ኢትዮጵያ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅትም ሆነ የቀድሞው የአፍሪካ አንድነት ድርጅትና የአሁኑ የአፍሪካ ሕብረት መስራች አገር እንደመሆኗ፤ ለዓለም አቀፋዊም ሆነ አህጉራዊ ሕጎች ትገዛለች። ለእነዚህ ሕጎች ተፈፃሚነትም ያለመታከት ሠርታለች፤ እየሠራችም ተገኛለች።
ከዚህ ባለፈም እንደ አንድ ሉዓላዊት አገር ነፃነቷን ሳታስደፍር ዘመናትን የተሻገረች፤ በዓለም ላይ ላሉ ጥቁሮች ሁሉ አርነት የሆነ ገድል የፈፀመች አገር መሆኗም ትልቅ እውነት ነው።
በዚህ መልኩ የሚገለፀው የሕግ አክባሪነት እና የጀግንነት ታሪኳ ድምር ውጤት ደግሞ የትኛውም አገር ሉዓላዊነቷን ተዳፍሮ እኔ አውቅልሻለሁ የሚል ውሳኔ ሊያሳልፍባት እንደማይችል የሚያስረግጥ እውነት መሆኑን ማወቅ ይገባል። ሉዓላዊነትሽን ተጋፍቼ በውስጥ ጉዳይሽ ላይ ገብቼ እፈተፍታለሁ የሚል ሃሳብንም ሆነ እርምጃ ጎንበስ ብላም እንደማትቀበል የታወቀ ነው።
ይህ ማለት፣ በወዳጅነትና ከልብ በመነጨ አጋርነት እንደግፍ የሚሉ አገራትና ተቋማትን አትቀበልም ማለት አይደለም። አሻጋሪ ሃሳብና በመከባበር ላይ የተመሰረተ ድጋፎቻቸውን አክብራ ለመቀበል እና እንደ ፈርጁ ጥቅም ላይ ለማዋል ሁሌም ዝግጁ ናት።
ይሁን እንጂ የኢኮኖሚ አቅማቸውን እና ጊዜ የፈጠረላቸውን ሃያልነት ተጠቅመው በድጋፍና ዕርዳታ ስም እጅሽን እንጥምዝዝ፤ እንዳሻን እንዘዝሽ፤ እንጀራሽን አቡክተን እንጋግርልሽ የሚሉ አገራትም ሆኑ ተቋማትን ለማስተናገድም ሆነ ለመሸከም የሚያስችል ጫንቃ በፍፁም የላትም።
በሌላ አነጋገር ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያውያን በዘመናት ሂደት ውስጥ ይሄን አይነት ታሪክ የሚገለጥበት የአሽከርነት ምዕራፍ የላቸውም። ያኔ ጥንትም ቢሆን ወራሪን አልሸከምም ያለ የኢትዮጵያውያን ወረራን ያለመቀበል ወኔ፤ ዛሬም ባለው ትውልድ ከአባቶቹ በደም ሥሩ የተላለፈ ነውና መሰል ተጽዕኖዎችን እና ጣልቃ ገብነቶችን ሊሸከምና ሉዓላዊነቱን ሊያስደፍር የሚወድ አገር ወዳድ ኢትዮጵያዊ እንደ ዜጋም እንደ መንግሥትም የለም።
ከሰሞኑ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት የኢትዮጵያን ወቅታዊ ጉዳይ አጀንዳ አድርጎ መምከሩ የሚታወስ ነው። በዚህ መድረክም በኢትዮጵያ ዙሪያ የቀረበው ረቂቅ መግለጫ የጋራ መስማማት ሳይደረስበት መቅረቱ ይታወቃል። በዚህ ረገድ አንዳንድ አገራት በፊት አውራሪነት በሚዘውሩት የምዕራቡ ጎራ በኢትዮጵያ የሰብዓዊ ድጋፍና የሰላም ማስፈን ሂደት ውስጥ እጅን የመስደድ ፍላጎት ከፍ ያለ እንደነበር ታይቷል።
በአንፃሩ እንደ ቻይና እና ሩሲያ እንዲሁም ህንድን የመሳሰሉ አገራት ደግሞ ይህ የአንድ ሉዓላዊ አገር ጉዳይ እንደመሆኑ፤ ሌሎች ይሄን መሰል ጣልቃ ገብነት ሊኖራቸው እንደማይገባ አስረግጠው በመንገራቸው የጣልቃ ገቦች ፍላጎት ሳይሳካ ቀርቷል። ይህ የሚያሳየው ደግሞ አገራት የግል ፍላጎታቸውን ለማሟላት እና በታዳጊ አገራት ጉዳይ ጣልቃ በመግባት በየአገራቱ ለእነሱ የሚታዘዝ አመንግሥት ለመፍጠር የፀጥታውን ምክር ቤትን ለመዘወር ሰፊ ፍላጎት ያለ መሆኑን ነው።
ሊታወቅ የሚገባው ግን፣ ኢትዮጵያ ያኔ ጥንት ከውጭ የመጣ ፋሽስት ወራሪን አሳፍራ በመመለስ ሉዓላዊነቷን ያረጋገጠች አገር መሆኗ ነው። በጥንት ዘመን ኢትዮጵያ ዛሬ በብልጽግና የሚታወቁ አገራት ችግር ላይ በወደቁ ጊዜ ከካዝናዋ ገንዘብ አውጥታ ድጋፍ ያደረገች አገር መሆኗን ነው።
ኢትዮጵያ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰላም አስከባሪ ጥላ ሥር ሆና ለሰባ ዓመታት የዘለቀ የሰላም ማስከበር ሚናዋን ስትወጣ የኖረች፤ አሁንም እየተወጣች ያለች መሆኗም ሊዘነጋ የማይገባው ሀቅ ነው።
ዛሬም ቢሆን ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያውያን ከውስጥ ጉዳዮቻቸው አልፈው ለቀጣናው ሰላምና መረጋጋት እያበረከቱ ያለውን ሚና ለማንም ገልጽ ነው። በኮሮና ቫይረስ ወረርሺኝ ወቅትም ቢሆን ጎረቤት አገራት ለሚገጥማቸው ተጨማሪ የተፈጥሮ አደጋ እጇን ያላጠፈች፤ ሱዳንን እንደ አገር፣ የሱዳን እህትና ወንድም ሕዝቦችንም እንደ ሕዝብ ካላት ላይ አካፍላ በመስጠት አለንላችሁ ያለች አገር ናት።
በውስጥም ቢሆን በተለያዩ አካባቢዎች የተፈጠሩ የጎርፍ መጥለቅለቆች ያስከተሉትን ጉዳት መቋቋም የቻለች፤ የእናት ጡት ነካሾች ለሥልጣን ጥማታቸው አገር ለማፍረስ ሲዳክሩም አደብ ማስያዝ የቻለችም ናት።
ከጁንታው ጥቃት ጋር ተያይዞ ጁንታውን ወደ መቃብር ከማውረድ ባሻገር፤ በክልሉ አፍርሶ የሄደውን የልማት አውታሮች መልሶ የመገንባት፤ በክልሉ ለሚኖሩ ዜጎችም አስቸኳይ የሰብዓዊ ድጋፍ እንዲደርስ በራሷ አቅም የሠራች አገር ናት።
እነዚህ እጀ ረዣዥም አገራት የሰብዓዊ ድጋፍን ምክንያት አድርገው ወደ ክልሉ በገቡበት ወቅት ላይም ቢሆን ያላደረጉትን እስከ 1 ነጥብ 87 ቢሊዮን የሚደርስ ብር በመመደብ 70 በመቶውን የሰብዓዊ ድጋፍ በራስ አቅም የሸፈነች አገርም ናት።
ይህ የሚያሳየው ደግሞ በኢትዮጵያ ውስጥ የሚፈጠሩ ማናቸውም ዓይነት ችግሮች ከኢትዮጵያውያን በላይ የሚመለከተውም፤ ተጋፍጦ የሚፈታውም አለመኖሩን ነው። እናም ትናንት ችግሩ ሲፈጠር እንዲደግፉ ሲጠየቁ ያቅማሙና ገብተውም ቢሆን ጠብ ያለ ነገር መሥራት ያልቻሉ አገራት፤ ዛሬ ላይ በክልሉ ገብተን ሰብዓዊ ድጋፍ ልናደርግ፤ ሰላሙንም ልናረጋጋ ይገባናል ሲሉን፤ መልሳችን ሊሆን የሚችለው ለራሳችን ችግር ራሳችን አለን፤ ከቻላችሁ ባላችሁበት ሆናችሁ የሚያስፈልገንን ስንጠይቅ አግዙን የሚል ነው።
እናም አንዳንድ አገራት በሌሎች አገራት የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ ለመግባት የሚያደርጉት ጥረት አደብ ሊገዛና ከእነ ሩሲያ፣ ቻይና እና ህንድ አይነት አገራት ልምድ ሊቀሰም ይገባል። አቅም ስላለኝ ልዘዛችሁ፤ ልጨፍልቃችሁ፤ እኔ አሻንጉሊት መንግሥት ልሰይምላችሁ፤ ከድህነት ሳትወጡ እየኖራችሁ የእኔን እጅ እያያችሁ ብቻ ኑሩ የሚሉ አካሄዶችም በፍፁም ቅቡልነት የሌላቸው መሆናቸው ሊሰመርበት ይገባል።
ሩሲያ በውጭ ጉዳይ ሚንስትሯ በኩል እንዳለችው፣ አሜሪካም ሆነች ሌሎች እሷን መሰል አገራት በሌሎች አገራት የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ በመግባት የሚያሳዩዋቸው ድርጊቶች ተቀባይነት አይኖራቸውም። መታወቅ ያለበት ጉዳይ ማንኛውም አገርም ሆነ ቡድን በሌሎች አገራት የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ በመግባት የሚያደርጉት እንቅስቃሴ ሊቆምና ጡንቻ አለኝ ተብሎ የአገሮችን ነፃነትና ሉዓላዊነት ከግምት ውስጥ ሳያስገቡና ሳያከብሩ የሚያሳልፏቸው ውሳኔዎች ተገቢ ስላይደሉ በማናቸውም ሁኔታ ኢትዮጵያውያን የማይቀበሉት መሆኑ ነው።
ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያውያንም በሁሉም ረገድ ለውስጥ ጉዳዮቻቸው አያንሱምና የቤት ሥራዎቻቸውን ሠርተው እንዲያጠናቅቁ የቻለ ማገዝ፤ ይህን ማድረግ ያልቻለ ደግሞ ጣልቃ ገብቶ ባለመጫን አጋርነቱን ሊያሳይ ይገባል። ከዚህ ውጭ ያለ ሉዓላዊነትን ያላከበረ ጣልቃ ገብነትና ጫና ግን እንደ ጥንቱ ሁሉ ዛሬም ኢትዮጵያውያን የሚሸከሙት አይሆንም። በሕግ በምትመራ ዓለምም የሕግ ቅቡልነትም አይኖረውም!
አዲስ ዘመን የካቲት 27/2013