መርድ ክፍሉ
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ከሚያወጣቸው መረጃዎች መገንዘብ እንደሚቻለው ዓለማችን በየቀኑ ለመኖር የማትመች እያደረጓት ያሉ ፈተናዎቿ በቁጥር እየጨመሩ ነው። እነዚህም ችግሮች መፍትሔ እንዲያገኙ ደግሞ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ከሚያደርጓቸው ድጋፎች በተጨማሪ የእያንዳንዱን የምድር ነዋሪ የበጎ ፈቃደኝነት አገልግሎት የሚሹ ሆነዋል።
ኢትዮጵያ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የመስጠት ባህል የነበራትና በፍጹም ወንድማማችነት ዜጎች የሚኖሩባት ችግራቸውን በጋራ በመተባበር የሚያሳልፉባት ሀገር ነች። ይህ በመስጠት የሚገለጸው በጎ ፈቃደኝነት የሀገሩ ባህል ነው። ልዩ ልዩ ዓይነት ልማድና ወግም ነበር።
ሲወልድ የግምዶ፣ ሲያዝን የዝን ብሎ ከመስጠት ጀምሮ ሲዘምት የስንቅ፣ ሲመለስ የደስታ፣ ሲሻር የሹመት አይደንግጥና ሲሾም የምስራች ብሎ እስከመስጠትም የረቀቀ ነው። ከነዚህ ሁኔታዎች አንፃር በመመልከት በአሁኑ ወቅት በተለያዩ ቦታዎች የበጎ አድራጎት ማህራት እየተቋቋሙ ይገኛሉ። ከነዚህም ውስጥ የፈረንሳይ ለጋሲዮን በጎ አድራጎት ማህበር ይጠቀሳል።
የፈረንሳይ ለጋሲዮን በጎ አድራጎት ማህበር የኮሙኒኬሽን ኃላፊ አቶ ቴዎድሮስ ክብካብ በፈረንሳይ ለጋሲዮን አካባቢ ነው ተወልዶ ያደገው። በተለያዩ ጊዜያት በአካባቢው የሚገኙ ድጋፍ የሚፈልጉ ሰዎችን ከጓደኞቹ ጋር በመሆን ሲረዳና ሲያስተባብር ቆይቷል።
ከስድስት ወራት በፊት ደግሞ የፈረንሳይ በጎ አድራጎት ማህበርን በመመስረት በኮቪድ 19 ምክንያት ረጂ የሌላቸውን ሰዎች ማዕድ በማጋራት ዘመቻ ሰፊ ስራዎችን አከናውኗል። ስለማህበሩ ስራ እንቅስቃሴ ከዝግጅት ክፍሉ ጋር ቆይታ አድርጓል። እንደሚከተለው አቅርበነዋል።
የማህበሩ ጅማሮና እንቅስቃሴዎቹ
የፈረንሳይ ለጋሲዮን አካባቢ ነዋሪ ቀደም ብሎም እራሱን አደራጅቶ የመኖር ልምድ ያለው ህዝብ ነው። የበጎ አድራጎት ማህበሩ ከተመሰረተ ስድስት ወራትን አስቆጥሯል። የአካባቢው ሰው ለመረዳዳት የግድ በማህበር መታቀፍ አያስፈልገውም። ለምሳሌ ለኩላሊት ህመምተኞች እንዲሁም ለሌሎች ታማሚዎች ከህብረተሰቡ እየተዋጣ እንዲታከሙ ይደረግ ነበር። ይህ በራሱ በነዋሪው ተነሳሽነት የሚሰሩ ስራዎች ናቸው።
ከሁለት ዓመት በፊት በፈረንሳይ ለጋሲዮን አካባቢ ማህበር ያስፈልጋል የሚል እንቅስቃሴ ነበር። ነገር ግን በወቅቱ በተወሰኑ ሰዎች የሚመሰረተው ማህበር የፖለቲካ ፓርቲ መሆን አለበት ሲሉ የተቀሩት ደግሞ ማህበሩ በሲቪክ ማህበር መደራጀት አለበት የሚል ሃሳብ አንስተው ነበር። የፈረንሳይ ለጋሲዮን ህዝብን በማህበር አጥሮ ማስቀመጥ ከባድ ቢሆንም የተወሰኑ ሰዎች በአካባቢው ስም ፖለቲካ ፓርቲ መስርቶ መንቀሳቀስ ፍላጎት ነበራቸው።
በአገሪቱ በተከሰተው የኮቪድ 19 ወረርሽኝ ምክንያት በተጀመረው የማዕድ ማጋራት መርሃ ግብር መሰረት ምን ምን ነገሮች መሰራት አለበት በሚለው የአካባቢው ነዋሪዎች ውይይት ተደርጓል። በቅርቡ የተመሰረተው የበጎ አድራጎት ማህበር ምንም አይነት የፖለቲካ አጀንዳ የሌለው ነው። ዋና ዓላማው ህብረተሰቡን በማሰባሰብ ደጋፊ ላጡ ሰዎች እርዳታ ማድረግ ነው። በኮቪድ 19 ማዕድ ማጋራት በተከናወነበት ወቅት ለሰዎች ገንዘብ እየተሰጠ ሳይሆን ላሳደጉን ሰዎች ጡረታ እየከፈልን ነው ተብሎ ነበር የሚታሰበው።
ድጋፍ ከሚደረግላቸው ሰዎች አብዛኛዎቹ እድሜያቸው የገፋ፣ በህመም ምክንያት አልጋ ላይ የዋሉ እንዲሁም በአካባቢው ተከራይተው የሚኖሩ አቅም የሌላቸው ሰዎችም ናቸው። የመረዳዳት ሃሳቡ ከመጣ በኋላ በተለያዩ ውጪ አገራት በሚኖሩ የአካባቢው ተወላጆች ገንዘብ የመሰብሰብ ስራ ተከናውኗል። በዚህም አንድ ነጥብ ሶስት ሚሊዮን ብር መሰብሰብ ተችሏል። ገንዘቡም ድጋፍ ለሚያስፈልጋቸው 470 ሰዎች እንዲከፋፈል ተደርጓል።
ይህን የድጋፍ ስራ እንደ መነሻ በመውሰድ በፈረንሳይ ለጋሲዮን አካባቢ ምን መሰራት አለበት የሚለው ላይ ትኩረት በመስጠት ውይይት ተደርጓል። ማህበሩ በትምህርት ዙሪያ ከመንግስት ትምህርት ቤት ጥሩ ውጤት አምጥተው ወደ ግል ትምህርት ቤት የሚገቡ ተማሪዎችን የመምረጥ፣ ድጋፍ የማድረግና የትምህርት እድሉን የሚያገኙበትን መንገድ የመፍጠር ስራ ማከናወን እና በመንግስት ትምህርት ቤት የሚገኙ ጎበዝ ተማሪዎችን ቅዳሜና እሁድ በበጎ ፈቃደኞች የማስጠናት ስራ አቅዷል።
ሌላኛው በስፖርት ዙሪያ ደግሞ ገንዘብ ከፍለው ስፖርታዊ እንቅስቃሴ መስራት ለማይችሉ ወጣቶች በአካባቢው ከሚገኙ ስፖርት መስሪያ ቤቶች ጋር በመነጋገር ስፖንሰር እንዲደረጉ የማድረግ ስራም ታስቧል። ለምሳሌ በአካባቢው የቴኳንዶ ስልጠና ከሚሰጥ ሰው ጋር በመነጋገር የተወሰኑ ወጣቶችን ለማሰልጠን ፈቃድ ተገኝቷል።
ሌሎችም በተመሳሳይ ቃል ገብተዋል። በፈረንሳይ ለጋሲዮን የሚኖሩ ወጣቶች ሊጫወቱበት የሚችል የኳስ ሜዳ አለ። ነገር ግን የኳስ መጫወቻ ሜዳው ምቹ አይደለም። ይህንን ሜዳ ለወጣቶቹ ምቹ ለማድረግ ከአዲስ አበባ ስፖርት ኮሚሽን ጋር በመተባበር አንደኛውን ሜዳ ወደ ስታዲየምነት ለመቀየር ስራዎች ተጀምረዋል። ሜዳውን ለመገንባት የግንባታ ፈቃድ ተጠናቆ ሜዳውን የመከለል ስራ ተጀምሯል።
በሙዚቃ ደግሞ በየካ ክፍለ ከተማ ወረዳ አንድ ውስጥ በሚገኘው ወጣት ማዕከል ውስጥ የሚገኙ ቢሮዎች ወደ ሌላ ቦታ እየተዘዋወሩ በመሆኑ ክፍት ቢሮዎችን በመጠቀም በፊት የነበረውን የኪነ ጥበብ እንቅስቃሴ ለመመለስ ሃሳብ አለ። በአካባቢው የሚኖሩ የሙዚቃ ፍቅር ያላቸው እቤታቸው ተቀምጠው ለሚገኙ ወጣቶች ለውድድርና ለልምምድ የሚሆኑ ቦታዎች ለማግኘት ጥረት እየተደረገ ነው። ቦታው ከተገኘ ድራማ፣ ውዝዋዜ እንዲሁም ለሚዘፍኑ ወጣቶች ትልቅ እድል ይፈጥራል።
በአካባቢው በሱስ ውስጥ የሚገኙ ወጣቶች እየተበራከቱ ይገኛሉ። ወጣቱ በግልፅ በሱስ ምክንያት ችግር ውስጥ እየገቡ ይገኛሉ። ወጣቱን ከሱስ ከማስወጣት በፊት ወደ ሱስ እንዳይገቡ የሚያስችሉ ስራዎች ተጀምረዋል። የመጀመሪያው የእግር ኳስ ሜዳውን ማስተካከል፣ የመዝናኛ ማዕከላትን ምቹ የማድረግ እንዲሁም ሌሎች ስራዎች እየተሰሩ ነው።
ማህበሩ ለአረጋውያንም የተለያዩ ስራዎችን ለማከናወን እንቅስቃሴ የጀመረ ሲሆን ቀደም ብሎ አረጋውያን የሚውሉባቸው ቦታዎች ነበሩ። በአሁኑ ወቅት ግን አረጋውያን አረፍ ብለው የሚጫወቱበትና እራሳቸውን የሚያዝናኑበት ስፍራ የላቸውም። ለዚህም የወጣት ማዕከላትን ለመጠቀም ዝግጅት እየተደረገ ይገኛል። አረጋውያኑ ለብቻቸው ሆነው የሚያወሩበት፣ የሚወያዩበትና የሚጫወቱበት ስፍራ ከተዘጋጀ በዛው ቦታ ላይ ደማቸውን የሚለኩበትና ህክምና የሚያገኙበት ሁኔታም ይፈጠራል።
ማህበሩ ድጋፍ የሚያደርግበት መስፈርት
ማዕድ ማጋራት ስራ በተጀመረበት ወቅት በፈረንሳይ ለጋሲዮን አካባቢ የሚገኙ ቀበሌዎች ውስጥ የማህበር ተወካይ ተዘጋጅቶላቸዋል። የተወከሉት ሰዎች በየቀበሌዎቹ በመሄድ ችግረኞችን ይለያሉ። የተለዩ ችግረኞችን ቦታው ድረስ በመሄድ የመመልከት ስራ ይከናወናል። በዚህም አስፈላጊ ድጋፍ ይደረጋል።
በትምህርት ዘርፉ ላይ ደግሞ ቅዳሜና እሁድ በሚሰጠው የድጋፍ ትምህርት ከተማሪዎችና ከትምህርት ቤቶች ጋር ቀረቤታ ይኖራል። በዚህም በተቀመጡ መስፈርቶች አስተማሪዎችንና ወላጆችን በማናገር ጎበዝና ድጋፍ የሚያስልጋቸውን ተማሪዎች የመለየት ስራ ይሰራል። በአካባቢው የሚገኘው የጤና ቡድን ህፃናትንም እያሰለጠነ ይገኛል። ህፃናቱ ስፖርት ከመስራት ባሻገር በትምህርታቸው ደካማ እንዳይሆኑም ክትትል ይደረጋል። ነገር ግን ልዩ ችሎታ ያላቸውን ወጣቶችና ህፃናት ችሎታቸውን ይዘው እንዲያድጉ በዋናነት ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራበት ነው።
የሙዚቃ ስራውንም በተጠናከረ መንገድ ለማስኬድና የእግር ኳስ ውድድሮችን ለማከናወን 20 ቡድኖች ምዝገባ አከናውነዋል። በአካባቢው የእግር ኳስ ውድድር ተካሂዶ የነበረው ከ23 ዓመት በፊት ነበር። ውድድሩ ሲዘጋጅ ምን ያክል የአካባቢው ወጣት ውድድሩን እንደሚፈልገው መረዳት ተችሏል። ለሙዚቃና ለስፖርቱ ውድድር ምንም አይነት መስፈርት አልተቀመጠም። የሙዚቃ ተሰጥኦ ላላቸው ልጆች ስልጠና የሚሰጡ በአካባቢው የሚገኙ ታዋቂ የኪነጥበብ ሰዎች ናቸው።
ማህበሩ ያጋጠመው ችግር
ማህበሩ የተለያዩ ችግሮች ያጋጠሙት ቢሆንም በአገሪቱ የሲቪክ ማህበራት እድገት አነስተኛ መሆን ዋነኛው ነው። ሲቪክ ማህበር ማለት ምንም አይነት ገንዘብ ሳይከፈል ለህብረተሰቡ የበጎ አድራጎት ስራዎች ላይ የሚሳተፍ ነው። ይህን አብዛኛው ሰው አይረዳውም። መንግስትም፣ የሃይማኖት ተቋማትም እንዲሁም የፖለቲካ ፓርቲዎችም ድጋፍ ማድረግ አለባቸው። በሌሎች አገራት ሲቪክ ማህበራት ፖሊሲ አርቅቀው ያጸድቃሉ። በኢትዮጵያ ግን እንደዚህ አይነት አሰራር የለም።
አብዛኛው ሰው ትርፍ ሰዓቱን በበጎ አድራጎት ስራ ማሳለፍ አይፈልግም። በትርፍ ሰዓት የሚሰሩ ሰዎች የተለየ ጥቅም ያገኛሉ ብሎ የማሰብም ሁኔታዎች አሉ። የማዕድ ማጋራት በተከናወነበት ወቅት እንኳን የተሰበሰበው ገንዘብ ሙሉውን ይሰጥ፣ በየወሩ ይደጎሙ እንዲሁም ሌሎች ክርክሮች ነበሩ። የበጎ አድራጎት ማህበራት መመስረት ህዝቡ እርስ በርስ ከመጋጨት ያድናል። አሁን የተሻሉ ህጎች በመሻሻላቸው በየአካባቢው ማህበራት እየተመሰረቱ ነው። በዚህም የኮቪድ 19 ወረርሽኝን መከላከል አስችሏል።
የአካባቢው ህዝብ ተነሳሽነት
የማዕድ መጋራቱ ሲጀመር በሁለት ዙር ነበር ድጋፍ የተደረገው። በመጀመሪያው ዙር በቁስ የሚፈልጉትን በቁስ፣ በገንዘብ የሚፈልጉትን በገንዘብ ነበር ድጋፉ የተደረገው። የሚረዱትን ሰዎች ለመምረጥ በተደረገው እንቅስቃሴ አሳዛኝ የሆነ ኑሮ የሚገፉ ሰዎች ተገኝተዋል። ለምሳሌ አንዷ ድጋፍ የተደረገላቸው አዛውንት የቤታቸውን በር አልፈው ከወጡ ቆይተዋል። በአካባቢው የሚገኙ ሰዎች ናቸው ምግብና የሚያስፈልጉ ነገሮችን ሲደግፏቸው የነበረው። ሌላም አካባቢ በተመሳሳይ ማየት የተሳናቸው ባለትዳሮች በራሳቸው ያለምንም ደጋፊ ህይወታቸውን ሲመሩ ነበር።
ድጋፉ በሚከናወንበት ወቅት በአካባቢው የሚገኝ ወጣት በደም ካንሰር ህመም ታማሚ ነበር። ለአረጋውያኑ ገንዘብ ከተሰጣቸው በኋላ ከተሰጣቸው ገንዘብ ላይ አዋጥተው ለልጁ ድጋፍ አድርገዋል። ይህ የሚያሳየው በችግር ውስጥ እንኳን ሆነው ሰውን የመርዳት ስሜት በአካባቢው ምን ያክል እንዳለ የሚያሳይ ነው። እንደዚህ አይነት በጎ ስራዎችን የሚያሳየው አደራጅቶ የሚመራ ከተገኘ ህብረተሰቡ እርስ በርስ ለመደጋገፍ ፈቃደኛ መሆኑን ነው።
በተመሳሳይ በአካባቢው ተከራይተው የሚኖሩ አንዲት አረጋዊት ሴት የሚኖሩበትን ቤት ኪራይ ለሁለት ወራት አልከፈሉም ነበር። ማህበሩ የሰጣቸውን 25 ኪሎ ጤፍ ያከራያቸው ሰው ተቀበላቸው። በቦታው በመሄድ አከራዩን የማህበሩ አባላት ባናገሩበት ወቅት ሰውየውም በተመሳሳይ በጣም ችግረኛ ነበር። እንደዚህ አይነት ችግሮችን ለመወጣት የግድ የበጎ አድራጎት ማህበራት መብዛት አለባቸው።
በቅርቡ በፈረንሳይ ለጋሲዮን ተከራይታ የምትኖር ሴት በእሳት አደጋ ልጇን ማጣቷ የሚታወስ ነው። ተጎጂዋ መኖሪያ ቤት ድረስ በመሄድ የማስተዛዘን ስራ ተሰርቶም ነበር። በወቅቱ ማህበሩ የ30 ሺህ ብር ድጋፍ ያደረገ ሲሆን መኖሪያ ቤቷ ስለተቃጠለ ሰው ቤት ነበር ለቅሶ የተደረሰችው። የፈረንሳይ ለጋሲዮን ነዋሪ ያለውን በማዋጣት ለተቸገረ ድጋፍ የሚያደርግ መሆኑን በወቅቱ አሳይቷል። የሴትየዋን የቤት ችግሯ እንዲፈታላት ወረዳውን ቦታ በመጠየቅ በተገኘው ቦታ ላይ በብሎኬት ግንባታ እየተከናወነ ይገኛል።
በቀጣይ የማህበሩ እቅድ
የፈረንሳይ ለጋሲዮን ህዝብ በፖለቲካ ምክንያት ከፍተኛ በደል ደርሶበታል። በዚህም አካባቢው በመሰረተ ልማት ያደገ እንዲሆን ማህበሩ ለመስራት እቅድ አለው። አካባቢው ሌሎች ሰፈሮች በለሙበት ልክ የለማ ባለመሆኑ ማህበሩ የመንግስት አካላት ለአካባቢው ትኩረት እንዲሰጡ ጥረት ያደርጋል።
ሌላኛው በፈረንሳይ ለጋሲዮን ትልቅ የማህበረሰብ ትምህርት ቤት የመገንባት እቅድ አለ። ትምህርት ቤቱን ሁሉም የሃይማኖት ተቋማት ገንዘብ አዋጥተው እንዲሰሩት ለማድረግ ዝግጅት ተደርጓል። በተጨማሪም ለወጣቱ የስራ እድል ለመፍጠር የሚያስችሉ የልማት ስራዎች ለማከናወን ታስቧል። በቀጣይ በገንዘብ የሚደረጉ ድጋፎችን በመቀነስ በዘላቂነት የሚቋቋሙበትን መንገድ ለመፈለግ እቅዶች ተዘጋጅተዋል።
በእግር ኳስና በኪነጥበብ ዘርፉም በተመሳሳይ ውጤታማ ወጣቶችን ለመፍጠር ሃሳብ አለ። ወጣቱ እራሱን የሚቀይርበት ሁኔታ ይፈጠራል። ለማህበሩ የተለያዩ ባለሀብቶች ድጋፍ የሚያደርጉ ቢሆንም በቀጣይ በአካባቢው በሚሰራው የእግር ኳስ ሜዳ ውስጥ ካፌዎችን በመክፈት የገቢ ምንጭ ለማግኘት ታስቧል።
በበጎ አድራጎት ስራው ላይ በፈቃደኝነት የሚንቀሳቀሱ ከ60 በላይ ሰዎች ይገኛሉ። የመጀመሪያውን የእርዳታ ስራ ለማከናወን በአብሮ አደግ ማህበር እሳቤ ነበር የተጀመረው። ነገር ግን በአሁኑ ወቅት በበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ኤጀንሲ ለመመዝገብ ስራዎች ተጀምረዋል።
አዲስ ዘመን ታህሳስ 2/2013