ከራማአ ማዶ
በአገራችን ታሪክ ውስጥ ብሄራዊ ምርጫ የተጀመረው እንደ ኣውሮፓውያን ኣቆጣጠር በ1957 በዓጼ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግስት ሲሆን፤ በ1955 የወጣውን ህገ -መንግስት መሰረት ያደረገ ንጉሱንና የላይኛውን ቤት ወይም ሴነቱን የማይመለከት ነገር ግን የተወካዮች ምክር ቤት አባላትን መምረጥ ላይ ያ ተኮረ ነ በር።
በወቅቱ የነበሩ እማኞች ምርጫውና ቆጠራው ሃቀኛ እንደነበር ይናገራሉ። ታዲያ ንጉሱ በነበሩበት ዘመን የነበሩት ምርጫዎች ጅማሪያቸው መልካም ቢሆንም ዓለም በማህበራዊ ለውጥ ላይ በነበረችበት በመጨረሻው ሰዓት የኢትዮጵያን ፖለቲካ ወደ ህገ-መንግስታዊ ሞናርኪ ቀይሮ የፖለቲካውን ስልጣንና የህዝቡን ተሳትፎ ማስፋት ስላልተቻለ ወታደራዊ ደርግ አብዮቱን ኣንግቦ ብቅ ኣለ።
ደርግ ወታደራዊ መንግስት ስልጣን ከያዘ በኋላ የሶሻሊዝም ርእዮት ተከታይ ነኝ በማለቱ በየማህበራቱ የሚደረጉት ምርጫዎች ሁሉ ከዚያው ከአንድ ምንጭ የሚቀዱትን የሶሻሊዝም ጓዶች መምረጥ ሆነ። ደርግ አብዮቱ ማለት ሞቱ ነበር። ይህ የሚሞትለት ምርጫ ደግሞ የሁሉም መሆን አለበት ብሎ ያምናል። በግድ ሁሉም ሰው ለአብዮቱ መገዛት ኣለበት። የመድብለ ፓርቲ ስርዓት ይህን የሚሳሳለትን አብዮት ያፈርሳል ብሎ ስለሚያምን አብዮቱ እንዳይቀለበስ ስለሚፈራ ምርጫ በአስተሳሰብ (ideology)ና ፖሊሲ ላይ ያተኮረ ሳይሆን ምን አልባትም በግለሰቦች ስብእና ላይ ያተኮረ እንዲሆን አደረገው። በዚህ ምክንያት በደርግ ዘመን የመድብለ ፓርቲ ስርዓትም ስላልነበረ ምርጫዎች ተካሄዱ ማለት አይቻልም።
ዓለም ወደ ዴሞክራሲ በጣም በተዘረጋችበት፣ ብዙ አገራት ወደ ዴሞክራሲያዊ ምርጫ በጣም ባደጉበት ጊዜ ወደ ስልጣን የመጣው ወያኔ መራሽ የኢህአዴግ መንግስት ደግሞ ስልጣን ከያዘበት ከ1983 ጀምሮ ላለፉት 27 ዓመታት አምስት ምርጫዎች ተደርገዋል። ለቀባሪ ማርዳት አይሁንብኝ እንጂ በወያኔ መራሽ ኢህአዴግ የስልጣን ዘመን የተካሄዱትን አምስት ምርጫዎች ስናይ ሁሉም ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን ያልጠበቁ በሚል የተከሰሱ፣ በተለይም የ1997ቱ ምርጫ የህዝቡን ቅስም የሰበረ፣ ስብራቱም እስካሁን ያላገገመበት ሁኔታ ፈጥሮ ቆይቷል። በዚህም ህዝቡ ምርጫ በመጣ ቁጥር በሰቀቀን ገላውን ይጨርሳል። አገር ትፈርስ ይሆን በሚል ይሸበራል።
ታዲያ ወያኔ መራሽ ኢህአዴግ ህዝብ ወዶኝና መርጦኝ መቶ በመቶ አሸንፌያለሁ ባለበት ምርጫ ማግስት የ27 ዓመት ግፍና መከራው፣ ውሸትና ሌብነቱ ያቅለሸለሸው ወጣቱ ትውልድ ውድ ህይወቱን ገብሮ ደሙን አፍሶ አጥንቱን ከስክሶ በአገሪቱ አሁን ላይ የመጣውን ለውጥ እንዲመጣ ግንባር ቀደም ሚና ተጯውቷል። ነገር ግን ወጣቱ ከፍተኛ መስዋዕትነትን ከፍሎ ያመጣው ለውጥ ተቋማዊና ዘለቄታዊ ሆኖ እንዲቀጥል አዝጋሚም ቢሆን የተለያዩ ስራዎች እየተሰሩ ነው፡፡
በአገሪቱ በመጣው የለውጡ ሃዲድም ባለፉት ሶስት ዓመታት የአገሪቱን መጻኢ ተስፋ የሚያለመልሙ የተለያዩ ፕሮጀክቶች ተከናውነዋል። እየተከናወኑም ይገኛሉ። የተለያዩ የሲቪክ ማህበራት ነጻነታቸውን አግኝተዋል። በአንጻሩ ባለፉት ሶስት ዓመት ስለ ኢትዮጵያዊነትና አንድነት አብዝቶ ቢነገርም ምድሪቷ አኬል ዳማ ሆና ሞት የረከሰባት ምድር ሆናለች። መተባበር ጠፍቶ መነቃቀፍ ነግሷል። በጥቅሉ የህዝቦች በሰላም ወጥቶ የመግባት ህልውና ጥያቄ ምልክት ውስጥ ገብቷል።
በዚህ ሁሉ ሀገራዊ ሁኔታ ውስጥም ቢሆን ምርጫው መካሄድ አለበት የሚል ውሳኔ ተላልፎ ተስፋና ስጋት ያዘለው ምርጫ 2013 ሊካሄድ ሽር እንጉድ እየተባለ ይገኛል። የምርጫ ቅስቀሳውም እየተጧጧፈ ይገኛል። በመሆኑም አሁን ላይ አገሪቱ ከገባችበት ውስብስብ ችግሮች አንጻር ምርጫ 2013 ለኢትዮጵያ ህዝብ ከህልውና በላይ በህይወት የመኖርና ያለመኖር ዋስትና ነው ቢባል ማጋነን አይሆንብኝም።
ታዲያ የአገሪቱን መጻኢ ተስፋ ይወስናል ተብሎ የታመነበት ምርጫ 2013 ሰላማዊ፣ ዴሞክራሲያዊና ታማኒ ሆኖ እንዲጠናቀቅ ተፎካካሪ ፓርቲዎች፣ ሲቪክ ማህበራትና ህብረተሰቡ የበኩሉን ድርሻ መወጣት ቢጠበቅባቸውም በተለይ በስልጣን ላይ ያለው የለውጡ ኃይል የአንበሳውን ድርሻ ሊወስድ ይገባል።
እዚህም እዛም በአገሪቱ በሁሉም ክፍል ምርጫው ሰላማዊ፣ ዴሞክራሲያዊና ታማኒ ሆኖ እንዲጠናቀቅ የሃሳብ የበላይነት ሊነግስ ይገባል የሚሉ አስተያየቶች ሲሰነዘሩ ይሰማል። ጠቅላይ ሚኒስትር ክቡር አብይ አህመድ (ዶክተር) ጭምር “የሃሳብ ልዕልና” የያዘ ያሸንፋል ሲሉ ደጋግመው ሲናገሩ ተደምጠዋል። የመገናኛ ብዙኋኑም ይህንኑ ሲያስተጋቡት ይደመጣሉ።
ነገር ግን በሴራ ፖለቲካ ጥርሳቸውን የነቀሉ የ60ዎቹ ትውልድ ርዝራዦች በሃሳብ ልዕልና ከማሸነፍ ይልቅ አንዱ አንዱን ጠልፎ ለመጣል፣ አንዱ የፖለቲካ ፓርቲ የሌላውን ስም ለማጠልሸት ሲሯሯጡ ይስተዋላል። እንዲሁም በአገሪቱ እንደአሸን የፈሉት የፖለቲካ ፓርቲዎች ያላቸው የፖለቲካ አይዶሎጂ ከአራትና ከአምስት ርዕዮተ አለም የማይበልጥ ነው። ነገር ግን አብዛኞቹ የቆሙለትን ብሄር ወይም ዘር ጥቅም ያስከብርልኛል የሚሉት ሃሳብ እንኳን የላቸውም።
ለዚህም በቀላሉ ማሳያ የሚሆነን በምርጫ 2013 ዓ.ም የሚወዳደሩ አንድ አንድ የፖለቲካ ፓርቲዎች ዘር ከመቁጠር ውጭ አገርን የሚያሻግር ሃሳብ የላቸውም። በመሆኑም እነዚህ ፓርቲዎች ሃሳባቸውን ለገበያ አውጥተው በሃሳብ ልዕልና የበላይ ሆነው ምርጫውን አሸናፊ እንዲሆኑ በሚል ሃሳባቸውን ለህብረተሰቡ እንዲያካፍሉ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ የመደበላቸውን የመገናኛ ብዙሃን የአየር ስዓትና የጋዜጣ አምድ እንኳ በአግባቡ መጠቀም ተስኗቸዋል። በዚህም በአዲስ ዘመን ጋዜጣ ለፖለቲካ ፓርቲዎች የተመደቡ የአምድ ኮለመን ሌጣውን አየር ላይ እየዋለ ይገኛል። በተለያዩ የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያዎች የምናየውም ይህንኑ ሃቅ ነው።
<<ጠንቋይ ለራሱ አያውቅ አውቅላቹህ ይላል>> እንዲሉ አንድ አንድ የፖለቲካ ፓርቲዎች ወንዝ የማያሻግር ሃሳብ ይዘው ሀገር እንመራለን ሲሉ ያሳፍራሉ። ከነዚህ ፓርቲዎች ይልቅ በሃሳብ ልዕልና ማሸነፍ እንደማይቸሉ ቀድመው የተረዱ አንድ አንድ የፖለቲካ ፓርቲዎች ገና በጥዋት <<የእናቴ መቀነት አደናቀፍሽ>> በሚል ከዚህ ታሪካዊ ምርጫ ራሳቸውን ያገለሉም አልጠፉም። በአንጻሩ ደግሞ በሃሳብ መሞገት የማይችሉ የድንጋይ ዘመን አስተሳሰብ ያላቸው በ21ኛው ክፍለ ዘመን ጫካ ገብተው በህጻናትና በእናቶች ደም የጨቀዩ ህገ አራዊቶችም አልታጡም። ስለዚህ እነዚህን በሰው ደም የሰከሩትን መንግስት አንድ ሊል ይገባል።
በጥቅሉ የኢትዮጵያ ህዝብ በሃሳብ ልዕልና የሚያምን አርቆ አሳቢና ደግ ህዝብ ነው። በዚያው ልክ ደግሞ አትንኩኝ ባይም ነው። ስለዚህ ህዝቡ የሃሳብ ልዕልና ላለው አይደለም ድምጹን ህይወቱን አሳልፎ እንደሚሰጥ የ1997ቱ ምርጫ ምስክር ነው። በመሆኑም የፖለቲካ ፓርቲዎች ከሴራና ከመጠላለፍ ፖለቲካ ወጥተው ሃሳባቸውን ለህዝቡ ሽጠው በሃሳብ ልዕልና በህዝብ ልብ ውስጥ ሊነግሱ ይገባል።
ህዝቡም በ21ኛው ክፍለ ዘመን አለም ወደ አንድ መንደር በመጣበት በብሄርና በዘር ታጥሮ ህይወቱን ከማቀንጨር ተላቆ፣ ከጎሳ አመለካከት ወጥቶ ድንበር ተሻጋሪ ሃሳቦችን በመሸመት የሃሳብ ልዕልና ያለውን ፓርቲ በማንገስ አገሩን ከተጋረጠባት አደጋ በማሻገር ታሪክ ሊሰራ ይገባል። ለዚህም ህብረተሰቡ የምርጫ ካርዱን በወቅቱ ወስዶ በምርጫው ወቅት በነቂስ ወጥቶ ያስተዳድረኛል ያለውን ሃሳብ ፍጹም ሰላማዊና ኢትዮጵያዊ ጨዋናት በተሞላበት መንገድ ሊመርጥ ይገባል። እዚህ ላይ ይብቃኝ። ቸር እንሰንብት።
አዲስ ዘመን ሚያዚያ 9/2013