ለምለም መንግሥቱ
ምድረግቢው ባለጉዳይ አያጣውም ።ሁሌም በሰዎች የተሞላ ነው ።ዶሴ በእጁ ይዞ በግቢው ከላይ ታች የሚራወጠው ባለጉዳይ ጉዳዩን ቶሎ ጨርሶ ለመሄድ በምልጃም፣ በጉርሻም ጥረት ሲያደርግ ይስተዋላል። ከችኮላው ብዛት ሁሉም የራሱን እንጂ የሌላውን አያይም ።አያዳምጥም። ብዙዎች ሲሉ እንደሚሰማው ትዕግሥት የሚፈተንበት ቦታ ነው። በለስ የቀናው ካልሆነ መመላለስ ግድ ነው። አንዱ ስለሰነድ መጥፋት፣ሌላው ባልተገባ መንገድ ስለመስተናገዱ፣ብቻ ብዙ ቅሬታዎች የሚሰማበት ቦታ ነው ።በዙሪያው የሚያንዣብቡ ‹‹እናስጨርሳለን›› ባይ ደላሎች ወከባ በመፍጠር ባለጉዳዮችን ግራ በማጋባትና ለተቋሙም አገልግሎት እንቅፋት መሆናቸው ተደጋግሞ ይሰማል ።የህገወጥ ሰንሰለት በማበጀት ህጋዊውንም ሰው በማሳሳት ይታወቃሉ፡፡
በአብዛኛው ወደዚህ ተቋም የሚመላለሰው ከመኖሪያና ከንግድ ቤት ጋር የተያያዘ ጉዳይ ለማስፈጸም ሲሆን፣አንዱ የይዞታ ማረጋገጫ፣ሌላው የውርስ፣የስጦታ፣የዕዳና ዕገዳ… ብቻ እንደ ባለጉዳዩ ከጎጆ ጋር የተያያዙ ጥያቄዎች ይስተናገዳሉ፡፡መንግሥትም በተቋማቱ የአገልግሎት አሰጣጥ ላይ ያለውን ክፍተት በማጥራት የተሻለ አሰራር ለመዘርጋት ለተወሰኑ ጊዜያቶች አገልግሎቱን ማቋረጡ ይታወሳል። ከህዳር 11ቀን 2013ዓ.ም ጀምሮ ግን አገልግሎቱ ተጀምሯል፡፡ቀደም ሲል ይነሱ የነበሩ አገልግሎቶች ስለመፈታታቸውና አሰራሩም ስለመሻሻሉ ለመተቸት ጊዜው ገና ቢሆንም ተገልጋዩ ግን እንደወትሮው በምድረግቢው ዶሴውን ይዞ ከወዲያ ወዲህ እያለ ይገኛል፡፡
አገልግሎቱ ከሚሰጥባቸው አንዱ በሆነው በአዲስ አበባ ከተማ በንፋስልክ ላፍቶ ክፍለከተማ የመሬት ይዞታ ምዝገባና መረጃ ኤጀንሲ ቅርንጫፍ ጽህፈትቤት ተገኝቻለሁ፡፡ከላይ ታች የሚለውን ባለጉዳይ ሳስተውል የዱላ ምርኩዝ ይዘው የሚንቀሳቀሱ ባለጉዳዮች ሁሉ ሳይቀሩ ሲደክሙ ነበር የታዘብኩት፡፡‹‹መጀመሪያ መቀመጫዬን›› እንዳለችው ጦጣ አይነት ገንዘቡንና አቅሙን አስተባብሮ ደክሞ የቀለሰው ጎጆው በመንግሥት እውቅና አግኝቶ ህጋዊ እንዲሆንለት ነው ይህ ሁሉ ድካም፡፡
እኔም ወደዚህ ተቋም ጎራ ማለቴ ሰው ለጎጆ ወይም ለማረፊያ ምን ያህል ዋጋ እንደሚሰጥ ለማየትና ለእናንተ አንባቢዎቼም ለማካፈል ነው፡፡ከተቋሙ ሳልወጣ አገልግሎቱን ፈልገው ወደ ተቋሙ ከሄዱት መካከልም አንዲት በግምት 70 ዓመት የሚሆናቸው ጉዳያቸውን ለማስፈጸም ከወዲህ ወዲያ ሲሉ ከነበሩ እናት ጋር ቆይታ አደረኩ፡፡እጅ ነስቼ ተዋወኳቸው። ወይዘሮ ለምለም አስማማው ብለው ተዋወቁኝ፡፡ጉዳያቸውንም ጠየኳቸው፡፡ የይዞታ ማረጋገጫ ሰነድ ለማግኘት በሥፍራው መገኘታቸውን ነገሩኝ፡፡
ወይዘሮ ለምለም ቀደም ሲል የያዙት የቤት ካርታ ይቀየራል ስለመባሉ እንጂ ጉዳዩ ግልጽ ሆኖላቸው አልነበረም በሥፍራው የተገኙት፡፡በስሚስሚ ስለሆነ የተሟላ መረጃም የላቸውም፡፡ጠይቀው የሚሏቸውን ለመፈጸም ነው የተዘጋጁት፡፡ከዚህ በኋላ ቤት ለመስራት የገንዘብም ሆነ የጉልበት አቅም የላቸውም፡፡በመሆኑም ያላቸውን እንዳያጡ ህጋዊ ሆነው ለመገኘት ለመረጃዎች ጆራቸውን ክፍት አድርገው ያዳምጣሉ። እውነታውን ለማጣራትም ደከመኝ ሳይሉ በቦታው ተገኝተዋል፡፡
ወይዘሮ ለምለም በንፋስልክ ላፍቶ ክፍለከተማ ወረዳ አንድ ጀሞ አንድ ተብሎ በሚጠራው የጋራ መኖሪያቤት ውስጥ የሚኖሩ ሲሆን፣በ2002ዓ.ም የዕጣ ዕድለኛ ሆነው ነው ቤቱን ያገኙት፡፡ቤታቸው ስቱዲዮ የሚባለው ባለአንድ ክፍል ነው፡፡ከአንድ ልጃቸውና ሁለት የልጅ ልጆቻቸው ጋር ነው የሚኖሩት፡፡ለቤተሰባቸው በቂ አይደለም፡፡ቤቱ ቢጠባቸውም የቤት ባለቤት መሆናቸውን እድለኛ እንደሆኑ ይቆጥሩታል። እርሳቸው በ2007ዓ.ም ቤት ለማግኘት ሲመዘገቡ ቤት ለመግዛት የነበራቸው የገንዘብ አቅም አነስተኛ ስለነበር ነው በስቱዲዮ የተወሰኑት፡፡ የወጣትነት ጊዜያቸውን ያሳለፉት የአሰብ ወደብ አገልግሎት በኢትዮጵያ ሥር በነበረበት ጊዜ አሰብ ውስጥ ነበር ።አሰብ ሲኖሩ በሰው ቤት ተቀጥረው ከመሥራት ጀምሮ ብዙ የኑሮ ውጣ ውረዶችን አሳልፈዋል። ከብዙ ድካም በኋላ የመኖሪያ ቤት ሰርተው፣ትዳር መስርተው፣ልጆች አፍርተው፣በወደቡ ላይ በጽዳት አገልግሎት ሥራም አግኝተው የተረጋጋ ኑሮ ላይ እያሉ ነበር ድንገት ያልተጠበቀ ነገር የገጠማቸው። እንዲህ እያጫወቱኝ በመካከል በትዝታ ወደ ኋላ ወጣትነታቸውን ያሳለፉበትን በምናባቸው በማስታወስ በሀሳብ ለደቂቃዎች ከእኔ ጋር አልነበሩም ።አዎ ግማሽ የሚሆነውን ዕድሜያቸውን ያሳለፉበት ያውም ሀብት ያፈሩበትን በቀላሉ መዘንጋት ከባድ ነው፡፡
ወይዘሮ ለምለም ቤት ንብረታቸውን ጥለው ከሚኖሩበት አሰብ እወጣለሁ ብለው አንድም ቀን አስበው አያውቁም፡፡ የታሪክ አጋጣሚው ከቀለሱት ጎጆ አውጥቶ በመጠለያ ውስጥ እንዲኖሩ አስገድዷቸዋል፡፡ሳሎን፣መኝታቤት፣ኩሽና ያለው የተሟላ ጎጆ የነበራቸው ሴት ብዙ ህዝብ በሚኖርበት ባልተመቸ ሁኔታ አራት ልጆቻቸውን ይዘው ከነባለቤታቸው ለዓመታት በመጠለያ ውስጥ ለመኖር ተገደዋል ።እርሳቸው እንደሚሉት መጠለያ ከዝናብ፣ፀሐይና ብርድ ለመከላከል ካልሆነ የግል ህይወት አይታሰብም፡፡አንድ ጎጆ ውስጥ ተከልሎ በአንድ ጊዜ ደግሞ ሰፊ ቁጥር ካለው ሰው ጋር መኖር ከባድ እንደሆነ መገመት አያዳግትም። የቀለሱት ጎጆ መጠለያ ብቻ ሳይሆን ዋስትናቸውም ነበር፡፡
ወይዘሮ ለምለም ተጠልለው ይኖሩበት በነበረው ጃንሜዳ ተብሎ በሚጠራ አካባቢ አትክልትና ፍራፍሬ በመነገድ የዕለት ኑሮአቸውን መምራት ብቻ ሳይሆን ልምዱ በሌላቸው ንግድ ውስጥ መግባታቸው ሥራንም ሥላስተማራቸው ከመጠለያ ወጥተው አቃቂ ቃሊቲ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ የግለሰብ ቤት ውስጥ በአቅማቸው ተከራይተው መኖር ጀመሩ። የኪራይቤቱ ከጊዜያዊ መጠለያ የተሻለ ቢሆንም እንደራስ የሚያዙበት አለመሆኑም ምቾት አይሰጥም። ኪራይ የሚጨምርበትም ጊዜ ስለማይታወቅ ነፃ መሆን አይቻልም፡፡ እንዲህ ያለው የወይዘሮ ለምለም ውጣ ውረድ ያበቃው 2002ዓ.ም ላይ የጋራ መኖሪያ የዕጣ ዕድለኛ ከሆኑ በኋላ ነበር ።ቤቱን የተመዘገቡት መጠለያ ሆነው ስለነበር የዕጣ ዕድለኝነታቸው በመጠለያ ያሳለፉትን ጊዜ ያስታውሳቸዋል ።በዕድሜ በገፉበት ወቅት የግላቸውን ጎጆ በማግኘታቸው የዕድለኝነት ስሜት ይሰማቸዋል፡፡
እንደወይዘሮ ለምለም ሁሉ ለጎጆ ትልቅ ዋጋ የሚሰጡት የንፋስልክ ላፍቶ ክፍለከተማ የመሬት ይዞታ ምዝገባና መረጃ ኤጀንሲ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሉሉ ገብረማርያምም በ1990ዎቹ ውስጥ ጎጆአቸውን ለመቀለስ ከመንግሥት የመሥሪያ ቦታ ለማግኘት የነበረውን ውጣ ውረድ፣መሬቱም ከተገኘ በኋላ ለግንባታው ገንዝብ ለማግኘት ብዙ ፍላጎትን በመቀነስ ያደርጉ የነበረውን ጥረት ያስታውሳሉ። የያኔው ድካማቸው ግን ለዛሬ እንደጠቀማቸው ይገልጻሉ፡፡ የጎጆ ጉዳይ ቅድሚያ የሚሰጠው እንደሆነም ይናገራሉ። በተለይ በዚህ ወቅት ከኑሮ ውድነቱ ጋር በተያያዘ በኪራይቤት ውስጥ መኖር ከባድ ነው። የመኖሪያ ቤት እጥረትን ሙሉ ለሙሉ ማስወገድ ባይቻልም ዘመናዊ አሰራር በመከተል ችግሩን መቅረፍ ይቻላል ይላሉ። ተቋማቸው እያከናወነ ባለው የይዞታ ማረጋገጫ አገልግሎት ፍትሀዊ የሆነ ክፍፍል እንዲኖር የሚያስችል እንደሆነ ይገልጻሉ። ይዞታን በማረጋገጥ ሂደት አላግባብ የተያዘ መሬትንና ክፍት ቦታን በመለየት ወደ መሬት ባንክ እንዲገባ በማድረግ ጥቅም ላይ ለማዋል የሚስችል አሰራርን ለመዘርጋት ያግዛል፡፡
እንደ አቶ ሉሉ ማብራሪያ 90 በመቶ የሚሆነው የተቋማቸው ሰራተኛ በኪራይ ቤት ውስጥ ነው የሚኖረው ።ተመሳሳይ ሁኔታዎች በሌሎችም በስፋት ይስተዋላሉ ።አሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ የመኖሪያቤት ፍላጎት ሰፊ ነው፡፡ፍላጎትና አቅርቦት አልተጣጣመም ።የመረጃ አያያዝን በማዘመንና ፍትሐዊ አሰራርን በመዘርጋት ችግሩን መቅረፍ የሚቻልበትን መንገድ ማመቻቸት ግን ይቻላል ይላሉ፡፡
ጎጆ መሰረታዊ ከሚባሉ አስፈላጊ ነገሮች ውስጥ እንደሆነ አስረጅ አያስፈልገውም ።ሰዎች ተከራይተውም ሆነ በግል ጎጆአቸው፣ጊዜያዊ መጠለያን ጨምሮ ከዝናብና ብርድ በሚከላከል እንደነገሩ በተሰራ ቤት ውስጥ ይኖራሉ፡፡ በአጠቃላይ ለጎጆ ያለው ግምትና ፍላጎትን በተመለከተ የማህበራዊ ሳይንስ ባለሙያና የሥነልቦና አማካሪ ብሌን ተዋበ ሙያዊ ሀሳባቸውን አካፍለውናል፡፡
ባለሙያዋ ብሌን እንዳሉት ሰዎች በጫካ ይኖሩ በነበረበት ዘመንም የራሴ ነው ፤የግሌ ነው፤ እኔን የሚገልጽ ቦታ ነው፡፡በሥፍራው በተደጋጋሚ በመገኘት የራሳቸው እንደሆነ ለማረጋገጥ ጥረት ማድረግ፣የራስ የሆነ ነገርን የመፈለግ ዝንባሌን የሚያሳዩ ናቸው ።ሰዎች ምቾት የሚሰማቸው የእኔ ነው በሚሉት ቦታ በመሆኑም ጭምር ነው ።አሁን በምናቀው ደረጃ የሚገኘው መኖሪያ ቤት ወይንም ጎጆ ግንባታ ከጥንት የመጣ ነው ማለት ይቻላል። መጠለያ ወይንም ጎጆ ከሰዎች ተፈጥሮና አኗኗር ጋር የተያያዘ እንደሆነም ጥናቶች ያመለክታሉ፡፡
ሌሎች ሰዎች ሊጋሯቸው የማይፈልጓቸው ነገሮች ሲኖሩ በተከለለ ቦታ መፈጸም ይፈልጋሉ የሚሉት ባለሙያዋ በጎዳና ላይ የሚኖሩ ሰዎች እንኳን ቢሆኑ በተደጋጋሚ የሚያድሩበትን ፣የሚውሉበትንና የሚገ ኙበትን የእኛ ነው፡፡ ወይንም የእኔ ነው እንደሚሉ ይገልጻሉ፡፡ ይሄ ለራሳቸው የሰጡትን እይታና ግምትም እንደሚያሳይ ይናገራሉ፡፡ጎጆን አብዝቶ መፈለግ ሰዎች በአኗኗር ዘይቤያቸውና በተፈጥሮም የራስ የሆነ ነገርን ከመፈለግ የመጣ መሆኑን ይናገራሉ።
ሰዎች ይህን ፍላጎታቸውን ማሟላት የሚችሉበት ጎጆ ባይኖራቸው ምን ይሰማቸዋል ለሚለው ጥያቄም ባለሙያዋ እንዳብራሩት በማህበሩ ዘንድ የሚሰጣቸው ግምት ያነሰ ሆኖ እንዲሰማቸው፣በመንግሥትም ደረጃ የዚህ መንደርና ቤት ነዋሪ ነው የሚል ማረጋገጫ አለማግኘት የስነልቦና ጫና ሊያሳድርባቸው ይችላል ።መጠለያ ካላቸው ሰዎች እራስን አሳንሶ ማየት፣ሊፈጠር ይችላል፡፡እንዲህ ያለው ተጽዕኖ ሰዎችን ድባቴ ለሚባለውና ለጤናማ ማህበራዊ ግንኙነት ችግር ለሥነልቦና መረበሽ ሊያጋልጣቸው ይችላል ።ይህ ሲባል ግን ቤት አልባ ሆነው ኑሯቸውን በጎዳና ላይ ያደረጉ ውጤታማ የሆኑ የማህበረሰብ ክፍሎች የሉም ማለት እንዳልሆነም ባለሙያዋ ያስረዳሉ ።በአመዛኙ ግን ሰዎች የራሳቸው የሆነ ጎጆ ባለማግኘታቸው ለከፋ ችግር እንደሚጋለጡ ጥናቶች ያመለክታሉ፡፡
እንደ ባለሙያዋ ማብራሪያ እራስን ማግለሉ፣ድብርቱ የሥነልቦና ጫና ሲበረታ ለተለያየ ሱስ መጋለጥ ይኖራል። ችግሩ በህጻናት ላይ ይበረታል ። የህፃናቱን የከፋ የሚያደርገው በቀጣይ ህይወታቸውም ላይ የሚያሳርፈው ጫና ከፍተኛ በመሆኑ ነው፡፡ባለሙያዋ ጎጆን በተመለከተ የሥነልቦና አገልግሎት በሚሰጡበት ወቅት ያጋጠማቸውንም ልምዳቸውን እንዲህ አካፍለውናል፡፡
ሰዎች መሠረታዊ የሆነው የጎጆ ፍላጎታቸው ቢሟላላቸውም ።ስለጎጆው ጥራት ይጨነቃሉ፡፡ህፃናት ላይ ደግሞ ጎልቶ ይስተዋላል ።ከትምህርት ቤት እና ከአካባቢ ጓደኞቻቸው ስለአኗኗራቸውና ስለቤታቸው ሁኔታ ሲወያዩ ወይንም አንዱ ስሌላው የቤት ሁኔታ ሲረዳ አነስተኛ ቤት ያለው ልጅ እርሱ ከጓደኛው ባነሰ በዝቅተኛ ቤት ውስጥ መሆኑን ሲረዳ ለከፍተኛ የሥነልቦና ጫና ይጋለጣል። በሙያቸው እንዲህ ያሉ አጋጣሚዎች መኖራቸውን አስተውለዋል፡፡ከዚህ አንጻር ጎጆ የሚጠለሉበት፣ግላዊ ክንውናቸውን የሚፈጽሙበት ብቻ ሳይሆን ለሌላው ዝቅተኛ መሆናቸውን አጋልጦ የሚሰጥ አለመሆኑን ማረጋገጥ ይፈልጋሉ፡፡
ሥነልቦናንም የሚገነባ ጭምር እንደሆነ መገንዘብ ይቻላል፡፡ ጎጆን በተመለከተ በማህበረሰብ ውስጥ የሚስተዋለው ውድድር በተለይ ህጻናቱና ወጣቶች ላይ አሉታዊ ጫና በማሳደር ጎልቶ ይታያል ።‹‹ጎጆ ሥነልቦና ላይ የሚፈጥረውን ጫና ስንመለከት ሰዎች ምንም አይነት ቤት ቢኖራቸው የእኔ ቤት ነው እኔ የምከለልበት ቤት ነው የሚል አመለካከት ካላዳበሩና አምነው ካልተቀበሉ በስተቀር ምንም መጠለያ ቢኖራቸው ጎጆ ያለው ሰው ሥነልቦና ወይንም ጤናማ አስተሳሰብ ላይኖራቸው ይችላል››በማለት የሚያስረዱት ባለሙያዋ ሰዎች መጠለያ ስላላቸው ብቻ ይበቃቸዋል ።ለጥራቱ መጨነቅ የለባቸውም የሚል አስተሳሰብ መኖር አለበት ብለው አያምኑም፡፡ለጥራት ትኩረት መስጠት ተገቢ ነው ይላሉ፡፡
የተሻለ ነገር ፍለጋ ከኑሮ እድገት ጋር የሚመጣ መሆኑንና በሂደትም መሻሻል እንዳለበት ይገልጻሉ፡፡መሻሻሎች እየተፈጠሩ እስኪሄዱ ግን ሰዎች ቢያንስ ጎጆ ካላቸው አምነውና ተቀብለው ህይወታቸውን ሊመሩ እንደሚገባ ይመክራሉ ።እርሳቸው እንዳሉት የሰው ልጅ በአንድ ነገር ላይ ብቻ ሳይሆን ጤናውን፣መንፈሳዊ ህይወቱን፣ኑሮውን፣እንዲሁም ማህበራዊ ግንኙነቱን ሚዛናዊ በሆነ መንገድ ጠብቆ ኑሮውን መምራት ይኖርበታል፡፡
ጎጆ ገመና ከታች ከመሆን ባለፈ ቋሚ ሀብት በመሆኑ ትልቅ ዋጋ ይሰጠዋል ።ሰዎች አቅማቸው በደከመ ጊዜ ወይንም ደግሞ መንቀሳቀስ የማይችሉበት አጋጣሚ ቢፈጠር ጎጆ ካላቸው ይረጋጋሉ ።ዛሬ ለከፋ የጤና ችግር የተጋለጡና ከፍተኛ ህክምና የሚያደርጉ ሰዎች ቤታቸውን በዋስትና በማስያዝና ሸጠው በመለወጥ ለጊዜውም ቢሆን የሰው እጅ ከማየት ይድናሉ፡፡
አዲስ ዘመን ህዳር 26 ቀን 2013 ዓ.ም