ፍሬህይወት አወቀ
በአዲስ አበባ ከተማ ከሚጠቀሱ ዋነኛና አንኳር ችግሮች መካከል ጎልቶ የሚሰማው የመኖሪያ ቤት ችግር ነው። ብዙ ጊዜም አዲስ አበባ ላይ ቤት ያለው ሰው “እሱ የታደለ ነው” ሲባል ይደመጣል። ምክንያቱም ከመሰረታዊ ፍላጎቶች አንዱ የሆነውን መኖሪያ ቤት በአዲስ አበባ ከተማ ምድር ላይ በቀላሉና በተመጣጣኝ ዋጋ ማግኘት ፈታኝ ከመሆኑም በላይ ለብዙዎች የማይታሰብ የህልም እንጀራ እየሆነ በመምጣቱ ነው።
የመሰረተ ልማት ተደራሽነትና የአገልግሎት ሰጪ ተቋማት መስፋፋት፤ ሰዎች ከገጠርና ከከተማ ዳርቻዎች ወደ መሐል ከተማ እንዲመጡ ምክንያት ስለመሆኑ ይነሳል። ይህ ደግሞ በከተማ ያለውን የመኖሪየ ቤት ፍላጎት ከፍ በማድረግ በኪራይም ሆነ በግዥ የሚታሰበው የቤት ዋጋ እንዲንር የራሱ አስተዋፅኦ አድርጓል። በአዲስ አበባ ከተማ እና በክልል ከተሞች የሚስተዋለው የመኖሪያ ቤት ዋጋ መናርም ከከተሞች መስፋፋትና ከህዝብ ቁጥር መጨመር ጋር የመጣ መሆኑ ግልጽ ነው።
በአዲስ አበባና በክልል ከተሞች ዕለት ከዕለት እየጨመረ የመጣው የመኖሪያ ቤት እጥረትና የዋጋው መናር ከሰዎች ገቢ በላይ በመሆኑ ለትልቅ ፈተና ሲዳርግ ይስተዋላል። ይህ ለዜጎች ፈተና የሆነው የመኖሪያ ቤት ዋጋ መረጋጋት የሚቻለው እንዴት ባለ መንገድ ነው? የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን የቤቶች ልማትና አስተዳደር ቢሮስ ችግሩን እንዴት ይመለከተዋል? ብለን ላነሳነው ጥያቄ የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን የቤቶች ልማትና አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ አቶ ታደሰ ከበበ የሚከተለውን ሀሳብ አካፍለውናል።
በኢትዮጵያ የሚታየው የመኖሪያ ቤት እጥረትና የዋጋ ንረት በጥናት በተለየው መሰረት በከተማ ደረጃ እና በአከታተም ሂደት የሚገለጽ ነው። እንደሳቸው ማብራሪያ በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ውስጥ ያለው የከተሞች ዕድገት እጅግ ፈጣን መሆኑን ጥናቱ ያሳያል። ይህም በየዓመቱ በአማካይ ከአራት ነጥብ አምስት በመቶ በላይ ከተሞች እያደጉ ይገኛሉ። ነገር ግን የከተሞች አደረጃጀትና በከተሞች አካባቢ የሚኖረው የህዝብ ቁጥር ከሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ጋር ሲነፃፀር እጅግ በጣም ዝቅተኛ ነው ። በመሆኑም በሀገሪቱ በከተሞች አካባቢ የሚኖረው ህዝብ 22 እና 23 በመቶ የሚሆነው ብቻ ነው።
በከተሞች የሚታየው ይሄ ፈጣን ዕድገትና መስፋፋት ዕለት ከዕለት እየጨመረ ካለው የህዝብ ቁጥር ጋር የማይጣጣም ከመሆኑም በላይ የሚያስከትለው ጫና ቀላል ግምት የሚሰጠው እንዳልሆነ ይታመናል። የከተሞች መስፋፋት በተለያዩ የመሰረተ ልማት አገልግሎቶች ላይ ከሚያሳድረው ጫና በተለየ ሁኔታ በመኖሪያ ቤት ላይ የሚፈጥረው ቀውስ ከፍተኛ መሆኑን የገለፁት አቶ ታደሰ፤ የመኖሪያ ቤት እጥረትና የዋጋ ንረቱ ከዕለት ዕለት እየተባባሰ መምጣቱንም ይናገራሉ።
በሀገሪቱ ያለው የመኖሪያ ቤት ዋጋ እጅግ ከፍተኛ በመሆኑ አብዛኛው ማህበረሰብ የራሴ የሚለው የመኖሪያ ቤት የሌለው ነው ይላሉ አቶ ታደሰ ፤ በተለይም ዝቅተኛ ወይም መካከለኛ ገቢ ያለው የህብረተሰብ ክፍል መኖሪያ ቤትን በኪራይም ሆነ በሽያጭ በተመጣጣኝ ዋጋ በቀላሉ የማግኘት ዕድሉ የጠበበ መሆኑን ያመለክታሉ። አብዛኛው የከተማ ነዋሪ ለመኖሪያ ቤት ኪራይ የሚያወጣው ወጪ ከሚያገኘው ገቢ ከ60 እስከ 70 በመቶ መሆኑንም ጠቁመዋል። በተመሳሳይ ቤት ለመግዛትም ቢሆን የሚጠይቀው ወጪ በጥናቱ የተገኘውን ውጤት ዋቢ በማድረግ ነው የሚናገሩት።
እንደሳቸው ማብራሪያ በአሁኑ ወቅት ዜጎች በኪራይም ሆነ በግዥ ለመኖሪያ ቤት የሚያወጡት ወጪ ተመጣጣኝ አይደለም። ምክንያቱም ሰዎች ከሚያገኙት ገቢ ለመኖሪያ ቤት ማውጣት ያለባቸው 35 በመቶ ብቻ ሲሆን ይህም በዓለም አቀፍ ደረጃ ተቀባይነት ያለው መሆኑን አቶ ታደሰ ያስረዳሉ። አንድ ሰው በግዥም ይሁን በኪራይ ከሚያገኘው ገቢ 35 በመቶ ያህሉን ለመኖሪያ ቤት ቢያወጣ ጤናማ ነው ያሉት አቶ ታደሰ፤ ነገር ግን ከዚህ በላይ ካወጣ ከፍተኛ ጫና ከማሳደሩም በላይ ለትምህርት፣ ለጤና እንዲሁም ሌሎች የሚውሉ ወጪዎችን ዝግ እንደሚያደርጋቸው ይታመናል ሲሉ ያብራራሉ።
አቶ ታደሰ እንዳሉት ፤ በከተሞች የሚገኙ ዜጎች ምን ያህል ናቸው? ወይም ደግሞ በከተሞች ከሚገኙት ማሟላት ይችላሉ? የሚለውን ለመለየት ጥናት እየተደረገ ነው። ከዚሁ ጋር በተያያዘም በየክልል ከተሞች የሚገኙ ዜጎች ከሚያገኙት ገቢ ምን ያህሉን ለመኖሪያ ቤት ወጪ እያደረጉ እንደሆነ እና ምን ያህል ማውጣት እንዳለባቸው ለማስቀመጥ ያግዛል። ጥናቱም ዓለም አቀፍ ከሆነው ደረጃ በመነሳት የሀገሪቱን ነባራዊ ሁኔታ ከግምት አስገብቶ መሰረት መጣል የሚያስችል በመሆኑ በተያዘው በጀት ዓመት እየተከናወነ መሆኑን አመልክተዋል።
የቤት ኪራይና የሽያጭ ዋጋ በትላልቅ የክልል ከተሞች በተለይም የኢንዱስትሪ ፓርኮች በሚገኙባቸው የክልል ከተሞች አካባቢ ተመጣጣኝ አለመሆኑን መረጃዎች እንደሚያሳዩ የጠቆሙት አቶ ታደሰ፤ በእነዚህ ከተሞች አካባቢ የተደረጉ አጫጭር የዕቅድ ምልከታዎችና ሪፖርቶችም የመኖሪያ ቤት ዋጋ ተመጣጣኝ እንዳልሆነ አመላካች ነው።
በሀገሪቱ አሁን ያለው የመኖሪያ ቤት ዋጋ ዜጎች ካላቸው የመክፈል አቅም ጋር ፍፁም ያልተጣጣመና በዓለም አቀፍ ደረጃ ተቀባይነት የሌለው መሆኑን የገለፁት አቶ ታደሰ የመኖሪያ ቤት እጥረትና የዋጋ ንረቱ በተለይም በክልል ከተሞች እጅጉን የበረታ መሆኑን ያነሳሉ።
ይህ ከህብረተሰቡ ገቢ ጋር ያልተጣጣመውን የመኖሪያ ቤት ዋጋ ለማመጣጠንና እጥረቱን ለመቀነስ መንግስት የተለያዩ እንቅስቃሴዎችን ያደርጋል። ይሁን እንጂ ችግሩ ተቃሎ ትርጉም ያለው ለውጥ ሲመጣ አይታይም። ለዚህም ምክንያቱ መንግስት አማራጮችን ባለመጠቀሙ እና ተግባር ተኮር የሆነ ሥራ ባለመስራቱ እንደሆነ ባለሙያዎች ያነሳሉ። በመሰረታዊነት የቤት ችግር የሚፈታው ቤት በመገንባት ነው። ነገር ግን ትኩረት መደረግ ያለበት በማን ቢገነባና እንዴት ቢገነባ ችግሩን ማቃለል ይቻላል የሚለውን መመለስ ዋናው ጉዳይ መሆኑን አቶ ታደሰ ይጠቅሳሉ።
በሀገሪቱ የሚስተዋለውን የመኖሪያ ቤት እጥረት ለማቃለልና ዋጋውን ለማረጋጋት መፍትሔው ቤት መገንባት በመሆኑ በዚህ ዙሪያ የተለያዩ አማራጮችን መጠቀም የግድ የሆነበት ጊዜ ላይ ተደርሷል። በመሆኑም መንግስት የተለያዩ አማራጮችን ተጠቅሞ ቤቶችን ለመገንባት በእስትራቴጂክ ዕቅዱ ላይ ካካተታቸው ዋነኛ ጉዳዮች መካከል አንዱ መሆኑን ገልጸዋል።
ቤቱን ለመገንባት የተለያዩ አማራጮችን መጠቀም እንደሚገባ የጠቆሙት አቶ ታደሰ፤ በቤት ግንባታ ላይ የሚሳተፉ ተዋናዮች መንግስት፣ ግለሰቦች፣ መንግስትና ባለሀብት በጋራ ሆነው ቤቶችን መገንባት እንደሚቻል ያስረዳሉ። በዚህም ላይ መንግስትን ጨምሮ ቤት መገንባት የሚችሉ አካላት ሙሉ አቅማቸውን ተጠቅመው መገንባት እንዳለባቸው ያሳስባሉ።
መንግስት የሚገነባው ቤት በሽያጭም ይሁን በኪራይ እንደ አማራጭ መቀመጥ አለበት። የግል ባለሀብቶችም ከመንግስት ጋር በጋራ ሆነው ቤቶችን የሚገነቡበትን ሁኔታ ማመቻቸትም የግድ ነው። ከዚህ በተጨማሪም የተለያዩ እራሳቸውን የቻሉ ትላልቅ የልማት ድርጅቶችንም በቤት ልማት ውስጥ ማሳተፍና አማራጮችን መጠቀም አስፈላጊ መሆኑን ይገልጻሉ።
የተለያዩ አማራጮችን ተጠቅሞ ቤት መገንባት አስፈላጊ ነው። አማራጮች ሲሰፉ ፋይናንሱም በዛው ልክ ይሰፋል ፤ስለዚህ አማራጮችን በመጠቀም ከመንግስት ተበድረውና በራሳቸው ሀብት የሚገነቡ ባለሀብቶች ይበራከታሉ። አንድ ባንክ ብቻ ሳይሆን የግል ባንኮችን ጨምሮ ፍላጎት ያላቸው የፋይናንስ ተቋማትን ተሳታፊ ማድረግ ተገቢ መሆኑን ይመክራሉ።
የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽንም ይህን ተግባራዊ ማድረግ እንዲቻል የረጅም ጊዜ ዕቅድ አቅዶ እየሰራ መሆኑን ነው አቶ ታደሰ የተናገሩት።
ቤት ለመገንባት በሀገር ውስጥና በውጭ ያሉትን የፋይናንስና የግንባታ አቅምን አደራጅቶ መጠቀምና ተግባራዊ ማድረግ ያስፈልጋል። የቤቶች ልማት ስትራቴጂም የአስር ዓመት ዕቅዱ ይህንን ታሳቢ ያደረገና በመንግስት ተቀባይነት ያገኘ የመፍትሄ አቅጣጫ መሆኑን ያስረዳሉ።
ይሁንና በአሁኑ ወቅት ቤት ገንብቶ በመሸጥ ለህብረተሰቡ ማዳረስ የማይቻልበት ደረጃ ላይ ተደርሷል። በየትኛውም ዓለም እያንዳንዱን ዜጋ የቤት ባለቤት አይደለም። ነገር ግን በመንግስትም ይሁን በግሉ ባለሀብት መኖሪያ ቤት የማቅረብ ስራ ይሰራል። የሚቀርቡት ቤቶችም የተለያዩ አማራጮች ያላቸው ሲሆን በኪራይ ወይም በግዥ ዕድል መፍጠር ነው።
ከዚህ ጋር ተያይዞ ህብረተሰቡ ጋር ያለው አመለካከት የተዛባ ነው። ቤት ማለት መኖሪያ እንደመሆኑ በኪራይም ይሁን በግዥ የተገኘውን ቤት እንደራስ ማየት ተገቢ ነው። ነገር ግን ህብረተሰቡ ጋር ያለው አመለካከት ‹‹ካርታው በእኔ ስም ካልሆነ የኔ አይደለም›› የሚል ነው። ይሄ መቀየር አለበት። ሰው የሚኖርበትን ቤት በኪራይም ይሁን በሌላ ካገኘ ‹‹ያ ቤት የእኔ ቤት ነው›› የሚል አስተሳሰብ ሊኖረው ይገባል ።
ይህን አመለካከት ለመቀየር በተለይም የኪራይ ቤቶች በስፋት መኖር እንዳለባቸው አቶ ታደሰ አንስተዋል። ሆኖም ግን ከኪራይ ቤት ጋር ተያይዞ ሊሰመርበት የሚገባው የኪራይ ቤት መተዳደሪያ ግልጽ የሆነ መመሪያ ማዘጋጀት ነው። ይህም የሚያስፈልገው ቤት ተከራይቶ ከአንድና ሁለት ወር በኋላ ውጣ የሚባልበት ሁኔታ እንዳይፈጠርና በመመሪያና ውል እንዲታሰር ለማድረግነው። ውሉ ላይም ተከራዩ መች ገብቶ መች እንደሚወጣ እንዲሁም የኪራዩም ዋጋ የተተመነበት ሊሆን ይገባል በማለት አቶ ታደሰ ያስረዳሉ።
የኪራይ ቤት በውል የታሰረና የኪራዩ ተመን የታወቀ ከሆነ ተከራዩ ተረጋግቶ ‹‹ይህ ቤት ያኖረኛል፤ የእኔ ነው ብሎ›› ይቀመጣል። አሁን ያለው የሀገሪቱ ሁኔታ ግን ዛሬ ያከራየውን ነገ የማስወጣትና በፈለገ ጊዜ ዋጋ የመጨመር ነገር በመኖሩ ሰው ተረጋግቶ እንዳይኖርና የእኔነት ስሜት እንዳይፈጥር አድርጓል። ይህም የቤት ችግሩን ከማባባስ ባለፈ ሰዎች ተረጋግተው እንዳይኖሩ አድርጓል።
ስለዚህ ከችግሩ ለመውጣት የኪራይ ቤቶችን በስፋት ማቅረብና አማራጭ የተባሉትን በሙሉ መጠቀም ያስፈልጋል። ይህ ካልሆነ ግን ችግሩ ከዚህም በላይ ገዝፎ መውጫው የሚቸግር እንደሆነ አመልክተዋል። ለእያንዳንዱ ግለሰብ መሬት ሰጥቶ ቤት በራሱ አድርጎ ማስቀጠል በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን በየትኛውም አደጉ በሚባሉ ሀገሮች ያልተቻለ መሆኑን ያብራራሉ።
ህብረተሰቡ በሚሊዮኖች የሚሸጥ ቤት በተመጣጣኝ ዋጋ በኪራይ ከቀረበለት ገንዘቡን ሌላ ስራ ሊሰራበት ይችላል። ስለዚህ የኪራይ አማራጮችን መጠቀም የግድ ይላል። ህብረተሰቡ የራሴ ቤት ብሎ ተረጋግቶ እንዲኖር ታዲያ ዋናው መንገድ የህግ ማዕቀፍ ማዘጋጀት ነው። ቤት መገንባት ብቻውን መፍትሔ እንዳልሆነ ያስረዳሉ።
እንዲሁም የተገነባውን ቤት በአግባቡና ፍትሐዊ በሆነ መንገድ ማስተዳደር ሌላው ትልቁ ሥራ መሆኑን ያስረዳሉ። ለጊዜው ግን የተለያዩ አማራጮችን በመጠቀም ቤት መገንባት አስፈላጊ መሆኑነ ያምናሉ። በቀጣይ እነዚህ ችግሮች ተቃለው ዜጎች መኖሪያ ቤትን በኪራይም ሆነ በግዥ በቀላሉ ማግኘት እንዲችሉ የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን የቤቶች ልማትና አስተዳደር ቢሮ ጥናት እያጠና መሆኑን አመልክተዋል።
ጥናቱ በዋጋው ላይ መሰረት መጣል የሚችልና የአከራይ ተከራይን ሁኔታም በህግ አግባብ እንዲፈፀም የሚያደርግ በመሆኑ ህብረተሰቡን እየፈተነው ያለውን የመኖሪያ ቤት ችግር የሚያቃልል እንደሚሆን ይታመናል ብለዋል።
አዲስ ዘመን ታኅሳስ 03 /2013