አገራችን በታሪኳ እንደዛ ያለ የተከበረና ታላቅ ሸንጎ፣ ስብሰባ በመዲናዋ አዲስ አበባ አስተናግዳ አታውቅም። ወደ ፊትም ታስተናግዳለች ብሎ ማሰብ ይቸግራል። ግርማዊነታቸውም ሆኑ ኢትዮጵያ እንደነሱ ያሉ ጥቁርና ከበባድ እንግዶችና ታዳሚዎች በአንድ ላይ “የመሸበት እንግዳ!” ብለው ፤ “ ቤት ለእንግዳ ! ግቡ ! “ ብለው አያውቁም። እንግዳ ማስተናገድ አኩሪ ባህላቸው እማይደል። እግር አጥበው ፣ ቤት ያፈራውን አቅርበው፣ መኝታ ለቀው አደግድገው አስተናግደዋል። የእነዚህን እንግዶች ማንነት ለማወቅ ደጋግማችሁ ብትሞክሮም ስለማትደርሱባቸው እኔው ልንገራችሁ። በ1964 ዓም በሸገር ታድመው የነበሩት የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የፀጥታዊ ምክር ቤት አባላት ናቸው። ለሀገሬው ቀጋ ፣ ለውጭ አልጋ የነበረው ንጉሣዊው አገዛዝ በዲፕሎማሲው ዘርፍ ደርሶበት የነበረውን ከፍታ ልብ ይሏል። ዕድሜ ለግብጽ ዛሬ ሀገራችን አብራ ባቋቋመችው የመንግሥታቱ ድርጅት ፤ ጠብ እርግፍ ብላ ባስተናበረችው የፀጥታው ምክር ቤት ክስ ቀርቦባታል። ለዛውም ከማህፀኗ ፈልቆ በሚገማሸረው የዓባይ ወንዝ የተነሣ። የፀጥታው ምክር ቤት የመጀመሪያ ስብሰባውን በለንደን በ1938 ዓ.ም “ የእንግሊዝ ስትንፋስ “ ተብሎ በሚታወቀው ዌስት ምኒስትር አጠገብ በሚገኝ ቤተ ክርስቲያን እንደ ተካሄደ ይወሳል። የፀጥታው ምክር ቤት ከቋሚ መቀመጫው ከኒውዮርክ ውጭ ስብሰባ ካካሄደባቸው ሌሎች አገራት መካከል በፓናማ፣ ፓናማ ሲቲ እና በስዊዘርላንድ ጄኔቫ ይገኙበታል።
ምክር ቤቱ 15 አባላት ሲኖሩት ከእነዚህ ውስጥ 5ቱ ቋሚ አባላት ናቸው። እነዚህ ቋሚ አገራት 2ኛውን የዓለም ጦርነት በአሸናፊነት የደመደሙ ናቸው። ቻይና፣ ፈረንሳይ፣ ሩሲያ፣ ዩናይትድ ኪንግደምና ዩናይትድ ስቴትስ የምክር ቤቱ ቋሚ አባላት ሲሆኑ አስገዳጅ የውሳኔ ሐሳብን፣ አዳዲስ አገራትን በአባልነት መቀበል፣ ዋና ጸሐፊው ሹመት ላይና በሌሎች ጉዳዮች ላይ ድምፅን በድምፅን የመሻር መብት / ቬቶ ኦፍ ፓወር / አላቸው። አሜሪካ እሥራኤልን የሚመለከቱ በመቶዎች የሚቆጠሩ የውሳኔ ሐሳቦችን ድምፅን በድምፅ የመሻር መብቷን ተጠቅማ ውድቅ በማድረግ የሚስተካከላት የለም። ከቋሚ አባላቱ ውጭ ያሉ 10 አገራት በየሁለት ዓመቱ አህጉራትን እንዲወክሉ ታሳቢ ተደርጎ ይሰየማሉ። የፀጥታው ምክር ቤት ፕሬዚዳንት ከአባላት መካከል በየወሩ በዙር ይመረጣል።
የተባበሩት መንግሥታት በተደጋጋሚ ዘመኑን የሚዋጅ ተቋም እንዳልሆነ ስሞታ ይቀርብበታል። በሥሩ ካሉ ስድስት ተቋማት መካከል አስገዳጅ ውሳኔ የማሳለፍ ሥልጣን ያለው የፀጥታው ምክር ቤት ብቻ ነው። አሳታፊና ፍትሐዊ አይደለም ክስ ከሚቀርብባቸው አደረጃጀቶችና አሠራሮች ቀዳሚው የማይገሰስ ሥልጣን ያለው ይኸው ምክር ቤት። ታላቁን የህዳሴ ግድብ አስመልክቶ ግብጽ ኢትዮጵያን የከሰሰችበትን ማመልከቻ የተቀበሉት የወቅቱ የፀጥታው ምክር ቤት ፕሬዚዳንት የእስቶኒያ የውጭ ጉዳይ ሚንስትር ኡርማስ ሬንሳሉ ናቸው። ለመሆኑ የግብፁ አቻቸው ሳሜህ ሾክሪ ማመልከቻው አልበቃ ብሏቸው በአናቱ በቀጭኑ ሽቦ በስልክ ምን አሏቸው ? በነገራችን ላይ እኝህ” ዲፕሎማት” ስለ ታላቁ የህዳሴ ግድብ በተነሳ ቁጥር ዲፕሎማሲያዊ ባልሆነ ቋንቋ የመጣላቸውን በመናገር ይታወቃሉ።
“ኢትዮጵያ ግድቡን በምንም ዓይነት ሁኔታ መሙላት የለባትም። ” በማለት ቡራ ከረዩ ከሚሉ ሰው ጋር መደራደር በራሱ ፈታኝ መሆኑን አበክሮ መገመት ይቻላል። አበው እማት የ…..ተቆጢታ እንዲሉ፣ ለፀጥታው ምክር ቤት የተላከው የፈርኦኖች ክስ ይዘት ምን እንደሚመስል ፈረንጆች ከፈረሱ አፍ እንዲሉ፤ የመካከለኛው ምሥራቅና የሰሜን አፍሪካ / MENA / ድረ ገፅ ለንባብ ካበቃው ዘገባ የቃረምኩትን ላጋራ።
ክሱ “ ኢትዮጵያ በመጠናቀቅ ላይ ስላለው ግድብ ( የታላቁ ህዳሴ ግድብን መሆኑ ነው፤ ) አሠራር ላይ የተጀመረውን ድርድር አቋርጣ መውጣቷንና በዚህም ሥጋት እንደተፈጠረባት የሚያትት ነው። ከስምንት ዓመታት በላይ አቋሟን እየቀያየረች ድርድሩን ስታስተጓጉልና ስታደናቅፍ እንዳልኖረች ዛሬ ኢትዮጵያን በዓለም አቀፍ መድረክ ለማሳጣት” ለመደራደር ዝግጁ ነኝ ፤ “ስትል መሙለጭለጯን ገፍታበታለች። ግብፅ መጀመሪያ አሜሪካ በድርድሩ እጇን እንድታስገባ በማድረግ ድርድሩን ከተፋሰሱ አገራትና ከአህጉራዊ ተቋማት አርቃ ቁጭ ብላ የሰቀለችውን ዛሬ ቁማ ማውራድ ሲሳናት ከአፈርኩ አይመልሰኝ እንዲሉ አሁን ደግሞ ወደ ፀጥታው ምክር ቤት ወስዳዋለች። ኢትዮጵያንም ድርድሩን በማጓተት ጊዜ በመግዛት ታክቲክና በግትርነት ከሣታለች። ይሄ ክሥ በመሠረቱ በሁለት ምክንያቶች ውሃ አያነሳም። በመጀመሪያ በባለብዙ የተፋሰሱ አገራት መድረክም ሆነ በባለሦስትዮሽ ድርድሮች እግሯን ስትጎትት የኖረችው ራሷ ግብጽ መሆኗ ጸሐይ የሞቀው የአደባባይ ሐቅ ነው። ሁለተኛው በሜቴክ ተንሰራፍቶ የኖረው ብልሹ አሠራርና ሙስና ግድቡን በማጓተቱ ለግብፅ ያለምንም ወጭ ጊዜ ስለገዛላት ነው። ዛሬ ሀገራችን በየመድረኩ በአሜሪካ አደራዳሪነት የተካሄደውን ስምምነት አልፈርምም ብላለች በሚል የፈጠራ ክስ የምትጎተተው። የዓለም አቀፉ ሚዲያ ዜና ማሟሻ የሆነችው።
የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳሜህ ሾክሪ ለፀጥታው ምክር ቤቱ ያስገቡትን ክሥ አገራቸው ምን ያህል ለድርድር ዝግጁ እንደሆነች የሚያረጋግጥና መውጫ ከሌለው የድርድር ቅርቃር የሚያወጣ የማሪያም መንገድ ሲሉ ያሞካሹታል። እዚህ ላይ የግብፅ ዲፕሎማሲ በመርህ የማይመራና የማይጨበጥ ጉም መሆኑን ያመለክታል። በየትኛውም የዓለም አቀፍ ዲፕሎማሲ አስተምህሮ ክሥ ለዛውም ሀሰተኛ ክሥ ለድርድር እና ለመፍትሔ በግብዓትነት ጥቅም ላይ ውሎ አያውቅም። ግብፅ በዚህ አታበቃም ኢትዮጵያን ዓለም አቀፍ ሕጎችን በመጣስና ድርድሩንም ከልብ እንዳልያዘችው አድረጋ በዚሁ ክሥ ለማሳጣት ሞክራለች። ጩኽቴን ቀሙኝ እንዲሉ ሀገራችንን ጨምሮ የተፋሰሱ አገራት ሲያቀርቡባት የነበረውን ክሥ ገልብጣ አይኔን ግንባር ያድርገው ብላ ከሣሽ ሆና መጥታለች። ይህን የግብፅ ወለፈንዲ ፣ ማፊያ ቀመስ እና ሥነ ምግባር የጎደለውን ዲፕሎማሲ ነው እንግዲህ እነ ያየሰው ሽመልስ ያለ ሐፍረት አፋቸውን ሞልተው የሚያሞካሹት። በተቃራኒው የሀገሪቱን መሪና የዲፕሎማሲ አካሄድ የሚያናንቁት። እውነታው ግን ለየቅል ነው።
ኢትዮጵያ በዓባይ ወንዝ ላይ እየገነባች ባለችው የታላቁ ህዳሴ ግድብ ምክንያት፣ ግድቡ በግርጌ የተፋሰስ አገሮች ላይ ሊኖረው የሚችለውን ተጽዕኖ ለመቀነስ ያስችላል የተባሉ ተከታታይ ውይይቶችን ላለፉት ስምንት ዓመታት ከግብፅና ከሱዳን ጋር አድርጋለች። ሆኖም የግድቡን የውሃ አሞላልና አለቃቀቅ የተመለከቱ ውይይቶች በተለያዩ ደረጃዎች ሲካሄዱ የቆዩ ቢሆንም እዚህ ግባ የሚባል ውጤት አለማምጣታቸውን እየታዘብን ነው። ድርድርና ውይይቱ ከጫፍ ሊደርስ ስንዝር ሲቀረው ግብፅ እንደ ልማዷ ራሷን በማግለል ጊዜ ትገዛለች። በዲፕሎማሲያዊ ማህበረሰብ መተላለፊያ / ኮሪደር / ታሻጥራለች። ታሴራለች። እንዲህ እንዲህ እያለች ድርድሩ በግድቡ ውሃ አሞላልና አለቃቀቅ ብቻ ሳይገደብ የውሃ ክፍፍልን ያካተት እንዲሆን አዲስ ቅድመ ሁኔታ ይዛ ብቅ አለች። ሰበብ አስባብ እየደረተች እዚህ ብትደርስም በዓባይ ወንዝ ላይ የሚገነባ ማንኛውም ግድብ በግብፅ ህልውና ላይ እንደተቃጣ እቆጥረዋለሁ ከሚለው ዘመናትን ከተሻገረው ግትር አቋሟ ግን ለማፈግፈግ ተገዳለች። ይሁንና ልቧ እያወቀ ተግባራዊ ሊሆኑ የማይችሉ ጥያቄዎችን መደርደሩን ቀጥላለች። ግድቡ ከ12 እስከ 21 ዓመታት ባለው ጊዜ እንዲሞላ፤ ከግድቡ በየዓመቱ 41 ቢሊዮን ኪዩቢክ ሜትር ውሃ እንዲለቀቅላት በመጠየቅ የሀገራችንን ሉዓላዊነት ተዳፍራለች። ኢትዮጵያ የታላቁን ህዳሴ ግድብ ውሃ ለመሙላት የግብፅ ይሁንታና ቡራኬ እንደማያስፈልጋት በመግለፅ ጥያቄዋን ውድቅ በማድረግ የግድቡ ውሃ ሙሊት ከአራት እስከ ሰባት ዓመታት ባለው ጊዜ እንደሚጠናቀቅና ከግድቡ የሚለቀቀው ውሃም በየዓመቱ ከ31 ቢሊዮን ኪዩቢክ ሜትር እንደማይበልጥ አቋሟን ግልፅ አድርጋለች። የሱዳን ሥጋት ከግብፅ የተለየ ነው። የግድቡ ግንባታ በጥራት ስለመካሄዱ ማረጋገጫ ትፈልጋለች። ግድቡ እየተገነባ ያለው ድንበሯ አጠገብ ስለሆነ አያድርገውና አንድ ነገር ቢሆን ስለምትጎዳ። የኢፌዴሪ መንግሥት በሥጋት ላይ ያነጣጠረው የሱዳን ሥጋት መነሳቱ ተገቢ እንደሆነና ግድቡ ግን ምንም ሥጋት በማይፈጥር የጥራት ደረጃ ሳይንሳዊ በሆነ አግባብ እየተረጋገጠ መከናዎኑን በተደጋጋሚ መተማመኛ መስጠቱን መንግሥት ይፋ አድርጓል ።
ዳሩ ግን ግብፅ የዓረቡ ዓለም መሪ በመሆኗና በእሥራኤል ፍልስጤም ጉዳይ ወሳኝ ሚና ስላላት አሜሪካንን በመጠቀም የግድቡን ጉዳይ ዓለም አቀፍ አድርጋዋለች። ይህን የግብፅ ቁማር በውል ሣንመረምር አሜሪካንንና የዓለም ባንክን “ በታዛቢነት “ እንዲገቡ መፍቀዳችን በተዘዋዋሪ ሌሎች የተፋሰስ አገራትን የድርድሩ አካል እንዳይሆኑ በማድረግ የመደራደር አቅማችንን ከማኮስመኑ ባሻገር ቀደም ሲሉ የተሠሩ ሥራዎችን በዜሮ በማባዛት ለግብፅ ብልጣ ብልጥ የድርድር ቁማር በር ከፍተናል። ሆኖም መንግሥት የፈጠረውን ስህተት ተገንዝቦ ከአሜሪካው ድርድር መውጣቱ ዋናውን እንዳይበላ አድርጎታል። ሰሞኑን ደግሞ ከእነጭራሹ ወደ ዋሽንግተኑ ድርድር እንደማይመለስ እቅጩን ተናግሯል ።
በዚያ ሰሞን በፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ ለተመራው የኢትዮጵያ የዲፕሎማሲ ልዑክ ከተፋሰሱ አገራት ሦስቱ የግብፅን ግትር አቋም በማውገዝ ከኢትዮጵያ ጎን ከመቆም አልፈው፤ ሁሉም የዓባይ ተፋሰስ አገሮች በተፈጥሮ ሀብታቸው የመጠቀም መብታቸው መረጋገጥ እንዳለበት የሩዋንዳ፣ የኡጋንዳና የኬንያ መሪዎች ጠይቀዋል። በተለይ ኡጋንዳ የተፋሰሱ አገሮች መሪዎች አስቸኳይ ስብሰባ እንዲጠራ ማሳሰቧ ይታወሳል። ይህ አሁንም እንዳልረፈደ ያሳያል። ስለሆነም መንግሥት ድርድሩን የአፍሪካ፣ የተፋሰሱ አገራት ጉዳይ ማድረግ፤ በ2002 ዓ.ም የተፈረመውን የትብብር ማዕቀፍ ስምምነት (Cooperation Frame Work Agreement) እና በ2007 ዓ.ም በግብፅ፣ በኢትዮጵያና በሱዳን መካከል የተፈረመውን የመርሆዎች መግለጫ (Declaration of Principles) መልሶ የመደራደሪያ ሰነዶች አካል ማድረግ ያሻል።
ዓረቦች ውሾች ይጮሐሉ ግመሉ ግን ጉዞውን ቀጥሏል እንዲሉ፤ የመጀመርያ ምዕራፍ የውሃ ሙሌት እንደሚከናወንና በዚህም 4.9 ቢሊዮን ሜትር ኪዩብ ውሃ እንደሚያዝ፤ ሁለተኛው ደግሞ በ2013 ዓ.ም የዝናብ ወቅት ለሁለት ወይም ሦስት ወራት እንደሚከናወንና 13.5 ቢሊዮን ሜትር ኪዩብ ውሃም በዚህ ወቅት እንዲሞላ ተደርጎ፣ የመጀመርያዎቹ ሁለት ተርባይኖች ኃይል እንዲያመነጩ እንዲሁም ሌሎቹ ተርባይኖች ላይ የኃይል ማመንጨት ሙከራ እንደሚደረግ ተመልክቷል። ሁለተኛው ዙር የውሃ ሙሌትም በተመሳሳይ በተለያዩ ምዕራፎች ተከፋፍሎ እንደሚከናወን በግድቡ የሚጠራቀመው የውሃ መጠን 49.3 ቢሊዮን ሜትር ኪዩብ እስከሚደርስ መሆኑን ኢትዮጵያ የህዳሴ ግድቧን የውሃ አሞላል በተመለከተ የያዘችውን አቋም ይፋ ባደረገችበት ሰነድ አትታለች።
እንደ መውጫ
ኔልሰን ማንዴላ በእሥር ላይ እያለም ሆነ ነፃ ከወጣ በኋላ ከአፓርታይድ የመጨረሻው መሪ ኤፍ ደብሊው ዴክላርክ ጋር ፓርቲውን የአፍሪካ ናሽናል ኮንግረስን ወክሎ ከመደራደሩ በፊት መጀመሪያ ያደረገው የእሱንም ሆነ የፓርቲውን የቅድመ ድርድር ጥንካሬና ድክመት መገምገም ነበር። እኛም ለሦስትዮሹ በተለይ ከግብፅ ጋር ለምናደርገው ድርድር እንዲሁም በዲፕሎማሲያዊ መስክ ለምንከፍተው ዘመቻ ያግዘን ዘንድ ድክመታችንና ጥንካሬያችን አንጥረን በመለየት ድክመታችንን መቅረፍ ጥንካሬያችን ማስቀጠል ይጠበቅብናል። ግብፅ ሕጋዊና ቴክንካዊ መከራከሪያዎቿ እንደማያዋጣት ስታውቅ መጀመሪያ ወደ ዋሽንግተን አሁን ደግሞ ወደ ፀጥታው ምክር ቤት በመውሰድ ኢትዮጵያ ላይ ፖለቲካዊ ጫና በመፍጠር እጇን ጠምዝዛ ወደ ድርድር ለማምጣት እግሯ እስኪቀጥን እየኳተነች ነው። የፀጥታው ምክር ቤት በተለያዩ አምስቱ ቋሚ አባላት ፖለቲካዊ፣ ታሪካዊና ኢኮኖሚያዊ በሆኑ ጠባሳዎች እና በየአገራቱ የውጭ ግንኙነት ፖሊሲ የተነሳ ከአሜሪካና ከግብፅ ጎን ይቆማሉ ተብሎ ባይታሰብም ሀገራችን የተቀናጀና የተናበበ ዲፕሎማሲያዊም ሆነ የፖለቲካ ዘመቻ ማድረግ ይጠበቅባታል። ለፀጥታው ምክር ቤት 15 አባላት በተለይ ለ5ቱ ቋሚ አባላት ማለትም ቻይና ፣ ፈረንሳይ፣ ሩሲያ፣ ዩናይትድ ኪንግ ደምና ዩናይትድ ስቴትስ ስለ ግድቡም ሆነ ስለቀደሙ ድርድሮች በቂ መረጃ መስጠትና የግብፅን የፈጠራ የሰለባነት ትርክት ማጋለጥ ይገባታል። እንግዲህ የፀጥታው ምክር ቤት የዓለምአችን ከፍተኛው መደምደሚያ ተቋም ነው። ሀገራችን አበክራ ግብፅ ከዚህ በኋላ ወዴት ልታመራ እንደምትችል በደንብ ተንትና ዙሪያ መለስ ዝግጅት ማድረግ ይጠበቅባታል። ምን አልባት በቀጣይ ልትወስደው ላሰበችው ወታደራዊ ጥቃት ሰበብ ምክንያት / ጀስቲፍኬሽን / ፍለጋ ይሆናል ፖለቲካውን እያጓነችው ያለው !?
“ የኢትዮጵያ ታላቁ የህዳሴ ግድብ ዓድዋችን ነው ! “ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ሒሩት ወልደ ማርያም፤
ከመንግሥታችን ጎን በመቆም ሉዓላዊነታችንንና ብሔራዊ ጥቅማችንን እናስከብር ! ! !
አዲስ ዘመን ግንቦት 8/2012
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን) fenote1971@gmail.com