አስመረት ብስራት
በሀገራችን ፊልም መሰራት ከተጀመረ አንስቶ የተለያዩ ውጣ ውረዶችን እያለፈ መሆኑን የፊልሙ ኢንዱስትሪ ውስጥ ያሉ አካላት ሲናገሩ ይሰማል። ተመልካቹም በሚሰሩት ፊልሞች ላይ የመሰለውን አስተያየት ሲሰጥ ይሰማል። በተለይ ግን ‹‹መልክ የሌላት ሴት ፊልም መስራት የለባትም›› የተባለ ይመስል በጣም የሚያማምሩ እንቦቀቅላ ወጣቶችን በፊልሙ መስኮት ብቅ ሲሉ መመልከት እየተለመደ ሆኗል።
እናም እነዚህ ቆነጃጅቶች ወደ ፊልሙ ሲገቡ ቅድሚያ የሚቀርብላቸው የፆታ ጥያቄ ነው። ያ ስለምን ሆነ? የሚሉ አስተያየቶች ከየቦታው ሲሰነዘሩ ይሰማሉ። ተስፋ የሚጣልባቸው የህብረተሰቡ ግማሽ አካል የሆኑ ወጣት ሴቶችን ተስፋ የሚያጨልም፣ የነገን ብሩህ ተስፋ እንዳይመለከቱ ስለሚያደርጋቸው በአደባባይ ስለሚነገረው ሚሰጥር ሰለባ ሆነሽ ነበረ ወይ? ብለን የጠየቅናት ወጣቷ ተዋናይት ሊድያ ሞገስ ‹‹ሰው የራሱ መስመር ኖሮት የራሱን ክብር እየጠበቀ እስከሄደ ድረስ የሌሎች ተፅእኖ ሰለባ መሆን አያሳስበውም›› ትላለች።
ሊድያ ሞገስ በአብዘኛው በመጀመሪያ ፊልሟ ‹‹በላምባ›› እጅግ በጣም የምትታወቅ ልጅ ናት። የኩላሊት ህመምተኞችን ህመም አስመስላ ሳይሆን የእውነት ታማ የፊልም ተመልካቹን በእንባ ያራጨች፤ ገና በጥዋቱ የወጣትነት እድሜ መጀመሪያ ላይ ትወናን በብቃት የተወጣች ጠንከራ ወጣት ናት።
በልጅነቷ በትምህርትም ሆነ በተለያዩ እንቅስቃሴዎች ተሳታፊ እንደነበረች ታስረዳለች። ሚኒ ሚድያ ውስጥ ለረዥም ጊዜ መሳተፏ በትምህርት ቤት ያሉ በርካታ እንቅስቃሴዎች ውስጥ መሳተፏ በራስ መተማመኗ ከፍተኛ እንዲሆን አድርጓታል። ከወላጆቿ ጋር ያላት ግንኙነትም በአግባቡ የፈለገችውን መርጣ ለመኖር እንዳገዛት ትናገራለች።
ትክክለኛ የአስተዳደግ መስመርን የተከተለ፤ የልጆች ውሎ፤ ጓደኞች ሙሉ የልጆች እንቅስቃሴን፤ በአግባቡ የሚከታተል የንስር አይን ያለው ቤተሰብ በዚህም ላይ ምንም አይነት ጫና ሳያደርስ ጎጅውንና ጠቃሚውን እየነገረ በአግባቡ እየቀጣና እያስተማረ ያሳደገ ቤተሰብ ውስጥ ነው ያደገችው።
ሊድያ ሞገስ ተወልዳ ያደገችው አዲስ አበባ 22 ማዞሪያ አከባቢ ነው። ሁለት ተከታይ እህቶች አሏት። ሊዲያ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ኮሜርስ ካምፓስ የአራተኛ አመት የቢዝነስ አድሚንስትሬሽን ተማሪ ናት።
ይህች ወጣት ብዙ ፊልም መስራት ህልሟ ነው። የራስዋን ፊልም ሰርታ ለተመልካች የማቅረብ ሀሳብም አላት፤ ነገር ግን እስካሁን የሰራችው ፊልም ‹‹ላምባንና ህዳር›› የሚሉ ፊልሞችን ብቻ ነው። ትምህርት፥ ስራ፥ ወላጆችን ማገዝ፥ በወጣትነት ብዙ ነገሮችን በነፃነት ለመሞከር በመጣጣር ጊዜዋን የምታሳልፍ ወጣት ነች።
በ‹‹ላምባ›› ፊልም ምርጥ ትወናን አሳይታ በሰዎች አእምሮ ውስጥ ተቀርፃ የቀረችው ይህች ወጣት የመጀመሪያው ፊልሟ ከወጣ ብኋላ በምን አይነት የአኗኗር ዘዬ ውስጥ እየኖረች እንደሆነ፣ ሴትነት ከፊልም ባለሙያነት ጋር ተያይዞ ያለባት ጫናዎች እንዴት እንደሚገለፁ እና ሌሎች ጉዳዮችን አንስተን እንዲህ ተጨዋውተናል። መልካም ንባብ።
ወጣት ሊዲያ ነጋዴ ናት። በዚህ እድሜዋ ሰርቶ የማግኘትን ጥቅም ቀድማ ተረድታለች። የተለያዩ የሴቶች አልባሳት መዋቢያዎችን ለተወሰነ ጊዜ ስትሸጥ ከቆየች በኋላ፤ እናቷ ከታች አንስቶ እየሰራች ያሳደገችውን ሽሮ ቤት በተሻለ መልኩ አስፋፍታ የመስራት ሀሳብ ሰንቃ እየተንቀሳቀሰች ትገኛለች። ሽሮን ለተለያዩ ሀገሮች በመላክ የውጭ ንግድ የመሰራት ሀሳብም አላት።
‹‹በአሰራ ሰባት አመት እድሜዬ ነው ወደ ፊልም ስራ የገባሁት። ያኔ ስራና ትምህርት የየራሳቸውን ጊዜ ተሰጥቷቸው እንዴት መሄድ እንዳለባቸው በበቂ መልኩ ለመማር ስለቻልኩኝ አሁን ከዩኒቨርሲቲ ትምህርት ጎን ለጎን የተለያዩ ሰራዎችን እሞክራለሁ›› የምትለው ሊድያ” ‹‹ትምህርቱ ራሱ ከንግድ ስራ ጋር የተገናኘ ስለሆነ ምንም አይነት ችግር አልገጠመኝም።›› ትላለች።
ወላጆቿ ቤተሰቡን በበቂ መልኩ ለማኖር የሽሮ ንግድ ውስጥ ገብተው በሚችሉት አቅም ወደ ተሻለ ደረጃ ለማድረስ ጥረት ሲያደርጉ የቆዩ ሲሆን እሷም የራሷን አስተዋፅኦ ለማድረግ በመጣጣር ላይ የምትገኘው ይህች ወጣት አዲስ ንግድ ለመጀመር መሰረት የያዘውን ወደ ታሻለ ደረጃ ለማድረስ ትታገላለች። ስራው በቀጣይ 20 አመታተ ሳይቋረጥ አድማሱን አስፍቶ ለማስቀጠል ለመጣር አቅዳለች።
ሊዲያ ከአስረኛ ክፍል ወደ አስራ አንደኛ ክፍል በተዛወረችበት ዓመት ገና የአስራ ሰባት አመት ታዳጊ በነበረችበት ወቅት ምንም አይነት የፊልም የመስራት ልምድ ሳይኖራት ነበር ‹‹ላምባ›› ፊልምን የሰራችው።
የቤተሰብ የምረቃ ፕሮግራም ላይ ታድማ በሄደችበት ወቅት የ‹‹ላምባ›› ፊልም ኤዲተር ኤፍሬም ምስጋና ልክ እንደተመለከታት ሊሰሩት ያሰቡት ፊልም ላይ ልትተውን የምትችል ልጅ ማግኘቱን የተረዳው። እዛው ላይ ነበር እንደዚህ አይነት ፊልም አለ እዛ ላይ መስራት አለብሽ ብሎ ስልኳንም ፎቶዋንም ተቀብሎ የሄደው። ለሌሎቹ የስራ ባለደረቦቹ በምርጫ ያሰቀመጠው ፎቶግራፍ ተመልክተው ይመርጥዋታል። ከዚህ በኋላ ነበር ወደ ፊልም መስራት ሂደት የገባችው። መጀመሪያ ፊልሙን ለመጀመር ቤተሰብ ማሳመን ከባድ እንደነበር ትናገራለች። እናት ብትስማማም አባቷን ለማሳመን የተወሰነ ጊዜ እንደወሰደባት ትናገራለች።
እንደ እድል ሆኖ በትክክለኛው መንገድ ተጉዛ ወደ ፊልሙ የተቀላቀለችው ሊዲያ በመጀመሪያ ፊልሟ ላይ የነበሩት አሰሪዎች በጨዋነትና በአክብሮት የተሞሉና ሀላፊነት የሚሰማቸው በመሆናቸው ወላጆቿ መልካም ነገሩን አይተው ወደ ፊልም ኢንዱስትሪው እንድትቀላቀል መፍቀዳቸውን ታስረዳለች።
”ከዛ በኋላ ግን ፊልም ለመስራት አልቻልኩም ነበር” የምትለው ሊድያ ፊልሙን ከሰራች በኋላ በብዙ ሰዎች መታወቅ፤ ከዛ የጉማ ሽልማት ላይ ተስፋ የሚጣልባት ወጣት ተዋናይት ተብላ መሸለሟ ከባድ ሀላፊነትን ያሸከመ በመሆኑ የተሻሉ አስተማሪና በጥሩ መንገድ ተቃኝቶ ለኢትዮዽያዊያን የሚመጥን ፊልም ለመሰራት መነሳቷን ትናገራለች።
ፊልም ባልሰራችባቸው አራት አመታት ውስጥ ትምህርት፣ የተለያዩ ስራዎችን ለመስራት የሞከረቻቸው ዝግጅቶች እና ከፊልም ጋር የሚመጡ ሌሎች ያልተገቡ ሁኔታዎች ይዘዋት እንደነበር ትናገራለች። ፊልም እንደ ፊልም በትክክለኛው መንገድ ተሰርቶ የሚወጣ ሳይሆን ሲቀር፤ ከጀርባው የሆነ ነገር የሚከፈልበት ከሆነ ራስንም ህብረተሰብንም ያዋርዳል። ራሱን ያላከበረ ተዋናይ ህብረተሰቡን አክብሮ አርአያ ሊሆን አይችልም። በተጨማሪም እንድትሰራ የተጠየቀችባቸው ፊልሞች ከትምህርት ፕሮግራሟ ጋር መጣረሱ እንዲሁም መጀመሪያ በታየችበት ካራክተር ልክ የበሰለ ፊልም ባለማግኘቷ ለአመታት ፊልም ሳትሰራ መቆየቷን ሊዲያ ትናገራለች።
ፎቶ ማንሳት፥ የልብስ ዲዛይን ማድረግ፥ ማብሰል፥ ማርሻል አርት መስራት፥ የተለያዩ ስራዎች ላይ መሳተፍ የህይወት ጉዞዋ አካል መሆኑን ትናገራለች። ”ብዙ ጊዜ እናቴ እኔ በህይወት እያለሁ ተጠቀሙብኝ መሆን የምትፈልጉትን ነገር በሙሉ ለመሆን አሁን እኔ እቅፍ ላይ እያላችሁ ጣሩ ትለናለች ̋ የምትለው ሊድያ ̋እናቴ አጠገቤ እያለች መሆን የምችለውን በትክክለኛ መስመር ላይ ለመቆም ሁሉንም ሞካሪ፣ ሁሉንም መስራት አለብኝ” በማለት ጥረቷን ትገልፃለች።
በጄ ቲቪ ላይ ይተላለፍ የነበረ የመዝናኛ ፕሮግራም ላይ አስተዋዋቂም እንደነበረች የምትናገረው ሊዲያ “ባሳለፍኳቸው አራት አመታት ውስጥ ከፊልም ውጪ የተለያዩ ነገሮችን በመሞከር፣ በምን በኩል ውጤታማ እንደምሆን፣ በምን በኩል ደግሞ ውጤታማ ልሆን እንደማልችል፣ ለምን እንደተፈጠርኩ የነፍሴ ጥሪ የቱ እንደሆነ ሳስብ ያመላከቱኝን ሙከራዎች አድርጊያለሁ።” ትላለች።
በኋላም ‹‹ህዳር›› የሚባል ፊልም ላይ ሰርታለች። በዚህ ፊልም ላይ ረዳት ተዋናይት ሆና የተሳተፈችው ይህች ወጣት ፊልሙ የአንድነት ሀሳብ ያለው ጠንካራና የተለያየ አይነት ጥሩ ማንነትን የሚየሳይ ከመሆኑም በላይ የዘንድሮው የጉማ አዋረድ ላይ በጣም የተዋጣለት የማጀቢያ ሙዚቃን ዘርፍ የወሰደ ፊልም ነው። እንደ እድል ሆኖ ወጣቷ ተዋናይት የተሳተፈችባቸው ሁለቱም ፊልሞች ጉማ ሽልማት ላይ የቀረቡ ሲሆን በአንድ ዘርፍ የተሸለሙ መሆናቸው ወደፊት የተሻለ አይን የሚገባ ፊልም እንደምታሳየን ተስፋ ሰጥቷል። ይህም እውነትም ተስፋ የሚጣልባት ተዋናይት መሆኗን ያመላከተ ነው።
ወጣት ሴት በፊልም ኢንዱስትሪ ውስጥ ብዙ ተግዳሮቶች ይገጥሟታል። በህይወት ተሞክሮ ውስጥ ሁልጊዜ ሁለት መንገዶቸ ይገኛሉ። አንዱ በውጣ ውረድ በልፋት በድካም የሚገኝ ሲሆን አንዱ ደግሞ አቋራጭ መንገድ ነው። ይህ ደግሞ ትክክልና ትክክል ያልሆነ ብለን እንለየዋለን።
የሁሉም ሰው ስኬት የተለያየ ነው። ለሊዲያ ስኬት ማለት ራስንን መሆን ነው፣ ራስን ፈልጎ ማግኘት ነው። ሁሉም ቦታ ሞከር ሞከር አድርጎ ብቻ ያልበሰለ ነገር ይዞ መምጣት የእለት ስኬትን ብቻ ማሳደድ ይሆናል። ራስን ፈልጎ አለማግኘትና እራስ ሆኖ አለመገኘት ለወንድም ለሴትም በወጣትነት ላይ የሚታዩ ችግሮች ናቸው።
አንደ ሰው ራሱን ችሎ ሰርቶ አቅሙን አጎልብቶ ራሱ ብቁ መሆኑን ካመነ በኋላ ሌሎችን በተግባር ለማሳመን አይቸገርም። ወጣትነት ያለውን አቅም በመጠቀም ራስን ወደ ከፍታ ማሳደግ ብሎም ያንን ለማድረግ ጥረትና ሙከራ ያስፈለጋል። የብዙ ወጣቶች ችግር ደግሞ ራስን ከሌሎች ጋር በውድድር ውስጥ ማስገባት ነው። ይህ ማለት አንድ ሰው በራሱ ማንነት ውስጥ የራሱ የሆነ ድንቅ ብቃት እያለው ራስን ከሌሎች ጋር ወድድር ውስጥ ማስገባት ትክክል ያልሆነ ማንነት ነው።
ጥበብን ውድድር ውስጥ ማስገባት ልክ አይደለም። የጥበብ ሰው አርቲስቱም፣ ዘፋኙም ሌላውም የጥበብ ሰው ታሪክ ነጋሪ ነው። ማንም በማንም መለኪያ የማንም መስፈርት መሆን አይችልም። ስለዚህ ሁሌ እጁ ላይ የደረሰውን ስራ በምን መልኩ በብቃት ማንነትን በጠበቀ መልኩ አውጥቼ ስራዬን በአግባቡ እሰራለሁ በሚል አስተሳሰብ ወጣቱ ተቃኝቶ ራሱን ለመሳደግ መነሳት ይኖርበታል።
ሴቶች እንደ ሴት በተለያዩ ተፅዕኖዎች ስር ያልፋሉ። በተለይ በፊልም ኢንዱስትሪ ፕሮፌሽናል ያልሆነ፤ ትምህርት፤ በቂ ብቃት፤ ለፊልም የሚገባ እውቀት የሌላቸው ሰዎች በፊልም ኢንዱስትሪው ውስጥ አሉ። እነዚህ ሰዎች ሁሌም ከስር ያሉ ሰዎችን በእውቀታቸው ልክ ሳይሆን በገንዘባቸው ሊገዟቸው ይሞክራሉ። ሴቶች በተለይም ወጣት ሴቶች ለምን ለአመታት አንጠብቅም፣ ፊልም መስራት ህልማቸው ከሆነ የግድ ወጣት፣ የግድ ቆንጆ፣ የልጅነት እድሜ ላይ መሆን አይጠበቅም። አንድ ልጅ በአስር አመቱም እድሜውን ሊመጥን የሚችል ካራክተርን መጫወት ይችላል። ሴቶች በራስ ተማምነው ሳይቸኩሉ አቋራጮችን ሳይጠቀሙ ወደፊት ለመሄድ መነሳት ይኖርባቸዋል።
ቀድመው ወደ ኢንዱስትሪው የገቡ ሴቶችም እነሱ ያለፉበትን ውጣ ውረዶች በማሳየት አዲስ ወደ ፊልሙ ኢንዱስትሪ የሚገቡትን ማስተማር፣ ማብቃት፣ መሞረድ፣ መደገፍ ተገቢ ነው። ሁሌም የተሻለ ሰው መስራት ለወደፊት የተሻለ መንገድ መጥረገያ መሆኑን ሊዲያ ትናገራለች።
አዲስ ዘመን መጋቢት 26/2013