ከላንዱዘር አስራት
ግራዝማች ዮሴፍ ንጉሤ የውጫሌ ውልን ወደ አማርኛ የተረጎሙና በውሉ ላይ በአማርኛና በጣሊያንኛ በተጻፈው መካከል ያለውን መሰረታዊ ልዩነት ያጋለጡና ለንጉሰ ነገስቱ በጥልቀት ያስረዱ ታላቅ ኢትዮጵያዊ ሊቅ ነበሩ፡-
ግራዝማች ዮሴፍ ንጉሤ ውልደታቸውና እድገታቸው ትግራይ የነበረ ሲሆን በኤርትራም የወቅቱን የቀለም ትምህርት ተከታትለዋል።
ኢትዮጵያ አንቀጽ 17 የውጫሌው ስምምነት ላይ፤ በጣሊያንኛ ቋንቋ የተጠቀሰውን የኢትዮጵያ ንጉስ ከውጭ አገራት ጋር የሚያደርጋቸውን ማናቸውንም ዲፕሎማሲያዊ ግንኑነቶችን ሁሉ፤ በጣሊያን በኩል ማድረግ ይኖርባታል የሚለውን ኢትዮጵያ ሉአላዊነቴን አሳልፌ አልሰጥም በሚል አልተቀበለችውም፡፡
ኢትዮጵያ ምስራቅ አፍሪቃን የመቀራመት ፍላጎታቸው ላይ ውሃ በሚቸልስ አኳኋን ስምምነቱን አሻፈረኝ በማለቷ፤ ጣሊያን የቅኝ ግዛት፤ የመስፋፋትና የበርሊን ኮንፈረስ አፍሪካን የመቀራመት አጠቃላይ ምኞን በወታደራዊ መንገድ ብቻ ለማሳካት ወሰነች።ሆኖም የውርደት ማቋን ተከናነበች፡፡
ኢትዮጵያ በጣሊያን ላይ በተጎናጸፈችው አንጸባራቂ ድል ምክንያት በዓለም ላይ የሚከተሉት የፖለቲካ ለውጦች ተከናውነዋል፤ ለዘመናት በዓለም ፖለቲካ ላይ የተጫነው የነጮች የበላይነት ዳግም ላያንሰራራ ተንኮታኮተ፤ በመላ አሜሪካ ከኢትዮጵያ ተሞክሮን በመውሰድ በይቻላል ስሜት የጥቁሮች የነጻነት ትግል ተቀጣጠለ፤ በኢስያ፤ በአውሮፓ እና በአፍሪቃ የአንገዛም ባይነት ሕዝባዊ እምቢተኝነቱ የትጥቅ ትግልን አካቶ በርትቶ ቀጠለ፡፡
እልፍ የሕይወት መስዋዕትነት ተከፍሎ ከ1960 በኋላ አብዛኞቹ የአፍሪቃ አገራት ከነጭ ቅኝ ግዛት ነጻ መውጣት ችለዋል፡፡
ዓለም ላይ የተከሰተው የፖለቲካ ለውጥ በጣሊያንም ቀጥሎ ምኒሊክ ለዘላለም ይኑር የሚሉ ሰልፈኞች አደባባዮችን ዘግተው አንለቅም በማለታቸው ምክንያት የሚከተሉት ለውጦች ጣሊያን ውስጥም ተደረጉ፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩና አጠቃላይ የዓድዋን ጦርነት የመሩ ጀነራሎች ማዕረጋቸው ተገርስሶ ከስራቸው ተባረሩ፤ የጣሊያን ጋዜጦችም በወቅቱ በፊት ለፊት ገጻቸው የሚኒሊክንና የጣይቱን ፎቶግራፍ ተጠቅመው ቪቫ ሚኒሊክ ቪቫ ጣይቱ በሚል በዓለም አደባባይ የኢትዮጵያን ድል አስተጋቡ።
ዓድዋ የዕርቅንና የይቅርታን ኃይል ያሳየም ጭምር ነው። በአካባቢ ግጭቶች የተቀያየሙ የግዛት መሪዎች፤ በንጉሱም ላይ ያኮረፉ የወላይታና የአንዳንድ አካባቢ ገዥዎችም፤ ቂምና ቁርሾን በእርቅ ሳይውል ሳያድር ሽረው ለአንድ አገራዊ ዓላማ በአንድነት እንዲቆሙ ያስቻለ የትውልዱ ዘመን ተሻጋሪ ታላቅ በድል የተጠናቀቀ ደማቅ የታሪክ ምዕራፍም ነው።
አገር ከሚያልፍ መንግሥታዊ ሥርዓት እንደምትበልጥ አስቀድመው ጠንቅቀው ከማንም በላይ የሚያውቁተ ኢትዮጵያውያን፤ ሀገር ሁል ጊዜም የምትድነው በዕርቅና በይቅርታ መሆኑን አምነው ልዩነቶቻቸውን አጥብበው በአንድነት መቆም ቻሉ። በተለያዩ አካባቢዎች አኩርፈው የሸፈቱም ሳይቀሩ ዕርቅና ሰላም እያወረዱ ከዓድዋው ዘማች ጋር አብረው ዘመቱ።
ዓድዋ የኢትዮጵያውያን የአመራር ጥበብ የታየበት ድልም ነው። ዳግማዊ ምኒልክና እቴጌ ጣይቱ በአራት መንገድ ሠራዊቱን አደራጅተው፤ ጠላት የውሃና የስንቅ አቅርቦት እንዳያገኝ መስመሩን በጀግንነት አቋርጠውበት፤ ዕውን ያደረጉት ድል እንጂ በአንድ ጀንበር የመጣ አልነበረም።
በተጨማሪም በሁለቱ በብስለትና በዕውቀት የታገዘ አመራርና ማስተባበር ሀገር ወዳድ የኢትዮጵያ የቁርጥ ቀን ልጆች በተለያዩ ዘዴዎች መሣሪያ በማሰባሰብ፤ ስንቅ በማዘጋጀት፤ ጥቂት ጊዜ መግዛት የሚያስችል የዲፕሎማሲና የቅድመ መረጃ ስራዎችን በማከናወን እና ሠራዊቱን በአንድነት አደራጅቶ በማዝመት የተቀዳጁት የመላ የጥቁር ሕዝቦች ድልም ጭምር ነው።
የጥቁር ህዝቦች የነጻነት ታጋይ የነበረው አሜሪካዊው ማርክስ ጋርቬይ ስለ ታላቁ የዓድዋ ድል የሚከተለውን ብለው ነበር ‹‹የአድዋ ድል የአፍሪካን ጥንታዊ ክብርና የወደፊት ተስፋ ከጥቁር ህዝቦች ጋር ያገናኘ የመላው የጥቁር ህዝቦች የነጻነት ተምሳሌት ማሳያ ድልድይ ነው››፡፡
ድሉ ለጥቁር ህዝብ የነጻነት ታጋዮች ለእነ ማርክስ ጋርቬይ፤ ጁሊየስ ኔሬሬ፤ ኩዋሜ ንኩርማህ፤ ስቲቭ ቢኮ፤ ሳንካራ እና ለሌሎች የጥቁር ህዝቦች የነጻነት ትግሎች፤ ለደቡብ አፍሪቃ የጸረ አፓርታይድም ሆነ ለሌሎች ለጸረ ቅኝ ግዛት ትግሎች ጉልበት መሆን መቻሉን የቀድሞው የደቡብ አፍሪካ ፕሬዚዳንት ታቦ ኢምቤኪ ‹‹የዓድዋን ጦርነት እኛ ሰለባ አይደለንም ነገር ግን እኛ አሸናፊዎች ነን›› በሚል ገልጸውትም ነበረ።
በአንድ ወቅት አንዲት የታሪክ ተመራማሪ ሚዲያ ላይ በእንግድነት ቀርበው ፤ የዓድዋ የድል በዓል አከባበርን አስመልክቶ በሰጡት ቃለ ምልልስ እንደገለጹት፤ የዓድዋ ድል የመላ ጥቁር ህዝቦች ድልና ኩራት ከመሆኑ አንጻር ላለፉት ዓመታት ዓድዋ በዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የሚገባውን ትኩረት እንዳላገኘ እንዲያውም አብዛኞቹ አፍሪካውያንና ጥቁር ህዝቦች እንኳን የዓድዋን ድል በደንብ እንደማያውቁ የሚያሳዩ ግኝቶች እንዳሉ ጠቁመዋል።
ይሄንን እውነታ ለመለወጥና ኢትዮጵያን እና አዲስ አበባን በአዲስ መንገድ ለማስተዋወቅ ተገቢ እና ደረጃውን የጠበቀ አከባበር እንደሚያስፈልግ አክለው መናገራቸውን አስታውሳለሁ፡፡
በዚህም ኢትዮጵያ የመላ አፍሪካውያንና በዓለም የተገፉ ህዝቦች የነጻነት ተምሳሌት ሆና እንድትቆጠር ጥንታውያን የሁላችንም ቅድም አያቶች አሻራቸውን በደምና አጥንታቸው አኑረዋል፡፡
የዓድዋ ድል የዛሬውም ትውልድ ለአገር ቅድሚያ ሰጥቶ ተፈጥሮአዊ ልዩነቶችን እንደ አምላክ ፀጋ ተቀብሎና በፖለቲካ ልዩነቶችም ቢሆን መቻቻልን መርህ አድርጎ፤ አካታች ለሆኑ የፖለቲካ ሃሳቦች ቅድሚያ ሰጥቶ በአንድነት ከተነሳ ከመንገዱ የሚያስቆመው ምንም አይነት ምድራዊ ኃይል እንደማይኖር አብነት የሆነ ታሪካዊ የአንድንት ድርና ማግ ነው፡፡
የነገ ማንነት በዛሬ ላይ መሰረት ተጥሎ እንደሚሰራ የተገነዘበ ትውልድ ስለመፈጠሩም ምስክር የማይሻ አቢይ ማሳያ ነው።ያንን ዘመን አይሽሬ ድል በጥልቀት የተረዳ ትውልድ ዛሬም እጅ ለእጅ ከተያያዘ ተመሳሳይ ዘመን ተሻጋሪ ድል እያስመዘገበ መሄድ እንደሚችል ዳግም ምስክር አይሻም፡፡
አሁን ላለውም ትውልድ የድል ጅማሬ ማሳያ፤ በሀገራችን እየተገነቡ ከሚገኙት ግዙፍ ፕሮጀክቶች መካከል አንዱ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ነው።በዓድዋ ዘመቻ ላይ ያሳየነውን የአብሮነታችንን ጥብቀት፤ የአንድነታችንን ውህደት እና ዘመን ተሻጋሪ የኢትዮጵያዊነት ቅርጽና ቀለም ለሚጠራጠሩም የትናንቱ አንድነታችን በብዙሀነታችን የደመቀ ቀለም መሆኑን በያንዳዱ ተግባራችን ወደፊትም ለጠላትም ለወዳጅም እያሳየን እንዘልቃለን፡፡
የአባይን የዘመናት ቋጠሮ መፍታት የአንድን አካባቢ ወንዝ ጠልፎ የጓሮ አትክልት እንደማልማት ቀላል አይደለም።አይችሉምን የቻልንበት፤ ትናንት በአንድነታችን ጸንተን በዓድዋ ያስገኘነውን ድል፤ በድጋሚ ያስመሰከርንበት፤ የትናንት ታላቅነታችን ማሳያ የውሃ ሀውልታችን ነው፡፡
ኢትዮጵያውያን ከመቸውም ጊዜ በላይ፤ በአገር ውስጥና በውጭ የሚኖሩ ፤ በሚቻላቸው ሁሉ በአንድነት ቆመው ለኢትዮጵያ ሁሉን አቀፍ ብሄራዊ ጥቅም ዲፕሎማሲያዊ ትግል በጋራ የሚያደርጉበትና በብሔራዊ ጥቅማችን ላይ የሚቃጡ ዓለም አቀፍም ሆነ አህጉራዊ ጫናዎችን የሚመክቱበት ትክክለኛ ጊዜ አሁን ነው፡፡
አገር ከሚያልፍ መንግስታዊ ሥርዓትና በየጊዜው ከሚለዋወጥ የፖለቲካ አስተሳሰብ የምትልቅ ስለሆነች ፤አንዳችን የሌላኛችንን ተፈጥሯዊም ይሁን ቀለም ውላጅ ልዩነቶች እክብረን በማስተናገድ፤ ልክ እንደ አባቶቻችን ሁሉ እጅ ለእጅ ተያይዘን ሆ ብለን ለጋራ አገር ግንባታ ልክ እንደ አንድ ሰው የምንቆምበት ጊዜ ላይ ነን።እንዲሁም ይመለከተኛል የሚል ዜጋ ሁሉ ዳር ቆሞ መመልከትንና በረባ ባረባ ሁሉ ላይ ትችት ማብዛትን ተሻግሮ፤ የድርሻውን በታሪክ የሚታወስ አሻራ እንዲያኖር የአገሪቱ ነባራዊ ሁኔታ ግድ የሚል ነው።
አዲስ ዘመን መጋቢት 5 ቀን 2013 ዓ.ም