ዘካርያስ ዶቢ
ቁጥር ወይም አሀዝ የመረጃ ማጠንከሪያ ነው። መረጃ ብቻውን ጥሩ ቢሆንም፣ በአሀዝ ሲደገፍ ደግሞ ከአልጫነት ይወጣል፤ ኮስተር ይላል። ነገር ይበልጥ ታማኝነትና ተሰሚነት እንዲኖረው ያስችላል።
ወንጀለኛው የትህነግ ጁንታ ቡድን በሰሜን እዝ ላይ የፈጸመውን ጥቃት ተከትሎ በትግራይ ክልል ሲወሰድ የቆየው ህግን የማስከበር ዘመቻ ብዙ ጉድ አሳይቶናል። ትህነግ ይህን ያህል ጥቃት በአይነኬው የመከላከያ ሰራዊት ላይ ሲሰነዝር መንግስት ምን እየሰራ ነበር? የሚሉ ጥያቄዎች ሲነሱ ቆይተዋል። እርምጃው ዘግይቷል፤ በዚህም ዋጋ አስከፍሏል የሚሉ አስተያየቶች ይሰነዘሩም ነበር። የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ በምክር ቤቱ ማብራሪያ በሰጡበት ወቅት ተመሳሳይ ጥያቄዎችን ሰንዝረዋል።
ለጥያቄና አስተያየቶቹ ምላሽና ማብራሪያ የሰጡት ጠቅላይ ሚኒስትሩም፣ መከላከያ በአንድ አካባቢ ሰዎች የተሞላ እንደነበር በመግለጽ በምን ቁመና ላይ እንደነበር በዝርዝር አሀዛዊ መረጃዎችን እየጠቀሱ አስረድተዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ መከላከያ ውስጥ ሪፎርም ከመደረጉ በፊት የነበረውን ሁኔታ ሲያብራሩ ከጠቀሷቸው መካከል አለፍ አለፍ ብለን እንመልክት። በሀገሪቱ የደህንነት ተቋማት የሉም ማለት ይቻላል፤ የግለሰብና የቤተሰብ ማህበራት ናቸው፤ የደህንነት ተቋምም ፈርሶ መሰራት የነበረበት ተቋም ነው። መከላከያን ግን እንደዚያ ማድረግ የራሱ ችግር ነበረው ብለዋል።
ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግር መረዳት እንደሚቻ ለውም፣ መከላከያ ምን እንደሚመስል በዳታ በእውቀት እንይ ተብሎ ተሰርቷል። ለምሳሌ፣ ያህል በመከላከያ ሚኒስቴር ውስጥ አራት ኮከብ ያላቸው ጀነራሎች /ሙሉ ጀነራሎች/ ከትግራይ ክልል 60 በመቶ ሲሆኑ፤ ከተቀሩት የሀገሪቱ ክልሎች 40 ብቻ ነበር።አንድ ደረጃ ዝቅ ተብሎ ሌተናል ጀነራል የሚባለው ሲታይም ቁጥራቸው ዝቅተኛ ቢሆንም፣50 በመቶው ከትግራይ ክልል ናቸው።
ስልጣንን በተመለከተም በመከላከያ ዋና መስሪያ ቤት አዲስ አበባ ሆነው መስሪያ ቤቱን የሚመሩት በዋና መምሪያ እና መምሪያ ደረጃ ያሉት 80 ከመቶው ከትግራይ ክልል ነበሩ።
ከመከላከያ አንድ ደረጃ ዝቅ ብለን ስንመለከት እዞች አሉ።ኢትዮጵያ ካላት እዝ አዛዥ እና ምክትል አዛዥ መቶ በመቶ ከትግራይ ክልል ነው።ይህ ብቻ ሳይሆን ምስራቅና ምእራብ እዝ አማራ፣ ኦሮሞ፣… ተብሎ ሎጂስቲክስ ወይንም የሰው ሀይል ተብሎ ይመደብ ይሆናል።ሰሜን እዝ ግን አዛዥ ምክትል አዛዥ ምክትል አዛዥ ሎጂስቲክስ የሰው ሀይል በሙሉ አራቱም ኮሚቴ ከትግራይ ክልል ነበሩ።
አንድ ደረጃ ከሊዝ ዝቅ ብለን ሜካናይዝድ ስናይ መቶ በመቶ፣ የኢትዮጵያ የመካናይዝድ አዛዥ መቶ በመቶ እንዲሁም እግረኛ ክፍለ ጦር 80 በመቶ ከትግራይ ክልል ናቸው።
በአጠቃላይ የመከላከያ አመራር በአብዛኛው የተያዘው በማን እንደሆነ እነዚህ ለአብነት የተጠቀሱ አሀዛዊ መረጃዎች ቢያመለክቱም፣መከላከያ ምን ያህል በአንድ አካባቢ ቡድን ተይዞ ስለመቆየቱ ቀደም ሲልም በሚገባ ይታወቃል።
በአንድ ወቅት አንድ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ስብሰባ ላይ ለዘገባ ተገኝቼ ነበር።ስብሰባው የምክር ቤቱ የስራ ዘመን የሚጠናቀቅበት ነበር፤በወቅቱ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊም ነበሩ። በዚህ ስብሰባ ላይ የተገኙት አንድ የምክር ቤቱ አባል በዚህ ስብሰባ ላይ የተለያዩ አስተያየቶችን ሰጥተው ሊያጠናቅቁ ሲሉ ‹‹በመጨረሻም የመከላከያ አመራር ኢትዮጵያዊ መልክ እንዲኖረው እጠይቃለሁ ማለታቸውን አስታውሳለሁ።እኚህ ሰው ዛሬ በህይወት የሉም።ጥያቄያቸው ግን የመከላከያ አመራር ምን ያህል በአንድ አካባቢ ሰዎች እንደተሞላ ያመላከተ ነበር።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህን ሀቅ በአሀዝ ቁልጭ አርገው ማሳየታቸው ደግሞ መከላከያ ምን ያህል በአንድ አካባቢ ስብስቦች እንደተበተበ በሚገባ ለማስረዳት ያስቻለ ነው።በእዚህ አይነት ሁኔታ ለሚገኝ የመከላከያ ተቋም ተልእኮ መስጠትም ሆነ መከላከያውን በጥናት ላይ ባልተመሰረተ ሁኔታ አመራሮቹን መንካት ምን ያህል አደጋ ሊፈጠር እንደሚችል መገመት አይከብድም። የጁንታው አጠቃላይ ሁኔታ ሲታይ አንድ አንድ ብሎ ተለቅሞ የሚጸዳ አልነበረም።
መንግስት ከሁሉም በፊት በመከላከያ ተቋም ላይ ሪፎርም ለማድረግ መነሳቱ ትክክለኛ እርምጃ ነው።ለእዚህ እንዲረዳው ያካሄደው ጥናትም ትልቅ ግምት ሊሰጠው ይገባል።በጥናቱም የተቋሙ አመራር እና ቁልፍ ክፍሎች በማን እንደሚመሩ ለማወቅ እና በዚህም ላይ በመመስረት ተቋሙን በለውጥ ጎዳና ላይ ለማስኬድ ተችሏል።
ጁንታው በሀገር መከላከያ ሰራዊት ሰሜን እዝ ላይ ጥቃት መሰንዘሩን ተከትሎ በተወሰደው የህግ ማስከበር ዘመቻ መከላከያ ድል እንዲቀዳጅ ካስቻሉት ምክንያቶች ዋናውም ይሄው ሪፎርም ነው ማለት ይቻላል። መንግስት በጥናት ላይ ተመስርቶ በትእግስት የወሰዳቸው እርምጃዎች ጁንታውን ከእነ ሰንኮፉ ነቅሎ ለመጣል አስችሏል።በእርግጥም ሪፎርም።
ከዚህ በመነሳት አሁንም አንድ ጥያቄ አለኝ። “በቁምህ ማርያም ታቁምህ!” እንዲሉ መንግስት በነካካው እጁ አሁንም ሊሰራው የሚገባው አለ። እንደ ጀመረው ሊጨርሰው የሚገባ ተግባር እንዳለ ይሰማኛል።
ጁንታው የሀገር መከላከያን ብቻ አይደለም ተቆጣጥሮ እንዳሻው ሲያደርግ የኖረው።በኢኮኖሚው መስክም ብዙ ወንጀሎችን ፈጽሟል።ኢትዮ-ቴሌኮም ርስቱ አልነበረም አይባልም።ድርጅቱን በሪፎርም ስም ሰራተኛውን ቀንሶ ከአንድ አካባቢ በተሰባሰቡ ሰዎች ሞልቶት እንደነበር ይታወቃል።
ይህን ወደ ግሉ ዘርፍ ይዙር እየተባለ ሲጠየቅ የምትታለብ ላም ማን አሳልፎ ይሰጣል ተብሎ ይነገርለት የነበረን ተቋም ይመሩት የነበሩት ኃላፊ ቢኖሩም፤ ዶክተር ድብረ ጽዮን እንዳሻቸው ያደርጉት ነበር።ኢትዮጵያ ውስጥ የቴሌኮም አገልግሎት የመስጠት ኃላፊነት ያለበት ኢትዮ-ቴሌኮም ሆኖ ሳለ የመንግስቱ ቀኝ እጆች እነ እያሱ በርሄ የቴሌኮም መሳሪያ በህገወጥ መንገድ በማስገባት የቴሌኮም አገልግሎት ይሰጡ ነበር።እነዚህ ሰዎች በቁጥጥር ስር ዋሉ ተባለ፤ ተፈቱ፤ ወደ ውጪ ሀገር የሚሸሹቱም እንዲሸሹ ተደረገ።ነገሩ በዚያው ቀረ።ኢትዮ ቴሌኮምን አሳጡት የተባለው ገንዘብ ጉዳይ ምን እንደደረሰ እንጃ።
በጁንታው ዘመን በህገወጥ መንገድ የቴሌኮም መሳሪያ አስገብተው ሲሰሩ ተገኙ የተባሉ ሌሎች ግን መሳሪያውን እየተወረሱ ወህኒ በህግ ተጠይቀዋል።የጁንታው ቡድን ግን ከዚህም በላይ ወንጀል ሲፈጽም የተባለው ነገር የለም። ጁንታው በሰሜን እዝ ላይ የሰነዘረውን ጥቃት ተከትሎ የትግራይ ክልል ከተቀረው ክልል ጋር በስልክ መገናኘት ባይችልም መቀሌ ውስጥ ስልክ ነበር ይባላል።ይህ የሚያመለክተው ጁንታው የራሱ የስልክ አገልግሎት ያለው መሆኑን ነው።ይህን ማድረግ የሚያስችል የህግ አግባብ የለም።
በጁንታው የንግድ ድርጅቶች ሀገራችን እና የግሉ ዘርፍ የደረሰባቸው ጉዳትም ተዘርዝሮ የሚያልቅ አይደለም። ፕሮጀክቶች እና ሌሎች ትላልቅ ስራዎች ያለጨረታ ወይም በልክ በተሰፉ ጨረታዎች ይሰጡ የነበረው ለእነዚህ ድርጅቶች ነበር። ፕሮጀክቶቹን በተጋነነ ዋጋ ይወስዱም እንደነበር ይታወቃል።ይህ ብቻም ሳይሆን ፕሮጀክቶቹ መጠናቀቅ ካለባቸው የጊዜ ሰሌዳ በላይ ረጅም ጊዜ እንዲወስዱ እየተደረገ ከተያዘላቸው በጀት ብዙ እጥፍ እንዲወጣባቸውም ይደረግ ነበር።
ኩባንያዎቻቸው፣ የጁንታው አባላት እና ተላላኪዎ ቻቸው ከሀገሪቱ የመንግስት ባንኮች ተበድረው ያልመለሱት ገንዝብ ምን ያህል ከፍተኛ እንደሆነ ይታወቃል። የኢፈርት ድርጅቶች ከመንግስት ባንኮች ተበድረው መመለስ አልቻሉም እየተባለ እዳ ይሰረዝላቸው ነበርም ይባላል።በጋምቤላ በግብርና ኢንቨስትመንት ስም ተበድረው የጠፉት አነማን ናቸው? በአፋር ክልል አንድ ወረዳ ወረዳው ከምትሸከመው በላይ በርካታ ሆቴሎችን እንገነባለን ብለው ቦታ ወስደው ከቀረጥ ነጻ አስፈቅደው በተደጋጋሚ ከውጪ እቃ እያስመጡ የቸበቸቡትስ እነማን ናቸው?
በአጠቃላይ በኢኮኖሚው መስክ በተለያዩ ቁልፍ የኃላፊነት ቦታዎች ላይ በመቀመጥ እንዲሁም ተላላኪዎቻቸውን በቁልፍ የኃላፊነት ቦታዎች ላይ በማስቀመጥ የህዝብና የሀገር ሀብት እንደፈለጋቸው ሲያደርጉ ኖረዋል።
የጁንታው የንግድ ድርጅቶች የሀገሪቱን የግል ዘርፍና መንግስትን ክፉኛ ስለመጉዳታቸው ይታወቃል።ይህ እውነታ ነው፤ ጸሀይ የሞቀው ሀቅ ነው።በመሆኑም መንግስት በመከላከያ ተቋማት ላይ እንዳደረገው ያለ ጥናት በማካሄድ ጁንታው ምን ያህል ኢኮኖሚውን እንደጎዳው በአሃዛዊ መረጃ ታሳየን ዘንድ እንጠይቃለን።
እናም መንግስታችን ጉዳዩ “በቁምህ ማርያም ታቁምህ!” ነውና ኢኮኖሚው ላይ ያደረሱትን ጉዳት በአሀዛዊ መረጃ አሳየን።ጁንታው አብቅቶለታል፤ ቢያበቃለትም የሰራውን ግፍ ማሳየት ይገባል።ይህ ሲሆን ሌሎች ይህን አይነቱን ግፍ ከመፈጸም እንዲቆጠቡ ያስችላል። ስለዚህ ኢኮኖሚው ላይ የደረሰውን ጉዳትና ጉዳት ያደረሱትንም በአሀዛዊ መረጃ አሳየን፡፡
አዲስ ዘመን ታህሳስ 4/2013 ዓ.ም