የእርስ በእርስ ጦርነት ህዝቦቿን እና ህንፃዎቿን የጨረሰባት የመን የተረፉት ህዝቦቿ እጅግ በአስከፊ የተላላፊ በሽታና ረሀብ አደጋ አንዣብቦባቸዋል። የፀደይ ወራት አብዮት የሚባለው የምስራቁ ዓለም አብዮት ከየመን ተነስቶ ሶሪያ፣ ሊቢያ እና ግብፅን አካሏል፡፡ ግብፅ የአሜሪካ ድጋፍ ስላላት መሪዋን ሆስኒ ሙባረክን አውርዳ ኢታማዦሩን ሹማ ብታጠናቅቅም የተሻለ የኑሮ መሰረት የነበራቸው ሶርያ፣ የመንና ሊቢያ ፈራርሰው የአሸባሪዎች መፈንጫ ሆነዋል፡፡ ህዝቦቻቸውም ለከፋ ጉዳት ተዳርገዋል፣ ገሚሱ ተሰዷል። በተለይ ሶሪያና የመን የኃያላን ጡንቻ መፈታተሻ ናቸው፡፡ በተለይ የመን የሚላስ የሚቀመስ የሌለባት ምድረ በዳ በመሆን የዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን ትኩረት የሳበች አገር ናት።
የዘጠኝ ዓመቱ አህመድ አብዛኛውን ጊዜውን ብቻውን ያሳልፋል፡፡ አንዳንዴ ደግሞ ቆሻሻዎችን በመልቀም ህይወቱን ይገፋል፡፡ ከሚኖርበት ግድግዳ ከፈንጂ ተርፈው የወዳደቁ የድሮ ጡቦችን አንስቶ እርቀት ላይ ለመውሰድ ይሞክራል፡፡ ላለፉት ስድስት ወራት ይህ የአህመድ የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴ ነበር፡፡
ከዚህም በተጨማሪ በሕይወቱ ውስጥ ያገኛቸውን አንዳንድ አስደሳች ጊዜያት ያስታውስለታል፡፡ ከስድስት ወር በፊት አህመድ አብዛኛውን የእረፍት ጊዜውን ከጓደኛው ሀሸም ጋር ሆዲዳህ ውስጥ ከሚገኘው ትምህርት ቤት ውስጥ እግር ኳስ በመጫወት ያሳልፍ ነበር፡፡ ነገር ግን በአለፈው ሰኔ ወር አካባቢ በአካባቢው ውጊያ ተከስቶ ስለነበረ አህመድ ለችግር ተዳረገ፡፡
በተከሰተው ጦርነት ከወላጆቹ እና ከታናሽ እህቱ ጋር ወደ ሰንዓ ሸሸ፡፡ ቤተሰቡ አሁን በዋና ከተማ ውስጥ በሚገኘው በሙሐመድ አብዱላህ ሳላህ ትምህርት ቤት ውስጥ ቅዝቃዜና እርጥበት ተቋቁመው እየኖሩ ይገኛሉ፡፡ እዚህ ቦታ ጥቂት ምግብ የሚገኝ ሲሆን በአገሪቱ ውስጥ የተፈናቀሉ ሰዎች በተበከለ ውሃ ለመታጠብ ተገደዋል፡፡ በየመን ቀይ ባሕር ዳርቻ ጠረፍ የሆነችው ሆዲዳህ በሀውቲ እና በሳዑዲ አረቢያ መካከል የሚያደርጉት ጦርነት እያስተናገደች የምትገኝ ከተማ ነች፡፡ በጦርነቱ ከ 445 ሺ በላይ የየመን ነዋሪዎች በበጋው ወቅት ከከተማው ሸሽተዋል፡፡ የአህመድ ወላጆች እንደሚሉት በየመን አራት ዓመት በተካሄደ ጦርነት አህመድ ከአሻንጉሊቶችና ከጓደኞቹ ውጪ ህይወቱን ለመምራት በመገደዱ የልጅነት ሕይወቱን አጥቷል፡፡ አህመድ ለአል ጀዚራ እንደተናገረው “በአገሪቱ ኢንተርኔት፣ ኮምፒዩተርና ቴሌቪዥን ባለመኖሩ ቀኑ ተመሳሳይና አሰልቺ ነው፡፡”
አባቱ ተሰደው ከመጡት ልጆች ጋር አዲስ ጓደኞች እንዲያፈራ ለማድረግ ሞክሯል፡፡ ይሁን እንጂ እናቱ እንደምትናገረው በየጊዜው የሚወድቁ ቦምብ እና የሚኖሩት ድህነት ስሜቱ ላይ ከባድ ጉዳት አድርሷል፡፡ በየዕለቱ በሆዲዳህ ውስጥ አዲስ ሕይወት ለመመሥረት ትግል እያደረገ እንደሚገኝ እናቱ ትገልፃለች፡፡ እንደ እናቱ አባባል፤ የአህመድ ባህሪው በጣም ተለውጧል:: በእህቱ ላይ የሚጮህበት እና ቤተሰቦቹን የሚያነጋርበት ሁኔታ አሁን ባለበት እድሜ ላይ ሊንፀባረቅ የሚገባው አይደለም፡፡
መማሪያ ክፍሎች እንደቤት ተቆጥረው እየተኖረባቸው ሲሆን ከክፍሎቹ አለፍ ብሎ ደግሞ በፕላስቲክ የተሰሩ መጠለያዎች ከድርቅ የተረፉ ሰዎች እየኖሩባቸው ይገኛሉ፡፡ በሆዳዲህ ያለው ሁኔታ ልጆቹን እንደጎዳበት የተናገረው ደግሞ አብዱላሂ ሀሰን ነው፡፡ ሀሰን የየመን መንግሥት ደጋፊ የሆኑት ሳውዲ አረብ ኢምሬት ጥምር ጦር ሆዲዳድን ሲቆጣጠሩ ከመጀመሪዎቹ ስደተኞች መካከል አንዱ ነው፡፡ በአሁኑ ጊዜ 16 ከሚሆኑ ከዘመዶቹ ጋር በትንሽ ክፍል ውስጥ ይኖራል፡፡ ሀሰን እንደሚለው፤ ልጆቹ እያለቀሱ ደህንነቱ ወደ ተጠበቀው ቦታ እንዲወስዳቸው በመጠየቃቸው ወደ ሰንዓ ይዟቸው መጣ፡፡
በወቅቱ ሃሰን ከገንዘብ እጥረት ማምለጥ አልቻለም፡፡ የመጓጓዣ ወጪዎች ለመሸፈን በቂ ገንዘብ አልነበረውም፡፡ በጉዞ መስተናገድ የሚችለው 50 ሺ የየመን ሪያል ወይም 100 ዶላር ለአጓጓዦቹ መክፈል የሚችል ሰው ብቻ ነበር፡፡ ሀሰን እንደሚለው፤ ‹‹ከየትም ብዬ ገንዘቡን ያገኘሁ ሲሆን ከባለቤቴ፣ ከሰባት ልጆቼ፣ እህቴ እና ሰባት ልጆቿን ይዤ ወደ ሰንዓ መጣሁ፡፡›› ከስድስት ሰዓት ጉዞ በኋላ በመጨረሻ የሚፈልጉት ከተማ ደረሱ፡፡ ከተማዋ ለአራት ዓመታት በዘለቀው አስከፊ የአየር ጥቃት ምክንያት ተዳክማለች፡፡ በከተማዋ የሚታዩት ሱቆች በቦምብ የፈራረሱ በመሆናቸው በአካባቢው ድህነት መስፋፋቱ አንዱ ምልክት ነበር፡፡
በካምፖች ውስጥ በብዛት ከሌላ ከተማ የመጡ ስደተኞች ይገኛሉ፡፡ ትምህርት ቤቶች ብቸኛ የመጠለያ ቦታ ሆነው እያገለገሉ ይገኛሉ፡፡ ብርድልብሶችና የቆሸሹ ሳህኖች መሬት ላይ ወድቀው ይታያሉ፡፡ ብዛት ያላቸው ሰዎች በአንድ ክፍል ውስጥ ታጭቀው ይኖራሉ፡፡ በመንገዶች እና ኮሪደሮች ውስጥ የሻጋታ እና የአሲድ ሽታ የሚሸት ሲሆን አንዳንዶቹ ስደተኞች እንደሚሉት፤ የገላ መታጠቢያ ቤቶች የሚፈለገው እቃና ውሃ አላሟሉም፡፡ ሀሰን ‹‹በሩዝና ዳቦ ህይወታችንን አቆይተናል፡፡›› ይላል፡፡ ጨምሮም በእጁ ምንም አይነት ገንዘብ እንደሌለ ይናገራል፡፡
እንደ ሰብዓዊ መብት ተቋማት አባባል የመን ከዓለም ላይ ዜጎች በአሰቃቂ ሁኔታ የሚኖሩባት አገር ሆናለች፡፡ እአአ 2014 ጀምሮ የሃውቲ አማፅያን ሰንዓን ከተቆጣጠሩ በኋላ ሁኔታው የተባባሰ ሲሆን በሆዲዳህ የሚደረገው ጦርነት አብዛኛው ሰው ወደ ሰንዓ እንዲሰደድ አድርጎታል፡፡ የየመን መንግስት ወደ ሰናዓ የሚወስደውን መንገድ በመዝጋት ሆዲዳህን መልሶ ለመቆጣጠር ጥረት እያደረገ ይገኛል፡፡ ከተማዋን መቆጣጠር ጦርነቱን ያስቆመዋል ተብሎ ይገመታል፡፡ ወደ 600,000 የሚደርሱ ነዋሪዎች የምትይዘው ሆዲዳህ በሀገሪቱ ውስጥ በጣም ትልቁ ከተማ ነበረች:: ከተማዋ 80 በመቶ የሚሆነው የንግድ ሸቀጦችን፣ እርዳታ እና የነዳጅ ገበያ የሚካሄድበት ወደብ ነው፡፡ ነገር ግን ወደቧ በሀውቲ አማፅያን ከተያዘ በኋላ አካባቢው የአግሮ ኢንዱስሪ መናኸሪያነቱ ቀርቶ የጦርነት አውድማ ሆኗል፡፡
አብዛኞቹ የትምህርት ቤቱ ነዋሪዎች እንደሚሉት፤ በሆዲዳህ ውስጥ ምን እንደሚጠብቃቸው ያውቁ ነበር፤ ምናልባትም በጦርነቱ ምክንያት በሆዲዳ ውስጥ ሞተው ይቀሩ ነበር:: ጋማዳን አቡ አሊ በሆዳዲህ ውስጥ ጋዜጠኛ የነበረ ሲሆን አሁን ስደተኛ ነው፡፡ እሱ እንደሚለው፤ ስደተኞቹ የሚኖሩበት አሰቃቂ ሁኔታ ሌላኛው የድብቅ “አሳዛኝ” ጉዳይ ነው፡፡ በስደተኞች ካምፖች ውስጥ የሚገኙትን ለመርዳት ያለው ብቸኛ መንገድ በሆዳዲህ ውስጥ ያለውን ጦርነት በማስቆም ነዋሪዎቹ ወደ አካባቢያቸው ተመልሰው እንዲኖሩ ማድረግ ነው፡፡ በሆዲዳህ ውስጥ ያሉ ነዋሪዎች በሰንዓ፣ ደሃማር እና ሃጃጃህ ውስጥ ተጠልለው ይገኛሉ፡፡ አሊ እንደሚለው ነዋሪዎቹ ያላቸውን ሁሉ ትተው መጥተዋል፡፡ በስደት በሚኖሩበት አካባቢ ውስጥ በከባድ ችግር ውስጥ እንዳሉ አሊ ይገልፃል፡፡ ሰንዓ ውስጥ ስደተኞች ከገቡ በኋላ የአፓርትመንት የቤት ኪራይ እየጨመረ መጥቷል፡፡ ‹‹በወር 60 ዶላር ተከራይቶ የነበረው አፓርታማ አሁን በ 100 ዶላር ክልል ውስጥ ይገኛል›› ሲል አሊ ይናገራል፡፡
በየመን አለም አቀፍ የስደት ኤጀንሲ ኮሙኒኬሽን ኦፊሰር ሳባ አል ሙአለሚ እንደሚለው፤ በቅርብ ጊዜ በእርዳታ የምግብ ሸቀጦችን፣ ፍራሽ፣ ብርድ ልብሶችን እና የጽዳት እቃዎችን ጨምሮ ገብተዋል፡፡ ይሁን እንጂ በዋና ከተማው ውስጥ የተሰብስበው በመቶ ሺዎች የሚቆጠር ስደተኛ በየጊዜው አነስተኛ የምግብ ራሽን እና መድሃኒት ይሰጣቸዋል፡፡ ነገር ግን ምንም ዓይነት እርዳታ ቢሰጥም የሚደርስባቸውን መከራ ለማስታገስ የሚበቃ አይደለም፡፡ አህመዲን፤ በቀጣይ በሰላም ግንባታ ዙሪያ ውይይቶች ከተደረጉ ለነዋሪዎቹ ተስፋ ይሰጣል፡፡ ነገር ግን በሆዳዲ ውስጥ ያለው ጦርነት የሚቆም አይመስልም፡፡ በጦርነቱ ምክንያት በልጆቹና በስደተኞቹ ላይ አደጋ ይደርሳል የሚል ፍራቻ እንዳለው ይናገራል፡፡
አዲስ ዘመን ጥር 13/2011
መርድ ክፍሉ