ዳንኤል ዘነበ
ኢትዮጵያ በ2022 ዓ.ም. መካከለኛ ገቢ ካላቸው አገሮች ተርታ የመሰለፍ ህልም አንግባ እየተንቀሳቀሰች ትገኛለች ። ሀገሪቷ ያላትን ፍላጎት ዕውን ለማድረግ ትምህርትን ተደራሽና ፍትሐዊ ማድረግ ብቻ ሳይሆን በጥራት ላይ አተኩራ መስራት እንዳለባት የዘርፉ ምሁራን ሲገልጹ ይታያል ።
በዚህ ረገድ መንግስት ባለፉት ሃያ ዓመታት ለከፍተኛ ትምህርትና ስልጠና ትኩረት በመስጠትና ጠቀም ያለ በጀት በመመደብ ዘርፈ ብዙ ስራዎችን መስራቱ የማይካድ ሀቅ ነው ።
የከፍተኛ ትምህርትና ሥልጠና ተደራሽነት፣ ጥራት፣ ተገቢነትና ፍትሃዊነትን ለማረጋገጥ በትኩረት የተሰራ ሲሆን፤ ከተደራሽነትና ከፍትሃዊነት አኳያ ተጨባጭ ውጤት ማምጣት መቻሉን ከሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ያገኘነውን መረጃ ያመላክታል ።
ጥራት አልባው ጉዞ
ሚኒስቴሩ ከ2013-2017 ዓ.ም በሚዘልቀው የአምስት ዓመት ስትራቴጂክ ዕቅድ ካዘጋጀው ሰነድ ላይ ባገኘነው መረጃ፤ በ2008 ዓ.ም በሀገር አቀፍ ደረጃ 33 የነበሩት ዩኒቨርሲቲዎች፤ በ2013 ዓ.ም ወደ 50 የመንግስት ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ማድረስ ተችሏል ። የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ በመጨመር በ2013 ዓ.ም የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት 258 ደርሰዋል ።
የከፍተኛ ትምህርት ተደራሽነትን ከማረጋገጥ አንፃር አበረታች ስኬቶች ያሉ ቢሆንም አሁን ያለው የአጠቃላይ የከፍተኛ ትምህርት (ተማሪዎች) ተሳትፎ 13.8 በመቶ ነው ። ይህም ከሰሃራ በታች ካሉ የአፍሪካ ሀገራት አንጻር ሲታይ የሀገራችን የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ቁጥር በዝቅተኛ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ያረጋግጣል ። በሀገራችን ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተደራሽነትና ፍትሃዊነት አንጻር የተሰሩት ሥራዎች እንደስኬት መነሳት የሚገባቸው ናቸው ።
በተመሳሳይ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማቱ ጥራቱን የጠበቀ ትምህርት ከመስጠት አኳያ ውድቀት የተመዘገበ ስለመሆኑ መንግስት ራሱ ያመነው ሀቅ ነው ። የትምህርት ጥራት ችግር ተብለው ከተለዩት መካከል የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት መምህራንን በጥራት ማቅረብ ካለመቻል ጋር ተያይዞ ክፍተት የተፈጠረ ስለመሆኑ ታምኖበታል ። ከመምህራን ጋር ተያይዞ ያሉትን ክፍተቶች ከመመልከታችን በፊት የመምህራን አቅርቦትና ጥራት ከትምህርት ጥራት ጋር ያላቸውን ቁርኝትመመልከቱ አስፈላጊ ይሆናል ።
የመምህራን ልማት
መምህራን በመማር ማስተማር፣ ምርምርና ማህበረሰብ አገልግሎት ካላቸው የሙያ ሚና ባሻገር የተቋማት አመራር ግንባታ ምንጭ በመሆናቸው የከፍተኛ ትምህርት ቁልፍ ምሶሶዎች ናቸው ። በዚህ ምክንያት የከፍተኛ ትምህርት ተልእኮዎችን ለማሳካት ሲታሰብ የመምህራን አቅርቦትና ጥራት ትኩረት የሚሻ ቁልፍ ጉዳይ ነው ።
መምህራን የትምህርት ጥራትን በማስጠበቅ ለሀገር እድገትና ብልጽግና ከፍተኛ ድርሻ የሚያበረክቱ ከመሆናቸውም በላይ በጥናትና ምርምር በመሳተፍ ለህብረተሰቡ ችግር ፈቺም በመሆን ትልቅ ስራዎችን ያከናውናሉ ።
በተጨማሪም የተማሪዎች ተሳትፎ፣ ፍትሐዊነት፣ ምርምርና የማህበረሰብ አገልግሎት፣ የትምህርት ጥራት፣ ዓለም አቀፋዊነት እንዲሁም የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን ውጤታማ ለማድረግ የመምህራን በተፈላጊው ጥራትና መጠን መገኘት አስፈላጊውና ዋነኛው ጉዳይ ነው ። በሀገራችን ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ያለው ሁኔታ፤ ከዚህ ፍፁም የተጣላ እንደሆነ በርካታ ጥናቶች አረጋግጠዋል ። ከእነዚህ ጥናቶች መካከል አንዱን እንጥቀስ ።
ጥቅምት 20 ቀን 2012 ዓ.ም. ጅማ ዩኒቨርሲቲ ‹‹ናሽናል ኮንፈረንስ ኦን ፒኤችዲ ትሬኒንግ ኢን ኢትዮጵያ ቻሌንጅስ ኦፖርቹኒቲስ ኤንድ ዌይ ፎርወርድ›› በሚል በተካሄደ ዓውደ ጥናት ላይ በቀረበ ጥናት እንዳረጋገጠው፤ በአብዛኞቹ የመንግሥት ዩኒቨርሲቲዎች የሚገኙና ሁለተኛ ዲግሪ ያላቸው መምህራን፣ የሁለተኛ ዲግሪ ተማሪዎችን በማስተማርና በማማከር እየሠሩ ይገኛሉ ። ይህም በትምህርት ጥራት ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ አሳድሯል።
በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ ከተፈለገ አንዱና ትኩረት መስጠት የሚገባው በሁሉም የትምህርትና ሥልጠና መስኮች ብቁና በቂ መምህራን እንዲኖሩ የመምህራንን ምጣኔ ማስተካከል ነው ። ይህም ሦስተኛ ዲግሪ ያላቸውን መምህራን ቁጥር ማሳደግ ይገባል ሲል መፍትሄውን ጠቁሟል ።
በጥናቱ እንደ ቀረበው፤ ከዘርፉ ምሁራን በኩል እየተነገረ ያለው፤ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማቱን ጉድለት መሙላት የሚቻለው የመምህራን ብቃት እና ስታንዳርድ ከዓለም አቀፍ መስፈርት ጋር አስታርቆ መጓዝ የሚገባ መሆኑን ነው ። ለመሆኑ አለም ዓቀፍ መስፈርት ምን ያካትታል?
ዓለም አቀፋዊነት ሚዛን
በተለያዩ ሀገራት በተወሰነ ደረጃ የተለያየ ትርጉም ቢሰጠውም እንደ አጠቃላይ ግን የከፍተኛ ትምህርት ዓለም አቀፋዊነት ማለት ዓለም አቀፍ መስፈርቶችና የተለያየ ባህላዊና ዓለም አቀፋዊ ይዘት ያላቸው ጉዳዮች ከተቋማቱ ግቦች እና ተግባራት (መማር ማስተማር፣ ምርምርና የማህበረሰብ አገልግሎት) ጋር የሚቀናጁበት ሂደት ነው ። በመሆኑም ዓለም አቀፋዊነት ማለት የከፍተኛ ትምህርት በዓለም አቀፍ የትምህርት ገበያ ውስጥ የሚኖረው ተሳትፎ የሚጨምርበት ሂደት ማለት ነው ።
ዓለም አቀፋዊነት የዩኒቨርሲቲዎች የጥራት ግብዓት መገለጫ እየሆነ የመጣበት ሁኔታም ተፈጥሯል ። የዓለም አቀፍ የከፍተኛ ትምህርት መምህራን ጥራት መደበኛ መለኪያ ደግሞ ከአጠቃላይ መምህራን የሶስተኛ ዲግሪ ያላቸው ድርሻ መጠን ነው ።
በዚህ መለኪያ በተለይ በምርምር ዩኒቨርሲቲዎች የሚጠበቀው የሶስተኛ ዲግሪ ያላቸው መምህራን ድርሻ 50 በመቶ እንደሆነ ዓለም አቀፍ የከፍተኛ ትምህርት ስታንዳርድ ያመለክታል ።
ከዚህ አንጻር ከፍተኛ ደረጃ ላይ የደረሱ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ጥራት ያለው ትምህርት ለመስጠት ብቻ ሳይሆን ላቅ ያለ ምርምር በማካሄድ ለቴክኖሎጂ ልማት ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያደርግ ተጨባጭ አቅም ይኖራቸዋል ።
ታዲያ በሀገራችንም የአለም አቀፍን መስፈርት መነሻ በማድረግ በሁሉም የትምህርትና ሥልጠና መስኮች ብቁና በቂ መምህራን እንዲኖሩ የመምህራንን ምጣኔ 0፡70፡30 (ዜሮ የመጀመሪያ ዲግሪ፣ 70 በመቶ ሁለተኛ ዲግሪና 30 በመቶ ሶስተኛ ዲግሪ መምህራን) ለማድረስ አልሞ ሲሰራ ነበር ።
ላለፉት አምስት ዓመታት በርካታ ጉልህ የሆኑ ስራዎች የተሰሩ ቢሆንም በልማት ፕሮግራሙ የመጨረሻ የበጀት ዘመን የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት መምህራን የትምህርት ደረጃ ስብጥር ማሻሻል 0:70:30 (የመጀመሪያ፣ ሁለተኛ እና ሶስተኛ ዲግሪ) ለማድረስ ቢታቀድም ውጤታማ መሆን እንዳልተቻለ ቁጥሮች ይናገራሉ።
የአምስት ዓመቱ ፕሮጀክት
በሀገራችን በአሁኑ ጊዜ በሁሉም የመንግሥት ዩኒቨርሲቲዎች ካሉት 35 ሺህ አካዳሚክ ሠራተኞች መካከል ሦስተኛ ዲግሪ ያላቸው 12 በመቶ ሲሆኑ፣ ሁለተኛ ዲግሪ መምህራን ደግሞ 68 በመቶ ናቸው ። በአብዛኞቹ የመንግሥት ዩኒቨርሲቲዎች የሚገኙና ሁለተኛ ዲግሪ ያላቸው መምህራን፣ የሁለተኛ ዲግሪ ተማሪዎችን በማስተማርና በማማከር እየሠሩ
ይገኛሉ። ይህም በትምህርት ጥራት ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ አሳድሯል። ጥራት ላይ መሥራት ከተፈለገ ሦስተኛ ዲግሪ መምህራን ቁጥር ማሳደግ እንደሚገባ በማመን ጥረት እየተደረገ ይገኛል ።
በሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር በኩል ከዓለም አቀፍ የጥራት መስፈርት የጎደሉና መሻሻል የሚሹ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትን ብቁ ለማድረግ የተለያዩ ፕሮጀክቶችን በዕቅድ መያዙን በተደጋጋሚ ሲገልጽ ቆይቷል ። ሚኒስቴሩ ከሰሞኑ ተግባራዊ ለማድረግ ካሰባቸው ፕሮጀክት መካከል አንዱ የሆነውን፤ የሀገር ውስጥ ትብብርና ትስሰርን በማጠናከር በመጪዎቹ 5 ዓመታት 5ሺህ መምህራንን በሶስተኛ ዲግሪ ለማሰልጠን የሚያስችል ፕሮጀክት ይፋ አድርጓል።
የሶስተኛ ዲግሪ ሥርዓተ ትምህርት ክለሳና ቀረጻ፣ የሀገር ውስጥና የውጭ ሀገራት ፕሮፌሰሮችን ማሰማራትና የምርምር፣ የላብራቶሪ ወርክሾፕ ግባቶችን አጠናክሮ ማሰቀጠል ፕሮግራሙ ከሚያተኩርባቸው ጉዳዮች መካከል ይገኙበታል ።
በፕሮግራሙ ማብሰሪያ ሥነ ሥርዓት ላይ የተገኙት የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዶ/ር ሳሙኤል ኡርቃቶ የከፍተኛ ትምህርት መምህራንን ሁለንተናዊ ልማት ለማሳደግ ፕሮጀክቱን ወደ ስራ ማስገባት ያስፈለገ መሆኑን ነው ያስረዱት።
በትብብርና ትስስር ተግባራዊ የሚሆነው “Home Grown Collaborative PhD Programs” በሁሉም መስክ ብቁ የሆኑ መምህራንን በማቅረብ የትምህርት ጥራትና አግባብነት ለማስጠበቅ በሚደረገው ጥረት ውስጥ ወሳኝ ሚና ይኖረዋል ። እንደ ሀገር የምናስበውን የልማትና ብልጽግና ጉዞ ለማሳከካት ብቃት ያላቸው መምህራን፣ ሳይንቲስቶችና ተመራማሪዎችን ማፍራት ወሳኝ መሆኑን ነው ያስገነዘቡት ።
የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ፕሮፌሰር አፈወርቅ ካሱ ደግሞ፤ ሀገሪቱ ያላትን ሃብትና አቅም በማስተባበርና በሚገባ በመጠቀም እውቀትና ክህሎት ያለው ዜጋ ለማፍራት በሚደረገው ጥረት ውስጥ የከፍተኛ ትምህርትና ስልጠና ተቋማት የሀገር ውስጥና አለም አቀፍ ትብብርና ትስስሮችን በማጠናከር ለፕሮግራሙ መሳካት የድርሻቸውን እንዲወጡ ጥሪ አቅርበዋል ።
የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ሳሙኤል ክፍሌ በበኩላቸው ወደሚፈለገው ደረጃ ለመድረስና የሚታሰበውን ግብ ለማሳካት የተቋማቱን አቅም መገንባትና ማጎልበት የሚኖረው ሚና ወሳኝ በመሆኑ ለተግባራዊነቱ የተለያዩ ስልቶችን ነድፎ መንቀሳቀስ እንደሚገባ አስታውቀዋል ።
አዲስ ዘመን የካቲት 15/2013