ልማዳዊ ድርጊቶች የሴቶችና ሕፃናትን አካላዊ፤ ስነ-ልቦናዊ፤ ሰብዓዊ መብት የሚጋፉ፤ ማሕበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተሳትፎ እንዲሁም ተጠቃሚነትን የሚነፍጉ መሆናቸውን መናገር ለቀባሪው አረዱት ይሆናል። ነገር ግን ዛሬም እነዚህ ጉዳዮች ልማድ ተደርገው በመወሰዳቸው ደጋግመን እንድናወራው ግድ ሆኗል። በተለይ በታዳጊ ክልሎች የሚታየው የለውጥ ሁኔታ አናሳ በመሆኑ ተደጋግሞ መነገርን ይሻል።
«ልጅ በእንጀራ አባቷና በአባቷ ትደፈራለች፤ ያለዕድሜዋ ትዳራለች።» ከዚያ ሲያልፍ ደግሞ ሰውነቷ ይተለተላል። የሚብሰው ደግሞ ሴት ሆና ሴት ልጇን በዚህ ህይወት ውስጥ እንድታልፍ የምታደርግ እናት መበራከቱ ነው። ችግሯ እንዳይታወቅ ትሸሽጋታለች፤ ማን እንዳደረገው እንዳትናገርም አፏን ታሳፍናታለች፤ ከማህበረሰቡ ስትገለል እንኳን ችግሯ ይህ ነው ብላ አታስረዳላትም። ምክንያቱም እርሷም የልማዱ ሰለባ ናትና። በዚህ ምክንያት ደግሞ አደጋ አድራሹም መብቴ ነው እያለ ይቀጥላል፤ ህግም ተጠያቂውን ያጣል። ይህ ደግሞ እየሰፋ ሄዶ ማህበረሰቡ በህጉም ሆነ በአድራጊው እየፈረደ ይቀመጣል። ይባስ ብሎም መብት ነው ብሎ ያምናል። ታዲያ ይህ አይደል ሴትና ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች ተዛምደው ቀጠሉ ማለት።
ለዚህ መነሻ የሚሆነን ሰሞኑን በጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች ዙሪያ የሴቶች፣ሕፃናትና ወጣቶች ሚኒስቴር ያዘጋጀው የውይይት መድረክ ላይ የቀረበው የትግራይ ክልል ተሞክሮ አንዱ ነው። ነገሩ እንዲህ ነው፤ ሕፃኗ የሁለት ዓመት ልጅ ናት። እናት ከባለቤቷ ተፋታ ስልሳ ዓመት ከሚሞላው ሰው ጋር በትዳር ተጣመረች። ሕፃኗ ብቻዋን መሆን ስለማትችልም ልጇን አንግባ ከሰውዬው ጋር ተዳበለች። ከእናት ይልቅ ሕፃኗን የመረጠው ባል ደግሞ ሕፃኗን ይደፍራል። እንግዲህ አስቡት የስልሳ ዓመት አዛውንት ከሁለት ዓመት ሕፃን ጋር።
ምንም የመንፈራገጥም ሆነ የመምታት አለያም የመተንፈስ አቅም የሌላት ሕፃን አምላክ ትረፊ ብሏት ብትቀመጥም መራመድም ሆነ መናገር ተስኗታል። ስለዚህም ህመሟ የበረታባት ሕፃን እማማ ማለት ማቆሟ ብቻ ሳይሆን ከአካል ጥቃት ብቻ ልታገግም የምትችልበትን ዕድል ተነፈገች። ይሁንና ጉዳዩ ያሳሰባት እናት በመጨረሻ ወስና ወደ ህክምና ወሰደቻት። ሰውዬውንም ለህግ አቀረበችው። ልጅቷ ግን አሁንም ጨለማ ህይወቷን እየገፋች ተገኛለች። ይህ ነው ጎጂ ልማዳዊ ድርጊትና ሴቶች ተዛምደው የኖሩበት ምክንያት።
ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች ከማሕበረሰቡ አኗኗር ጋር አብረው የተገመዱ ማሕበራዊ እሴቶችና ሀብቶች ወይም ዋጋዎች ናቸው። በዚህም ያምኑበታል፤ ይታዘዙለታል ፣ይኖርበታልም ይላሉ በሴቶች፣ ሕፃናትና ወጣቶች ሚኒስቴር የሴቶች ዘርፍ ሚኒስትር ድኤታ ወይዘሮ ስመኝ ውቤ። ምክንያታቸውም ድርጊቶቹ አገሪቷ የተቀበለቻቸውን ዓለም አቀፍ ስምምነቶችና የዜጎችን ደህንነት ለማስጠበቅ ያወጣቻቸውን ህጎች በጽኑ የሚቃረኑ ተግባራት መሆናቸው ነው። ይህ ድርጊት በተጠቂዎች ህይወት፣ አካልና ስነልቦና ላይ ጉዳት በማምጣት የሰዎችን ሰብዓዊ መብት ይገፋል፤ የሴቶችን ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ተሳታፊነትና ተጠቃሚነትን ያጓትታል፤ ከዚያ ልቆም የአገሪቱን ዕድገት ለከፍተኛ ጉዳትና ኪሳራ ይዳርጋል ይላሉ።
እንደ ወይዘሮ ስመኝ ገለጻ፤ የሚያስከትለውን ጉዳትና ወንጀል ለሕብረተሰቡ በማስገንዘብ የአመለካከት ለውጥ ለማምጣት በመንግሥትም መንግሥታዊ ባልሆኑ ድርጅቶችም በርካታ ሥራዎች እየተሠሩ ናቸው። ይሁንና ድርጊቶቹ ለረጅም ጊዜ ሲከናውኑ በመቆየታቸውና እንደ አንድ ባህል መገለጫ ስለሚቆጥሩት እየቀነሱ ቢመጡም ሙሉ ለሙሉ ማስወገድ ግን አልተቻለም። ይልቁንም ታዳጊ ክልሎች ባሉበት እየሄደ ነው ማለት ይቻላል።
የሴቶችን ህይወት ከማሕበራዊ ጉዳይ፣ የታዳጊ ሴቶች ሚናን ከቤት ውስጥ ጋር ብቻ እንዲተሳሰር የሚያደርገው ልማዱ ነው። እኩል ያልሆነ የስርዓተ ጾታ ግንኙነት እንዲኖር፣ ለሴቶች ትምህርት ዋጋ እንዳይሰጥ፣ የተማሩ አርአያ የሚሆኑ ሴቶች እንዲጠፉ ያደርጋል። ከጋብቻ ውጪ ያሉ አማራጭ መንገዶች እንደሌሉ በማድረግ ሴቶችን በማሳመን በልማዳዊ ድርጊት ውስጥ ብቻ እንዲያልፉ እንደሚገደዱ ይናገራሉ።
« ውስን የሕግ ማስከበር ሥራ መኖሩ ሴቶች በልማዳዊ ድርጊቶች ውስጥ እንዲቆዩ አድርጓቸዋል» የሚሉት ደግሞ በሴቶች፣ ሕፃናትና ወጣቶች ሚኒስቴር የሴቶች ተሳትፎና ንቅናቄ ማስፋፊያ ዳይሬክተር አቶ ስለሺ ታደሰ ናቸው። እርሳቸው እንደሚገልጹት፤ እነዚህ ድርጊቶች በአብዛኛው የጾታ እኩልነት አለመኖር በወንዶችና ሴቶች መካከል የኃይል ሚዛን አለመመጣጠን የሚያመለክቱ ናቸው። በማሕበራዊና ኢኮኖሚያዊ ትስስር ውስጥ ስር የሰደዱና ሴቶች መሰረታዊ የሰብዓዊ መብቶቻቸውን እንዳያጣጥሙ እንቅፋት ይሆናሉ።
የተጠናው ጥናት የሚያሳየው ከግማሽ በመቶ በላይ የሚሆኑት ዕድሜያቸው ከ15እስከ19 የዕድሜ ክልል የሚገኙ ታዳጊ ሴቶች ጋብቻቸው በቤተሰቦቻቸው የሚወሰን ነው። ዕድሜያቸው በጨመረ ቁጥር በጉዳዩ ላይ የመወሰን አቅማቸው በትንሹም ቢሆን የመጨመር አዝማሚያ ቢያሳይም የህግ አሠራሩ ስለሚመልሰው ወደነበሩበት ይገባሉ። ይህ ደግሞ በድርጊቱ ውስጥ የሚቆየውን ሰው ቁጥር ያበራክተዋል ይላሉ።
ጥናቱ እንደሚያሳየው ከ140 በላይ የጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች ዓይነት አለ። ሆኖም አገሪቱ በተለይ በስፋት ይፈጸማሉ ያለቻቸው ላይ እየሠራች ትገኛለች። ከእነዚህም መካከል ያለዕድሜ ጋብቻና ግርዛት የመጀመሪያዎቹን ቦታ እንደሚይዙ የጠቆሙት አቶ ስለሺ፤ የኃይል ጥቃትን እንኳን ሲታይ ከሦስቱ ወጣት ሴቶች ውስጥ አንዳቸው ላይ በቅርብ አጋር ጥቃት ተፈጽሞባቸዋል። ስለዚህም በቅርብ አጋር የተደረገ ጥቃት ደግሞ አካላዊ ብቻ ሳይሆን ስነልቦናዊ ጉዳቱ የላቀ መሆኑን ይናገራሉ።
እንደ አቶ ስለሽ ማብራሪያ፤ ከባለፉት 10 ዓመታት በተደረገ ንጽጽር በ2025 ድርጊቱን ለማጥፋት አሁን ካለንበት 10 እጥፍ መፍጠን ይገባል። በ2030 በዘላቂ ልማት ግብ መሰረት ደግሞ 6 እጥፍ መፍጠን ይገባል። ይህ የሚጠበቅ ፍጥነት በክልሎች መካከል ልዩነት ስላለው ችግሩ አሳሳቢ እየሆነ መጥቷል። ጥሩ ለውጥ ያመጡት ትግራይ፣ አማራ፣ ደቡብና አዲስ አበባ ብቻ ሲሆኑ፤ ታዳጊ ክልሎች ግን አሁንም በጣም መሥራት ያለባቸውና ከድርጊቶቹ ጋር የተጋቡ ይመስላሉ። ስለዚህም ከሌሎቹ በበለጠ ሚኒስቴሩ ትኩረቱን አድርጎ የሚሠራ መሆኑን ይጠቅሳሉ።
«በአሁኑ ሰዓት 47በመቶ ዕድሜያቸው ከ15እስከ 19 የሚገኙ ታዳጊ ሴቶች የሴት ልጅ ግርዛት ተፈጽሞባቸዋል» ያሉት ደግሞ በደቡብ ብሔር ብሔረሰቦች ክልላዊ መንግሥት የሴቶች፣ ሕፃናትና ወጣቶች ቢሮ ከፍተኛ የህዝብ ግንኙነት ባለሙያው አቶ ሀብታሙ አበበ ናቸው።
ከእነዚህም መካከል 16በመቶ ዕድሜያቸው ከ15 ዓመት በታች የሚሆኑት ታዳጊ ሴቶች መሆናቸውን ይገልጻሉ። ይበልጡን በገጠር አካባቢና በተለይ በሙስሊም የሃይማኖት ተከታዮች ዘንድ አይሎ መገኘቱንም ይጠቁማሉ። መንስኤዎቹ በጋብቻ ሊኖር ስለሚገባ ታማኝነት ጋር የተያያዘ ምክንያት መስጠት፣ በአንዳንድ ሁኔታ ከሃይማኖት እምነት ጋር መያያዙ፣ የማሕበረሰብ ቅጣትና መገለል ፍራቻ፣ አነስተኛ የቤተሰብ ትምህርት፣ የሕግ እውቀትና አፈጻጸም በዋናነት የሚጠቀሱ መሆናቸውን ይናገራሉ።
በ2030 ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶችን ለማስቆም ሰባት እጥፍ ፈጥኖ መሥራት እንደሚገባ ሚኒስቴሩ ያጠናው ጥናት ያመላክታል የሚሉት አቶ ሀብታሙ፤ ወረዳዎችን ከጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች ነፃ ማድረግ ላይ እየሠሩ መሆኑን ይናገራሉ። በተለይም ገራዦችን ወይም በተለምዶ አጠራር «የፌስታል ሀኪሞችን» በማወያየትና የሥራ አማራጮችን እንዲያገኙ በማስቻል ድርጊቱ እንዲቆም እየተደረገ ነው። የፌስታል ሀኪሞቹ ዋና የገቢ ምንጫቸው ግርዛት በመሆኑ ለጊዜው እንቢታቸውን አሳይተው ነበር። ሆኖም ለተወሰኑት ከብቶችን በመስጠት እገዛ ሲደረግ ሲያዩ ይህንን ተግባራቸውን ቀይረዋል ይላሉ።
ይሁንና ዕቅዱን ለማስፈጸም አለመንቀሳቀስ፣ ወቅታዊ የመረጃ ልውውጥ አለመኖር፣ የበጀት እጥረትና በጥምረት ያለመሥራት ክፍተቶች አሁንም ፈተናዎች ናቸው ያሉት አቶ ሀብታሙ፤ ክፍተቱ በሚታይበት ዙሪያ መሥራት እንደሚገባ መስሪያቤቱ ያምናል። ስለዚህም ቀጣይ ትኩረቱ ይህ ይሆናል ብለዋል።
በአማራ ክልል የሴቶችና ሕፃናት ቢሮ ኃላፊ አቶ ስማቸው ዳኘ በበኩላቸው፤ ለልማዳዊ ድርጊቶች መንሰራፋት መንስኤው በተለይም ገራዦች መግረዝን እንደ ገቢ ማስገኛ አድርገው የሚቆጥሩ መሆናቸው፣ የተጠያቂነት ስርዓት መላላት፣ ውስን የሕግ አፈፃፀም መኖሩ፣ በጾታ የተከፋፈለ ጥራቱን የጠበቀ መረጃና ማስረጃ አለመኖር፣ የጥበቃና እንክብካቤ አገልግሎቶች ውስን መሆናቸው በዋናነት ይጠቀሳሉ ። በዚህ ምክንያት በተለይ በክልሉ ከዚህ ድርጊት ለማውጣት ፈታኝ የሆነው ጉዳይ በእስልምና እምነት ውስጥ ያሉ ሴቶች በእምነቱ ይህ ተብሏል በሚል ድርጊቶቹን ሊተው አለመቻላቸውን ይገልጻሉ።
እንደ አቶ ስማቸው ማብራሪያ፤ የእስልምና እምነት ተከታዮች በተለይ ያለዕድሜ ጋብቻ ላይ ሰፊ ሥራ ለመሥራት ቢሞከርም በቁርዓኑ አስራ አምስት ዓመት ስለሚል አስራ ስምንት ድረስ መቆየት የለባትም ይላሉ። በዚህም ብዙ ሰዎችን ተጠያቂ ለማድረግ ተገደናል። እስከአሁን በ2025 አገሪቱ ከገባችው ቃል ኪዳን አኳያ በተሰጠን አቅጣጫ መሰረት ያለዕድሜ ጋብቻን ሊፈጽሙ ካሰቡት ውስጥ ያልገቡ መረጃዎች ቢኖሩም 5ሺ600 ሰዎችን በገባው መረጃ ብቻ ማስቆም ተችሏል። በግርዛትም እንዲሁ 98 በመቶ የሚሆነው ተሳክቷል። ስለዚህ በቀሪዎቹ ላይ ይህንን ሥራ አጠናክረን እንቀጥላለን።
ሴቶችንና ሕፃናትን ከዚህ ጎጂ ልማዳዊ ድርጊት ጋብቻ የማፋታት ሥራ የሁሉም ኃላፊነት ነውና ዘመቻው ይቀጥል።
አዲስ ዘመን ጥር 4/2011
ጽጌረዳ ጫንያለው