ሰሜን ጎንደር ዞን ደንቢያ ወረዳ የሚኖሩት ወይዘሮ ክፉኛ ተቸግረው ከርመዋል። ጊዚያትን ላስቆጠረው የቤታቸው ጎዶሎ መላና መፍትሄ አጥተውለት ሲብሰለሰሉ መቆየታቸውን ብዙዎች አይተው ታዝበዋል። ሴትዮዋ ላሉበት ችግር ፈጥኖ የሚደርስላቸው መፍትሄ ገንዘብ መሆኑን ጠንቅቀው ያውቁታል። ያሰቡትን አግኝተው ጉዳያቸውን ፈጥኖ ለመሙላት ግን አንድ ሁለት ብለው የሚቆጥሩት አንዳች ብር ከእጃቸው የለም።
ወይዘሮ ቀለቤ ችግራቸውን ለበርካቶች ሲያዋዩ ቆይተዋል። ለሚሹት ጉዳይ የሚውል የገንዘብ ብድርም ዘመድና ወዳጆቻውን ደጅ ሲጠኑ ከርመዋል። አብዛኞች እንደሳቸው እያዘኑ አሰናብተዋቸዋል። አንዳንዶች ደግሞ በ‹‹የለንም›› ምላሽ ከበር መልሰዋቸዋል። ጥቂቶችም በዛሬ ነገ ተስፋ ለቀናት ሲቀጥሯቸው ከርመዋል።
ወይዘሮ ቀለቤ ያሰቡትን ለማሳካት አልሆን ቢላቸው ወራትን በትካዜ አሳለፉ። ገንዘቡን ለማግኘት የሚሸጡት የረባ ንብረትና የሚያሲዙት ጥሪት የላቸውም። በሴትነት አቅማቸው አሳርሰው በዓመት አንዴ እህል ከሚያገኙበት የእርሻ መሬት በቀር ተስፋ ይሉት መመኪያ የላቸውም።
ቀለቤ በሀሳብ አንገታቸውን እንደደፉ ጊዚያትን መቁጠር ያዙ። ጓዳቸው ነጥፎ እጅ ሲያጥራቸው በየቤቱ ዞረው ደጅ የጠኑበትን ክፉ ቀን አስታወሰው ሆድ ባሳቸው። ያለአንዳች መፍትሄ ወራትን የገፉት ወይዘሮ አንድ ቀን ከአንድ አባወራ ቤት ዘልቀው በር አንኳኩ። በፈገግታ የተቀበሏቸው የቤቱ ባለቤት በእሳቸው መፈለጋቸውን ቢያውቁ የሚሉትን ሁሉ ለማዳመጥ ልባቸው ፈቀደ። ወይዘሮዋ ሰውዬው ጆሮ ሰጥተው ማተኮራቸው ቢያስደስታቸው ቀጣዩን የገንዘብ አበድሩኝ ጥያቄ አስከተሉ ።
አባወራው አሁንም ፈገግታቸው ሳይደበዝዝ ጥያቄቸውን በአግባቡ አዳመጡ። አዳምጠውም የልባቸውን መሻት እውን እንደሚያደርጉ ቃል ገቡላቸው። ወይዘሮዋ ገንዘቡን በብድር እንደሚያገኙ ሲረዱ የውስጣቸው ተስፋ ለመለመ። እስካሁን በበርካቶች ፊት በደጅ ጥናት ያሳለፉትን ጊዜ አስበውም የደስታ ዕንባ ተናነቃቸው።
ጥቂት ቆይቶ አበዳሪው አንድ ቅድመ ሁኔታ አስቀመጡ። ገንዘቡን የሚሰጡት በአመኔታ ብቻ ሳይሆን ላበደሩት መተማመኛ የሚሆን መሬትን በዋስትና ይዘው መሆኑን አሳወቁ። ወይዘሮዋ ይህን ሲሰሙ ውስጣቸው በድንጋጤ ደነዘዘ። ያላቸው መተዳደሪያ መሬታቸው ብቻ ነው። እሱኑ አስይዘው ገንዘቡን መቀበል በእጅጉ ይከብዳቸዋል። ያም ሆኖ ገንዘቡ በእጅጉ ያስፈልጋቸዋል። ካላቸው መሬት ገሚሱን ከፍለው ቢበደሩበት ሊበጃቸው እንደሚችልም መላልሰው አሰቡበት። አስበውም ከውሳኔ ደረሱ።
ቀለቤ በተባለው ጊዜ ብድራቸውን እንደሚመልሱ ለውስጣቸው ነገሩት። ይህ ባይሆን መሬታቸው በዕዳ እንድሚያዝ ያውቃሉ። ምርጫ አልነበራቸውም። በተባለው ጊዜ የተበደሩትን እንደሚመልሱ ቃል ገቡ። ይህን ያረጋገጡት አበዳሪ የውል ሰነዱን አስፈርመው ሁለት መቶ ሰባ ብር /270/ ብር ለተበዳሪዋ ቆጥረው አስረከቡ። ገንዘብና መሬት ተለዋውጠውም አበዳሪና ተበዳሪ በስንብት ተለያዩ።
ወይዘሮ ቀለቤ የተበደሩትን ሁለት መቶ ሰባ ብር ሳይከፍሉ ጊዚያት ተቆጥረዋል። ቀለቤ አብሯቸው የዘለቀ ዕዳ እንዳለባቸው ጠንቅቀው ያውቃሉ። ይህን ባስቡ ጊዜም ልባቸው ይደነግጣል። ገንዘቡን ካልከፈሉ መሬታቸው እንደማይመለስ ጠንቅቀው ያውቃሉ። ለዚህም በእማኞች ፊት ፈርመው ያረጋገጡት ማስረጃ በአበዳሪው እጅ ይገኛል።
ቀለቤ እንዳሰቡት ሆኖ የተበደሩትን ገንዘብ በወቅቱ መመለስ አልቻሉም። በተባለው ጊዜ ዕዳቸውን መክፈል ያለመቻላቸውን ያወቁ አበዳሪም መሬቱን በባለቤትነት እያረሱ ሲጠቀሙበት ቆዩ። ይህ መሆኑ የሚያንገበግባቸው ተበዳሪ መሬቱን ባዩ ቁጥር ያንገበግባቸው ያዘ። ለጥቂት ገንዘብ ሲባል ምርት የሚያፍሱበትን መሬት እንደዋዛ ማጣታቸውን እያሰቡ ጥቃት ተሰማቸው።
እንዲህ ከሆነ ከጊዚያት በኋላ የአበዳሪው ድንገቴ ሞት ተሰማ። የቤቱን ሃላፊነት የተረከበው የሟች የበኩር ልጅም አባቱን ተክቶ ጉዳዮችን ማስፈፀሙን ቀጠለ።
ከዓመታት በኋላ…
እነሆ ! ይህ ታሪክ ከተፈፀመ ከአስራ አምስት ዓመታት በላይ ተቆጠሩ። እነዚህ ዓመታት ለወይዘሮዋ እጅግ ከባድ የሚባሉ የቁጭት ጊዚያት መሆናቸው አልቀረም። ገንዘብን ማስያዣ አድርገው የእርሻ መሬታቸውን ማስረከባቸው ሁሌም ያሳዝናቸው ይዟል። ዛሬ ላይ ቆመው ማስተዋል ሲጀምሩም በደል እንደተፈፀመባቸው ያምናሉ። ይህ ስሜትም ከሟች አበዳሪው ህጋዊ ወራሽ ጋር አለመስማማትን ፈጥሮ ዘወትር ያጣላና ያጨቃጭቃቸው ጀምሯል።
ክርክር…
በወይዘሮ ቀለቤና በሟች ህጋዊ ወራሽ አቶ አየልኝ ደርበው መካከል የተፈጠረው ያለመግባባት መነሻ ቀድሞ ውል የተፈፀመበት የገጠር መሬት ስለመሆኑ ብዙዎች ያውቃሉ። ጉዳዩ በቀላሉ የሚፈታ አለመሆኑን የተረዱ ጥቂቶችም ችግሩ በአካባቢው ደንብና ባህል መሠረት ይታይ ዘንድ ወደ ግልግልና እርቅ ኮሚቴ ልከው መፍትሄን አመላክተዋል።
ሁለቱ ወገኖች ከአካባቢው የግልግል ኮሚቴ ፊት እንደቀረቡ አቤቱታቸውን ተራ በተራ አስረዱ፤ ወይዘሮ ቀለቤ ከዓመታት በፊት ከገንዘብ አበዳሪያቸው ሟች ለወሰዱት ብድር የገጠር መሬታቸውን በማስያዣነት መስጠታቸውን በማስታወስ የተፈፀመባቸው ድርጊት በደል መሆኑን ተናገሩ። የሟች አበዳሪ ልጅ በበኩላቸው ጉዳዩ የተፈፀመው በሁለቱ መካከል በነበረው የውል ስምምነት መሰረት መሆኑን ጠቅሰው፤ እንደ ህጋዊ ወራሽነታቸው የወይዘሮዋን ሀሳብ አጥብቀው እንደሚቃወሙ ተከራከሩ።
ለወራት የፈጀው የሁለቱ ወገኖች ውዝግብ በመጨረሻ ከአንድ ስምምነት ላይ ሊደርስ ግድ አለው። ወይዘሮዋ ከዓመታት በፊት ከሟች አበዳሪው ጋር ያደረጉት የገጠር መሬት የዕዳ ውል ፈርሶ፣ በምትኩ በሌላ ህጋዊ መሬታቸው ላይ የሚገኘውና አርባሁለት ቆርቆሮ ማልበስ የሚችል ቤት ማሰራት የሚችለው ይዞታ ለወራሽ እንዲሰጠው የሚል ውሳኔ ተላለፈ።
ወይዘሮ ቀለቤ በወቅቱ የተላለፈባቸውን የፍርድ ውሳኔ ተቀብለው በህጋዊ ይዞታቸው ላይ የሚገኘውን መሬት ለአቶ አየልኝ ደርበው ሊያስረክቡ ተስማሙ። እንደተባለው ሆኖም የሟች አበዳሪው ህጋዊ ወራሽ በደንቡ መሰረት ቀርበው መሬቱን ከወይዘሮዋ እጅ ተረከቡ።
አቤቱታ አንድ…
በወይዘሮ ቀለቤ ተስፋና በሟች ህጋዊ ወራሽ አቶ አየልኝ ደርበው መካል ሲካሄድ የቆየው ክርክር በውሳኔ ከተጠናቀቀ በኋላ ወይዘሮ ቀለቤ የክስ ማመልከቻቸውን ይዘው ለደንቢያ ወረዳ ፍርድ ቤት ‹‹አቤት›› ሲሉ ቀረቡ። በማመልከቻቸው ‹‹ፍትህ ተጓድሎብኛል፣ በደል ተፈጽሞብኛል›› ያሉት ወይዘሮ የመሬት መያዣ ውሉን የፈረምኩት ተገድጄ እንጂ ፈቅጄ አይደለም በማለት ተከራከሩ።
‹‹የውል ይፍረስልኝ›› የክስ ማመልከቻቸውን ተቀብሎ መመርመር የጀመረው የደንቢያ ወረዳ ፍርድቤት የአመልካችን ቃል ተቀብሎ ተጠሪውን አቶ አየልኝ ደርበውን አቅርቦ አነጋገረ። በሁለቱ ወገኖች መካከል ያለውን የክስ መዝገብ በማየትም የእማኞችን ምስክርነትና ተያያዥ ማስረጃዎችን አመሳክሮ ወይዘሮዋ ያቀረቡት ማመልከቻ ተገቢ ያለመሆኑን አረጋገጠ።
ፍርድቤቱ በመጨረሻው ውሳኔ አመልካች ውሉን እንዲፈርሙ ያልተገደዱ በመሆኑና ስምምነቱ በሁለቱ ወገኖች ይሁንታ መፈፀሙ በመረጋገጡ ጥያቄ የቀረበበት የውል ይፍረስልኝ ጉዳይ ተግባራዊ ሊሆን አይገባም ሲል ብይኑን አሳለፈ።
ሐምሌ 11 ቀን 2002 ዓም ተጠሪው አቶ አየልኝ ደርበው ከደንቢያ ወረዳ የተሰጠውን የፍርድ ውሳኔ በአሸናፊነት ተቀብለው ተመለሱ። አመልካች ወይዘሮ ቀለቤ ከፍርድ ቤቱ የተላለፈውን ውሳኔ አክብረው ቢቀበሉም ፍርዱ ተገቢ ነው ሲሉ ለመቀበል ውስጣቸው አልፈቀደም። አሁንም ከፍብለው ቃላቸውን ለማሰማትና ይግባኝ ለማለት ማመልከቻቸውን አዘጋጁ።
አቤቱታ ሁለት…
ወይዘሮዋ ክወረዳው የተላለፈውን የፍርድ ውሳኔ ይዘው ወደዞኑ ከፍተኛ ፍርድቤት ገሰገሱ። የይግባኙን ማመልከቻ የተቀበለው የሰሜን ጎንደር ዞን ከፍተኛው ፍርድ ቤትም የክሱን ፍሬ ነገር ከስሩ መርምሮ ተጠሪውን በማቅረብ አነጋገረ። ፍርድ ቤቱ ለወይዘሮዋ ከወረዳው የተሰጠውን ውሳኔ ዋቢ አድርጎ ማስረጃዎችን ሲመረምር ለሁለቱም ወገኖች ተገቢ ነው ያላቸውን ጥያቄዎች እያነሳ አከራከረ።
በአመልካችና በተጠሪው መካከል የነበረው የሕግ ሂደት እንደተጠናቀቀም ፍርድቤቱ ለመጨረሻ ውሳኔ ቀጠሮ ሰጠ። በቀነ ቀጠሮው ሁለቱንም ወገኖች አቅርቦ የውሳኔ ትዕዛዙን ሲያሰማም የደንቢያ ወረዳ ፍርድ ቤት ያሳለፈውን ውሳኔ በማጽናት ሆነ።
የሰሜን ጎንደር ዞን ከፍተኛው ፍርድቤት በመጨረሻው ቀን በሰጠው ብይን የአመልካቿን የይግባኝ ጥያቄ አለመቀበሉን በመጥቀስ ቀደምሲል ከደንቢያ ወረዳ የተላለፈው ውሳኔ ትክክል መሆኑን አስታወቀ። ወይዘሮዋ ውሉ እንዲፈርስ ያቀረቡት ጥያቄ አግባብ ባለመሆኑም ፍርድቤቱ የአቤቱታውን ተገቢነት ያላመነበት መሆኑን በማመልከት መዝገቡን ዘጋ።
ወይዘሮዋ በዞኑ ፍርድቤት ያቀረቡት የይግባኝ ጥያቄ አሁንም ተቀባይነት ማጣቱ አሳዘናቸው። ይህኔ ቀለቤ ውስጣቸው በእጅጉ ተከፋ፣ በየቦታው ሲዞሩ ያሳለፉትን አስበውም ድካም ተሰማቸው። ያም ሆኖ ግን ተስፋ መቁረጥ ልባቸው አልዘለቀም። ጥቂት ጊዚያትን በመብሰልሰል የቆዩት ሴት አንድ ቀን ማመልከቻቸውን ዳግም አድምቀው ሊጽፉት ከቁርጥ ውሳኔ ደረሱ።
ወይዘሮ ቀለቤ በአካባቢ የግልግልና እርቅ ሰነድን ከማስመርመር ጀምሮ እስከ ወረዳና ዞን ፍርድ ቤቶች የዘለቀ የይግባኝና አቤቱታ ምልልስ ሲያደርጉ ቆይተዋል። እሳቸው ፍርድ ተዛብቷል፣ ሕግ ተጥሷል ሲሉ ባመለከቱባቸውና ይግባኝ በጠየቁባቸው ቦታዎች ሁሉ ያገኙት እውነት ጥያቂያቸውን የሚመልስ ሆኖ አልተገኘም። አሁንም ግን ይህ ጥያቄ ተገቢውን ምላሽ ሊያገኝ እንደሚገባው ያስባሉ።
አቤቱታ ሦስት…
ወይዘሮዋ ተከታዩን ማመልከቻቸውን ይዘው ወደ አማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ጠቅላይ ፍርድቤት ሰበር ሰሚ ችሎት ቀረቡ። ከዚህ በፊት በየፍርድቤቶቹ ያደረጉትን ክርክርና የይግባኝ አቤቱታዎች መሰረት አድርገውም ፍትህ ይሰጣቸው ዘንድ ጠየቁ።
የክልሉ ጠቅላይ ፍርድቤት ሰበር ሰሚ ችሎት የአመልካቿን የይግባኝ ጥያቄ ተቀብሎ ማስረጃዎችን አገላበጠ። ቀደም ሲል በዞኑ ፍርድቤትና በስር ወረዳው ፍርድቤት የተሰጠውን ውሳኔም ተገቢ ባለው መንገድ ሲመረምር ቆየ። በመጨረሻ ከዚህ በፊት በፍርድቤቶቹ የተላለፈው የፍርድ ሂደት የሕግ ስህተት የለበትም ሲል ወስኖ የወይዘሮዋን ጥያቄ በድጋሚ ውድቅ በማድረግ የቀደመውን ውሳኔ አፀና።
ወይዘሮ ቀለቤ አሁንም ‹‹ይግባኝ›› ሲሉ ያቀረቡት ጥያቄ አልተሳካም። በየደረጃው የተጓዙባቸው የፍርድ ውሳኔዎች እሳቸውን የሚደግፉና ሀብት ንብረታቸውን የሚያስመልሱላቸው አልሆኑም።
ቀለቤ እስካሁን አቤት ያሉባቸው ፍርድቤቶች ሁሉ ሚዛናቸው ለእሳቸው ያለማድላቱን ያውቁታል። በየደረጃው ያገኙት ምላሽም በእሳቸው ላብ የተዋዛ ድካም አርፎበታል።
አቤቱታ አራት…
ብርቱዋ ሴት ዛሬም ተስፋ መቁረጥ ይሉት ስሜት አልያዛቸውም። አሁንም በጀመሩት ቀጥለው ከመጨረሻው ውሳኔ ለመድረስ ትግላቸውን ቀጠሉ። አንድቀን ወደባህርዳር ከተማ ተመልሰውም የክልሉን የሴቶችና ወጣቶች ጉዳይ ቢሮን አንኳኩ። ተከፈተላቸው። በራቸውን ከፍተው ጉዳያቸውን በውል ካደመጡ ጆሮዎች ትኩረትን አላጡም። ሀሳቡን የተረዱ የቢሮው የሕግ ባለሙያዎች ተገቢ ያሏቸውን መረጃዎች መርምረው ለሌላ የፍርድ ሂደት ሰ ነዶችን አዘጋጁ።
ቢሮው አጣርቶ በደረሰበት እውነት እስከዛሬ የነበረው የፍርድ ውሳኔ የሕገ መንግሥቱን አንቀጽ 40 ንዑስ አንቀጽ 3 እና 4ትን የጣሰ መሆኑን አረጋግጧል። ይህ እውነታም የመጨረሻው ዳኝነት የሚወሰነው በሕገ መንግሥት ጉዳዮች አጣሪ ጉባኤ መሆኑን አረጋግጦ ጉዳዩን ለጉባኤው ሊያስተላልፍ ግድ ብሎታል።
ምርመራ…
ቢሮው ባስተላለፈው ውሳኔ መሰረት የፌዴራል ሕገ መንግሥት ጉዳዮች አጣሪ ጉባኤ የቀረበለትን የሕገ መንግሥት የትርጉም ጥያቄ ሲመረምር ቆይቷል። ሰነዶቹን በማጠራት ሂደትም የፍርድቤቶቹን የፍርድ ውሳኔ መሰረት አድርጎ ሕግ የተጣሰበትንና አፈፃፀሙ የተጓደለበትን እውነታ ለማወቅ ጥረት አድርጓል።
ጉባኤው በምርመራ ቆይታው እንዳረጋገጠው በፍርድቤቶቹ በየደረጃው የተሰጡ ውሳኔዎች አርሶአደሩን ከመፈናቀል የማይታደጉና በመሬት የመጠቀም መብትን ተግባራዊ የማያደርጉ መሆናቸውን ለይቷል። በዚህ መነሻነት የተሰጡ ብይኖችም የተቀመጡ ድንጋጌዎችን የሚቃረኑ ስለመሆናቸው አረጋግጧል፡
ምክርቤቱ ከግለሰቧ የቀረበውን አቤቱታ በጥልቀት እንደማየቱ የአገሪቱን ሕጎች ያገናዘበ ውሳኔ ለመስጠት የሚያስችለውን ድንጋጌ በግልጽ አስቀምጧል። መሬት የማይሸጥና የማይለወጥ የህዝቦች የጋራ ንብረት በመሆኑም በሁለቱ ወገኖች መሐል የተደረገው ውል በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ተቀባይነት እንደሌለው በመግለጽ ለመጨረሻው ውሳኔ ደርሷል።
ውሳኔ
በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት በየደረጃው ያሉ የሥር ፍርድቤቶች የአመልካቿን አቤቱታ በማየት ከሕገ መንግሥቱ ድንጋጌዎች ጋር ሳያገናዝቡ ያሳለፉት ውሳኔ ተገቢ ያለመሆኑን ምክርቤቱ ባደረገው የማጣራት ሂደት አረጋግጧል። ከደንቢያ ወረዳ ፍርድ ቤት እስከ ክልሉ ጠቅላይ ፍርድቤት ሰበር ሰሚ ችሎት የተሰጠው ውሳኔ አግባብ ያለመሆኑን የጠቀሰው የምክር ቤቱ ችሎት የአመልካቿን የመሬት ባለይዞታነት መብት በውሳኔው ሂደት አረጋግጧል። ይህ ውሳኔ ተፈፃሚ ይሆን ዘንድም ምክር ቤቱ ለአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ጠቅላይ ፍርድቤት ትዕዛዝ በማስተላለፍ የመጨረሻውን መዝገብ አጠናቋል።
አዲስ ዘመን ግንቦት 22 /2012 ዓ.ም
መልካምሥራ አፈወርቅ