ያቤሎ በኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት የቦረና ዞን ዋና ከተማ ስትሆን ከአዲስ አበባ 464 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ትገኛለች፡፡ ከተማዋ ከጥር 11 እስከ 13 ቀን 2011 ዓ.ም 17ኛውን የኦሮሚያ አርብቶ አደሮች ቀን አስተናግዳለች፡፡ በኢትዮጵያ ከሚገኙት አርብቶ አደር አካባቢዎች አብዛኛውን ሽፋን የሚይዘው የኦሮሚያ ክልል ሲሆን፤ በክልሉ ሰባት የአርብቶ አደር መገኛ ዞኖች አሉ፡፡ በነዚህም ውስጥ አርባ ሁለት ወረዳዎች በአርብቶ አደርነት የሚተዳደሩ ናቸው፡፡
በዓሉ የአርብቶ አደሩን ሁለንተናዊ እንቅስቃሴ ለመቃኘት የሚያስችል የመስክ ጉብኝት በማድረግ የተጀመረ ሲሆን በድሬ፣ሚኦ፣ድቡሉቅና ያቤሎ ወረዳዎች አርብቶ አደሩ ያከናወናቸውን ተግባራት መጎብኘት ተችሏል፡፡ በድሬ ወረዳ የሚገኘው የሳር ባንክ እና ሚኦ ወረዳ ያለው የእንሰሳት የውሃ ጉድጓድ፣ የእንሰሳት ህክምናና መሰል አገልግሎት መስጫ ጣቢያ የጉብኝቱ አካል ነበር፡፡
በዲድ ያቤሎ ወረዳ በለቡ ውኋ ግድብ ተጠቃሚ ከሆኑት አርብቶ አደሮች አንዷ ወይዘሮ ሉጮ ገባቦ ናቸው፡፡ እርሳቸው እንደሚሉት በቀበሌያቸው የተገደበውን የለቡ ውኋ በመጠቀም እንደ ጎመን፣ካሮትና በቆሎ የመሳሰሉትን በመዝራት የራሳቸውን ፍላጎት አሟልተው ለገበያ በማቅረብ ጥሩ ገቢ ማግኘት ጀምረዋል፡፡ ለቀበሌው አርብቶ አደር ግንባር ቀደም በመሆንም ከእለቱ የክብር እንግዳ የምስክር ወረቀት ተሸልመዋል፡፡ የመስኖ ሥራ በአካባቢው አዲስ ነገር እንደሆነ የጠቀሱት ታታሪዋ እንስት ከአርብቶ አደርነታቸው በተጨማሪ በቀጣይም ገቢያቸውን ለማሳደግ ጠንክረው እንደሚሠሩ አስረድተዋል፡፡
በድሬ ወረዳ የዲደ ጃርሳ ቀበሌ ሊቀመንበር አቶ ገርቢቻ ዲዳ እንደሚያስረዱት የአካባቢው አርብቶ አደር በማሕበር በመደራጀት የአየር ለውጥ በሚከሰትበትና ድርቅ በሚፈጠርበት ግዜ እንሰሳት በምግብ እጥረት እንዳይጠቁ የሳር ባንክ አዘጋጅተዋል፡፡ ነገር ግን ሳር አጭዶ የሚያስር ማሽን እጥረት እንዳለባቸው ገልጸው እስከ አሁን ማጨድ ያለባቸውን ሳር አላጨዱም፡፡ ቀደም ሲል የታጨደውም ቢሆን መጠለያ ስለሌለው በጸሀይና በዝናብ እየተበላሸ ነው፡፡ የሳር ባንክ መኖሩ ለእንሰሳት ደህንነት ብሎም ለገቢያችን ማደግ ትልቅ አስተዋጽኦ አለው ያሉት አቶ ገርቢቻ በሽታንና ድርቅን የሚቋቋሙ፣ የሥጋና የወተት ምርት መስጠት የሚችሉ ገበያ ላይ የሚፈለጉ ምርጥ ዘሮችን እያረቡ መሆናቸው ኢኮኖሚያዊ እድገት አስገኝቶላቸዋል፡፡ በዚህም ጥሩ መኖሪያ ቤት ከመስራት አልፈው፣ ብር በባንክ ማስቀመጥ ችለዋል፡፡
ቀደም ሲል የነበረውን ባህላዊ አሠራር በማሻሻል ምርታማ ቢሆኑም በአካባቢያቸው ያለው የገበያ ሁኔታ ከአርብቶ አደሩ ይልቅ ነጋዴውን የበለጠ ተጠቃሚ እንዳደረገ በመግለጽ ይህንንና በአካባቢው ያለውን የውኋ ችግር በተመለከተ የሚመለከታቸው አካላት መፍትሄ እንዲያፈላልጉላቸው ጠይቀዋል፡፡ በሚኦ ወረዳ የሜልበና ቀበሌ ሊቀመንበር አቶ ጠቻ ሀለኬ በበኩላቸው መንግሥት ነባሮቹን የቦረና ከብቶች በማሻሻል ምርጥ ዘር ማቅረቡ ለምርታማነታቸው መጨመር ጥሩ አስተዋጽኦ እንዳደረገላቸው ገልጸው፤ በአካባቢው የስጋ አቅራቢ ድርጅቶችና እና የቆዳ ፋብሪካዎች ቢኖሩ ተጠቃሚነታቸው ከዚህም በላይ ሊጨምር እንደሚችል አስረድተዋል፡፡
አያት ቅድመ አያቶቻችን እንሰሳትን በማርባት ይኖሩ ነበር፤ ባህላችንም ከእንሰሳት ውጭ አይታሰብም ያሉት የቦረና ዞን አስተዳዳሪ አቶ ደንጌ ቦሩ በበኩላቸው ይህ ዝግጅት ያስፈለገው የአርብቶ አደሩን የኑሮ ሁኔታ ለማሻሻል ነው፡፡ እንሰሳት ለእኛ የማንነታችን መገለጫዎች፣ የኑሮአችንም መሰረቶች፤ ከህይወታችን ጋር የተሳሰሩ ክብራችንና ልብሳችንም ናቸው ብለዋል፡፡
በኦሮሚያ ኢንሹራንስ ኩባንያ የአነስተኛ ኢንሹራንስ ሥራ ክፍል ኃላፊ አቶ መልካቸው ተመስገን አርብቶ አደሩ የእንሰሳት ኢንሹራንስ አገልግሎት ተጠቃሚ በመሆን እንሰሳቱን በድርቅና በተፈጥሮ መዛባት ምክንያት ከሚከሰቱ አደጋዎች አስቀድሞ መከላከል የሚያስችል አገልግሎት እንደተመቻቸለት አስረድተዋል፡፡ ኢንሹራንሱ ከተቋቋመ አስራ ሶስት ዓመታትን እንዳስቆጠረ የገለጹት ባለሙያው በቦረና ዞን ባለፉት ሰባት ዓመታት የካሳ አገልግሎት በማቅረብ የአርብቶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት በማረጋገጥ በኩል የበኩሉን ድርሻ እየተጫወተ እንዳለ ገልጸዋል፡፡
የኢንሹራንሱ ዋና ዓላማ በሳተላይት መረጃ ተመስርቶ ድርቅ ይከሰታል ተብሎ በሚገመተው ቦታ ቀድሞ በመድረስ አርብቶ አደሩ ሳር፣ውሃ መድሀኒትና አስፈላጊውን ነገር ሁሉ አስቀድሞ እንዲያዘጋጅ የካሳ አገልግሎት መስጠት እንደሆነ አስረድተዋል፡፡ ያም ሆኖ ሁሉም አርሶ አደሮች ስለ ኢንሹራንሱ በቂ ግንዛቤ ስለሌላቸው በአገልግሎቱ ያላቸው ተጠቃሚነት አናሳ ነው ያሉት አቶ መልካቸው በቀጣይ ሰፊ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራ በመሥራት አርብቶ አደሩ በእንሰሳቱ ላይ ያለው ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ዋስትና እንዲያገኝ ኩባንያው ጠንክሮ እንደሚሰራ ተናግረዋል፡፡
የክልሉ አርብቶ አደር አካባቢ ልማት አስተባባሪ ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ ሊበን አሬሮ በበኩላቸው አርብቶ አደሩ የመሰረታዊ ልማት ተጠቃሚ በመሆን ምርታማነቱ እንዲጨምር የተለያዩ ጥናቶች እየተደረጉ መሆናቸውን ጠቅሰው የትምህርትና የጤና አገልግሎቶች መሻሻል እንደሚደረግባቸው ገልጸዋል፡፡
የኦሮሚያ ክልል ምክትል አስተዳዳሪ ወይዘሮ ጠይባ ሀሰን በዓሉን አስመልክተው ባስተላለፉት መልዕክት መንግሥት ለዘርፉ ከምንግዜውም በላይ ትኩረት እንደሰጠው በመጥቀስ አርብቶ አደሩ የራሱንም ሆነ የሀገሪቱን ኢኮኖሚ ለማሳደግ የሚያስችሉ ምቹ ሁኔታዎች እየተፈጠሩለት እንደሆነ አስረድተዋል፡፡ ዛሬ ህዝባችን የፖለቲካ ጥያቄዎቹ እየተመለሱለት በመሆኑ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነቱን ለማረጋገጥ ጠንክሮ መሥራት እንዳለበትም አስገንዝበዋል፡፡ ምንም እንኳን በክልሉ በዋናነት የተለዩት የአርብቶ አደር ዞኖች ሰባት ናቸው ቢባልም አብዛኛውን የክልሉ ህዝብ ኑሮው ከእንሰሳት ከሚያገኘው ጥቅም ጋር የተሳሰረ መሆኑን በመግለጽ አርብቶ አደሩ በዘመናዊ አስተሳሰቦችንና አሰራሮች እየተመራ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነቱን የበለጠ ማረጋገጥ እንዳለበት አሳስበዋል፡፡ በዞኑ አርብቶ አደሩን እየተፈታተነው ያለውን የውኋ እጥረት ለመቅረፍም የክልሉ መንግሥት ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ወይዘሮ ጠይባ በያቤሎ ወረዳ ዲድ ያበሎ ቀበሌ የተገነባውንና አንድ ነጥብ አምስት ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ ውኋ መያዝ የሚችለውን የለቡ ግድብንና የድቡሉቅና ዲሎ ከተሞችን የሚያገናኘውን የ85 ኪሎ ሜትር የጠጠር መንገድ መርቀዋል፡፡
በክብረ በዓሉ ከተከናወኑ ዋናዋና ተግባራት አንዱ የአርብቶ አደሩን ህይወት ሊያሻሽሉ የሚችሉ ጥናታዊ ጽሁፎች የቀረቡ መሆኑ ነው፡፡ በዚህም በረሀማነትን ስለመቀነስ፣ ስለአየር ንብረት ለውጥ፣ ስለመሬት አጠቃቀም፣ ስለአርብቶ አደሩ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትና ስለእንሰሳት ኢንሹራንስ አጠቃቀም በሙያተኞች ማብራሪያ ተሰጥቷል፡፡
በውይይቱ ላይ ቀደም ሲል አርብቶ አደሩ ትኩረት አጥቶ በግብርና ሥር እንዲመራ መደረጉና ለዘርፉ ትኩረት ያለመሰጠቱ ነገር ግን ትልቅ ኢኮኖሚያዊ አቅም ያለው ዘርፍ ሆኖ ሳለ ብዙም እንዳልተሠራበት፣ በዕቅድና በስተራቴጂ ያለመመራቱ ፣ የግጦሽ መሬትና የደን አካላት እየቀነሱ መምጣታቸውና የእርሻ መሬት እየጨመረ መምጣቱ፣ የአርብቶ አደሩ መረጃ አለማግኘት፣ ዘመኑ የደረሰባቸውን የሳይንስ ግኝቶች ከነባራዊው ሁኔታ ጋር አጣጥሞ ያለመጠቀም፣ ዘርፉን የሚደግፉ መንግስታዊም ሆኑ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ተሳትፎ አናሳ መሆን፣ ከእንሰሳት የሚገኘውን ኢኮኖሚያዊ ጥቅም አሳንሶ ማየት፣ የገበያ ትስስር ያለመፍጠር፣ ሚዲያው ለአርብቶ አደሩ የሚሰጠው ሽፋን አናሳ መሆን፣ የአርብቶ አደሩን አካባቢዎች ከቱሪዝም ጋር የማስተሳሰር ችግሮች ወዘተ በውይይቱ ትኩረትን የሳቡ ጉዳዮች ነበሩ፡፡
17ኛው የኦሮሚያ አርብቶ አደሮች ቀን ‹‹ የአርብቶ አደሩ የላቀ ተጠቃሚነት ለሀገራዊ አንድነት ›› በሚል መልዕክት በያቤሎ ከተማ የተከበረ ሲሆን በመርሀ-ግብሩ የሶስት ቀናት ቆይታ የአርብቶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት የሚያሳዩ ጥናታዊ ጽሁፎች ቀርበዋል፣ የማበረታቻ ሽልማቶች ተሰጥተዋል፣ አስተያየቶችና ውይቶች ተካሂደዋል፡፡
አዲስ ዘመን ጥር 21/2011
ኢያሱ መሰለ