በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)
fenote1971@gmail.com
በዚያ ሰሞን ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ከመጸሐፋቸው ሽያጭ 200 ሺ ብር ከአንድ ወር ደመወዛቸው ጋር እንዲሁም ሦስት ቦቲ መኪናዎችን ለንጹህ መጠጥ ውሃ ማመላለሻ ለግሰዋል። ሰሞኑን ደግሞ የኦሮሚያ ፣ የጋምቤላ፣ የቤኒሻንጉል ጉምዝ ክልሎች 282 ሚሊዮን ብር መቐለ በመገኘት በመለገስ አለኝታነቸውን አረጋግጠዋል። የኢፌዴሪ ትምህርት ሚኒስቴር በተለይ ለትምህርት ዘርፉ መልሶ ግንባታ 320 ሚሊዮን ብር በጀት አዙሮ እየሰራ ይገኛል ። ከዚያ በፊት የአፋርና ሌሎች ክልሎች እንዲሁም የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እና የተለያዩ ተቋማት ለትግራይ ሕዝብ የገንዘብና የተለያዩ የዕለት ደራሽ ድጋፎችን አድርገዋል ። የፌዴራል መንግስት ከ4 ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑ ወገኖች እርዳታ ያቀረበ ሲሆን አለምአቀፍ ግብረ ሰናይ ድርጅቶችም የጩኸታቸውን ያህል ባይሆንም መጠነኛ ድጋፍ እያደረጉ ነው።
ይህ አኩሪ የተቀናጀ ርብርብ ዜጎችን ከርሀብና ከጠኔ ከመታደጉ ባሻገር የትግራይ ሕዝብ በክፉ ቀኑ የሚደርስለት አለኝታ መንግስትና ወገን እንዳሉት ከማረጋገጡ በሻገር የትህነግን የፈጠራ ትርክት እርቃን ያስቀረ ሰናይ ተግባር ነው። እጣ ፈንታውና መጻኢ እድሉ ከትህነግ ጋር እንዳልነበረና እንዳልሆነ ያሳያል ። የክልሉ የብልጽግና ፓርቲ ከፍተኛ አመራር አቶ ሀጎስ ወልደኪዳን ሰሞኑን በተለይ ለአዲስ ዘመን ፤”ህዝቡን አቅርቦ ማወያየትና ከጎኑ እንዳሉ ማሳየትም ከምንም በላይ ተገቢ ነው ፤ “ሲሉ ያስገነዘቡት ለዚህ ነው። የሕግ የበላይነትና የህልውና ዘመቻው ከሞላ ጎደል በድል የተጠናቀቀ ቢሆንም በዲፕሎማሲውና በሕዝብ ግንኙነቱ አውደ ውጊያ ግን ለጊዜውም ቢሆነ እንደ መንግስትም ሆነ ሕዝብ በውሸት ትርክታችንን ተነጥቀናል። ይህ ንጥቂያ የትግራዋይን ልብም እንዳያሳጣን በችግሩና በመከራው ከጎኑ መሆናችንን ደግመን ደጋግመን ማረጋገጥ አለብን ። የትግራዋይን አእምሮና ልቦና በፍቅር ፣ ያለንን በማካፈል በማጽናናትና ፍቅር በመስጠት መማረክ ይጠበቅብናል። የሕግን የበላይነት ከማረጋገጥና ከህልውና ዘመቻው ያልተናነሰ የፍቅር ዘመቻ መሆኑን አጢኖ በወረት ሳይሆን ቀጣይነትና ዘላቂነት ባለው አግባብ መስራት ይጠይቃል። ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር እንዳሉት ታሪክን ወይም የቀደመውን ወዲያው የመዘንጋትና የመርሳት አባዜ ስላለብን ዛሬም በድጋሜ የሕግ የበላይነት ዘመቻውን በድል አጠናቀን የትግራዋይን ልቦናና አመለካከት ማሸነፍ ካልቻልን ድሉ ምልኡ አይሆንምና በጥበብና በማስተዋል እንስራ ስል በአክብሮት ደግሜ አሳስባለሁ።
ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይ ወደ መሪነት ከመጡበት ሰዓት አንስቶ በትግራይ ክልል ይህ ቀውስ እንዳይቀሰቀስ እፉኝቱንና መዥገሩን ትህነግ ለማግባባት ያልፈነቀሉት ድንጋይ አልነበረም። ያላደረጉት ጥረት የለም ። ከባዕለ ሲመታቸው የፓርላማ የመጀመሪያ ንግግር እስከ ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም ትህነግ ታላቁንና የክፍለ ዘመኑን ክህደት በሰሜን ዕዝ ፣ በሉዓላዊነታችንና በሀገራችን ለመፈጸም ዝግጅት እያደረገ እስካለባት የመጨረሻዎቹ ሰዓታት ድረስ ልዩነቱ በሰላም ይፈታል የሚል በተስፋ ላይ ያነጣጠረ ተስፋ ነበራቸው ። በዚሁ ምሽት ከዛን ጊዜው የክልሉ ርዕሰ መስተዳደር ከዛሬው በረኸኛ ሽፍታ ጋር በስልክ የክልሉን ኢኮኖሚ ለማነቃቃት ስለተያዙ እቅዶች ከተወያዩ በኋላ አዲሱን የብር ኖት ለማድረስና አሮጌውን ብር ለማምጣት ሁለት የኢትዮጵያ አየር መንገድ አውሮፕላኖች ምሽት መቀሌ አርፈዋል ። ይሁንና ይህ ቡድን ከስልጣኑና ከዘረፋ ውጭ ለትግራይ ሕዝብም ሆነ ለክልሉ ልማት ደንታ ስለሌለው የከተማውን መብራት በማጠፋትና ኔት ወርኩን በማቋረጥ ጥርሱን የነቀለበትን ዘረፋ ለመፈጸም በአውሮፕላን ማረፊያው ተኩስ በመክፈት አዲሱን የብር ኖት ለመዝረፍ ያደረገውን ሙከራ መከላከያ ደርሶ አክሽፎታል።
ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ለሰላም ካላቸው ቁርጠኝነትና ጦርነት ምን ያህል አስከፊ እንደሆነ በውትድርና ህይወታቸው ጠንቅቀው ስለሚያውቁት ፤ ጓደኞቻቸውንና ወንድማቸውን ስለነጠቃቸው ፤ ጦርነት የሀገርን ኢኮኖሚ ምን ያህል እምሽክ ድቅቅ እንደሚያደርግና እንደሚያወድም አበክረው ስለተገነዘቡና ፤ የትግራይ ሕዝብም ጦርነት ይበቃዋል በሚል እምነትና የጦርነት ነጋሪት የሚጎስሙ ኃይሎች የድሀን ልጅ የእሳት ራት ያደርጋሉ እንጂ እነሱ አይዋጉም በማለት ለትግራይም ሆነ ለሌሎች ሕዝቦች ደህንነት ሲሉ እስከ መጨረሻው ሰዓት ሆደ ሰፊነትንና ትዕግስትን መርጠዋል ። አበው ጎሽ ለልጇ ስትል ተወጋች እንዲሉ በከሀዲውና የእናት ጡት ነካሹ በሆነው ትህነግ መከላከያችን ፣ ሉዓላዊነታችን፣ ሀገራችንና ሕዝባችን ለሰላም በታመኑ ከጀርባ ተወጉ። ባጎረሱ ተነከሱ።
ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር አይደለም ጦርነትን ተራ ግጭት እንኳ ለመከላከል ሲሉ ኦነግና እነጃዋር ለያዥ ለገናዥ አስቸገርው እያለ ከዛሬ ነገ ይለወጣሉ ፣ ይመከራሉ ፣ ይዘከራሉ ሲሉ በሆደ ሰፊነትና አንዳንድ ጊዜም አይተው እንዳላዩ በማለፋቸው መንግስታቸው እንደደካማ በመታየቱ በአውሮፕላንና በአውቶብስ የገባው ኦነግ “ ማን የማንን ትጥቅ ያስፈታል !? “ እስከሚል እብሪት ደረሰ። የኦነግ ጭንግፍ የሆኑትና የከሀዲው ትህነግ ተላላኪዎች ሸኔ _ ኦነግና አባ ቶርቤ በምዕራብ ኦሮሚያ ፣ በቦረና ፣ በጉጂ ፣ በወለጋ ዞኖችና በሌሎች የክልሉ ከተሞች በኦሮሞና በአማራ ሕዝቦች ላይ ለማየት የሚዘገንን ለመስማት የሚሰቀጥጥ ጭካኔ የተሞላበት ግፍ ፈጽመዋል ። ሰሞኑንም ኦነግ_ሸኔ ህጻናትና ሴቶች ሳይቀሩ ሆሮጉድሩ ላይ ተመሳሳይ ዘግናኝ ጭፍጨፋ ፈጽመዋል ። እነ ጃዋርም ተከታዮቻቸውንና ደጋፊዎቻቸውን በተሳሳተ ትርክትና መስመር በማነሳሳት በኦሮሚያ ክልል አንድን ብሔርና እምነት ኢላማ ያደረጉ ተደጋጋሚ ጭፍጨፋዎች ንጹሐን ላይ ሊፈጸሙ ችለዋል። ከመስከረም 25 በኋላ መንግስት የለም የሚለውን ጀብደኝነት ጨምሮ ሕገ መንግስቱን በኃይል እስከመናድ በመንቀሳቀስ የመጨረሻውን ቀይ መስመር አለፉ።
ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ሀገሪቱን ከጠብ መንጃ አዙሪት ለማውጣትና ከዚህ ቀደም የነበሩ ገዥዎች ያልሄዱበትን የሆደ ሰፊነትና ቁጭ ብሎ የመነጋገር መንገድ በመምረጣቸው በልኩ እውቅና ሊሰጣቸውና አብዛኛው ዜጋ ከጎናቸው ሊቆም ሲገባ መንግስታቸው በልፍስፍስነት ከመወቀሱ ባሻገር ፓርቲያቸውም ሆነ እሳቸው ቁጥሩ ቀላል ያልሆነ ደጋፊያቸውና ተከታያቸው ብዥታና ድንጋሬ ላይ እንዲወድቁ አድርጓል ። ይሁንና የእፉኝቱ ትህነግ የጥቅምት 24ቱን ታላቅ ክህደት ተከትሎ የሕግ የበላይነትን ለማስከበርና የሀገር ህልውናን ለማስቀጠል ያሳዩት ቁርጠኝነት እና ሰራዊቱ ከተፈጸመበት ታሪክና ትውልድ ይቅር ከማይለው ክህደት በኋላ ሞራሉና ወኔው አንሰራርቶ በእልህና በቁጭት ተነሳስቶ እጅን በአፍ የሚያስጭን አንጸባራቂ ድል በማስመዝገብ ላይ ነው ። እፉኝቱ ትህነግ ይታበይበትና ይመካበት የነበረውን ልዩ ኃይልና ሚሊሻ አይቀጡ ቅጣት እየቀጣ መቀሌን በዘጠኝ ቀናት ውስጥ ነጻ ማውጣት ችሏል ። ዘጠኝ ያልሁት እጅ የመስጫ ሁለቱን ቀነ ገደቦች ማለትም ስድስቱን ቀናት ቀንሼ ነው።
የሀገራችንን ፓለቲካና ታሪክ እንደ አዲስ የሚበይን፤ የሀገሪቱን ህልውና በጽኑ መሰረት ላይ የሚያኖር እና መጻኢ እድሏን ወገግ የሚያደርገው ይህ አንጸባራቂ ድል የተመዘገበው በእሳቸው እና በየደረጃው ያለው ወታደራዊና ሲቭል አመራር የተንሰላሰለና የተቀናጀ ብልህ አመራር በመስጠቱ ነው። የአለም ታሪክ እንደሚያስታውሰን ጦርነትና የቀውስ ጊዜ የሀገራት መሪዎች ተቀባይነት የሚወሰነው ጦሩነቱ በመሩበት ስልትና ባስመዘገቡት ድልና ቀውሱን በፈቱበት አግባብ ነው ። ከዚህ አንጻር ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሆኑ ሰራዊቱ በአብዛኛው ኢትዮጵያዊ ዘንድ አድናቆት እያተረፉና ምስጋና እየጎረፈላቸው ነው። በአራቱም የሀገሪቱ ማዕዘናት ሕዝቡ ያለ ልዩነት ደጀንነቱን ማረጋገጡ ለዚህ ጥሩ ማሳያ ነው። ከፍ ብዬ ለማንሳት እንደሞከርሁት እሳቸውም ሆኑ መንግስታቸው ለሰላም ፣ ለሆደ ሰፊነት፣ ተቀራርቦ ለመነጋገርና ሀገሪቱም ሆነ የትግራይ ሕዝብ ጦርነት ይበቃቸዋል በማለታቸው ያጡትን ተቀባይነትና ተከታይ ብቻ ሳይሆን ዳር ቆመው ለውጡን በመጠራጠር ያዩ የነበሩትን ሳይቀር አቋማቸውን እንደገና እንዲመረምሩ አድርጓቸዋል። የትህነግን ፣ የኦነጎችን ( ቢያንስ ስድስት በኦነግ ስም የሚንቀሳቀሱ ስብስቦች እንዳሉ ስለሚነገር ነው፤) እና የእነ ጃዋራን ልብና አመለካከት ለማሸነፍ ስንት ዋጋ የተከፈለበት ጥረት በምታውቁት መንገድ ተጠናቋል። እየተጠናቀቀ ነው ። የሕግ የበላይነትን የማረጋገጥና የህልውና ዘመቻው በአንጸባራቂ ድል እንደተጠናቀቀ የትግራዋይን ልብና አእምሮ በሰላምና በፍቅር ለመማረክ ዘመቻው ተጠናክሮ ቀጥሏል ። ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትርና መንግስታቸው ድንጋዩንና በእብሪት የተደፈነውንና የትህነግ ልብ በሰላምና በፍቅር ለማራራት ያደረጉት ጥረት ባይሳካም ክልሎችም ሆኑ መላ ኢትዮጵያውያን ከትግራይ ሕዝብ እንዲቆሙ ጥሪ በማድረግና በማግባባት የትግራይን ሕዝብ ልብ የሚያማልሉ በርካታ ተግባራትን እያከናወኑ ይገኛል ።
ፈጣሪ ከብልቶቻችን ሁሉ ያስቀደመው ልባችንን ነው። እንደ ፈሪሳውያንና ሰዱቃውያን ሁሉ እንደ የሕግ አዋቂ ፈጣሪን ሊፈትነው ፤ “ መምህር ሆይ ፥ ከሕግ ማንኛይቱ ትእዛዝ ታላቅ ናት? ብሎ ጠየቀው። “ ፈጣሪም በታላቁ ቅዱስ መጽሐፍ ማቴዎስ 22 ÷ 37 _ 38 ላይ እንዲህ ሲል ይመልስለታል ፤ “ ጌታ አምላክህን በፍጹም ልብህ በፍጹም ነፍስህም በፍጹም አሳብህም ውደድ ። ታላቂቱና ፊተኛይቱ ትእዛዝ ይህች ናት ። “ በዚህ ታላቅና ቀዳሚ ትዕዛዝ እየሱስ ክርስቶስ ከነፍስም ሆነ ከአሳብ በፊት ልብን እንዳስቀደም እንረዳለን ። የ32ኛው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት የፍራንክሊን ዴሎን ሮዝቬልት ባለቤትና ቀዳማይ እመቤት ኤሌንኖር ሮዝቬልት ፤ ሮዝቬልትን ጨምሮ የበርካታ ፕሬዚዳንቶች አማካሪና ሊቅ የነበረውን በርናንድ በሩክ፤ “ አእምሮዬና ልቤ በሀሳብ ቢለያዩ ማንኛውን ልከተል !? “ ስትል ትጠይቀዋለች፣ እሱም ያለምንም ማወላወል ፣” ልብሽን ተከተይ“ ሲል ይመልስላታል ። እነዚህ መንፈሳዊና አለማዊ ዋቢዎች ልብ በሰው ልጅ ዘንድ ያለውን ከፍ ያለ ስፍራ ያሳያል።
ይህ ሕግን የማስከበርና የህልውና ዘመቻ ሶስት ግንባሮች አሉት ። የመጀመሪያው ከእፉኝቱና ከሀዲው ልዩ ኃይልና ሚሊሻ ጋር ሲሆን ፤ ሁለተኛው ደግሞ ሀሰተኛ ፣ የተዛባና በሴራ ኀልዮት የተለወሰና የተበረዘ መረጃ ከሚነዛው የትህነግ መደበኛና ማህበራዊ ( ዲጂታል ወያኔ ) ሚዲያ ጋር ነው። ስለ እነዚህ ሁለት ዘመቻዎች በዚሁ ጋዜጣ ቀደም ባሉ ተከታታይ እትሞች አስነብቤያለሁ ። ሶስተኛው ዘመቻ ደግሞ ትህነግ ላለፉት 50 አመታት በአንድ ለአምስት አደረጃጀት ጠርንፎ በስሙ ሲነግድበት ፣ ሲምል ሲገዘትበትና በፈጠራ ትርክት ፣ በአስገድዶ ማጥመቅ ( ኢንዶክትሬሽን) እና በፕሮፓጋንዳ ያለ ፈቃዱ ሲወቀር ፤ የልቦና ውቅሩንና ኢትዮጵያዊነቱን ሲያስጥለው የኖረውን የትግራዋይ ልብ የመመለስና የመማረክ ዘመቻ ነው።
በዲፕሎማሲው መልክዓ ከ30 አመታት ወዲህ ብቅ እንዳለ የሚነገርለት የመማረክ ወይም የማግባባት ጥረት ( የሶፍት ፓወር ) መንግስታት እንዴት በሌሎች ሀገራት ላይ ተፅዕኖ እንደሚያሳድሩ ለመረዳት የማይተካ ሚና እንዳለው መስከረም መግቢያ ላይ ለንባብ የበቃው “ ፎሪን ፓሊሲ “ መጽሔት ያትታል ። አሜሪካዊው የፓለቲካ ሳይንቲስት ጆሴፍ ኔይ ፤ ሶፍት ፓወር አንድ ሀገር በምትከተለው የፓለቲካ ስርዓት ፤ ፓሊሲ ፣ እሴቶች እንዲሁም በሲቭል ማህበረሰቧና በባህሏ አማካኝነት ሀገራትን የመማረክና የመሳብ ዲፕሎማሲያዊ ሀቲት ነው ። የሕዝቦችን አእምሮና ልብ በመማረክ ( አትራክሽን ) ላይ የተመሰረተ የዲፕሎማሲ አይነት ነው ። ሀርድ ዲፕሎማሴ ከዚህ በተቃራኒው ወታደራዊ ኃይልንና ጉልበትን የሚጠቀም ነው ። አሜሪካ የሳዳምን በማስከተል የታሊባንን አገዛዞች በጦር ሜዳ ማንበርከክ ብትችልም ፤ የኢራቃውያንንና የአፍጋኒስታውያንን ልብና አእምሮ መማረክ ላይ ባለመስራቱ ተልኮውና ሙሉ በሙሉ ሊያሳካና ግቡን ሊመታ አልቻለም ። ሶፍት ፓወር ምን ያህል ወሳኝ ሚና እንዳለው ከዚህ መረዳት ይቻላል ። የአሜሪካ ዴሞክራሲ ፣ እሴቶች ፣ ኢኮኖሚያዊ ብልጽግና ፣ የሰላም ጓድ ፣ ዩኤስኤይድ ፣ ሆሊውድ ፣ የትምህርት ተቋማት ሙዚቃው ፣ ወዘተረፈ የሀገራትን ልብና አእምሮ መማረኪያ የሶፍት ፓወር አካል ናቸው።
እንደ መውጫ
እንደ ፈርኦን ልቡ በእብሪትና በግፍ ደንድኖ እና እንደ መቃብር ተዘግቶ እንጂ ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ የመጀመሪያውን የወይራ ዝንጣፊ ሀገር እየተመለከተና እያዳመጠ በግልፅ ለትህነግ የላኩት በመጋቢት 24 ቀን፣ 2010 ዓም የበዓለ ሲመት ንግግራቸው ነበር ። የሀገር ሽማግሌዎች ፣ የሀይማኖት አባቶች ፣ እናቶች ፣ ክብርት ሙፈራያት እያለቀሱ እግሩ ስር ወድቀው ለምነውት ነበር ። ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትርም ግፈኛው ፣ ዘራፊውና ሴረኛው ትህነግ ስራውን ስለሚያውቅና ለሌላ ዙር ጥፋት ለመዶለት በመማጸኛ ከተማው መክተት ጀምሮ እያለ ስለ እሱ ኃጢያት ተሸካሚ ሆነው የኢትዮጵያ ሕዝብን ይቅርታ ጠይቀውለት ነበር ። ከዚያ በኋላም በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ ስለሰላም፣ እርቅና አካታችነት ያላነሱበት ጊዜ አልነበረም።
ይህ ጽኑ አቋማቸው እሳቸውንም ፓርቲያቸውን ውድ ዋጋ አስከፍሏል። ለውጡ ግለቱን ጠብቆ እንዳይሄድ ተፅዕኖ እስከማሳደርና ለሴራ ፓለቲካ እንዲጋለጥ በር እስከመክፈት ደርሶ ነበር። የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መረጃ ማጣሪያ በዚያ ሰሞን ይፋ ባደረገው ሰነድ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ክልሉ በልማትና በሰላም ላይ እንዲያተኩር በተደጋጋሚ መክረዋል ዘክረዋል። ትህነግ በተደጋጋሚ በሰላማዊ መልኩ እንዲንቀሳቀስና ለውጡን ለትግራይ ሕዝብ ሰላም እንዲጠቀምበት ይፋዊ ሊባሉ የሚችሉ ወደ 20 የሚጠጉ ጥሪዎች የተደረጉለት ሲሆን ምላሹ ግን የጦርነትና የሽብር ነጋሪት መጎሰም ነበር ። እውነትና ንጋት እያደር ይጠራል እንዲሉ ለትግራይ ሕዝብ ግን ሀቁን የመገንዘብ እድል ያመቻቸ ነበር።
የለውጥ ኃይሉም የሕግ የበላይነትንና ሕልውና ከማረጋገጥ ጉን ለጎን የትግራይን ሕዝብ ልብና አእምሮ መማረክ የሚችሉ ስልቶችን ነድፎ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል። ይህ ታላቅ ኃላፊነት ለመንግስት ብቻ የሚተው ስላልሆነ ዜጎችና የግል ድርጅቶች ሊቀላቀሉት ይገባል።
ሀገራችን ኢትዮጵያ በሀቀኛ እና ጀግኖች ልጆቿ ታፍራና ተከብራ ለዘላለም ትኑር !!!
አሜን።
አዲስ ዘመን መጋቢት 5 ቀን 2013 ዓ.ም