ፍሬህይወት አወቀ
በሀገሪቱ ያለውን የመኖሪያ ቤት ችግር ማቃለል እንዲቻል መንግስት የተለያዩ ሙከራዎችን ያደርጋል። ይሁን እንጂ ችግሩ ከዓመት ዓመት እየተባባሰ በመምጣቱ በህብረተሰቡ ዘንድ የየዕለት ፈተናው ሆኖ ቀጥሏል። የመኖሪያ ቤት እጥረት በተለይም በከተሞች አካባቢ ጎልቶ የሚስተዋል ቢሆንም በክልሎችም የሚታይ ሀገራዊ ችግር ነው።
ዜጎች በየጊዜው የተሻለ ኑሮ ፍለጋ ከገጠሪቱ ኢትዮጵያ ወደ ከተማ በመፍለሳቸው ምክንያት የመኖሪያ ቤት ችግሩ በከተሞች የከፋ እንዲሆን አድርጎታል። በመሆኑም መንግስት ከ1997 ዓ.ም ጀምሮ በተለያዩ የቤት ፕሮግራሞች ዜጎችን የቤት ባለቤት ለማድረግ ስራ የጀመረ መሆኑ ይታወቃል። በዚህም ጥቂት የማይባሉ ዜጎች የጋራ መኖሪያ ቤት ተጠቃሚ ሆነዋል።
ዳሩ መንግስት የሚገነባቸው የጋራ መኖሪያ ቤቶችና የተመዝጋቢዎች ቁጥር ካለመጣጣሙም በላይ በተለያዩ ብልሹ አሰራሮች ምክንያት ተመዝግበው ለ15 ዓመታታ ሲጠብቁ የነበሩ ዜጎች መኖሪያ ቤት ማግኘት እንደናፈቃቸው ቀርተዋል።
ታድያ ይህን ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሰ የመጣውን የመኖሪያ ቤት ፍላጎትና አቅርቦት ማጣጣም ያልተቻለበት አንዱ ምክንያትም የግንባታ መጓተት እንደሆነ ሲነገር ይደመጣል።
ማንኛውንም ስራ ለመስራት ቅድመ ዝግጅት ማድረግ ተገቢ እንደሆነ ይታመናል። በተለይም የቤት ግንባታን ለማከናወን ደግሞ በቀዳሚነት መሬት ማዘጋጀት አስፈላጊ ነው። ቀጥሎም በዛ መሬት ላይ ምን አይነት ግንባታን ማከናወን እንደሚቻል በማጥናት የዲዛይን ስራ መስራት የግድ መሆኑን ባለሙያዎች ያስረዳሉ።
መሬት ከሌለ ቤት መገንባት የማይቻል መሆኑን የሚያነሱት ባለሙያዎች በተመሳሳይ ዲዛይኑንም አስቀድሞ ማዘጋጀት የቤት ግንባታውን ቀልጣፋ ለማድረግ ከሚያስችሉ ዋና ዋና ጉዳዮች መካከል አንዱ መሆኑን ይናገራሉ።
በከተማዋ ለሚታየው የመኖሪያ ቤት እጥረት አንዱ ምክንያት የሆነው የግንባታ መጓተትን ለማስቀረት ከተማ አስተዳደሩ የተለያዩ እንቅስቃሴዎችን እያደረገ ይገኛል። በመሆኑም በአሁን ወቅት በቤቶች ልማት ኮርፖሬሽን ስር ተደራጅተው የነበሩ ሁለት ተቋማትን በአንድ ላይ በማዋሀድ እንዲሁም የግንባታ ዲዛይን ኤጀንሲን አቋቁሟል።
እነዚህ በአዲስ መልክ የተዋቀሩ ተቋማት በከተማው የሚታየውን የመኖሪያ ቤት እጥረት በማቃለል ሂደት ምን ሚና ይኖራቸዋል በማለት ላነሳነው ጥያቄ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የግንባታና ዲዛይን ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ ቴዎድሮስ አያሌው የሚከተለውን ምላሽ ሰጥተዋል።
ኤጀንሲው በዋናነት በከተማዋ የሚታየውን የመኖሪያ ቤት ችግር ለመቅረፍ ከሚያስችሉ ጉዳዮች መካከል የሆነውን የግንባታ መጓተት ለማስቀረት የተቋቋመ ነው። በመሆኑም ኤጀንሲው በቀጣይ በከተማዋ ለሚገነቡ ቤቶች የተሟላ ዲዛይን አስቀድሞ በማዘጋጀት የማማከርና የግንባታ ክትትልና ቁጥጥር ስራን ይሰራል።
በከተማዋ የሚገነቡ የጋራ መኖሪያ ቤቶች የዲዛይን ስራቸው አስቀድሞ ካለመጠናቀቃቸው ጋር ተያይዞ የግንባታ መጓተት ሲስተዋልባቸው ነበር። ነገር ግን በአሁን ወቅት መሬቱ ከተገኘ በኋላ በፍጥነት የዲዛይን ስራው ተከናውኖ ወደ ግንባታ ይገባል።
ግንባታው በፍጥነት እንዲከወንም ኤጀንሲው ክትትልና ቁጥጥር ያደርጋል። ግንባታው ተፋጠነ ማለት ደግሞ ህብረተሰቡ በፍጥነት የቤት ባለቤት እንዲሆን ያስችለዋል።
ለግንባታ መጓተት በምክንያትነት ከሚጠቀሱት መካከል የዲዛይን ስራው ቀድሞ ባለመሰራቱ እንዲሁም የግንበታ ክትትልና ቁጥጥር ማነስ መሆኑን ያነሱት ሀላፊው፤ ኤጀንሲው ከዚህ በፊት የነበሩ ችግሮችን በማቃለል ክፍተቶችን ለመድፈን ይሰራል።
በከተማዋ የሚሰሩ ቤቶችን አስቀድሞ ዲዛይኑን በማዘጋጀት ግንባታው በጥራትና ባጠረ ጊዜ እንዲከናወን የማድረግ ተግባርና ስልጣንም ተሰጥቶታል። ስለዚህ የዲዛይን ክፍተቱን እግር በእግር እየተከታተለ በመድፈን በከተማዋ የሚገነቡ የጋራ መኖሪያ ቤቶች በዲዛይኖቻቸው መሰረት እንዲሁም በታቀደላቸው የጊዜ ገደብና የጥራት ደረጃ መገንባታቸውን ከዚህ በፊት የነበረው አሰራር ግንባታውን የሚያከናውነው ባለቤት የግንባታ ቁሳቁሶችን አቅርቦ የሚሰራ በመሆኑ የግንባታ ቁሳቁሶች ሲያጥሩ ግንባታው የሚቋረጥበት ጊዜ ነበር።
ነገር ግን ይህ አሰራር በጥናት ተለይቶ ባለቤቱ የግንባታ ቁሳቁሶችን ሳያቀርብ ኮንትራክተሩ አስፈላጊ የሆኑ ቁሳቁሶችን በሙሉ በማቅረብ ግንባታና ዲዛይን ኤጀንሲ በሰጠው ዲዛይን መሰረት ያከናውናል። በዚህ ጊዜም ኤጀንሲው ግንባታው በተያዘለት የጊዜ ገደብ እንዲጠናቀቅና በዲዛይኑ መሰረት እንዲገነባ ክትትልና ቁጥጥር ያደርጋል።
ከዚህ በፊት በነበረው አሰራር መንግስት በጀት ሲያገኝ ቤቶቹን የሚገነባበትና በጀት ሲያጥረው ደግሞ ግንባታው የሚቋረጥበት ሂደት እንደነበር ሀላፊው አንስተዋል። ይህም በከተማዋ ለሚስተዋለው የመኖሪያ ቤት እጥረት እንደምክንያትነት የሚጠቀስ ነው። ስለሆነም በአሁን ወቅት መንግስት የግንባታ ቁሳቁሶችን በማቅረብ ስራው ላይ ሙሉ ለሙሉ ተሳታፊ አይሆንም። ኮንትራክተሩ በራሱ ቁሳቁሶቹን አሟልቶ ይገነባል። ኤጀንሲውም በተቀመጠው መስፈርት መሰረት እየተገነባ መሆኑን ክትትል ያደርጋል።
በከተማዋ የሚገነቡ ቤቶችን በተሻለ ጥራትና ፍጥነት እንዲገነቡ ማስቻል መኖሪያ ቤት እጥረቱን ያቃልላል ያሉት ሀላፊው፤ ይህን ተግባራዊ ማድረግ የሚቻለውም በቀዳሚነት የዲዛይን ስራውን በተገቢው መንገድ ማዘጋጀት ሲቻል ነው። በአሁን ወቅትም በከተማዋ ለሚሰሩ የጋራ መኖሪያ ቤቶች የተሻለ የዲዛይን ስራ መሰራቱን እና በቀጣይም የሚሰራ መሆኑን አመላክተዋል። በዲዛይን ስራውም ከዚህ በፊት ያልነበረ የአደጋ ጊዜ መወጣጫ፣ የቆሻሻ ማስወገጃ፣ ወደፊት አረንጓዴ ማድረግ ሲያስፈልግ ምላሽ መስጠት የሚያስችሉ ዲዛይኖች ተካተዋል።
ኤጀንሲው ከመቋቋሙ በፊት የግንባታውን ሂደት ለማፋጠን ጥናት መደረጉን ያስታወሱት ሀላፊው በጥናቱም በኮዬፈጬ ሳይት የነበረው የግንባታ ሂደት በመልካም ተሞክሮ መወሰዱን አንስተዋል። ተሞክሮውን ወደ ትግበራ በማምጣትም በአሁን ወቅት መንግስት ግንባታውን በመቆጣጠር ብቻ ተሳታፊ እንዲሆን ተደርጓል።
የግንባታና ዲዛይን ኤጀንሲም ከ2012 ዓ.ም መጨረሻ ጀምሮ ሰራተኞችን በማሰልጠን እና በማብቃት ወደ ስራ ገብቷል። በአሁን ወቅትም በከተማዋ የተለያዩ አካባቢዎች የሚገነቡ 26 ሺ 80 አባወራዎችን መያዝ የሚችሉ የተለያዩ ህንጻዎችን ዲዛይን ስራ ሰርቶ አጠናቋል።
ከተማ አስተዳደሩ የቤት ልማቱ በሚፈለገው ፍጥነት ያልተገነባው ለምንድን ነው በሚል ጥናት መደረጉን ያስታወሱት የግንባታና ዲዛይን ምክትል ዳይሬክተር አቶ አማረ ደምለው በበኩላቸው፤ የግንባታና ዲዛይን ኤጀንሲ የግንባታ መጓተቱን ለመቅረፍ መቋቋሙን አንስተዋል።
ከዚህ ቀደም የአዲስ አበባ ከተማ የቤቶች ልማት ፕሮጀክት ጽህፈት ቤት እና የቁጠባ ቤቶች ኢንተርፕራይዝ በ20/80 እና በ40/60 ተከፋፍለው ቤቶችን ሲገነቡ ቆይተዋል። በእነዚህ ፕሮግራሞች ሲገነቡ የነበሩ ቤቶችም እጅግ የተንዛዛ አሰራርን ይከተሉ ስለነበር በታቀደው መሰረት ቤቶቹ ለተጠቃሚዎች አልደረሱም። ይህም በከተማዋ ያለውን የቤት ፍላጎትና አቅርቦት እንዳይጣጣም በማድረግ ችግሩ ይበልጥ እንዲባባስ ምክንያት ሆኗል።
ቤቶቹ በታቀደላቸው ጊዜ ተገንብተው ለምን ለተጠቃሚዎች አልደረሱም የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ በተደረገው ጥናት ሙሉ ለሙሉ ያለቀለት የግንባታ ዲዛይን ተይዞ ወደ ግንባታ ያለመግባት ችግር በቀዳሚነት ተለይቷል።
በተጨማሪም የኮንስትራክሽን ሂደቱ በሚፈተሽበት ጊዜ ግንባታውን የሚያከናውኑ ተቋማት ከመሬት አቅርቦት ጀምሮ በሁሉም የግንባታ ሂደቶች ተሳታፊ መሆናቸው ነው። ተቋማቱ ጥቃቅን የሚባሉ የግንባታ ቁሳቁሶችን ሳይቀር በማቅረብ ተሳታፊ ነበሩ። ይህ ማለት ደግሞ መንግስት በእያንዳንዱ የኮንስትራክሽን ሂደት ላይ ጣልቃ በመግባት ግብዓቶችን ሲያቀርብ ቆይቷል።
በከተማዋ የሚገነቡ ህንጻዎች ሰፊ ከመሆናቸው ጋር ተያይዞ አላስፈላጊ የሆነ ብክነት እንዲፈጠር እና በርካታ ግዥዎች መፈጸማቸውም በጥናቱ ተለይቷል። እነዚህ በጥናት የተለዩትና ለግንባታው መጓተት ምክንያት የሆኑ ችግሮችን በመለየት ከተማ አስተዳደሩ ተቋሙን እንደ አዲስ አዋቅሯል።
በዋነኝነት የቤት ልማቱን የሚያጓትቱ ችግሮችን ለመቅረፍ በ20/80 እና በ40/60 ተደራጅተው የነበሩ ሁለት ተቋማትን በአንድ ላይ በማዋሀድ የአዲስ አበባ ቤቶች ልማት ኮርፖሬሽን ተብለው እንዲቋቋሙ ተደርጓል። ኮርፖሬሽኑም እንደ ባለቤት ሆኖ በከተማው ያለው የቤት ልማት በፍጥነት እንዲከናወን አስፈላጊ የሆነውን በጀት መድቦ ወደ ስራ እንዲገቡ ተደርጓል።
በሁለተኛነት የተቋቋመው የአዲስ አበባ ከተማ ግንባታና ዲዛይን ኤጀንሲ ሲሆን፤ ኤጀንሲው ከዚህ ቀደም ሙሉ ለሙሉ የዲዛይን ስራው ሳይጠናቀቅ ወደ ግንባታ ይገባ የነበረውን አካሄድ በማስቀረት መሬት ከተገኘበት ጊዜ ጀምሮ ሙሉ ለሙሉ የዲዛይን ስራውን አጠናቆ ወደ ግንባታ እንዲገባ ያደርጋል።
በተጨማሪም ወደ ግንባታ ከተገባ በኋላ ኤጀንሲው ክትትልና ቁጥጥር በማድረግ ቤቶቹ ተገንብተው ለተጠቃሚው እስኪደርሱ ያለውን የግንባታ ሂደት በመቆጣጠር ክትትል ያደርጋል።
በሶስተኛ ደረጃ የተቋቋመው የአዲስ አበባ ከተማ የግንባታ ኢንተርፕራይዝ ሲሆን፤ በዋነኝነት እንደ ኮንትራክተር ሆኖ ግንባታውን ብቻ እንዲያከናውን ተቋቁሟል። እነዚህ ሶስት አካላት ማለትም ባለቤት የሆነው የአዲስ አበባ ቤቶች ልማት ኮርፖሬሽን፣ ዲዛይኑን የሚያዘጋጅና ግንባታውን የሚከታተል አማካሪ የግንባታ ዲዛይን ኤጀንሲ እና ኮንትራክተሩ ወይም የሚገነባው አካል በጋራ ሆነው ይሰራሉ። በቅንጅት እንዲሰሩም በአዋጅ ተቋቁመዋል። ይህም በከተማዋ የሚገነቡ ቤቶችን በተሻለ ጥራትና በተቀመጠላቸው የጊዜ ገደብ ማጠናቀቅ የሚያስችል መሆኑ ይታመናል።
እነዚህ በአዲስ መልክ የተዋቀሩ ተቋማትም ባለሙያ ተመድቦላቸው ከግንባታ ጀምሮ ቤቶቹ ለተጠቃሚው እስኪደርሱ ያለውን ስራ ለመስራት እንቅስቃሴ ጀምረዋል። በዚህ መሰረትም ባለቤት የሆነው የአዲስ አበባ ቤቶች ልማት ኮርፖሬሽን ከሚመለከተው አካል ጋር በመሆን በበጀት ዓመቱ ለሚያከናውነው የቤት ልማት አስፈላጊ የሆነው መሬት እንዲዘጋጅለት ከቢሮ ጋር በሚፈጥረው ስምምነት መሰረት ቦታ ያዘጋጃል።
ያገኘውን ቦታም ለግንባታና ዲዛይን ኤጀንሲ የዲዛይን ስራው እንዲሰራለት ነጻ የሆነውን መሬት ለግንባታና ዲዛይን ያስረክባል። ኤጀንሲውም በግንባታ ዲዛይን ዝግጅቱ ቦታው ምን ያህል ፎቆችን መሸከም እንደሚችል እና ምን አይነት ፎቆች መገንባት እንዳለባቸው በማጥናት ዲዛይኑን ያዘጋጃል።
ከዲዛይን ስራው ቀጥሎም ግንባታውን የሚያከናውነው ኮንትራክተር ከአዲስ አበባ ቤቶች ልማት ኮርፖሬሽን ጋር ውል በመፈፀም ወደ ግንባታው ይገባል። በዚህ መሀል ከዲዛይን ስራው በተጨማሪ አማካሪ ሆኖ የሚያገለግለው የግንባታ ዲዛይን ኤጀንሲ ግንባታው በተያዘለት የጊዜ ገደብ ተገንብቶ እንዲጠናቀቅ ክትትል በማድረግ የግንባታ ሂደቱ ፈጥኖ እንዲከናወን ያደርጋል። በግንባታ ሂደት ለሚነሱ ጥያቄዎችም ምላሽ በመስጠት ችግሮችን ይፈታል።
በአሁን ወቅት በከተማዋ አራት የተለያዩ አካባቢዎች የሚገነቡ የጋራ መኖሪያ ቤቶች የዲዛይን ስራቸው ተጠናቅቆ ግንባታቸው ተጀምሯል። እነዚህ የጋራ መኖሪያ ቤቶች የሚገነባባቸው ሳይቶችም አንደኛው ለገሀር፣ ሁለተኛው አራዳ ሶስት ወይም በተለምዶ አሮጌው ቄራ አካባቢ ሲሆን ሶስተኛው ኮልፌ ሁለት ቤተል መንገድ ላይ ይገኛል። አራተኛው ደግሞ ጀርመን አደባባይ ሳይት ነው።
የግንባታና ዲዛይን ኤጀንሲ የእነዚህን አራት ሳይቶች የዲዛይን ስራቸውን ሙሉ ለሙሉ አጠናቅቆ ለኮንትራክተሮች በመስጠት የግንባታ ሂደቱን በመከታተል ላይ ይገኛል። በተጠቀሱት አራት ሳይቶች ላይ የሚገነቡት የጋራ መኖሪያ ቤቶች የተለያየ መጠን እና ይዘት ያላቸው ህንጻዎች ሲሆኑ፤ ኤጀንሲው በሚያደርገው ክትትል ግንባታው በተገባው ውል መሰረትና በተያዘለት የጊዜ ገደብ ተጠናቅቆ ለተጠቃሚዎች ተደራሽ መሆኑን ያረጋግጣል።
የጋራ መኖሪያ ቤቶቹ ተገንብተው ሲጠናቀቁ ከዚህ በፊት ተመዝግበው በመጠባበቅ ላይ ያሉ ዜጎችን ተደራሽ ለማድረግ በዕጣ የሚተላለፍ መሆኑን ያነሱት ምክትል ዳይሬክተሩ፤ በቅድሚያ ግን የጋራ መኖሪያ ቤቶቹ ግንባታ በፍጥነትና በጥራት እንዲጠናቀቁ ማድረግ የኤጀንሲው ተቀዳሚ ተግባር በመሆኑ እዚህ ላይ አጠናክሮ መስራት ያስፈልጋል ብለዋል። ኤጀንሲው በቀጣይም በከተማዋ የሚታየውን የግንባታ መጓተት ለማስቀረት የሚሰራ ሲሆን፤ የመኖሪያ ቤት ችግሮችን ከፈታ በኋላ በከተማው የሚገነቡ የተለያዩ ማህበራዊ አገልግሎት ሰጪ ተቋማት ላይ በመሳተፍ ግንባታቸው እንዲፋጠን የግንባታ ዲዛይኖችን በተሻለ ጥራት የሚሰራ ይሆናል።
አዲስ ዘመን ታኅሣሥ 10/2013