና በምርት ሂደት በሚከሰት ልቀት አማካይነት የአየር ንብረትን ለመበከል ከፍተኛውን ድርሻ እንደሚይዝ ይታወቃል።
ከዚሁ ጋር በተያያዘ በአለም ላይ እየጨመረ በመጣው የነዳጅ ዋጋ ምክንያት የሀይል ማመንጫ ግንባታዎች ዋጋ እየናረ መጥቷል። በዚህም ሀገራት ከውጪ ከሚመጡ ሀይል ማመንጫ ጥገኝነት ለመላቀቅና አስተማማኝ የሀይል ማግኛ መሰረት ለመጣል አማራጭ የሀይል ምንጮችን ለመጠቀም የተለያዩ እንቅስቃሴዎችን እያደረጉ ሲሆን አስካሁን ከ 146 ቢሊዮን ሜትሪክ ቶን በላይ ባዩ ማስ ጥቅም ላይ በማዋል የኤሌክትሪክና ሌሎች የሀይል ምንጮችን ጥቅም ላይ እየዋሉ ይገኛል። በዚህም በማደግ ላይ ባሉ ሀገራት ሰላሳ አምስት ከመቶ የሚሆነውን ዋነኛ የሀይል ምንጭ ከባዩ ማስ ለማዋል ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ይገኛል። ይህም በአረምና ሌሎች አላስፈላጊ ተክሎች የተያዙ መሬቶችን ለእርሻ ጥቅም እንዲውሉ በማድረግና የእርሻውን ኢኮኖሚ ለማነቃቃት ከፍተኛ አስተዋፅኦ ያለው ነው።
በኢትዮጵያም በየወቅቱ እየጨመረ የመጣውን የሀይል ፍላጎት በማገናዘብ ይህንን የሀይል ፍላጎት በከፊል ለመተካት የሚያስችል አማራጭ ሀይል ማምረት አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል። በመሆኑም ፕሮጀክት ከስድስት አመት በላይ በኢስት አፍሪካን ሆልዲንግ ማእድንና ኢነርጂ ኩባንያ ጥናት ሲያደርግ ቆይቷል። በውጤቱም በአፋርና በሱማሊያ ክልል ከሁለት ነጥብ ሁለት ሚሊየን ሄክታር በላይ በመውረር የአርብቶ አደሩንና የከፊል አርብቶ አደሩን ቦታ በመያዝ ስጋት የሆነውን መጤ አረም ጥቅም ላይ ለማዋል አስፈላጊውን ዝግጅት አጠኗቋል ። ይህም ከውጪ ሀገር በከፍተኛ ምንዛሬ እየገባ ያለውን የድንጋይ ከሰል ከአርባ እስከ ሀምሳ በመቶ ለመተካት የሚያስችለው ይሆናል።
መንግስት በአለም አቀፍ ደረጃ የካርቦን ዳዮይኦክሳይድ ልቀትን ለመከላከል የገባው ግዴታ አለ። ከሲሚንቶ ፋብሪካዎች የሚለቀቀውን አሁን ካለበት አንድ ቶን ሲሚንቶ ሲመረት ከሚወጣው ዜሮ ነጥብ 667 ካርቦን ዳዮክሳይድ ልቀት ወደ ዜሮ ነጥብ 628 ለማውረድ የያዘውን ስትራቴጂ የሚያሳካ ይሆናል። በአሁኑ ወቅትም ወደተግባር ለመግባት ለዚህ ፕሮጀክት የማጨጃና መፍጫ ግዢ የሚውል ከአንድ መቶ ሰባ ሚሊየን ብር በላይ የሙከራ ስራ ለመጀመር ቅድመ ሁኔታዎች ተጠናቀዋል። በተጨማሪ ተመሳሳይ የባዮ ጋዝና የሀይል ምንጭ አማራጮችን በተመለከተ ልምድ ለመውሰድ በከፍተሻ ወጪ ናሚብያ፤ ኦስትሪያ፤ ኪዩባና ሌሎች ሀገራት ባለሙያዎችን በመላክና ባለሙያዎችን በማስመጣት ወደ ስራ ለመግባት እንቅስቃሴ ጀምሯል። ለዚህም የኢስት አፍሪካን ሆልዲንግ ማዕድንና ኢነርጂ ኩባንያ የድሬዳዋ የሲሚንቶ ማምረቻ ለሙከራ ክፍት በማድረግ አስፈላጊ ግብዓቶችንም ለማቅረብ በጀት መድቦ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል። ይህ ቴክኖሎጂ በቀጣይ ለሁሉም ሲሚንቶ ፋብሪካዎች እንዲዳረስ የሚደረግ መሆኑንም አቶ ገዛኸኝ ተናግረዋል።
አዲስ ዘመን ሚያዚያ 19/2013