
ብርሃን ፈይሳ
አንዳንዶች እግር ኳስን ከቴአትር ጋር ያመሳስሉታል:: ሜዳን እንደ መድረክ፣ ተጫዋቾችን እንደ ከያኒ፣ ደጋፊን እንደተመልካች፣ የአሰልጣኝን ታክቲክ እንደ ድርሰት መመሰል ቢቻል ተወዳጁ ስፖርት እግር ኳስ ቴአትርን ይመስላል:: የየራሳቸውን ገፀ ባህሪ የሚጫወቱ ተዋንያን በቴአትር ጽሁፍ ነፍስ ዘርተው ተመልካችን ለማዝናናት በጥምረት የሚያደርጉት ጥረትም የቡድን ጨዋታ ከሆነው እግር ኳስ ጋር ተመሳሳይነት አለው:: በቲያትርም ይሁን በእግር ኳስ መድረክ ተመልካች ከግምትና መላ ምት በዘለለ የመጨረሻውን ውጤት ማወቅ አይችልም፣ ወደ ፊት የሚመጣን ክስተትም እንደዚያው:: ሁለቱን መድረኮች የሚለያቸው ነገር ቢኖር ቴአትር የመጨረሻውን ክስተት ተዋንያኑም ይሁኑ ደራሲው ማወቃቸው ሲሆን በእግር ኳስ የመጨረሻውን ውጤት ተጫዋቾችም ይሁኑ አሰልጣኞች ማወቅ አለመቻላቸው ነው:: ለዚህም ነው እግር ኳስ በዓለም ሕዝብ ዘንድ ተወዳጅ የሆነው::
እግር ኳስና ቴአትር ምንጫቸው ጥበብ ነውና በጥሎ ማለፍ መርሃቸው የአንዱን ስኬት ከሌላኛው ውድቀት ጋር ቁልጭ አድርገው ያሳዩናል:: በጨዋታ ብልጫ የነበረው አሸንፎ ወደሌላኛው ደረጃ ሲሸጋገር ብንመለከትም እንኳን ባልታሰቡ ሁነቶችና ጡዘቶች ያልተጠበቀው የበላይነቱን ይጎናጸፋል:: እንዲህ ዓይነቱ በአጓጊ ትዕይንቶች የተዋቀረ ቴአትር ከተመልካቹ ህሊና እንደማይሰረዝ ሁሉ፤ በክስተታዊና በሽርፍራፊ ዕድልን ተጠቅሞ የተገኘ ድልም ደጋፊዎች ለረጅም ጊዜ የሚያጣጥሙት ይሆናል::
ታሪካዊ ድሎች፣ ያልተጠበቁ አሸናፊና አሳዛኝ ተሸናፊዎች፣ ታሪክ ለዋጭ ቅጽበቶች፣ ውሳኔዎችና አስደናቂ ችሎታን የሚያሳዩ በርካታ የእግር ኳስ ግጥሚያዎችን ከስፖርቱ የታሪክ ማህደር ማንሳት ይቻላል:: ለኢትዮጵያዊያን ግን በጥሩ ደራሲያን እንደተዋቀረና በምርጥ ተዋንያን እንደተሰራ ቴአትር ከእዝነ አእምሮ ሳይጠፋ ምንጊዜም ከሚያጣጥሟቸው ድሎች ቀዳሚዎቹ የአፍሪካ ዋንጫ ተሳትፎ ስለመሆናቸው እሙን ነው:: የስፖርት ቤተሰቡ በትዕግስት ተፈትነውና ረጅም ዓመታትን ጠብቀው የሚያገኙት ይህ የአህጉሩ ታላቅ የእግር ኳስ ውድድር በእርግጥም የተለየ ትርጉም ያለው ነው::
በስምንት ዓመታት ልዩነት የተገኙት ሁለት ተሳትፎች ደግሞ የምን ጊዜዎቹም ምርጥ ትውስታዎች ናቸውና ለመንደርደሪያ ያህል የደቡብ አፍሪካውን ዋንጫ በጥቂቱ እንመልከት:: በኢትዮጵያ እግር ኳስ እንደ ጥቅምት 04/2005ዓም በጉጉት የተጠበቀ ቀን ስላለመኖሩ፤ በፈለቀ ደምሴ ‹‹የኢትዮጵያ እግር ኳስ ጉዞ›› በሚል ርዕስ የተዘጋጀው መጽሃፍ ያትታል:: ከሱዳን ጋር በሚካሄደው የመጨረሻው የማጣሪያ ጨዋታ የስፖርት ቤተሰቡ በአዲስ አበባ ስታዲየም ድጋፉን ለመስጠት የተገኘው አንድ ቀን አስቀድሞ ነበር:: ከኳስም በላይ የነበረው የወቅቱ ሁኔታ ‹‹በሁለት ጎል ልዩነት ማሸነፍ›› የሚለው ስሌት በሁሉም ዘንድ ተስፋና ስጋትን በእኩል ሚዛን ያሳደረ ነበር:: አጓጊው ጨዋታ ጊዜው ደርሶ ቢጀመርም በመጀመሪያው አጋማሽ በሁለቱም ቡድኖች ግብ ሳይቆጠር ተጠናቀቀ:: በሁለተኛው አጋማሽ ግን እድል ከዋሊያዎቹ ጋር ነበረችና በሶስት ደቂቃዎች ልዩነት አዳነ ግርማ እና ሳልሃዲን ሰኢድ ግብ በማስቆጠር ኢትዮጵያ 2ለ0 በሆነ ውጤት መምራት ጀመረች:: ይሁን እንጂ የስፖርት ቤተሰቡ የጨዋታውን ማብቂያው ፊሽካ ድምጽ እስኪነፋ እርግጠኛ መሆን አልቻለም ነበር:: ግቦቹ ከመቆጠራቸው አስቀድሞ የነበሩት ከስልሳ በላይ ደቂቃዎች አጭር ነበሩ:: በአንፃሩ ግቦቹ ከተቆጠሩ በኋላ የነበሩት ጥቂት ደቂቃዎች ረዝመው ታዩ:: ጨዋታው ሊጠናቀቅ ጥቂት ደቂቃዎች ሲቀሩ ግብ ጠባቂው ጀማል ጣሰው በመጎዳቱ በአማካይ ተጫዋቹ አዲስ ህንጻ መተካቱ የግድ ሆነ::
መደበኛው የጨዋታ ሰዓት ተጠናቆ በተሰጠው ጭማሪ ሰዓት አስደንጋጭ ሁኔታ ተከስቶ ነበር:: ይኸውም የግብ ጠባቂውን ጓንት የተረከበው አዲስ ህንጻ የመታት ኳስ በሱዳናዊው አጥቂ እግር ስር መገኘቷ ነው:: ወደጎልነት ከመቀየሯ በፊት ግን የዳኛው ፊሽካ ተሰማ:: ለኢትዮጵያዊያንም ደስታ ሆነ፤ ሊቢያ እአአ 1982 አዘጋጅ በነበረችበት 13ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ለመጨረሻ ጊዜ ተሳታፊ የሆነችው ኢትዮጵያ በድጋሚ ወደ መድረኩ መመለሷን አረጋገጠች::
ከሊቢያው የአፍሪካ ዋንጫ በኋላ የነበሩት ሶስት አስርት ዓመታት ኢትዮጵያ መስራች ከነበረችበት የአፍሪካ ዋንጫ እንዲሁም ሌሎች አህጉር አቀፍ ውድድሮች ላይ መሳተፍ ባለመቻሏ የበይ ተመልካች በመሆን ነበር ያሳለፈችው:: በእነዚህ ጊዜያት ከስፖርቱ ርቆም ሆነ በተስፋ መቁረጥ ፊቱን መልሶ የማያውቀው እግር ኳስ ወዳዱ የኢትዮጵያ ህዝብ በታላላቅ ውድድሮች ተሳትፎ ጥም ተሰቃይቷል:: የእግር ኳስ ምስረታቸውን ከኢትዮጵያ በኋላ ያደረጉ በርካታ ሃገራት በበኩላቸው የተጠናከረና አቅም ያለው የእግር ኳስ ቡድኖቻቸውን ይዘው በተደጋጋሚ በመድረኩ ተሳታፊዎች ሆነዋል:: ከተፎካካሪነትም ባለፈ ዋንጫውን እየተፈራረቁ የግላቸው ሲያደርጉ ቆይተዋል፤ እግር ኳሳቸውንም በዓለም ደረጃ አስተዋውቀዋል:: ኢትዮጵያ ግን በእነዚህ ጊዜያት፤ ከዳር ቆማ ነበር ያቀናችውን ውድድር መድረክ የምትመለከተው::
29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ለኢትዮጵያውያን የተለየ የሆነበት ምክንያትም ለስፖርት ቤተሰቡ የሰላሳ ዓመታት ጥያቄ ምላሽ የሆነ የድል ዜና ይዞ መከሰቱ ነው:: ካፍ የአፍሪካ ዋንጫ የሚካሄድበትን ጊዜ ወደ ጎዶሎ ቁጥር ዓመት መመለሱን ተከትሎ እአአ በ2013 በደቡብ አፍሪካ ለሚካሄደው ውድድር በቂ የሚባል ዝግጅትና የወዳጅነት ጨዋታዎችን ያላካሄደው የኢትየጵያ ብሄራዊ ቡድን በመጀመሪያ የማጣሪያ ውድድር ተሰለፈ:: ማጣሪያዎቹን አልፎም መቼም ከአእምሮ ሊሰረዝ የማይችል ትዝታን በሚያሳድር ድራማዊ ሁኔታ የአፍሪካ ዋንጫ ተካፋይነት ተረጋገጠ:: ከናይጄሪያ፣ ቡርኪናፋሶ እና ዛምቢያ ጋር የተደለደለው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን፤ አንድ ግብ አስቆጥሮና 7 ግቦችን አስተናግዶ የምድቡን የመጨረሻ ደረጃ በመያዝ በጊዜ ከውድድሩ መሰናበቱ እውን ሆኗል:: ይሁን እንጂ ትልቁ ነገር ተሳትፎ እንደመሆኑ ምንጊዜም ከስፖርት ቤተሰቡ ልብ የማይፋቅ ትዝታ አኑሮ አልፏል::
ወደ አፍሪካ ዋንጫው በድጋሚ ለመመለስ በዳግም ዓመታትን መታገስ ቢጠይቅም እንደቀድሞ ባለ ሁለት አሃዝ ዓመታትን ግን መጠበቅ ግድ አላለም:: ይልቁንም በስምንተኛው ዓመት በእውቅ ጸሃፊ እንደተከሸነ ቴአትር አስደማሚና ድራማዊ በሆነ መልኩ ኢትዮጵያ ወደናፈቀችው የውድድር መድረክ ልትመለስ ቻለች:: በአቢጃን ከኮትዲቯር ጋር ወሳኙንና የመጨረሻውን የማጣሪያ ምዕራፍ ያደረገው ቡድኑ፤ ተሳትፎውን ለማረጋገጥ በተመሳሳይ ሰዓት ማዳጋስካር ከኒጀር የሚያደርጉት የጨዋታ ውጤት ወሳኝ ነበር:: ዋሊያዎቹ ሶስት ለአንድ እየተመሩ የቆዩበት ጨዋታ 83ኛው ደቂቃ ላይ በመሃል ዳኛው መታመም መቋረጡ ደግሞ ሌላኛው ልብ አንጠልጣይ ትዕይንት ሊሆን በቃ:: ሙሉ የጨዋታ ሰዓቱ ሳይጠናቀቅ ጨዋታቸውን ያቆሙት ዋሊያዎቹ የማዳጋስከርና ኒጀር ጨዋታ መጨረሻ (ውጤት) ማወቅ እጣ ፋንታቸውን ጠቋሚ ነበርና ትንፋሻቸውን ውጠው መጠበቅ የግድ ነበር:: ጨዋታው ያለምንም ግብ መጠናቀቁ እስኪታወቅ በነበረው በዚያን የጭንቅ ወቅት ዋሊያዎቹ ምን ዓይነት ሁኔታ ላይ ነበሩ የሚለውን የቡድኑ አባላት እንዲህ ያስታውሱታል::
የብሄራዊ ቡድኑ አማካይ ስፍራ ተጫዋች መስኡድ መሃመድ፤ ‹‹የማዳጋስካርና ኒጀር ውጤት እስኪታወቅ ባለው ሰዓት የኛ ጨዋታ ተቋርጦ ነበርና አመራሮቻችን ስልክ በመደወል ያለውን ሁኔታ ያጣሩ ነበር:: በመጨረሻ ማለፋችንን ሲነግሩን አላመንም፤ አብዛኛው ሰው ደስታውን በለቅሶ ነበር የገለጸው›› ሲል መልበሻ ቤት የነበረውን ድባብ ያጋራል::
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንትና በኮትዲቯር ተገኝተው ጨዋታውን የተመለከቱት አቶ ኢሳያስ ጅራ በበኩላቸው፤ ‹‹አቢጃን ላይ ያደረግነው ጨዋታ ሲቋረጥ እኔ የማዳጋስካርና ኒጀርን ጨዋታ የአንድ ክለብ ቡድን መሪ በስልክ እያስተላለፈልኝ ነበር ስከታተል የነበረው:: በመጨረሻ ፊሽካው ተነፍቷል ብሎ ሲነግረኝ የክቡር እንግዶች መቀመጫ ትሪቡን እየጮኽኩ ነበር የወጣሁት:: በወቅቱ የቡድኑ አባላት ሜዳ ላይ ተንበርክከው እየጠበቁ ነበር፤ የእኔን ድምጽ ሲሰሙ ሁሉም መጮህ ጀመሩ:: የሚያለቅስም ነበር፤ እውነት ለመናገር ማዳጋስካርን ካሸነፍን በኋላ በነበሩት አምስትና ስድስት ቀናት እንቅልፍ አልነበረንም:: ሁሉም ሰው የሚያስበው የመጨረሻውን ጨዋታ ስለነበር በዚያ የጭንቅ ሰዓት የመጣውን ደስታ እያጣጣምኩት እገኛለሁ›› ሲሉ ይናገራሉ::
በእንዲህ ዓይነት ድራማዊ ክስተቶች ለ33ኛው የካሜሮን አፍሪካ ዋንጫ ማለፋቸውን ያረጋገጡት ዋልያዎቹ በድጋሚ ወደ ጨዋታ ተመልሰው በሌላ ተተኪ ዳኛ መሪነት የቀሩትን ዘጠኝ ደቂቃዎች አጠናቀዋል:: ቡድኑ የ3ለ1 ሽንፈት ቢያስተናግድም ከተጋጣሚው አይቬሪኮስት ጋር ተከታትለው ወደ ካሜሩን የሚጓዙበትን ትኬት ቆርጧል:: ውጤቱ የፈጠረው ደስታም በኢትዮጵያዊያን የስፖርቱ ወዳድ በአደባባይ ደስታ ገልጸዋል:: በቡድኑ አባላት ዘንድ ምን ዓይነት ስሜትን እንዳሳደረ ደግሞ አመለ ሸጋው ተጫዋች መስኡድ፤ ‹‹ለሃገር ተጫውቶ ውጤት ማምጣትና በአፍሪካ መድረክ መሳተፍ የሁሉም ተጫዋች ህልም እንደመሆኑ እግር ኳስ የሚወደው የኢትዮጵያ ህዝብ ስለተደሰተ እኛም በጣም ደስ ብሎናል:: በካሜሮን ተሳትፎ ብቻ ሳይሆን ሃገራችንን የሚመጥን ውጤት ለማስመዝገብ ጥረት እናደርጋለን›› ሲል ቃል ገብቷል::
ቡድኑን ከኢንስትራክተር አብረሃም መብራህቱ ተረክበው ለአፍሪካ ዋንጫ ያበቁት አሰልጣኝ ውበቱ አባተ በበኩላቸው፤ ‹‹በአቢጃን በመጨረሻ የተመዘገበው ውጤት ጥሩ ነው፤ አስበን የሄድነው ነጥብ ለማስመዝገብ ነበር:: ነጥቡ በአፍሪካ ዋንጫው ተሳታፊ እንድንሆን የሚያስችለን በመሆኑ ተጫዋቾቼ የሚችሉትን አድርገዋል:: ነገር ግን ሁኔታው አልፈቀደም፤ የገጠምነው ጠንካራዋን ኮትዲቯርን መሆኑ የማይካድ ነው:: በዕለቱ የነበረው የአየር ሁኔታም ከባድ በመሆኑ እንዳሰብነው ባይሳካም በምድቡ ሌላ ጨዋታ ማዳጋስካር ነጥብ በመጣሏ ተሳታፊነታችንን ልናረጋግጥ ችለናል›› ሲሉ ይገልጻሉ::
ወደ አፍሪካ ዋንጫው በቶሎ መመለስ መልካም ነገር ቢሆንም ፍላጎታቸው ከረጅም ዓመታት ጥበቃ በኋላ ለአፍሪካ ዋንጫ አለማለፍ ነው:: ነገር ግን ከተሰራ በቶሎ ቶሎ በማለፍ ኢትዮጵያ የምትካፈልበት መድረክ እንዲሆን ማድረግ እንደሚገባም ጠቁመዋል:: አያይዘውም ‹‹ምንም ነገር በአንድ ቀን አያድግም የራሱ ሂደት አለው፤ አሁን እየተገነባ ያለው ቡድን ወጣቶችና ልምድ ያላቸው ተጫዋቾች ያሉበት ነው:: በመሆኑም ሃገራት የሚታወቁበት አንድ ነገር እንዳለ ሁሉ እኛም የራሳችንን ቀለም ለመፍጠር ጥረት እያደረግን እንገኛለን:: በአንድ ቀን መስራት ባይቻልም በሂደት ወደዚያ ለመሄድ በመሆኑ በቀጣይ አፍሪካ ዋንጫ ላይ የተሻለ ቡድን ይዘን እንቀርባለን›› ሲሉም ሃሳባቸውን ያካፍላሉ::
ህዝቡ ደስታውን ሲወጣበት የነበረው መንገድ ምን ያህል ደስታ ተጠምቶ እንደነበር የሚያሳይ መሆኑን የሚጠቁሙት ደግሞ የፌዴሬሽኑ ፕሬዚዳንት ኢሳያስ ጅራ ናቸው:: በቀጣይ መሆን የሚገባውን ሲያመላክቱም ‹‹አሰልጣኝ ውበቱ አባተ ተሳታፊ መሆን ብቻውን ግብ አለመሆኑን አውቆ በቀጣይ ካሜሮን ላይ ጠንካራ ተፎካካሪ ለመሆን የሚያስችል ዕቅድ ያዘጋጃል የሚል እምነት አለኝ:: ይህ ድል ቀጣይነት እንዲኖረውም ሁሉም የየራሱን የቤት ስራ መወጣት አለበት›› ብለዋል::
ዋሊያዎቹ ወደ ሃገራቸው ሲመለሱ ደማቅ አቀባበል ተደርጎላቸዋል፤ በቀጣዩ ቀንም በአዲስ አበባ ከተማ ዋና ዋና ጎዳናዎች ላይ በመዘዋወር በስስት ከሚመለከታቸው የስፖርት ቤተሰብ ጋር ደስታውን ተጋርተዋል:: ዋሊያዎቹ ባለፉባቸው ጎዳናዎች ወጣቶች በሩጫ አጅበው ሲከተሉ፣ በመንገድ ዳርና ዳር ቆመው በጭብጨባና ሆታ ደስታቸውን ሲገልጹ፣ በህንጻዎች ላይ ሆነው ሲያበረታቱና በእጅ ስልኮቻቸው ታሪኩን ቀርጸው ለማስቀመጥ ሲሞክሩ፣ መኪኖችም በጥሩምባቸው ከተማውን ሲያደምቁት ነበር:: በሰንደቅ ዓላማ የታጀቡት የቡድኑ አባላትም ለሃገራቸው ያላቸውን ፍቅርና ደስታቸውን በማዜም ጭምር ሲገልጹ ታይተዋል
አዲስ ዘመን መጋቢት 26/2013