ግርማ መንግሥቴ
በርዕሴ የተከተልኩት ስልት ጌትነት እንየው በላይን የወንዶች ሁሉ ወንድ፤ የጀግኖች ሁሉ ጀግና፤ የአርበኞች ሁሉ ቁንጮ መሆኑን ለመግለፅ “በላይ የወንዶች ቁና” ሲል የተጠቀመበትንና በላይን ከለካበት፤ በላይን የወንዶች ሁሉ አለም አቀፍ መለኪያ፣ መስፈርትና ሚዛን ካደረገበት ትያትሩ ነው። “ፑቲን – የመሪዎች ቁና”።
“ቁና” ከጌትነት ትያትር አይነቱ ጥበባዊ ፋይዳ ባለፈ በበርካታ የፈጠራ ስራዎች ውስጥ በቁልፍነት እየገባ የሚያገለግል ሲሆን አንዱም ስነቃል (ቃላዊ ፈጠራ) ነው። ለዚህም “በሰፈሩት ቁና መሰፈር አይቀርም፣ “ለስሟ መጠሪያ ቁና ሰፋች”ን መጥቀስ ይቻላል። “ቁና ቁና ይተነፍሳል”ንም እንደዛው።
ባጭሩ “ቁና” ባህላዊ ቁስ፣ የአያት ቅድመ አያቶቻችን የአዕምሮ ፈጠራ ውጤትና እሴታችን ሲሆን፤ ማህበረ-ባህላዊም ሆነ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታው ዛሬም ድረስ ዘልቆ ይገኛል። (ዛሬ ፑቲን “ያለ ባህሌ” ካላሉን በስተቀር በቁናችን እንሰፍራቸው ዘንድ ተነስተናል።)
ጌትነት በላይን “የወንዶች ቁና” ሲል የጀግኖች … ሁሉ መለኪያና መስፈርቱ የበላይ ሰብዕናና አኩሪ ተግባር እንጂ ሌላ ሊሆን አይችልም እያለ ነው።
ቭላድሚር ቭላዲሚሮቪች ፑቲንንም ከዚሁ አኳያ ስናነሳ እኛም ይህንኑ እያልን፤ ከአፅናፍ አፅናፍ የናኘ ፖለቲካዊና የመሪነት ሚናቸውን፣ ያመጡትን ለውጥና ያስገኙትን ውጤት በእኛው ቁና እየሰፈርን ነውና እንቀጥል።
በመሰረቱ ሰውን እንደየግብሩና ባህርይው መግለፅ፣ ማመስገን፣ መመረቅም ሆነ ማወደስ ወይም በተቃራኒው ማድረግ ምንም አዲስ ነገር አይደለም፤ “አካፋን አካፋ ማለት . . .” እንደሚባለው ማለት ነው፤ ግን ደግሞ በጨዋነት። በመሆኑም ነው፤ በተለይ በኪነ-ጥበብ ስራዎች ውስጥ ጀግናን ማወደስ፣ የአገር ባለ ውለታን ማመስገን ወዘተ እንግዳ ሆኖ የማያውቀው።
በተለይ በተለይ መሪን፤ ከራሱ ጥቅም በላይ ለአገሩና ለሚመራው ህዝብ ክብር፣ ጥቅም፣ ሉአላዊነት ወዘተ ሲል እራሱን አሳልፎ እስከ መስጠት የደረሰ ከሆነ በዘመን ተሻጋሪነት ሁሉ ተስተካካይ የለውም።
ታሪክ እንደሚያሳየው ጀግና ወዳጁ “ሁሉም” ነው። ጠላቱ ሳይቀር ያከብረዋል፣ ያደንቀዋል፤ እየጠላውም ሁሉ ይወደዋል። ለዚህ ደግሞ ተጠቃሽ አገር ቢኖር እኛ ነን – ኢትዮጵያ።
ፋሺስት ጣሊያን መጣ፤ ተገርፎ ተሸኘ። ከ40 አመት ከፍተኛ ዝግጅት በኋላ እንደገና ተመልሶ መጣ፤ ልቡ እስኪጠፋ ተለጥልጦ፣ ተደልዞ፣ ተወቅጦ፣ ተፈጭቶ (ባጭርና በተለመደው አገላለፅ አይቀጡ ቅጣት ተቀጥቶ) በመጣበት እግሩ ወደ መጣበት ተመለሰ፤ አለምም ጉድ አለ።
“ነጭ በጥቁር ተደመሰሰ፤ የጥቁር የጦር የበላይነት ነገሰ” የሚለው ለነጩ ወገን ጭራሽ አልዋጥ አለ። እውነት እውነት ነውና በመጨረሻ ሁሉም ዋጠው።
ፋሺስት ጣሊያን ወደ መጣበት ሲመለስ ሲመጣ ተመርቆ እንደ ተሸኘው አይደለም፤ የጠበቀው ርግማንና ውግዘት ነበር። “የማይነኩ ህዝቦችን ነክቶ፣ የማይደፈር ምድር ደፍሮ፣ የማይገጥሙትን ገጥሞ አዋረደን …” ከሚለው አንስቶ “ማን ሂድ አለህና ነው የጣሊያንን ህዝብ ያዋረድከው፣ ምን ጥልቅ አድርጎህ ነው አንገታችንን ቀና አድርገን እንዳንሄድ ያደረከን” ወዘተ ወዘተ እስከሚለው ድረስ የዘለቀ ውግዘት ነበር የጠበቀው።
ይህ ሁሉ የሆነው ደግሞ በአንድ ወገን ወይም የህብረተሰብ ክፍል ሳይሆን በሁሉም የጣሊያን ህዝብ ነበር። (የሚገርመው ነገር አሁንም ህዝባችን የሚሉትን አካል ለስነልቦና ድቀትና ለዘላቂ ውርደት የሚዳርጉ መሪ ተብዬ መሪዎች (እታችም ይሁን እላይ) መኖራቸው ነው።)
ከእነዚህ የፋሺስቱ ሞሶሎኒ ተቃዋሚዎች መካከል የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችና ማህበረሰብ አባላት የሚገኙ ሲሆን ድርጊቱን (አፍሪካን የመቀራመት የእብዶች ስምምነት ለመፈፀም መሯሯጡን) አምርረው የተቃወሙትም እነሱ ነበሩ።
በተማሪዎቹ ተቃውሞ ሰልፍ ወቅት ሲስተጋቡ ከነበሩትና ሞሶሎኒን ከሚያወግዙት መልእክቶች ጎን ለጎን ምኒልክን የሚያደንቁ፣ የሚያወድሱና የሚያሞግሱ፤ በተፃፈ መፈክር የተደገፉ መልእክቶች የነበሩ መሆናቸው ሲሆን፤ በብዙ የታሪክ ተመራማሪዎችና ድርሳናት ውስጥ ሳይጠቀስ የማይታለፈው ግን አንዱ ነው።
“ምኒልክ ጀግና!! ኢትዮጵያ ጀግና!!” ወይም በቋንቋቸው እንዳስቀመጡት “VIVA DE MENELIK, VIVA DE ETHIOPIA” ነበር ያሉት። (በጉዳዩ ላይ ከተሰሩ በርካታ ስራዎች አንዱንና በዚህ ፀሀፊ እምነት የተዋጣለትን፤ “The Battle of Adwa, African Victory in the Age of Empire” (Raymond Joseph,) ያነቧል።) ልክ ነበሩ። በታሪክም ልክ እንደሆኑ እስካሁን አሉ፤ ይኖራሉም።
(ስለ አድዋ ድልና አፄ ምኒልክ የMarcus Garvey, W.E.B. Du Bois, Bob Marley (በዜማ), George, Padmore Raymond Joseph እና ሌሎችንም በርካታ ስራዎች መመልከት ይቻላል።) ወደ ተነሳንበት እንመለስ።
አለም ቭላድሚር ቭላዲሚሮቪክ ፑቲንንም ልክ እንደ ምኒልክ ቢያደንቅ ቢያሞካሻቸው ተገቢ ነው፤ እየጠላቸውም ቢሆን በስራና ተግባራቸው፤ በውጤታቸውና ስኬቶቻቸው ሊያደንቃቸው ይገባልና አንዳንዶቹን እንይ።
ሩሲያን ከወደቀችበት ብቻ ሳይሆን ከፈራረሰችበትም እንዳነሷት በአድናቆት የሚነገርላቸው ፑቲን ከአገራቸውም ባለፈ በአለም አቀፉ መድረክም ሆነ የፖለቲካ አደባባይ ላይ ተዘወታሪ ተጠቃሽ ብቻ ሳይሆኑ ተፈሪም፤ በጥርጣሬ የሚታዩም ጠንካራ መሪ ናቸው።
በመሆኑም ነው ሲኤንኤን “ከአለማችን እጅግ ሀይለኛው ሰው”፤ “ከአለማችን እጅግ ታዋቂውና ዝነኛው ሰው”፤ ሲላቸው ቢቢሲም “የተግባር ሰው” (Action man) በማለት ገልጿቸዋል። Forbes በበኩሉ “የአለማችን እጅግ ሀይለኛ ሰው” (አራት ጊዜ – ከ2013 እስከ 2016) ሲል በተደጋጋሚ አድንቋቸዋል። የየአመታቱም ምርጥ አድርጎም አስቀምጧቸዋል። ሌሎችም በርካቶች ከዚህም በላይ በሆነ አገላለፅ የገለጿቸው ሲሆን አነጋጋሪነታቸውንም እንደዛው።
አገራቸውን በተለያዩ ዘርፎች ማገልገላቸውና በተለይም ቁልፍ ቁልፍ በሆኑ ቦታዎች ላይ መስራታቸው፤ ለምሳሌ በአገሪቱ የስለላ ድርጅት ውስጥ ለ16 አመታት በኦፊሰርነት፣ በጠቅላይ ሚኒስትርነት (2008 እስከ 2012)፣ በተጠባባቂ ፕሬዚዳንትነት፣ በመከላከያው እስከ ሌትናንት ኮሎኔልነት ማእረግ መዝለቃቸውና በጠቅላይነታቸውም ሆነ አሁን የአገሪቱን ወታደራዊ አቅም ለማሳደግና ለማዘመን ባደረጉትና እያደረጉት ባለው ከፍተኛ ጥረት፤ ሩሲያን የተለየችና የምትከተለውም የዲሞክራሲ ስርአት ከራሷ ጋር የተስማማና “የተገራ ዲሞክራሲ” ይሆን ዘንድ “Managed democracy” ፅንሰ ሀሳብን በማፍለቅ ተግባራዊ እንዲሆን በመጣር ላይ መሆናቸው፣ ከፍተኛ የህዝባቸውን ፍቅር ማግኘታቸው፣ ይህም የክሬምሊኑ ባለስልጣናት ሳይቀሩ “ፑቲን ባይኖር ኖሮ የዛሬዋ ሩሲያ አትኖርም ነበር”፣ “ፑቲን ከሌሉ ሩሲያ የለችም” (“There is no Russia today if there is no Putin.”፤ “No Putin, No Russia.”) እስከማለት ድረስ ያስኬዱ መሆናቸውና በፖለቲካ ህይወታቸው ውስጥ ያጋጠሟቸውን መሰናክሎች በጣጥሰው የመጡበት መንገድና ችሎታቸው ወዘተ ወዘተ (በዚህ ፅሁፍ ዘርዝረን በማንጨርሳቸው ምክንያቶች) ለእውቅናም ሆነ ዝናቸው የመሰረት ድንጋዮች ናቸው። (ምንም እንኳን እነአሜሪካ በብቸኝነት ይዘውት የነበረው የበላይነት በፑቲን አማካኝነት ከእጃቸው ተፈልቅቆ በመወሰዱ ምክንያት ባይወዷቸውም።)
ከዚሁ ከፖለቲካ ሰብዕናቸውና የመሪነት ብቃታቸው፤ በዚህም ሩሲያን ከወደቀችበት ማንሳታቸውና አሁን ያለችበት ደረጃ ላይ ከማድረሳቸው በተጨማሪ ሁለ ገብነታቸው (በስፖርቱ፣ ባህረኝነቱ፣ ሀይማኖተኝነቱ፣ ጁዶው ወዘተ) ሁሉ እውቅናቸው በዓለም እንዲናኝ አድርጎታል።
በተለይ ለሩሲያ የሚገባትም ሆነ የሚመጥናት “የተገራ የዲሞክራሲ” ሥርዓት እንጂ ከየትም የመጣውና ልቅ የዲሞክራሲ ሥርዓት አይደለም በማለት እያራመዱት ያለው የፖለቲካ ፍልስፍናም እንበለው የርዕዮት መስመር በካፒታሊስቶች ዘንድ ባይወደድላቸውም በሌላው በተለይም በሚመሩት ህዝብ ዘንድ ተቃውሞ ሲያስነሳ አልተሰማም።
(ቢሳካላቸው ጠ/ሚ ዐቢይ አህመድም “መደመር” ሲሉ ይዘውት የተነሱት ፍልስፍናም ወደ ፊት ከዚሁ አኳያ ሊታይ የሚችል ይመስለናል።)
አራተኛው የሩሲያ ፕሬዚዳንት (ከ2012 ጀምሮ፤ በ2018 እንደገና በመመረጥ)ቭላድሚር ቭላዲሚሮቪች ፑቲን (የመጀመሪያው ቦሪስ የልሲን ናቸው) በተለያዩ የኃላፊነት ቦታዎች አገራቸውን አገልግለዋል።
ለአቅመ ስልጣን ከደረሱ በኋላ አንድም ወቅት ያለ ስልጣንና ኃላፊነት ያሳለፉበት ጊዜ የለም ማለት እስከሚቻል ድረስ እያቀያየሩና እየተቀያየሩ ሰርተዋል። በእነዚህ ጊዜያት ሁሉ ግን በሰው ልጅ ላይ፤ በተለይም በአንድ አገር መሪና ፖለቲከኛ ላይ ሊደርሱ የሚችሉ፣ ህይወታቸውን እስከ ማጥፋት ድረስ የዘለቁ ሴራዎች (ከውስጥም ከውጭም) ተሴሮባቸው ሁሉንም በሚገራርሙ ታክቲክና ቴክኒኮች አልፈው ዛሬ ያሉበት ደረጃ ላይ ከመድረሳቸውም ባለፈ “ፑቲን የሉም ማለት ሩሲያ የለችም ማለት ነው” (No Putin, No Russia) የሚባሉበት ደረጃ ላይ ደርሰዋል። (እነ ሲኤንኤ፣ ቢቢሲ … ያሉትን ያስታውሷል)
በተለይ ፑቲን ወደ ስልጣን ከመምጣታቸው በፊት የነበረውን አስከፊ የኢኮኖሚ ይዞታ በሚያስደንቅ ሁኔታ መቀየራቸው፤ አንድም ቢሊየነር የሌላትን ሩሲያ በእሳቸው ዘመን ከ110 በላይ ቢሊየነሮችን ማፍራት መቻሏና ሌሎችም ከዚህም ከዚያም “ፑቲን …”፣ “ፑቲን …” የሚሉ ድምፆች እንዲበራክቱ ምክንያት ሆኗል።
ባለፈው ዓመት ኢትዮጵያ የነበረባትን ከ163 ሚሊዮን ዶላር በላይ ውዝፍ እዳ የሰረዘችው ሩስያ (ጥብቅ ወዳጅነታችንና ለወሳኝ ጉዳዮች ፈጥኖ ደራሽነቷ ሳይረሳ) ለዚሁ ለዘመነ ፑቲን የኢኮኖሚ ብልፅግና ጉዞ ማሳያ አድርገው የሚገልፁም ብዙዎች ናቸው።
እንደ ሲኤንኤን ዘጋቢ ፊልም ትንተና አለማችን በርካታ ጠንካራ መሪዎች አሏት፤ የአሜሪካና የቻይና መሪዎችም ጠንካራ መሪዎች ናቸው። ፑቲንን ከሁሉም ለየት የሚያደርጋቸው ምንም አይነት የተመቻቸ ሁኔታ በሌለበት የስልጣን ዘመናቸው ውስጥ ያንን ሁሉ ፈታኝ ሁኔታ አልፈው እዚህ መድረሳቸውና አገሪቱንም ለዚህ ደረጃ ማብቃታቸው ብቻ በጥንካሬያቸው፣ በፖለቲካ ፍልስፍናቸው፣ የአመራር ብቃትና እውቀታቸው፣ አሰራር ክሂላቸው በአለማችን ጠንካራ ከሚባሉት መሪዎች ሁሉ ለየት ያደርጋቸዋል፤ እጅግ ጠንካራው መሪም ያስብላቸዋል።
ከዛም አልፈው ዓለም አቀፍ ተፅእኖ ፈጣሪ ለመሆን መብቃታቸው ሲታከልበት ደግሞ ሰብዕናቸውን እጅጉን ማግዘፉ የታወቀ ነውና “ፑቲን – የመሪዎች ቁና” ያስኬዳል እያልን ነው።
ኮሚኒዝምና ካፒታሊዝም አይንና ናጫ እንደሆኑት ሁሉ ያለፈ ያገደመ የአሜሪካ መሪ ሁሉ ከፑቲን ጋር በተለባበሰ (አሁን ከሳይበር ጋር በተያያዘ እየከረረ መጥቷል) ጥላቻ ውስጥ እንዳሉ አሉ።
ከሁሉም ግን እንደ ሂላሪ ክሊንተን አይን ያወጣ አፀያፊነት የታየበት የነጩ ቤተ መንግስት ሰው ታይቶ የሚታወቅ አይመስልም። ፑቲንን ሙልጭ አድርጎ ባደባባይ በመሳደብ በኩል ያለ ተወዳዳሪ የቆሙት ሂላሪ ከትራምፕ ጋር ተወዳድረው ለመውደቃቸው፣ ከላይ የጠቀስነው የሲኤንኤን ዘጋቢ ፊልምን ጨምሮ፣ የፑቲን እጅ እንዳለበት በእርግጠኝነት የሚናገሩም ሞልተዋል። በመሆኑም ይመስላል ከዛ ወዲህ በአሜሪካን ፖለቲከኞች ዘንድ “የኮምፒውተር ስርዓት ሰርሳሪው ፑቲን” የሚል ተለዋጭ መጠሪያን የደረቡላቸው።
ከ2012 ጀምሮ በፕሬዚዳንትነት አገሪቱን እየመሩ ያሉት ቭላዲሚር ቭላዲሚሮቪክ ፑቲን በብዙ ነገሮቻቸው ልዩ ናቸው። በመሆናቸውም ከሚጓጓዙበት ፕሬዚዳንታዊ አውሮፕላናቸው ጭምር በሳቸው ልክ የተሰፋና ባሰፉት ልክም የሚጠቀሙበት እጅግ ዘመናዊ ሁለገብ መሳሪያቸው ነው።
በመሆኑም “የቦርድ ቁጥር አንድ (8 ተሽከርካሪዎች እና ሁለት ሄሊኮፕተሮች አሉት) መጓጓዣ ብቻ አይደለም፤ በተመሳሳይ ጊዜ የአንድ አገር ተንቀሳቃሽ የመቆጣጠሪያ ማዕከልና ቢሮ ጭምር እንጂ። የአገሪቱን የጉምሩክ አሰራር፣ (የኮሚቴውን ጭምር)፣ የአየር ንብረቶችን፣ አጠቃላይ የአገሪቱን ደህንነትና የሰራዊቱን ሁኔታ ሳይቀር ይቆጣጠራል፤ ይመራልም።”
ባጭሩ ፑቲን በጉዞ ላይ እያሉ “በጉዞ ላይ ናቸው እንጂ ስራ ላይ አይደሉም ብሎ የሚዘናጋና ለሴራ ፖለቲካው ጭዳ ሊያደርጋቸው የሚፈልግ ካለ እሱ አስቀድሞ ተበልቷልና ቢቀርበት ይበጀዋል።” አይነት ዘገባዎችን ማንበብም ሆነ ማዳመጥ አዲስ ነገር ያልሆነው። (እሳቸው ወደ ስልጣን ከመጡ ወዲህ ያሰሩትን የ”ቦርድ ቁጥር 1”ን አጠቃላይና አስደናቂ ሁኔታ ከተገቢ ምንጭ መርምሮ መረዳት ተገቢ ነው።) ፑቲን አገር ብቻ ሳይሆን ለአገራቸው ክብር ሲሉ መስዋእት የሆኑ የቀድሞ ጦር ሰራዊት አባላት ሁሉ ሳይቀር ጠበቃ ናቸው። (ይህ በራሱ የቀድሞ ሰራዊት አባላትን “የከሰሩ” (losers) ካሉት ከአሜሪካው ትራምፕ በእጅጉ እንዲለዩ ያደርጋቸዋል።)
ከ4ሺህ 700 (1945) በላይ የሚሆኑ የሶቪየት ወታደሮች ኮሪያን ከጃፓን ወረራ ነፃ ለማውጣት (የኮሪያ ባህረሰላጤ እኤአ ከ1910 እስከ 1945 በጃፓን ቅኝ ግዛት ስር ነበር) በተደረገው ጦርነት የህይወት መስዋዕትነት ከፍለዋል። ማስታወሻ ይሆናቸው ዘንድም በፒዮንግያንግ ሀውልት ቆሞላቸዋል።
ይህ ሀውልት (መቃብር) በጥሩ ሁኔታ በመያዙ ፑቲን ለኪም ጆንግ ኡን የማስታወሻ ሜዳሊያ ሸልመዋል። ይህ የሆነው ደግሞ ሩሲያ በሁለተኛው የዓለም ጦርነት የጀርመኑን ናዚ በማሸነፍ ድል የተቀዳጀችበትን 75ኛ የመታሰቢያ አመት በምታከብርበት ቀን ሲሆን እለቱና የፑቲን ተግባር ብዙዎች ልብ ውስጥ ገብቶ ሰውየውን ያደንቋቸው ብቻ ሳይሆን ያመልኳቸው ሁሉ ዘንድ ግድ ብሏል። (በሰሜን ኮሪያ 1375 የሩሲያ ወታደሮች የተቀበሩበት 11 የጅምላ መቃብሮችና 345 የሚሆኑ የግለሰብ መቃብሮች መኖራቸው ይታወቃል።
ኢትዮጵያም በኮሪያ ጦርነት ግንባር ቀደም ተሳታፊ መሆኗ ይታወቃል፤ አንድ ቀንም እንዲህ እንደ ፑቲን የሚያስብና በመረጃ የተደገፈ ማስረጃ የሰጠን መሪ ይመጣ ይሆናል ብለን እናስባለን።)
ቆምጬውና ኮስታራው ፕሬዚዳንት፣ ሌተናል ኮሎኔሉና የደህንነት ባለሙያው ቭላዲሚር ቭላዲሚሮቪክ ፑቲን በማንም ዘንድ የሚደፈሩ አይደሉም፤ ሲቀላምዱም ሆነ ሲዘላብዱ አይሰሙም፤ ቃላቸው ሁሌም ቁም ነገር ነው። በአቻዎቻቸው ዘንድ ቅኔ እንደሚናገሩና ሁሌም ንግግራቸው ውስጠ ወይራ ነው ተብለው መጠርጠራቸው እውነት ቢሆንም ፑቲን ግን እኔ በጭራሽ፤ የተናገርኩት እውነታውንና ያለውን እውነት ብቻ ነው እስከ ማለትና የማረጋጋት ጥግ ድረስ እስከ መሄድ ደርሰው እንደነበር ሁሉ ተፅፏል።
ፑቲን ከፖለቲካው መድረክ ባለፈ የሚዲያውም ድምቀት ናቸው። እሳቸው ብቅ ሲሉ ጆሮውን ጣል የማያደርግ አድማጭም ሆነ ተመልካች የለም። ምንም አሉ ምን ይደመጣሉ።
ለዜጎቻቸውና አገራቸው ልዩ ፍቅር ያላቸው ሲሆን “የሩሲያ ድንበር (ቦርደር) መጨረሻ የለውም” እስከ ማለት የደረሱና እነ ቢቢሲ ይህችን ሀሳብ መዘው እስከ ማብጠልጠል የደረሱበት ጊዜም ሁሉ ነበር።
ፑቲን በሚከተሉት ጥብቅ የፖለቲካ ሥርዓት (political system)፣ በሚያራምዱት የፖለቲካ ፍልስፍናቸው (“philosophical rules for state behavior” እንዲሉ)፣ ተቺዎቻቸው “Putinism” ቢሉትም፣ ፖለቲካል ኢኮኖሚ አስተሳሰባቸው . . . የተለያዩ አተያዮች ያሉ ሲሆን የተቺዎቻቸው ትችቶችም ከሂትለር እስከ ዘመናዊ ማኪቬሊዝም፣ ከወግ አጥባቂነት እስከ ድሮ ናፋቂነት፣ ከስልጣን ፈላጊነት እስከ ሴረኛነት ወዘተ ወዘተ ድረስ የዘለቁ ናቸው። (በጉዳዩ ላይ “Putin’s Political Philosophers: Neo-Orthodoxy, Identitarianism, and the Russian Federation” (2018) በሚል የተጠናውን የShaun Kenney ስራ ማንበብ ጠቃሚ ነው (ፒዲኤፉ አለ)።)
አዲስ ዘመን ታኅሣሥ 13/2013