መርድ ክፍሉ
በኢ.ፌ.ዴ.ሪ ሕገ መንግሥት ትኩረት ተሰጥቷቸው ከተከበሩ መብቶች መካከል የዜጎች የመደራጀት መብት በዋነኝነት ይጠቀሳል። የአገሪቱ ሕገመንግሥት አንቀጽ 31 የሚከተለውን ይደነግጋል። ‹‹ማንኛውም ሰው ለማንኛውም ዓላማ በማህበር የመደራጀት መብት አለው።
ሆኖም አግባብ ያለውን ሕግ በመጣስ ወይም ሕገመንግሥታዊ ሥርዓቱን በሕገወጥ መንገድ ለማፍረስ የተመሰረቱ ወይም የተጠቀሱትን ተግባራት የሚያራምዱ ድርጅቶች የተከለከሉ ይሆናሉ።›› በመሆኑም ዜጎች ሕገመንግሥቱ ያጎናፀፋቸውን የመደራጀት መብት በመጠቀም በበጎ አድራጎት ወይም በማህበር ሊደራጁ ይችላሉ።
ማኅበራዊ ሕይወት ከውልደት እስከ ሞት የሚኖር እና ቀጣይነት ያለው ሂደት ሲሆን በትምህርት እና ከሌሎች ሰዎች ጋር በሚኖረን ግንኙነት የሚዳብር ነው። የሰው ልጅ ስለራሱ እና ስለሚኖርበት ማኅበረሰብ የሚኖረውን ዕውቀት በተለያየ መልኩ ማለትም የመግባቢያ ቋንቋ በመማር፤ አካባቢያዊ ሁኔታውን በመመልከት እንዲሁም ማኅበራዊ ክህሎቶችን በመማር እያሳደገ ይሄዳል። ይህ የማኅበራዊ ሕይወት ክህሎት በአግባቡ መዳበር ለተሟላ ስብዕና እና ዕድገት ወሳኝነት አለው።
በጎ ፍቃድ አገልግሎት ማለት በፍቃደኝነት ላይ የተመሰረተ ተሳትፎ በማድረግ ውስጣቸው ከሚሰማቸው ሰብአዊ አመለካከት ተነስተው ለሚኖሩበት ማህበረሰብ ሰፊ የልማት አውታሮችን በመዘርጋት የዜግነት ኃላፊነትን የሚገነዘቡ ሀገራዊና ብሔራዊ ግዴታዎችን የሚያውቁበት በማህበራዊ ሚናዎች ስር ግንባር ቀደም የሚሆኑና የሀገርና የወገን ፍቅርን የሚያዳብሩበት ትልቅ ሚና ያለው ተግባር ነው።
እነዚህ ወጣቶችም ባላቸው የእረፍት ጊዜያቸውን መስዋዕት አድርገው ልማትን ለማምጣትና ለአካባቢ ደህንነት ነፃ ጊዜያቸውን፣ ገንዘባቸውን፣ ጉልበታቸው እና እውቀታቸውን በተጨማሪም በጎ አመለካከትን የሚያውሉበት ሥራ ሲሆን ሌሎችን ከመርዳት አኳያም በጎ ምኞትን ተላብሰው ከማህበረሰባቸው ጎን ሆነው የሚያውቁትን የሚያስተምሩበትና ከሌሎች አካላትም የሕይወት ክህሎት የሚቀስሙበት ዋነኛ መንገድ ነው።
በመሆኑም የበጎ ፍቃደኝነት አገልግሎት ጽንሰ ሃሳብ እንደየኅብረተሰብ የእድገት ደረጃ አካባቢያዊ ሁኔታ የሚለይና አንድ ወጥ የሆነ ትርጉም ባይኖረውም ወጣቶች በራሳቸው ተነሳሽነትና በመልካም ፍቃደኝነት ላይ መሠረት ያደረገ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች ውስጥ በመሳተፍ ያልተዳሰሱ ሥራዎችን በማየት አመርቂ ውጤት የሚያበረክቱበት ሊሆን ይገባል። ይህም በዕድሜ፣ በጾታ፣ በማህበራዊ ደረጃና በመልካምድራዊ ወሰን ሳይገድብ ሰብአዊነትን ተመስርቶ የሚሰጥ አገልግሎት ነው።
ሰው ከእንስሳ ከሚለይባቸው ነገሮች መካከል አንዱ ከፍ ያለ አስተሳሰብ የሚያራምድ አእምሮ ባለቤት መሆኑ ነው። ይህ ከፍ ያለ አስተሳሰብ ከሚገለፅባቸው መንገዶች አንዱ ደግሞ ለሰዎች በምናደርገው ድጋፍ ነው።
በአገራችን ሰዎችን መርዳት እንደ ጠንካራ ባህል የሚወሰድ በጎ ተግባር ነው። ሰውን መርዳት እንደ ፅድቅ የሚቆጠር ተግባርም ነው። አብዛኛው ለፈጣሪው ይበልጥ የሚቀርብበት መንገድ አድርጎ ስለሚቆጥረው በተለያዩ አካባቢዎች ድሆችን መርዳት የተለመደ ነገርም ነው። ይሁን እንጂ እንዲህ ዓይነት በጎ ተግባራት አሁን አሁን ከተወሰኑ ምክንያቶች ጋር ብቻ እየተያያዙ በሌላ ጊዜ የሚጠፉበት ሁኔታ ይስተዋላል።
ነገር ግን የመረዳዳትም ሆነ በልክ የመኖር ባህሎች ዛሬም እንዳሉ የሚያሳዩ ተግባራት እንዳልጠፉ በርካታ ማሳያዎችን ማንሳት ይቻላል። በተለይ በቅርቡ የኮቪድ 19 ወረርሽኝ መከሰትን ተከትሎ በርካታ ዜጎች ለከፍተኛ የኑሮ ጫና መዳረጋቸው ይታወሳል። ይህንን ክፉ ጊዜ ለማለፍ ደግሞ የደጋግና ቅን ልቦች መኖር ትልቅ አስተዋፅኦ ማድረጉን ስንመለከት የመረዳዳት ባህላችን ዛሬም ጠንካራ መሆኑን እንገነዘባለን። ዛሬ በቆቦ ከተማ አቅም የሌላቸው እናቶችን፣ ተማሪዎችንና ወጣቶችን እየደገፈ ስለሚገኘው ድንበር የለሽ የበጎ አድራጎት ማህበር እንቃኛለን።
የማህበሩ አመሰራረትና እንቅስቃሴ ድንበር የለሽ የበጎ አድራጎት ማህበር ሊቀመንበር ወጣት ሀብታሙ ጫኔ እንደሚናገረው፤ ማህበሩ ከአምስት ዓመት በፊት በዋናነት በኪነጥበብ ቡድንነት ተቋቁሞ ይሰራ ነበር። ከሁለት ዓመት በፊት ባህርዳር ከሚገኘው ድንበር የለሽ በጎ አድራጎት ማህበር ጋር በመነጋገር ቆቦ ላይ አንድ ቅርንጫፍ በማድረግ ሥራው ተጀመረ።
እንደ ወጣት ሀብታሙ ገለፃ ማህበሩ ሥራ ሲጀምር ‹‹የፍቅር መንገድ›› የተባለ ፕሮጀክት ተነደፈ። ፕሮጀክቱ በዋናነት በወቅቱ በአካባቢው የነበረውን ግጭት ለማብረድ ከሁሉም ሃይማኖት መሪዎች ጋር በመተባበር ፕሮጀክቱ ወደ ተግባር ገባ። ፕሮጀክቱ በአካባቢው በሚገኙ የሃይማኖት ተቋማት ውስጥ ችግኝ የመትከል ሥራ የተጀመረ ሲሆን በተጨማሪም ‹‹አንድ ልጅ ለአንድ እናት›› የሚል መርሃ ግብርም ተካሂዷል:: በመርሃ ግብሩ አንድ ወጣት የሚችለውን ነገር ለአንዲት እናት በማድረግ የሚከናወን ነበር። በመርሃ ግብሩ የተገኘውን እርዳታ ለችግረኛ እናቶች መስጠት ነበር::
ሁለተኛው ፕሮጀክት ደግሞ ሰላሳ ሰዎችን ለመርዳት የታለመበት ነበር። ነገር ግን በተሰራው ሥራ 48 እናቶችን መርዳት ተችሏል። ዘይት፣ ዱቄት፣ ስኳርና ሌሎች ለምግብነት የሚውሉ ነገሮች ለችግረኞች ተሰጥተዋል::
ለተማሪዎች የመማሪያ ቁሳቁስ ድጋፍ ተደርጓል:: በአንበጣ መንጋ ወረርሽኝ መከላከል ላይ ከመከላከያ ሰራዊትና ከአማራ ልዩ ኃይል ጋር በመተባበር ማህበሩ ተሳትፎ ማድረጉን ወጣት ሀብታሙ ይጠቁማል::
የኮሮና ወረርሽኝ በተከሰተበት ወቅት ማህበሩ በገበያ ቦታዎች ላይ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎችን ይሰራ እንደነበር የሚናገረው ወጣት ሀብታሙ፤ በሌላ በኩልም በየአስራ አምስት ቀኑ ከመንገዶች ላይ ማስክ የማፅዳት ሥራ እንደሚከናወን ይናገራል:: ማስክ በማፅዳት ዘመቻው ሕፃናት የወደቀ ማስክ አንስተው እንዳያደርጉ ይረዳል:: በማፅዳት ዘመቻው ኅብረተሰቡ ማስክ መጠቀምና በአግባቡ ማስወገድ እንዳለበት ግንዛቤ ይሰጣል:: በየሳምንቱ እሁድ በከተማው ደረጃ ፅዳት እንደሚካሄድም ያስረዳል::
የተሻሉ ፕሮጀክቶችን በመንደፍ እናቶችን ለመደገፍ የመረጃ መሰብሰብ ሥራው የተጠናቀቀ ሲሆን በአሁኑ ወቅት ከለጋሽ ድርጅቶች ጋር በውይይት ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ይጠቁማል። በፕሮጀክቱ ከ70 በላይ እናቶች የተመዘገቡ ሲሆን በተለይ በጥጥ ፈትል፣ በዶሮ እርባታ፣ በጉልት ሥራና በሌሎች ዘርፎች እንዲሰማሩ ለማድረግ ዝግጅት መደረጉን በመጥቀስ፤ እናቶቹ በሚፈልጉት የሥራ ዘርፍ ሥራ ተፈጥሮላቸው ከችግሮቻቸው እንዲወጡ ለማመቻቸት እየተሰራ እንደሚገኝ ያመለክታል።
እንደ ወጣት ሀብታሙ አባባል፤ በሌላም በኩል ለመስራት አቅም ለሌላቸው ደግሞ በቀጥታ የሚረዱበት መንገድ እየተመቻቸ ሲሆን ገቢ ለማሰባሰብ የሥነፅሑፍ ምሽት ተዘጋጅቷል። በተጨማሪም ከሥነ ፅሑፍ ምሽት በሚገኘው ገቢ ጎዳና ላይ ይኖሩ የነበሩ ወጣቶችን ለማንሳት ታቅዷል።
ለአስራ አንድ ጎዳና ተዳዳሪዎች በሚዛን፣ በሱቅ በደረቴና በጫማ መጥረግ ሥራ እንዲሰማሩ ዝግጅት እየተደረገ ነው። ወጣቶቹ የሚኖሩበት ቤት እየተፈለገላቸው ሲሆን አንድ ቤት ለአራት የሚኖሩበት ሁኔታ ይመቻቻል። ሁለተኛው ገቢ ማሰባሰብ ለቤት ኪራይና ሥራ እስኪጀምሩ ለአንዳንድ ወጪ የሚሆናቸው ከማዘጋጀት ጥረት እየተደረገ ይገኛል:: በቋሚነት ማህበሩ ድጋፍ የሚያገኘው ከኅብረተሰቡ ነው። ሌላው ደግሞ በሚዘጋጁ ኪነጥበብ ምሽቶች የሚገኘው ገቢ ነው። በኪነጥበብ ምሽቶች ድጋፍ የሚያደርጉ ሰዎችም ይመጣሉ።
ሌላው የማህበሩ አባል የሆነው ወጣት አክሊሉ ትኩ እንደሚናገረው፣ ማህበሩ ለመመስረት የበቃው ቀድሞ የኪነጥበብ ቡድን የነበረውን ወደ በጎ አድራጎት ሥራ እንዲሰፋ በማድረግ ነበር። የማህበሩ አባላት በግጥም እና በሌሎች ኪነጥበብ ሥራዎች ይሳተፉ ነበር። ማህበሩ ከተመሰረተ በኋላ የተለያዩ እንቅስቃሴዎችን አድርጓል።
ማህበሩ ‹‹አንድ ልጅ ለአንድ እናት›› በሚል አምስት ኪሎ ዱቄት፣ አምስት ሌትር ዘይት፣ ሁለት ማካሮኒና ፓስታ እንዲሁም ሌሎች ለምግብነት የሚውሉ ነገሮች ድጋፍ ተደርገዋል። ወላጅ ለሌላቸው ተማሪዎች ደግሞ ደብተርና እስኪርቢቶ መሰጠቱን ይናገራል።
ለመከላከያ ሰራዊቱ የደም መለገስ፣ የኮሮና ወረርሽኝ በተከሰተበት ወቅት የግንዛቤ ሥራ፣ የአንበጣ ወረርሽኝ በተከሰተበት ወቅት ወጣቶችን በማስተባበር የመከላከል ሥራ እንዲሁም ሌሎች ሥራዎች መከናወናቸውን ያመለክታል።
የኮሮና ወረርሽኝ በተከሰተ ጊዜ በየአካባቢው በመዘዋወር የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎች ሲከናወኑ ነበር። ውሃ በማይኖርባቸው አካባቢዎች በጋሪ ውሃ በማመላለስ እንዲሁም ሌሎች የግንዛቤ ሥራዎች ማህበሩ ሲያከናውን እንደነበር ወጣት አክሊሉ ያስረዳል።
የሕዝቡ ተሳትፎ
ማህበሩ ሥራውን በጀመረበት ወቅት የኅብረተሰቡ አቀባበል ችግር ነበረበት። ለዚህ ደግሞ ወጣቱ የተለያዩ ጥያቄዎች ስለነበሩበት አለመተማመኖች ነበሩ። ‹‹አንድ ልጅ ለአንድ እናት›› ፕሮጀክት አዳራሽ ውስጥ ነበር ድጋፍ የተደረገው። አብዛኛው ማህበረሰብ ተከታትሎት ነበር።
በዚህም ከታቀደው በላይ ድጋፍ ተገኝቷል። በወቅቱ ድንገት የመጡና ምዝገባ ውስጥ ያልተካተቱ ሰዎች ሲመጡ ኅብረተሰቡ ከኪሱ እያዋጣ ድጋፍ አድርጓል። ከዚህ ፕሮጀክት በኋላ ኅብረተሰቡ በቋሚነት ማህበሩን እየደገፈ ይገኛል። ጎዳና ተዳዳሪዎቹን ለመርዳት በሚደረገውም እንቅስቃሴ ኅብረተሰቡ በየግል ድጋፍ እናድርግላቸው የሚል ጥያቄ ያነሳል። ነገር ግን በተረጂዎቹ መካከል ልዩነት እንዳይኖር ከለጋሾቹ ጋር ወይይት እየተደረገ መሆኑን ወጣት ሀብታሙ ያመለክታል።
ያጋጠሙ ችግሮች
ከመንግሥት አካላት በኩል ቢሮክራሲው አስቸጋሪ እየሆነ ነው። በከተማው ባህልና ቱሪዝም ቢሮ እና በማህበሩ መካከል አለመግባባቶች አሉ። የቢሮው አቋም ማህበሩ በኪነጥበብ ስም ተቋቁሞ በጎአድራጎት ውስጥ መሳተፍ የለበትም የሚል እንደሆነ ወጣት ሀብታሙ ይገልፃል። ‹‹የበጎ አድራት ሥራ የምትሰሩ ከሆነ ብሎ ቢሮና መለማመጃ አዳራሾችን ተቀምተናል። የሚመለከተው አስተዳደር ጋርም ቢኬድ መፍትሄ እስካሁን አልተገኘም። የከተማው አስተዳደር ማህበሩ የበጎ አድራጎት ሥራ ቢሰሩ ችግር እንደሌለው ቢነግረን
በተግባር ግን እገዛ እያደረገ አይደለም።›› ይላል። ከዚህ ውጪ በፀጥታ ጉዳይና በሌሎች ጉዳዮች የከተማ አስተዳደሩ አስፈላጊውን ትብብር እያደረገ ይገኛል። በተለይ ሴቶችና ሕፃናት ቢሮ ከፍተኛ የሆነ ትብብር እያደረገ ሲሆን ሌሎች ቢሮዎች ከፍተኛ ትብብር እያደረጉ መሆኑን ወጣት ሀብታሙ ይጠቁማል።
ወደ በጎ ሥራ ሲገባ ችግሮች አይጠፉም የሚለው ወጣት አክሊሉ፤ ድጋፍ ለማሰባሰቡ በሚደረጉ እንቅስቃሴዎች ላይ እንቅፋት እንደማይጠፋ ይናገራል። ስለ በጎ አድራጎት ጠለቅ ያለ ግንዛቤ የሌላቸው ሰዎች ለራሳችሁ ልትወስዱት ነው የሚል አመለካከት እንዳላቸው ይገልፃል። እንደዚህ ዓይነት ሁኔታዎች እየተሰሩ ባሉ የግንዛቤ ሥራዎች በአሁኑ ወቅት እየቀነሱ መምጣታቸውን ይጠቁማል።
አስገራሚ ክስተት
‹‹አንድ ልጅ ለአንድ እናት›› ፕሮጀክት እየተከናወነ ባለበት ወቅት የተወሰኑ ሰዎች ድጋፍ ማሰባበሰብ አትችሉም ብለው ከልክለው ነበር። ከኅብረተሰቡ ገንዘብ ሰብስባችሁ መሄድ አትችሉም በሚል ግጭት ውስጥ እስከመግባት ተደርሶም ነበር። ገንዘብ ሰብስበን ይዘን አልሄድንም የተሰበሰበውም ገንዘብ በደረሰኝ ስለሆነ ሕጋዊነት እንዳለው በወቅቱ ለማስረዳት ተሞክሮ ነበር። ነገር ግን መግባባት ላይ መድረስ ባለመቻሉ ከማህበሩ አባላት ጋር የከረረ ግጭት ውስጥ መገባቱን ወጣት ሀብታሙ ያስታውሳል።
ሁኔታውም ወደ ሕግ ከመውሰድ ይልቅ ልጁን በግል ማነጋገር እንደሚሻል ስለታመነበት ልጁን በግል የተወሰኑ ሰዎች እንዲያናግሩት ተደረገ። ልጁም ድጋፍ በሚደረግበት ቦታ እንዲመጣም ተጋበዘ። ድጋፍ በተደረገበት ጊዜም ልጁ ተገኝቶ ሁኔታዎችን ተመለከተ። ማህበሩ ያሰባሰበው ድጋፍ ለሁሉም ሳይዳረስ በመቅረቱ ልጁ የተረፉትን እናቶች በግሉ ለመርዳት ቃል ገባ። በአሁኑ ወቅት በየወሩ ለእናቶቹ 500 ብርና ሌሎች ድጋፎችን እያደረገ እንደሚገኝ ያስረዳል።
የማህበሩ ቀጣይ እቅድ
‹‹ማህበሩ በቀጣይ አባላትን እያበዛ የመሄድ ፍላገት አለው›› ወጣት ሀብታሙ፤ የኪነጥበብ ምሽቱ በሚካሄድበት ጊዜም አባላትን ለመጨመር ጥረት እንደሚደረግ ያመለክታል። በአሁኑ ወቅት ቋሚ ድጋፍ ለሚያስፈልጋቸው ሰዎች ወደ ማቆያ የሚገቡበት መንገድ ለማመቻቸት ታስቧል። ይህ እስከሚሳካ አዛውንቱን ባሉበት በቋሚነት መርዳትና ሕፃናቱን ባሉበት ሁኔታ ለመደገፍ ሁኔታዎች እየተመቻቹ መሆኑንም ያብራራል።
በቀጣይ በጎዳና ላይ የሚገኙ ወጣቶችን በማሰባሰብ በሊስትሮና በሚዛን እንዲሁም እንደወጣቶቹ ፍላጎት ወደ ሥራ እንዲሰማሩ ለማድረግ ሁኔታዎች እየተመቻቹ መሆኑን ወጣት አክሊሉ ይጠቁማል። ስለ ድጋፉም ወጣቶቹን በማሰባሰብ ውይይት የተካሄደ ሲሆን ወደ ተግባር ለመግባት ድጋፍ የሚያደርጉ አካላትን የማነጋገር ሥራ መጀመሩን ይናገራል።
ድጋፍ ያደረጉ አካላት ያሉ ሲሆን በተጨማሪም ከቴክኒክና ሙያ ማሰልጠኛዎችም ጋር በመነጋገር የልብስ ስፌት ስልጠና እንዲወስዱ ለማድረግ መታሰቡን ያመለክታል። እናቶችን በጥጥ ፈተላ እና ጥጥ ለመፍተል አቅም የሌላቸውን የገንዘብ እርዳታ ለመርዳት መታቀዱን ይገልፃል።
አዲስ ዘመን ታህሳስ 16/2013