የጥምቀት በዓል በዓለም በሚገኙ የክርስትና እምነት በተለይም የኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮች ዘንድ በድምቀት ይከበራል። የበዓሉ ታሪካዊና ሃይማኖታዊ መሰረት ተመሳሳይነት ቢኖረውም ከሀገር ሀገር ያለው የአከባበር ሥርዓት ደግሞ እንየወጉና ባህሉ መሰረት ለየቅል ነው። ለአብነትም የጥምቀት በዓል የማክበር ልምድ ካላቸው ሀገራት መካከል የተወሰኑትን መርጠን ሥርዓቱ ምን እንደሚመስል ተመልክተናል።
ጥምቀት በግሪክ
በአብዛኛዎቹ የአውሮፓ እና አሜሪካ ሀገራት ዘንድ ገናን ካከበሩ ከ12 ቀን በኋላ ጥምቀትን ስለሚያከብሩ ስያሜውን 12ኛው ምሽት እያሉ ይጠሩታል። በሌላ በኩልም የሶስቱ ንጉሶች ቀን የሚል መጠሪያም አለው። በግሪካውያን ዘንድ ደግሞ ጥምቀት «ታ ፖታ» ወይም ደግሞ «ቴዎፋኒያ» የሚል መጠሪያ አለው።
የበዓሉ ዋዜማ ቀናት ህጻናት ቤት ለቤት እየዞሩ የበዓሉን መምጣት የሚያስተጋባ ዝማሬ ያቀርባሉ። ከዚህ በተጨማሪ ትልቁ የዋዜማ ሥርዓት የሚደረገው በግሪክ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያኖች ነው። ከቤተክርስቲያን ሃይማኖታዊ ሥርዓት አከናውነው የወጡ ቄሶችና ዲያቆናት መስቀልና መልካም መዓዛ ያላቸውን ተክሎችን ይዘው ቤት ለቤት እየተዟዟሩ ቡራኬአቸውን ይሰጣሉ።
አሁን አሁን ክንውኑ እየቀረ ቢመጣም ቆየት ባሉ ጊዜያት ግን ግሪካዊያን ለበዓሉ ማድመቂያ የአቴናን ሃውልት ባህር አቅራቢያ ይዘው በመሄድ በውሃ እንደሚያጸዱት ታሪክ ያስረዳል። በዋናው የጥምቀት ቀን ግሪካውያን ቄሶች የቤተክርስቲያን ልብሳቸውን እንደለበሱ በአውራ ጎዳናዎች ላይ ምዕመናንን አስከትለው በሰልፍ ወደ ወንዝ ወይንም ወደ ጥምቀተ ባህሩ ይሄዳሉ:: ጥምቀት በግሪክ ብሔራዊ ክብረ በዓል ነው፤ በመሆኑም በተለያዩ ከተሞቻቸው ካህናቱ በወታደራዊ ማርሽ ሳይቀር ይታጀባሉ። ከጉዞው በኋላ በጥምቀተ ባህሩ ስፍራ እንደደረሱ ደግሞ የዕለቱ ሃይማኖታዊ ሥነ ሥርዓት በጸሎት እና በቡራኬ ይከናወናል። በመጨረሻ ግን ብዙዎች ጎብኚዎች እና ግሪካውያኑም የሚናፍቁት ሥርዓት ይመጣል።
ለበዓሉ የተመደቡ አንድ ቄስ በአነስተኛ ጀልባ ላይ ቆመው የእጅ መስቀል ወደ ባህሩ ይወረውራሉ። ወዲያውም ይህን ክንውን በአይነቁራኛ ይጠበቁ የነበሩ እና ልብሳቸውን አወላልቀው ለዋና የተዘጋጁ ነዋሪዎች እየተቻኮሉ ወደ ባህሩ ይገባሉ። ከዚያም መስቀሏን ቀድሞ ለማግኘት ሁሉም በየፊናው ይሰማራል። መስቀሉን ያገኘው ሰው በእድሜው መልካም ነገሮች እንደሚያጋጥሙት ግሪካውያኑ ስለሚያምኑ እንደ ጀግና ይቆጠራል። ለፍለጋ የገቡ ሌሎች ሰዎችም ባህሩ ውስጥ በመግባታቸው እንደጥምቀት ይቆጠርላቸዋል። ከዚህ በኋላ ጀግናቸውን አጅበው ወደየቤታቸው በመሄድ በምግብ እና በመጠጥ ሥነሥርዓት በዓሉን ያከብራሉ።
ወግና ልማዳቸውን ያልለቀቁ አንዳንድ ግሪካውያን እናቶች ደግሞ «ሎውኮማዴስ» የተሰኘውን ጣፋጭ ምግብ ያዘጋጃሉ። ምግቡ እንደ አሜሪካውያኑ ዶናት የተሰኘው ምግብ መሰል ሆኖ ከስንዴ ዱቄት የሚሰራ ሲሆን በህጻናት ዘንድ ተወዳጅ ነው። «ፎቶ ኮሊቫ» የተሰኘው ባህላዊ
ምግብ ደግሞ በአንዳንድ ገጠራማ አካባቢዎች የሚዘጋጅ ጥንታዊ ምግብ ነው። ይህ ምግብ ከባቄላ እና አተር ዝርያዎች ይሰራል። ከሎሚና እና ከወይራ ዘይት ጋር በሾርባ መልክ የሚዘጋጅ ነው። ግሪካውያኑም በእርሻ ቦታቸው ላይ ተገኝተው ለአዕዋፍ እና ለከብቶቻቸው ሳይቀር እየበተኑ ይመግቡታል። በረከት የሚያመጣ እና መርገምን የሚያስቀር ነው ብለው ስለሚያስቡ በተለይ ባህላቸውን ያልዘነጉ አዛውንቶች በጥምቀት ሰሞን ምግቡን ያዘጋጃሉ።
ጥምቀት በግብፅ
አሁን ደግሞ የግብጽን የጥምቀት አከባበር እንመልከት። ግብጻውያን የኮፕቲክ ኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮች ከተቀረው የአገሪቷ ሙስሊም ህብረተሰብ ጋር ሲነጻጸሩ በቁጥር እጀጉን ያንሳሉ። ይሁንና ጥምቀትን በደመቀ ሃይማኖታዊ ሥርዓት ማክበራቸውን ሳያስተጓጉሉ ለዛሬ ደርሰዋል።
በግብፅ ኮፕቲክ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ልክ እንደ ኢትዮጵያውያን ሁሉ ጥምቀት በዓልን የሚያከብሩት ጥር 11 ቀን ላይ ነው። በበዓሉ ቀን ህጻናት እና አረጋውያን ሳይቀሩ በቤተክርስቲያን በመሰባሰብ ጸሎት እና መዝሙር ለአምላክ ያቀርባሉ። በዕለቱ በሃይማኖታዊ ሥርዓቱ መሰረት በዓሉን ማክበር ጥብቅ ህግ በመሆኑ አብዛኛዎቹ የኮፕቲክ ኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮች ጥምቀትን በቤተክርስቲያን ሊያሳልፉ ይችላሉ።
በጥምቀተ ባህሩ የተሰባሰቡ ምዕመናን እና የሃይማኖት አባቶች የአንድነት ጸሎታቸውን ካጠናቀቁ በኋላ ትልቅ መስቀል ላይ መብራት እና አበባ ተደርጎ ይዘጋጃል። የተንቆጠቆጠው ትልቅ መስቀል በሁለት ሰዎች ተይዞ በጥምቀተ ባህሩ ላይ እንዲንሳፈፍ ይደረጋል። ከዚያም የሐይማኖት አባቶች ህዝቡን ያጠምቃሉ። ቀደም ባሉ ጊዜያት በተለይም ግብጻውያን ክርስቲያኖች በአባይ ወንዝ ዳርቻ ነበር ጥምቀትን የሚያከናውኑት። በጥምቀት በዓሉ የሸንኮራ አገዳ መብላት ሥነሥርዓትም ይደረጋል። አሁን ላይ በአነስተኛ ገንዳዎች ነው በዓሉ በብዛት የሚከናወነው።
ጥምቀት በሩሲያ በዩክሬን
ሩሲያዊያን እና ዩክሬናውያንም ጥምቀትን የሚያከብሩት በዛሬው ዕለት ነው። በቀኑ በተለይ ሩሲያዊያን በከፍተኛ ቅዘቃዜ ምክንያት በረዶ በሰሩ ወንዞችና ሀይቆቻቸው ላይ የመስቀል ቅርጽ ያላቸው የበረዶ ጉድጓዶችን ያዘጋጃሉ። ቦታው እንደጥምቀተ ባህር ሆኖ ያገለግላል። ውሃውም ሃይማኖታዊ ሥርዓቱን በሚያስፈጽሙ የሩስያ ኦርቶዶክስ ቄሶች በአራቱም አቅጣጫ መስቀለኛ ተደርጐ ይባረካል።
ከዚያም በአካባቢው የተሰባሰቡ ተሳታፊዎች በቀዝቃዛው ውሃ ውስጥ ገብተው ይጠመቃሉ። በዚህ ጊዜ ውሃ ውስጥ ሶስት ጊዜ ብቅ ጥልቅ እያሉ አፍንጫቸውን ይዘው ነው የሚጠመቁት። ሲወጡ በፍጥነት ሙቀት እንዲያገኙ በሚል ቤተሰብ አሊያም ጓደኞቻቸው ፎጣ እና ወፍራም ልብሶችን ይሰጧቸዋል።
ሩሲያውያኑ በበረዶአማው ውሃ ከተጠመቁ በኋላ ኃጢያታቸውን በሙሉ አምላካቸው ይቅር እንዳላቸው ያምናሉ። በመሆኑም የዕለቱን የጥምቀት ሥርዓት ለመከወን የታመመ ሰው ቢሆን ቅዝቃዜውን እቋቋመዋለሁ ብሎ ካሰበ ሊሳተፍበት ይችላል። በመጨረሻ ደግሞ የጥምቀተ ባህሩን ውሃ በተለያዩ እቃዎች በመያዝ ወደየቤቶቻቸው ይሄዱና ቤታቸውን ይረጫሉ። በቤተክርስቲያኖች ደግሞ ህዝብ ተሰብስቦ ጸሎት ያደርሳል። መሪያቸው ቭላድሚር ፑቲን ጭምር የዚህ ሥነሥርዓት የረጅም ጊዜ ተሳታፊ ናቸው።
ጥምቀት በዩክሬን በተመሳሳይ ከወቅቱ ጋር ተያይዞ በቀዝቃዛ ውሃዎች ውስጥ ነው የሚከበረው። በአብዛኛው ከሩሲያውያኑ ጋር የተመሳሰለ ሃይማኖታዊ ሥርዓትም አለው። ጥምቀት የተቀደሰ፣ ንፁህና በሽታን የሚፈውስ እንደሆነ ይታመናል፡፡ ከበረዶ የተሰራ ትልቅ መስቀል ይቆማል ዳር እና ዳር ደግሞ የመላዕክ ምስል ያላቸው እና ባለክንፍ የበረዶ ሃውልቶች ይሰራሉ። ‹‹ዮዳን›› ቀን በሚሉት የጥምቀት ዕለት በጆርዳን ወንዝ ዳር ሄደው ይጠመቃሉ።
ጥምቀት በሜክሲኮ
ላቲኖች በስፔን ቅኝ ግዛት ስር የኖሩ በመሆናቸው በአብዛኛው የስፔኖቹን የጥምቀት አከባበር ሥርዓት ይከተላሉ። በተለይ በሜክሲኮ እና በጓቲማላ ከገና ይልቅ በጥምቀት ነው ለህጻናት የተለያዩ ስጦታዎች የሚበረከትላቸው።
ሜክሲኮአውያን ጥምቀትን የሚያከብሩት እ.አ.አ. ጥር 6 ቀን ነው፤ ቀኑንም የሶስቱ ጠንካራ ሰዎች ‹‹በዓል›› እያሉ ይጠሩታል። ሶስቱ ሰዎች ኢየሱስ ክርስቶስ በተወለደ ጊዜ በኮከብ ተመርተው የጠየቁ ሰብአሰገል ምሳሌዎች ናቸው። በዋዜማው ህጻናት ጫማዎቻቸውን አውልቀው ለሶስቱ ሰዎች ደብዳቤ ይጽፋሉ። የሚፈልጉትን ስጦታዎችም ጽፈው በጫማዎቻቸው ውስጥ ያስቀምጣሉ። አንዳንድ ጊዜም በሂሊየም ጋዝ በተሞላ ፊኛ አድርገው ወደሰማይ ይልኩታል። በጠዋት ሲነቁም የሚፈልጉትን ስጦታ ለቤተሰባቸው ይሰጣቸዋል።
ሜክሲኮአውያን የጥምቀት በዓልን ልዩ ልዩ ባህላዊ አልባሳትን አድርገው፣ በፈረስ እና በተለያዩ ክፍት መኪናዎች በጎዳና ላይ በመዘዋወር ቀኑን ያደምቁታል። ከሁሉም በላይ ግን በትልቅ ክብ ቅርጽ የሚሰራው ኬክ ለበዓሉ አስፈላጊ ነው። ሜክሲኮዎች ጥምቀትን ሲያከብሩ ያለኬክ ማሰብ ከባድ ነው። በመሆኑም ከእንቁላል እና ከዱቄት በጣፋጭ መልክ የተዘጋጀው ኬክ ውስጡ በትንሽ የተሰራ እና የኢየሱስ ክርስቶስን የልጅነት መስል የሚወክል አሻንጉሊት ይደረግበታል። ኬኩን ሲበላ አሻንጉሊቷን ያገኘ ሰው ታማሌስ የተባለውን ከስጋ የሚሰራ ባህላዊ ምግብ በሌላ ቀን እንዲያዘጋጅ ይደረጋል። እንዲህ እንዲህ እያለ ቀኑን ሜክሲኮአውያን ዘመድ አዝማዶቻቸውን እየጠየቁ በፌሽታ ያሳልፉታል። በዚህ መልኩ ጥምቀት በተለያዩ የዓለም አገራት በድምቀት ይከበራል። የማይረሳ ትዝታም ጥሎ ያልፋል።
አዲስ ዘመን ጥር 11/2011
ጌትነት ተስፋማርያም