እኛ ሰዎች እኮ እንዲሞላልን የምንጎድል ጉዶች ነን። ሰማዩ ሲገልጥ አይናችንን ገልጠን ከጎጇችን እንሾልካለን። ከዚያስ? ላይ ታች ስንል ይመሽብናል። ሲመሽ ገብትን እንተኛለን። ማለዳ ደግሞ ማልደን እንነሳልን፤ ተመሳሳይ የህይወት ዑደት ለመቀጠል። አእምሯችንና አካላችን ዕረፍት ይሻል። ግን በየት በኩል? “አንደኛዬን ስሞት አርፈዋለው” ብለን ተራቾችም አይደልን። ለነገሩ አይፈረድብንም፤ የያዘን ይዞን ነው።
መኖር በየመሃሉ አካልና አእምሮን ሌላ ዐውድ ውስጥ በመክተት ዘና ማድረግን ይፈልጋል። እንዲህ ያለው ሂደት መዝናናት ይባላል። መዝናናት ከተለመደው ተግባራችን ተላቀን እፎይ እያልን፣ አእምሯችንን አሳርፈን መንፈሳችንን የምናድስበት እና አካላችንን የምናፍታታበት በሳቅ ጨዋታ ሜዳ የሚከወን ተግባር ነው። ብዙዎቻችን ግን የማይሞላ ኑሮ እንዲሞላልን ስንኳትን ከዚህ በረከት ጎድለናል። ተነቃቅተን በአዲስ መንፈስና ብርቱ ጉልበት በስራችን ላይ እንድንገኝ ታስቦ የተበጀልንን የዓመት ፈቃድ እረፍት እንኳን በገንዘብ እንዲቀየርልን የምንጠይቅ ምስኪኖች ነን።
መፃህፍትን በማንበብ፤ የእግር ጉዞ በማድረግ፤ ጊዜ ወስዶ ከጓደኛ ጋር በመጫወት፤ ሙዚቃ በማዳመጥ፤ በማንጎራጎርና በመወዛወዝ፤ ስፖርታዊ ውድድሮችን በማየት፤ ቲአትርና ፊልም በመመልከት፤ የእግር፣ የእጅ፣ የጠረጴዛና የቅርጫት ኳስ በመጫወት፤ ዋና በመዋኘት፤ ቀላል የአካል እንቅስቃሴዎችን በማድረግ፤ ታሪካዊ ቦታዎችንና ቅርሶችን መጎብኘት፤ በተለያዩ ባህላዊ ክብረ በዓሎች ላይ መሳተፍ፤ አዝናኝ የቴሌቭዥን ፕሮግራሞችን በመከታተል፤ አዲስ አካባቢን በመጎብኘት እና ወዳጅ ዘመድን በመጠየቅ አእምሮንና አካልን ዘና ማድረግ ይቻላል።
እንዲህ ላሉ ተግባራት በቂ ጊዜ ስንመድብ መንፈሳችን ይታደሳል፤ ንቁዎች እና በስራችን ውጤታማ እንሆናለን። ደስተኛና ጤነኛ ስለምትሆን ተግባራትንም በተቀላጠፈ መንገድ የመስራት እድል ይፈጥርልሃል ። ወዳጄ … እንዲሞላልህ ከፈለግክ ከመዝናናት አትጉደል ! አሻፈረኝ ካልክ ግን ውጥረት ይወጥርሃል። መጠነኛ ውጥረት ትጋትን ይጋብዛል ቢባልም ያንተ ግን ልኩን ስለሚያልፍ ልክ አይሆንም። አእምሮህ እና አካልህ ለተለያየ ጤና ችግር ይጋለጣል። ራስህ ላይ ጭንቀትን ትጋብዛለህ። ጭንቀት ደግሞ ላጤ እንዳይመስልህ፤ ጓዘ ብዙ ነው። ድብርት፣ ደም ብዛት፣ እንቅልፍ ማጣት፣ ከልክ ያለፈ ውፍረት፣ በሽታ የመከላከል አቅም መቀነስ፣ የልብ ህመም፣ ቀድሞ ማርጀትና የመርሳት በሽታን ያስከትላል። 70 በመቶ የሚሆኑት ታካሚዎች ሀኪም ጋር የሚቀርቡበት ከውጥረት ጋር በተያያዘ የጤና ችግር እንደሆነ ይነገራል።
ወትሮውንም የጭንቀት ጎተራ ከሆንክማ ኮቪድ19 ሲታከልብህ ነገርህ “በደንባራ በቅሎ ቃጭል ተጨምሮ” ይሆናል። ስለዚህ ወዳጄ በሆነው ባልሆነው እንዲሞላልህ አትጉደል የትናየት ፈሩ መጨነቁን እርግፍ አድርገህ ዘና በል። ለጭንቀት ፊት መስጠት አያስፈልግም። እርሱ እንደው ፊት ብትነሳውም ካልጎበኘውህ ብሎ ማስቸገሩ አይቀርም። ዕድሜ ዘመንህን ጭንቀት በየጊዜው በርህን ሲያንኳኳ ትሰማለህ። ግን አንተ በርህን ከፍተህ አታስገባው። “ወፎች ከራስህ በላይ እንዳይበሩ ልትከለክላቸው አትችልም፤ በራስህ ላይ ጎጇቸውን እንዳይሰሩ ማድረግ ግን ትችላለህ።” እንደሚባለው ጭንቀትም እንዲሁ በርህን እንዳያንኳኳ ልትከለክለው አትችልም። ነገር ግን ወደ ውስጥ ገብቶ እንዳይረብሽህ በርህን ክርችም ማድረግ ትችላለህ። ይህን ማድረግ ከቻልክ ሳትጎድል ትሞላለህ።
ታዲያ ሳይጎድሉ መሙላት እንደምናወጋው ቀላል አይደለም፤ ተጋድሎን ይጠይቃል። እውቁ የስነ ጽሑፍ ሃያሲ ቴዎድሮስ ገብሬ እንደሚለው፣ ተጋድሎ በትግልና ውጊያ ድልና አክሊል እስኪገኝ ድረስ የሚወጡት ግዳጅና የሚቀበሉት መከራ ነው። ተጋድሎ መንፈሰዊ አሊያም ሃይማኖታዊ፣ ስጋዊ ወይም መንፈሳዊ ሊሆን ይችላል። እንደ ተጋድሎው አይነት የተጋድሎውም ዓላማና ውጤት፣ ከተጋድሎ ተይዞ የሚወጣው በረከት ይለያያል። ሙሽሪትን ሊወስድ እንደሚመጣ ሙሽራ ጭንቀት ሆ እያለ ይመጣል። በዚህ ጊዜ “አላስገባም ሰርገኛ” እያልክ በርትተህ በርህን መጠበቅ አለብህ። ደርምሶህ ከገባ ግን ሙሽራው ሙሽሪቱን እንደሚወስድ፣ ጭንቀትም ሙላትህን ከፍቶ ያጎድልሃል። አንድ ጊዜ ውስጥ ከገባ ሁለመናህን ተቆጣጥሮ ምርኮኛው ያደርግሃል። ከዚያም ምኞትህና ፍላጎትህ ወሰን አጥቶ በብዙ ነገሮች መጨነቅ ትይዛለህ። አንተ በዓለም ውስጥ መኖርህ አብቅቶለት ዓለም በአንተ ውስጥ መኖር ይጀምራል። ስለዚህ ጭንቀትን መጋደል ያለብህ ግዳዩ ከመሆኑ በፊት ነው። አንድ ጊዜ እጅ ሰጥተህ ምርኮ ከገባ ግን ነፍስን የሚፈነቅል ምክር ያስፈልግሃል። ግብጻዊው አቡነ ሺኖዳ ሶስተኛ “The Release of the Spirit” በተሰኘ መጽሐፋቸው እንዲህ ይመክሩሃል፡“ውድ ወንድሜ ሆይ! ጥቂት ወደ ልብህ ዘልቄ ልግባና እውነት የሆነውን ነገር በግልጽ ላነጋግርህ። አብዝተህ ትኩረት የምትሰጣቸው ታላላቅ ተስፋዎች ልቦናህን መከፊል ሞልተውታል።
እነዚህ ተስፋዎችህ በምናብህም ስለተቀረጹ በቁም ሳለህም ሆነ ተኝተህ በቅዠትና በሕልምህ ይታዩሃል። በግልጽ የምታውቃቸውና የማትክዳቸው ዓላማዎችም ይኖሩሃል። ታዋቂ ሰው በመሆን በሌሎች ፊት መሞገስንም ትወዳለህ። ዝናና ክብር፣ ሥልጣንና ኃይል ይኖሩህም ዘንድ ተስፋ ታደርጋለህ። ሀብት፣ ማዕረግ፣ ዕውቀት፣ ከበሬታ፣ ዋጋም ሌሎች ተስፋዎችህ ናቸው። ቤት፣ መኪና፣ ምግብ፣ ልብስና የተለያዩ ስጋዊ ፍላጎቶችህም እንዲኖሩህ ትሻለህ። በአለሙ ውስጥ የምትኖረው አንተ ሳትሆን አለሙ ባንተ ውስጥ ስለሚኖር ልቦናህን፣ አእምሮህን፣ አስተሳሰብህንና ፈቃድህን ሁሉ ይቆጣጠረዋል፤ ተጽእኖም ያደርግበታል። ነፍስህም በእነዚህ ሁሉ ጉዳዮች እስረኛ ስለምትሆን ነጻ መውጣትን አጥብቃ ትፈልጋለች። ”
እየጎደሉ መሙላት፣ እያፈሰሱ መቅዳት ነው። እንዲሞላለህ አትበድል። እንዲሞላልህ አትግደል። እንዲሞላለህ አትቅጠፍ። እንዲሞላልህ አትዝረፍ። ክፉውን መልካም መልካሙን ክፉ ለሚሉ፣ ጨለማውን ብርሃን ብርሃኑን ጨለማ ለሚያደርጉ፣ ጣፋጩን መራራ መራራውን ጣፋጭ ለሚያደርጉ ወየውላቸው መባሉን አትርሳ። እንዲሞላለህ ሙሉ ሁን። በርካቶች 30 የስኬት መንገዶች፣ 10 ጭንቀትን ማበረሪያ ዘዴዎች፣ ሰባት የስኬታማ ሰዎች ባህሪያት፣ 12 ራሰ በረሃነትን መከላከያ መንገዶችና ወ.ዘ.ተ … እያሉ መጽሐፍ እስከ ማሳተም ደርሰዋል። እንዲህ ያለ ርዕስ ያላቸውን መጽሐፍት ማጣጣሌ አይደለም። የቸከና የተሰለች አካሄድ መሆኑን ለመግለጽ ያህል ነው።
አንዳንድ ጊዜ ግን በዚህ መንገድ እጅን በአፍ የሚያስጭኑ መረጃዎች ይቀርባሉ። ከዚህ የሚከተለውም አንዱ ነው። በዕለት ተዕለት ህይወትህ ውስጥ የሚፈጠሩ የውጥረት ምንጮችን ለመቀነስና ለመቆጣጠር ተከታዮቹን ሶስት ጉዳዮች በማድረግ አትጉደል።
ፋታ በማጣት አትጉደል
በየዕለቱ ፋታ የምታገኝ ጊዜ ይኑርህ። ከየትኛውም አይነት ሀላፊነትና ተግባር ራስህን ነፃ በማድረግ አእምሮህንና አካልህን አሳርፍ። የእጅ ስልክ፣ ቴሌቪዥን፣ ራዲዬና ላፕቶፕ አጠገብህ አይኑር። የጽሞና ጊዜ ይኑርህ። ጽሞና በማንኛውም ቅጽበት መላ ቀልባችንን አሁን ላይ ማድረግ የምችንልበት ጥበብ ነው። አንድ ስዕል ላይ ወይም አንዳች ነገር ላይ ብቻ ትኩረት አድርጎ አእምሮ ውጥረት የፈጠሩበትን ነገሮች እንዲዘነጋና እንዲረጋጋ የማድረግ ስልት ነው። በብዛት የምስራቃዊያኑ ባህል ነው። በተለይ የአእምሮ ጤንነትን በመጠበቅ ረገድ አይነተኛ ሚና ይጫወታል።
ፅሞና በእንግሊዝኛ “ሜዲቴሽን” ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ አለው። አንዱ ጠቀሜታው ውጥረትን መቀነስ ነው። በቀን ለአንድ ወይም ሁለት ጊዜ ለሀያ ደቂቃ ያህል “ሜዲቴሽን” ማድረግ በርካታ ጠቃሜታ ያስገኛል። የቋጥ የባጡን እየፈተለ ውጥርጥር ያለን አእምሮ ፅሞና ረጋ ያደርጋል። አእምሮ በቫይረስ መጠቃት የለበትም። ሁልጊዜ ሊጸዳ ይገባዋል። አእምሮ ከሰከረ ሌሎች የሰውነት አካላት መስራት ይሳናቸዋል። አእምሮህ በአደገኛ ቫይረሶች እንዳይጠቃ ከእንቅልፍ በፊት “ስካን” መደረግ አለበት። ለ30 ደቂቃ ያህል ብቻህን ሆነህ ወደ ውስጥ ካሰላሰልክ ጽሞናን ከወንክ ማለት ነው። ራስህን ለማድመጥ ጊዜ በላመስጠት አትጉደል
መለወጥ የማትችለውን እውነታ ባለመቀበል አትጉደል
ልትለውጠው የማትችለው ነገር የውጥረትህ ምንጭ ከሆነ ተቀበለውና ከጭንቀትህ ተገላገል።
የቅርብ ሰው ሞትን፣ በህክምና ሊድን የማይችል ህመምን፣ የማትደሰትበትን የአካል ክፍልህንና ያመለጠህን ደግሞ የማይመጣ ዕድል አሜን ብለህ ተቀበል። ዘወትር “ለምን እንዲህ እና እንዲያ ሆነ?” የምትል ከሆነ ውጥረት ውስጥ ትገባለህ። በአንድ በኩል ክስተቱ የሚፈጥረው ውጥረት አለ፤ በሌላ በኩል ደግሞ ለምን የሚለው መልስ አልባ ጥያቄህ የሚያመጣው ጭንቀት ተጨማሪ ህመም ይሆናል። መለወጥ የማይችለውን ነገር ከተቀብልክ ግን ራስህ የፈጠርከውን ሁለተኛውን ችግር መቅረፍ ትችላለህ።
ህይወትህን በማክበድ አትጉደል
ሕይወትን በሁሉም መስክ ቀላል ማድረግ መቻል በሕይወት ከባዱ ነገር እንደሆነ ይነገራል። “Simplicity is the ulitimate complexity” የሚባለው ለዚህ ነው። በተቻለ መጠን ሕይወትን ቀልጣፋ እና ቀላል የሚያደርጉ አማራጮችን መከተል ብልህነት ነው። ለዚህ ደግሞ ሁነኛው መላ ከፍ ዝቅ የማይል የውስጣዊ ግለት ባለቤት መሆን ነው። ፓስቸራይዜሽን በምግብ ውስጥ የሚገኙ የማይክሮ ኦርጋኒዝሞችን እድገት የማዘገየት ሂደት ነው። “pasteurization” የሚለው ቃል ከፈረንሳዊው ኬሚስት ከሉዊስ ፓስተር ስም የተወሰደ ነው። ሉዊስ ፓስተር የሚክሮባል ችግሮችን ለመፍታት እ.ኤ.አ ከ1857 እስከ 1862 ድረስ ምርምሩን አካሂዷል። ሊዊስ ፓስተርና ክላውድ በርናንድ ሚያዚያ 20 ቀን 1862 የመጀመሪያውን የተሳካ ሙከራ አካሄዱ።
ምርምራቸውን የሰሩት ቢራና ወይን ለምን በቶሎ እንደሚበላሹ ለማወቅ ነበር። የብልሽቱ ምክንያትም ከአየር ወደ መጠጡ የሚገቡት ጀርሞችና ሌሎች በአይን የማይታዩ ጥቃቅን ነገሮች (micro – organisms) መሆናቸውን ተረዱ። እነሱን ለማጥፋት ደግሞ ሙቀት በቂ እንደሆነ በሙከራ በማረጋገጥ የወይኑና እና የቢራውን የሙቀት መጠን 57 ነጥብ ሁለት ሴንቲ ግሬድ ላይ ሲያደርሱት ችግሩን ለመፍታት ቻሉ። ወተት እንዳይበላሽ ደግሞ በ61 ነጥብ ስድስት ሴንቲ ግሬድ የሙቀት መጠን ለግማሽ ሰዓት ያህል መቆየት ይኖርበታል። ፓስቸራይዝድ የሆነ ወተት ከላም በቀጥታ ታልቦ ከመጣው በተሻለ ሳይበላሽ ይቆያል። ፓስቸራይዜሽን ሙሉ በሙሉ ሁሉንም ጀርሞች አይገድልም። ጥቂት ጠቃሚ የሆኑ ጀርሞችን ያሰቀራል። ይሁንና ፓስቸራይዝድ የሆነ ወተት በፍሪጅ ወይንም በሌላ ቀዝቃዛ ስፍራ ከተቀመጠ የጠቃሚ ጀርሞቹ እንቅስቃሴ የተገደበ ይሆናል። አንተም እንዲሁ ጥቃቅን በሆኑ ጉዳዮች ውስጥህ እንዳይጎዳ እንደ ማህጸን የሙቀት መጠን የማይዋዥቅ ውስጣዊ ግለት ሊኖረህ ይገባል።
ውስጣዊ ግለት ሁሉንም አይነት ውጥረቶችን አያባርርም። እንደ ፓስቸራይዜሽን ትጋትን የሚጋብዙና በጎ ውጤትን የሚያስከትሉ በጎ የሆኑ መጠነኛ ውጥረቶችን ተቀብሎ ያስተናግዳል። በአንፃሩ ፓስቸራይዝድ የሆነ ወተት በፍሪጅ ወይንም በሌላ ቀዝቃዛ ስፍራ ከተቀመጠ የጠቃሚ ጀርሞቹ እንቅስቃሴ እንደሚገደብ አንተም ዙሪያህን በጭንቀታም ሰዎች ከተከበብክ የሚያተጉህ ውጥረቶች አቅም ያጣሉና ከባቢህን ፈትሽ፡፡ ይህ ሲሆን ብዙ ወደ ጭንቀት የሚገፉ ጥቃቅን ግፊቶችን መቋቋም ችለህ ሳትጎድል ትሞላለህ።
አዲስ ዘመን ሐምሌ 25 ቀን 2012 ዓ.ም
የትናየት ፈሩ