
ኢትዮጵያ ለኦሊምፒክ ድል አዲስ ባትሆንም ውጤቷ በአትሌቲክስ ብቻ የተገደበ ስለመሆኑ እርግጥ ነው።ተሳትፎዋም ቢሆን ከቦክስ፣ ብስክሌትና ውሃ ዋና ስፖርቶች ያልዘለለ ነው።ጃፓን በመዲናዋ ቶኪዮ ከአራት ወራት በኋላ በምታስተናግደው የ2020 ኦሊምፒክ ግን ኢትዮጵያ በታሪኳ አዲስ በሆነ ስፖርት ተሳታፊ መሆኗ ታውቋል።ይህ ብስራት የተሰማው ከኢንተርናሽናል ቴኳንዶ ስፖርት ሲሆን፤ ወጣቱ አትሌት ሰለሞን ቱፋ የታሪኩ ባለቤት መሆኑን አረጋግጧል።ሰለሞን ለዚህ ስኬት እንዲበቃ ከስድስት ዓመታት በላይ በአሰልጣኝነት አብሮት የደከመው ማስተር አዲስ ኡርጌሳም ከዚህ ታሪክ ባለቤትነት ጋር አብሮ ይነሳል።በአፍሪካ ካሉ ስመ ጥር የወርልድ ቴኳንዶ አሰልጣኞች ትልቁ ነው።በዓለም አቀፉ ወርልድ ቴኳንዶ ፌዴሬሽን ደግሞ ብቸኛው ኢትዮጵያዊ የአሰልጣኞች እና የዳኞች አሰልጣኝ ነው።
የአፍሪካ ወርልድ ቴኳንዶ አሰልጣኞች ሊቀመንበር በመሆንም እያገለገለ ነው።ማስተር አዲስ ዑርጌሳ።በ2010/11 የውድድር ዓመት በተሳተፈባቸው ዓለም አቀፍ እና አህጉራዊ ውድድሮች ላይ ባልተመቻቸ ሁኔታ በጥቂት ስፖርተኞች ተሳትፎ 5 ወርቅ 2 ብር እና 3 የነሀስ ሜዳሊያዎች በሚያሰለጥናቸው ስፖርተኞች አማካኝነት ለኢትዮጵያ አስገኝቷል።ባለፈው ሪዮ ኦሊምፒክ የማጣሪያ ውድድሮች በሁለቱም ፆታ ያሰለጠናቸው ተወዳዳሪዎች ወደ ታላቁ መድረክ ለማለፍ ከጫፍ ደርሰው ሳይሳካላቸው ቀርቷል።ከሃያ ዓመታት በላይ በስፖርቱ ውስጥ ያሳለፈው ማስተር አዲስ ዛሬ ላይ ህልሙ እውን ሆኖ ታላቁ የስፖርት መድረክ ላይ ደርሷል።በአገራችን ወርልድ ቴኳንዶ ስፖርት ተስፋና ስጋት እንዲሁም ሌሎች በርካታ ጉዳዮችን ከአዲስ ዘመን ጋር ባደረገው ቃለ ምልልስ እንደሚከተለው ይናገራል።
አዲስ ዘመን፡- በዓለም ላይ ስጋት የሆነውን የኮሮና ቫይረስ ተከትሎ ኦሊምፒክ ሊራዘም እንደሚችል ስጋት አለ፣ ምናልባት የሚራዘመው ለረጅም ጊዜ ከሆነ እንደ ወርልድ ቴኳንዶ አይነት ብዙ ልፋትና ዋጋ የሚከፈልባቸው የማጣሪያ ውድድሮች ዳግም ወደ ማጣሪያ የሚገቡበት አጋጣሚ ይኖራል?
ማስተር አዲስ፡- አይመስለኝም፤ እስካሁንም እንዲህ የሚል ህግ አላየሁም።ምናልባት ከአንድ ዓመት በላይ የሚራዘም ከሆነ ሊባል ይችል ይሆናል።ነገር ግን አሁን ባለው ሁኔታ እስከ መጨረሻው ነገሮችን ሳይመለከቱ ወደዚህ ውሳኔ ይገባሉ የሚል እምነት የለኝም፤ ቢያራዝሙ እንኳን ጥቂት ወራትን ሊሆን ይችላል የሚል ግምት ነው ያለኝ።
አዲስ ዘመን፡- የኦሊምፒክ ማጣሪያውን አልፋችሁ ትልቅ ደረጃ ላይ ስትደርሱ የነበረው ሂደት እንዴት ነበር?
ማስተር አዲስ፡- ማጣሪያው ወደ 34 የአፍሪካ አገራት የተሳተፉበት ትልቅ ውድድር ነበር።ለአራት ዓመታት ያደረግነውን ዝግጅትም ከ100 በላይ ከሚደርሱ ስፖርተኞች ጋር ተወዳድረን ነው የመዘንነው።እንደሚታወቀው ሰለሞን ሶስቱን ዓመት እስከ አውሮፓ በመጓዝ በተለያዩ ውድድሮች ላይ ነው ያሳለፈው።በቱርክና በፖላንድ ከተሳተፈባቸው ውድድሮች ባሻገር የአፍሪካ ዋንጫንና ፕሬዚዴንሺያል ዋንጫን ጠቅልሎ በመውሰድ በአፍሪካም ኮከብ በመባል ነበር ያጠናቀቀው።ይህም ወደ ማጣሪያው ሲገባ ትልቅ ደረጃን ይዞ በመሆኑ ውጤቱም መልካም ሆኗል፡፡
አዲስ ዘመን፡- ቀደም ባሉት ዓመታት በወርልድ ቴኳንዶ ስፖርት ውጤት ይመጣበታል የሚል ብዙም እምነት አልነበረም፣ ይህን አስተሳሰብ ሰብሮ ፈታኝ የሆኑ ማጣሪያዎችን በማለፍ ለኦሊምፒክ ስፖርተኛን ማብቃት ከባድ መሆኑን መገንዘብ አይከብድም፣ ነገር ግን ይህ ስኬት ትልቅ ቦታ ተሰጥቶታል ብለህ ታምናለህ?
ማስተር አዲስ፡- በማጣሪያው ላይ ከሰለሞን ጋር ውድድር ያደረገው ስፖርተኛ በዓመት ውስጥ ከ13 ያላነሱ ውድድሮችን አድርጓል፤ በዓለምና በአፍሪካ ያለው ደረጃም በጣም ጥሩ ነው።ሰለሞን በአንጻሩ ከአራት ያልበለጡ ውድድሮች ላይ ብቻ ተሳታፊ ሆኖ ነው ለአሸናፊነት የበቃው።ይህንን ድል መድገም አይቻልም ነገር ግን የተሰጠው ክብር ብዙም አይደለም።
አዲስ ዘመን፡- ከዚህ ቀደም በምትሳተፉባቸው ውድድሮች ብዙም ድጋፍ እንደማይደረግላችሁ ይታወቃል።በዚህ ማጣሪያስ ድጋፉ እንዴት ነበር?
ማስተር አዲስ፡- ድሮ ከነበረው በጣም የተሻለ ነበር፤ በተለይ የኢትዮጵያ ኦሊምፒክ ኮሚቴ ጥሩ ድጋፍ አድርጎልናል።ፌዴሬሽኑም ያለውን አቅም ተጠቅሟል፤ ከዚህ ቀደም ውድድሮች ሲኖሩብን ለአጭር ጊዜ ነበር ቡድናችንን የምናዘጋጀው አሁን ግን ለረጅም ጊዜ በዝግጅት ላይ እንድንቆይ መደረጉ መልካም ነው።በአንጻራዊነት እንደ አጠቃላይ ያለው ነገር የተሻለ ነው ለማለት ያስችላል።
አዲስ ዘመን፡- ማለፋችሁን ተከትሎስ የኢትዮጵያ ኦሊምፒክ ኮሚቴ ምን አደረገላችሁ?
ማስተር አዲስ፡- እስካሁን ምንም የተደረገልን ነገር የለም፡፡
አዲስ ዘመን፡- ከሰለሞን ባሻገር በአፍሪካ ደረጃ ውጤት ያስመዘገቡ ስፖርተኞች ተስፋ ቢጣልባቸውም አሁን ላይ አናያቸውም ምክኒያቱ ምንድነው?
ማስተር አዲስ፡- በእኛ ስፖርት ችግሩ የክለቦች አለመኖር ነው፤ ስለዚህም ወጣቶቹ ስራ ሳይሰሩና ትምህርት ሳይማሩ ስፖርቱ ላይ ብቻ ተሳታፊ እየሆኑ መቆየት አስቸጋሪ ነው።ብዙዎቹ ሰልጣኞች ሌላ ገቢ ስለሌላቸው ከብሄራዊ ቡድን በኋላ ወደ ሌላ ነገር ይሰማራሉ፣ አሊያም ስፖርቱን ይተውታል።ስለዚህም ፌዴሬሽኑ አሁን የመጣው ውጤት ላይ ተመርኩዞ በርካታ ስራዎችን ማከናወንና የማስተዋወቅ ስራ ይጠበቅበታል።በመገናኛ ብዙሃን በኩልም አበረታች የሆኑ ስራዎች በይበልጥ መሰራት ተገቢ ነው።
አዲስ ዘመን፡- በኢትዮጵያ እጅግ ተዘውታሪ ከሆኑ ስፖርቶች መካከል የማርሻል አርት ስፖርቶች ተጠቃሽ ናቸው።ነገር ግን በሺዎች ከሚቆጠሩ ተሳታፊዎች ከዓመታት በኋላ ነው አንድ ስፖርተኛ ያገኘነው፤ ምክንያቱ ምንድን ነው?
ማስተር አዲስ፡- ከሩቅ ሆኖ ሲታይ ነገሮች ተመቻችተው ይመስላል፤ ነገር ግን እንደ ሌሎች አገሮች ስፖርቱ ኢንቨስት እየተደረገበት አይደለም።ሌሎች አገራት ዝግጅት የሚያደርጉት ለዓመታት ነው፤ በተለያዩ ውድድሮች ላይም ተሳታፊ በመሆን አቅማቸውን ይፈትሻሉ።እኛጋ ግን በዚያ ደረጃ እየሄደ አይደለም፤ ከስር በርካታ ማሰልጠኛ ማዕከላት ይኑሩ እንጂ ከዚያ የሚወጡትን ሰልጣኞች የሚያቅፍ ክለብ የለም።ለአብነት ያህል ከሰለሞን ጋር ዝግጅት የሚያደርግና በእርሱ ደረጃ የሚገኝ ስፖርተኛ ማግኘት ከባድ ነው።ወደ ሌሎች ክለቦች ሄደንም የወዳጅነት ልምምድ ለማድረግም ለእኛ ከባድ ነው።
አዲስ ዘመን፡- በቶኪዮ ኦሊምፒክ ላይ የተለየ እቅድ አላችሁ?
ማስተር አዲስ፡- ከ20 ዓመት በፊት በተካሄደው የሲድኒ ኦሊምፒክ ላይ የመገኘት እድል ገጥሞኝ ነበር፤ ወቅቱ ቴኳንዶ የኦሊምፒክ ስፖርት የሆነበት ስለነበር ተጋባዥ በመሆን ነው የታደምኩት።የዚያኔ ለራሴ በኦሊምፒክ ተሳታፊ እንደምሆን ነግሬው ከዓመታት በኋላ ስኬታማ ሆኛለሁ።አራት ኦሊምፒኮችን ከሞከርኩ በኋላም በአምስተኛው እድል ቀንቶኛል።ወደ ቶኪዮ የምንሄደው ደግሞ ለተሳትፎ ሳይሆን ለማሸነፍ ነው።
አዲስ ዘመን፡- የአገራችን በርካታ ፌዴሬሽኖች እንኳን ለ20 ዓመታት የአንድ ዓመት እቅድም ሲያወጡና ሲፈፅሙ አይታዩም፣ አንተ በግልህ ይህን አሳክተሃልና ከዚህ ምን መማር ይቻላል?
ማስተር አዲስ፡- እኔ በተለያዩ አገራት ተዘዋውሬ እንደተመለከትኩት ከሆነ ለአንድ ስፖርት መሰረትም አስፈላጊውም አሰልጣኝ ነው።አሰልጣኞችን ለማብቃት ደግሞ ፌዴሬሽኖች መስራት ይገባቸዋል፤ ምክንያቱም አሰልጣኝ ሁሌም በልጦ መገኘት አለበት።መንግስትም የፌዴሬሽኖች በጀት ላይ ድጎማ ማድረጉ ተገቢ ነው፤ የሚሰሩትንም ማበረታታት ያስፈልጋል።ሌላው ነገር በአህጉር አቀፍ ደረጃ ተፎካካሪ መሆን ነው፤ ከዚያ በኋላ በደረጃ ወደ ዓለም ማውጣት ይቻላል።
አዲስ ዘመን፡- እንዲህ አይነት ስኬቶች ሲመዘገቡ ከእውቅናና ማበረታቻ ጋር በተያያዘ ምን መደረግ ይኖርበታል ትላለህ?
ማስተር አዲስ፡- ሁሌም ስለ አንድ ነገር መወራት ያለበት ውጤት ሲመጣ ብቻ መሆን የለበትም።ውጤት ባይመጣም ስፖርተኞች መበረታታት አለባቸው፤ ምክንያቱም በውድድር ዕለት በጥቂት አጋጣሚ ከውጤት ውጪ መሆን ይከተላል።በመሆኑም ውጣ ውረዱና ልፋቱ ሊታይ እንዲሁም ላሉበት ደረጃ በመብቃታቸው ሊበረታቱ ይገባል።ይህ ሲሆን ደግሞ ለቀጣይ መነሳትን ይፈጥራል።
አዲስ ዘመን፡- ማስተር አዲስ ለሰጠኽን ጊዜ ከልብ አመሰግናለሁ፡፡
ማስተር አዲስ፡- እኔም አመሰግናለሁ፡፡
አዲስ ዘመን መጋቢት 14 /2012
- ማስተር አዲስ ኡርጌሳ
ብርሃን ፈይሳ