የዓድዋ ጦርነት መነሻው ምን ነበር?
በኢትዮጵያ እና በጣልያን መካከል እ.አ.አ ግንቦት 2 ቀን 1889 አንድ ስምምነት ይፈረማል። ይህም ሃያ አንቀጾችን የያዘ እና ሁለቱ ሀገራት ወዳጅነታቸውን ለማጠናከር የፈረሙት ነበር። ስምምነቱ የውጫሌ ውል/ስምምነት ይባላል። ይህም ስምምነት ለሁለቱ ሀገራት በሚያመች መልኩ በአማርኛ እና በጣሊያንኛ ቋንቋዎች ተፅፎ የተዘጋጀ ነበር። የታሪኩ መነሻ የሁሉ ነገር መጠንሰሻ ከዚህ ጀመረ። የጣሊያን መንግሥት የውጫሌውን ውል ተንተርሶ ኢትዮጵያን እንደፈለገው ለማድረግም ተመኘ። በስምምነቱ አንቀጽ 17 ላይ በጣሊያንኛው ትርጉም የተቀመጠው ኢትዮጵያ ከሌሎች ሀገራት ጋር ለሚኖራት ጉዳይ ሁሉ የጣሊያንን መንግሥት ይሁንታ ማግኘት እንዳለባት ወይም በጣሊያን መንግሥት አማካይነት ብቻ እንድትፈጽም የሚልና በዚህም ኢትዮጵያ እንደተስማማች የሚደነግግ ነበር።
በአማርኛ የተጻፈው ደግሞ ኢትዮጵያ ከሌሎች ሀገራት ጋር ለሚኖራት ጉዳይ የጣሊያንን መንግሥት የመጠየቅ ግዴታ እንደሌለባት የሚገልፅ ነበር። የዚህ ትርጉም ታዲያ በኢትዮጵያዊያን ዘንድ ኢትዮጵያ በተጨባጭ የጣሊያን ረዳትነትን መቀበል እንደምትፈልግ የሚያሳይ ነበር። የዚህን ትርጉም ስህተት የተረዱት ቀዳማዊ አጼ ሚኒሊክ ስምምነቱን አለመቀበላቸውንም በይፋ ለአውሮፓ ኃያላን አስታወቁ። ትርጓሜውን በማሳሳት ሆን ብላ የፈጸመችው ጣሊያንም ውሉን በግድ ተግባራዊ ለማድረግ ጦሯን ወደ ኢትዮጵያ ማስገባት ጀመረች። ጦሯንም በኢትዮጵያ 20 ሺህ ወታደሮች አሰማራች። በኢትዮጵያም በኩል በአፄ ሚኒሊክ መሪነት የክተት አዋጅ ታወጀ። ህዝቡም ተነሳ። በኢትዮጵያ የቀን አቆጣጠር 1888 ዓ.ም ዓድዋ ላይ ለጥቁሮች ነፃነት የሆነ ዓለምን ያስደነቀ ዜና ተሰማ። ኢትዮጵያ የካቲት 23 1888 ዓ.ም ወራሪውን ጣሊያንን ድል በማድረግ አኩሪ ታሪክ አስመዘገበች።
ስለ ዓድዋ ድል ጸሐፍት ምን አሉ?
“ጦርነቱ ባለ ብዙ ገጽታ ነው። ለምሳሌ፤ ሽፍቶችና ባንዳዎች ቀደም ሲል በነራስ ስብሐት እንዳየነው እንዳመጣጣቸው ተስተናግደዋል። ለአገር ሲሆን ሽፍታም ይጨምት ነበር” ይለናል ወንድወሰን ውቤ። ደጃዝማች ጓንጉል ዘገየ በዓጤ ምኒሊክ ላይ ሸፍተው ከምኒልክ ጭፍሮች ጋር በጦርነት የተፈታተኑ ሰው ናቸው። በዚህም በትግራይ ዘመቻ ጊዜ በምኒሊክ ላይ እንደሸፈቱና በረሐ እንደገቡ ናቸው። ምኒሊክ ሕዳር 24 ቀን መርሳ ላይ ሰፍረው ሳሉ የደጃዝማች ጓንጉል መልክተኛ ከዓጤ ምኒሊክ ዘንድ መጣ። መልእክተኛውም “ጃንሆይ ከእርስዎ ተጣልቼ በረሐ ገብቻለሁ።
አሁን ግን በአገሬ ላይ የውጭ ጠላት ስለመጣባት የእርስዎና የኔ ጉዳይ ቀርቶ ይማሩኝና መጥቼ ከእርስዎ ከጌታዬ ጋር ሁኜ ያገሬን ጠላት ልውጋ ብለዋል” ብሎ ተናገረ። ዓጤ ምኒሊክም ተደስተው “ይምጣ ምሬዋለሁ” ብለው ላኩ። ደጃዝማች ጓንጉልም መጥተው ካጤ ምኒሊክ ጋር ተገናኙ። ሠራዊቱም መኳንንቱም በእንደዚህ ያለ ጊዜ መጥቼ ከጌታዬ ጋር ልሙት በማለታቸው እጅግ ተደሰቱ።” (ጳውሎስ ኞኞ፣ዓጤ ምኒሊክ፤ ፬ኛ እትም 2006 ዓ.ም ማንኩሳ አሳታሚ፤ ገጽ 167)
የታሪክ ተመራማሪው ፕሮፌሰር ባህሩ ዘውዴ፤ “የኢትዮጵያ ታሪክ- ከ1848 እስከ 1966” በሚል መጽሐፋቸው፤ የኢጣሊያ ጦር ደጋፊ የነበረ ጆርጅ በርክሌ የተባለ ጸሐፊ ስለ ክስተቱ የዘገበውን በመጥቀስ “ከሰፊው የፖለቲካና የታሪክ ትንታኔ አኳያ የዓድዋ ጦርነት በአፍሪቃ ምድር አዲስ ኃይል መነሳቱን የሚያበስር ይመስላል። የዚያች አህጉር ተወላጆች የማይናቅ ወታደራዊ ኃይል ሊሆኑ እንደሚችሉ ልናሰላስል ተገድደናል። እንዲያውም፤ አሁን ነገሩ አስቂኝ ቢመስልም፤ ይህ ሁኔታ (ማለትም ዓድዋ) ጨለማይቱ አህጉር በላይዋ ላይ ሥልጣኗን ባንሰራፋችው በአውሮጳ ላይ የምታደርገው አመፅ የመጀመሪያ ምዕራፍ ነውም ተብሏል።”
ፕሮፌሰር ባህሩ ዘውዴ “History of modern Ethiopia“ በሚል መፅሐፋቸው የድህረ ዓድዋን ጦርነት ሁኔታ ሲገልፁ ቅድሚያ የሚሰጡት ድሉ ለተቀሩት ጥቁሮች የነፃነት ተስፋ የጫረ መሆኑን በማስቀመጥ ነው። ፕሮፌሰር ባህሩ ጨምረውም፤ ድሉን የፓን-ኣፍሪካኒዝም መንፈስ እና የአፍሪካ አንድነት ራዕይ የመገናኛ ድልድይ ነው ይሉታል። ከዚህ በተጨማሪ ድሉ የኢትዮጵያን መፃኢ ጊዜ ከተቀሩት የአፍሪካ ሃገራት የተለየ ያደረገ ሲሆን፤ በፖለቲካውና በኢኮኖሚው ዘርፍ ከነበረው ተፅእኖ በተጨማሪ በህዝቡ ስነ-ልቦና ላይ በአዎንታ የሚታይ ጫና ፈጥሯል።
የሚኒሊኩ ቤተ-መንግሥት ታሪክ ፀሐፊው ፀሐፌ ትዕዛዝ ገብረ ሥላሴ “ታሪክ ዘመነ ሚኒሊክ” ብለው በሰየሙት መፅሐፋቸው ከብዙ ጊዜ አለመግባባት በኋላ በመንገሻ ዮሐንስ እና በአፄ ሚኒሊክ መካከል እርቅ እንደወረደ ገልጸው፤ መንገሻ ዮኸንስ አዲስ አበባ ድረስ በመሄድ ከንጉሹ ዙፋን ድረስ እንደቀረቡ፣ ንጉሹም በታላቅ ክብር እንደተቀበሏቸው መዝግበዋል። በተቀራራቢ ጊዜም የአገውን ዋግሹም ብሩን እና የጎጃሙን ንጉስ ተክለ ሃይማኖት አፄው አስተናግደው እንደሸኙ ይጠቁማል።
የተለያየ የኢትዮጵያ ክፍል የሚያስተዳድሩ ነገሥታት፣ መሳፍንት እና መኳንንት ከጊዜ ወደ ጊዜ የውጭውን ኃይል ለማባረር ወደ አንድ መግባባት የመጡ ሲሆኑ፤ ከመግባባታቸው በኋላ ያለው ሂደት የገዢዎች መስማማት በኢትዮጵያውያን ዘንድ ትልቅ ነፃ የመውጣት ወኔ ሊፈጥር፤ ጣሊያኖች በከባድ ስጋት ውስጥ እንዲገቡ እንዳደረጋቸው ፅሐፌ ትዕዛዙ ገልጸዋል። ለዚህም ከዓድዋው ድል በፊት የተደረጉት የእምባአላጀ እና የመቐለ ጦርነቶች በማሳያነት አቅርበዋል።
ታሪክ ፀሐፊው ተክለ ፃድቅ መኩሪያ የኢትዮጵያ ታሪክ ከቴዎድሮስ እስከ ኃይለስላሴ ባሉት መፅሐፋቸው እንዳሰፈሩት፤ የካቲት 23 ቀን 1888 ዓ.ም ዕለተ ዕሁድ ጠዋት 12 ስዓት ጦርነቱ ተጀመረ። ግማሽ ቀን ብቻ ፈጀ በሚባለው በዚህ ጦርነት ከውስጥ ቁመህ ጠብቀኝ ጠበንጃዎች ውጪ ይህ ነው የሚባል መሳሪያ ያልታጠቀው የኢትዮጵያ ጦር በወኔ እና በታላቅ የእምቢ ባይነት ስሜት ወራሪውን ጣሊያን አሸነፈ።
“በሠራው ወጪፎ ባመጣው እርሳስ
ተፈጠመ ጣልያን ከአበሻ እንዳይደርስ።”
በማለት የጣልያንን ፍፃሜን ገልጸዋል። እኝህ የታሪክ ፀሐፊ ጨምረውም ከድሉ ጀርባ የነበሩት ጀግኖች ሲያወሱ የወቅቱ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ጳጳስ አቡነ ማቴዎስ ተዋጊውን የማበረታታት፤ የሸሸውን የማወገዝ ሚና እንደነበራቸው ያስረዳሉ። በጦርነቱ በሺዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን እስከ ሕይወት መስዋእትነት ድረስ የሚሄድ ዋጋ ከፍለው የሃገራቸውን ነፃነት ያስከበሩ ሲሆን፤ ራስ ኣሉላ እንግዳ እና ሌሎች አርበኞች የጦርነቱ ኮከቦች ሁነዋል። ራስ ኣሉላን ባማረ ቋንቋ የሚገልፃቸው እስራኤላዊው የታሪክ ፕሮፌሰር ሃጋይ ኤርሊፕ፤ ከዳግማዊ ቴድሮስ ሞት በኋላ ምድረ አቢሲንያ ያፈራቸው ድንቅ የጦር መሪ ኘ የአቢስንያው ጋሪባርዲ፤ ገና ሳስባቸው ደሜን የሚያሞቁት ጀግና ይላቸዋል።
የዓድዋ ድል ምን ጥቅም ሰጠ?
በአፄ ምኒሊክና በተቀሩት ጀግና የጦር መሪዎቻቸው የሚመራው የኢትዮጵያ ወታደር በወራሪው ኢጣሊያ ላይ ድል ከተቀዳጀ ይኸው 124 ዓመት ሆነው። ከረጅም ዓመታት ጀምሮ የዓድዋ በዓል በየዓመቱ ይከበራል። በአሁኑ ወቅት ሁሉም ኢትዮጵያዊ ይህንን ታላቅ የድል በዓል ያከብራል። ነገር ግን የዓድዋ የድል በዓል እንደ ታሪክ ምን ተማርንበት? ምንስ ጠቀሜታ አስገኘ? ወጣቱ ትውልድ ታሪኩን እንዲያውቅ የተሠሩት ሥራዎች ምንድን ናቸው? እንዲሁም የዓድዋን የድል በዓል በየዓመቱ ከማክበር ባለፈ ምን ጥቅም ላይ ዋለ? የሚለው ሲታይ መልሱ “ምንም ነው” ማለት ይቻላል።
በባህልና ቱሪዝም ዘርፍ ጋዜጠኛ የሆኑት ሄኖክ ስዩም እንደሚናገሩት፤ የዓድዋ የድል ታሪክ እንደ አገር ጥቅም ላይ አልዋለም። ከድሉ ማግስት ጀምሮ ድሉን የተጎናጸፉት መሪዎች እንዳለፉ ሁሉ በዓድዋ ድል የተገኙ ክብርና አስተሳሰቦችም ጠፍተዋል። ምክንያቱም ከመሪዎቹ በኋላ የነበረው አስተሳሰብና ስሜት አገርን ከፍ ከማድረግ ይልቅ እንዲወድቅ አድርጎታል። የዚህንም ውጤት ከ40 ዓመታት በኋላ ታይቷል። የኢጣሊያ ጦር ለሁለተኛ ጊዜ ኢትዮጵያን ለመውረር ሲመጣ የታየ ጉዳይ ነው።
በዓድዋ ድል ወቅት በጦር ትምህርት፤ በጦርነት ብቃትና በስነ ልቦናም ጠንካራ የነበረች አገር ከአርባ ዓመት በኋላ አውሮፕላን ምን እንደሆነ ሳታውቅ በአውሮፕላን ጥቃት ደርሶባታል። የዚህ መንስኤ ደግሞ የዓድዋን ድል በአግባቡ ያለመጠቀም ጉዳይ ነው። በአሁን ወቅት ያለው ሁኔታ ሲታይ በድሉ የመኖር እና ድሉን ተጎናፅፎ ከመቀጠል ይልቅ ከዓመት ዓመት የዓድዋ ክብርና ድል እየጠፋ በተለያዩ ነገሮች ቅኝ የመገዛት ነገሮች አሉ። በጥላቻ፤ ባለመሰልጠን፤ ባለማደግ፤ ባለመማር እንዲሁም በሌሎች ጉዳዮች በቅኝ ግዛት ውስጥ እንገኛለን።
ቅኝ ገዥን በእልህ አስጨራሽ ትግል በማስወገድ የተገኘ ድል ለአፍሪካ አገራት ምሳሌ እንዳልነበረ ተረስቶ በአሁን ወቅት የሚታየውና የሚሰማው ነገር ሁሉ አንገት የሚያስደፋ መሆኑን ይናገራሉ። በአገሪቱ ውስጥ የመውደቅና የመሸነፍ ሁኔታ የሚስተዋል ሲሆን፤ ይህ ደግሞ የዓድዋን ድል በአግባቡ የአገር ኩራት አድርጎ ካለመውሰድ የመነጨ መሆኑን ያስረዳሉ።
የዓድዋ ድል በዓል መከበሩ በደንብ ታሪኩን ተጠቅመንበታል ወይም የቱርፋቱ ባለፀጋዎች ነን አያስብልም። ምክንያቱም በዓሉን ኢትዮጵያውን ባያከብሩት የአፍሪካ አገራት ያከብሩታል። በሌላም በኩል፤ ለአገር የሚቆረቆሩ ወገኖች በዓሉን በተለየ ሁኔታ ሊያከብሩት ይችላሉ። እንደ አገር ደግሞ የአርበኝነቱ መንፈስ እየቀነሰ ቢመጣም በዓድዋ በዓል ወቅት የሚከበርባቸው ሁኔታዎች እንዳሉ ይጠቅሳሉ። ማሸነፍ ሲባል ከኢጣሊያ ጋር ብቻ ገጥሞ ማሸነፍ ሳይሆን፤ በብዙ ነገሮች አሸናፊነት ተገኝቶ ነበር። ለምሳሌ ያክል፤ መኪና ማስገባት፤ ጠንካራ ኢኮኖሚ መገንባት፤ ለዓለምና ለጥቁሮች ለነፃነታቸው የሚጨነቁና የሚታገሉ መሆናቸውን
ማሳየት የተቻለበት እና ብሄራዊ ጥቅም ከፍ ብሎ የታየበት ወቅት እንደነበር ይጠቁማሉ።
እንደ አቶ ሄኖክ ገለጻ፤ የዓድዋ የጦርነት ታሪክ የተወሰኑ አስገራሚ ነገሮች ያሉት ሲሆን፤ በወቅቱ ከማዕከላዊው መንግሥት ጋር ተኳርፈው የነበሩ የአካባቢ ገዥዎችና የጦር አበጋዞች ሳይቀሩ ‘ከአገር የሚበልጥ ጉዳይ የለም’ ብለው እርቅ እየጠየቁ የመጣውን የአገር ጠላት አብረን እንመክት ብለው በጋራ ያመጡት ድል ነው። በአሁኑ ወቅት ግን እንደዚህ ዓይነት ሁኔታዎች የሉም። የፖለቲካ መስመሮች ከተለዩ በኋላ የአገር ብሄራዊ ጥቅም ብዙ ሰዎች የማይቀበሉት ጉዳይ ነው። ከፖለቲካ መስመር ውጪ የመጡ ነገሮች አገርን ጠቀመምም ጎዳም ማንም አይመለከተውም የማለት ሁኔታዎች ተፈጥረዋል። በዚህም ምክንያት ከዓድዋ ድል አርባ ዓመት በኋላ ኢጣሊያ በጦርነት አሸንፎ ኢትዮጵያ ውስጥ አምስት ዓመት መቆየት ችሏል።
እንደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር 1928 ዓ.ም ላይ ኢጣሊያ ለዳግም ወረራ ሲመጣ የአገር ውስጥ ባንዳዎች እገዛ አድርገዋል። ኢጣሊያ ከኢትዮጵያ ከተባረረ በኋላም በተመሰረቱ መንግሥቶች ውስጥ ባንዳዎች በመኖራቸው የአገር አንድነት እንዲጠፋ ምክንያት መሆናቸውን ይናገራሉ። ሰዎች በፖለቲካ አስተሳሰባቸው ልዩነት ካላቸው በአገር ጉዳይ የሚደራደሩበትና አገራቸውን አሳልፈው የሚሰጡበት ስሜት እያደገ ይገኛል። ይሄ የሚያሳየው ከዓድዋ የድል ታሪክ ያለመማር ውጤት ነው ብለው እንደሚያምኑም ያመላክታሉ። የዓድዋ ድል ታሪክ ጥቅም ላይ ቢውሉ የአገር አንድነት ስሜት በመፍጠር የጋራ ዓላማ ያለው ማህበረሰብ መፍጠር እንደሚቻልም ያብራራሉ።
በታሪክ ትምህርቶች ውስጥ የሚታዩት ክፍተቶች ብሄራዊ ስሜትና ብሄራዊ ክብርን ከግላዊ ፖለቲካ መስመር አቆራኝቶ ከማየት የመጣ ነገር ነው። በሁሉም አቅጣጫ በኢትዮጵያ ውስጥ የነበሩ ወጣቶች ለዓድዋ ድል ውጤት የየራሳቸውን አስተዋፅኦ አበርክተዋል። ዛሬ ባለው የፖለቲካና የአስተሳሰብ መስመር ልዩነት ሰዎች አያቶቻቸውን ከዓድዋ ጎራ ለማውጣት ሲጥሩ ይታያል።
አያቶቻቸውን ከዓድዋ ጎራ ለማውጣት ሲሞክሩ ደግሞ ሌላ አዲስ ታሪክ መፃፍ፤ መናገርና ለትውልድ ማውረስ አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ የታሪክ ትርክቶች እየተበላሹ መምጣታቸውን አቶ ሄኖክ ይገልፃሉ። የታሪክ ትምህርት የተዛባ መሆን “የዓድዋ ድል ለኔ ምኔ ነው” የሚል ትውልድ እየተፈጠረ ይገኛል። የዓድዋን የሽንፈት ታሪክ ከኢጣሊያ እኩል የሚያጣጥምና እራሱን እንደ ኢጣሊያ የሚመለከት ኢትዮጵያዊ የተፈጠረበትንም ምክንያት የታሪክ ትምህርት ትርክት ከብሄራዊ ጥቅም ይልቅ ፖለቲካዊ እይታና አስተሳሰብ እየተስፋፋበት ስለመጣ የችግሩ ሰለባ እንዲሆን ማድረጉን ያብራራሉ።
እንደ አቶ ሄኖክ አባባል፤ የዓድዋን ድል ጥቅም ላይ ለማዋል በሦስት ነገሮች ላይ መስማማት ይገባል። ዓድዋ የአያቶች ውጤት እንደመሆኑ በሁሉም የኢትዮጵያ አካባቢዎች የሚገኙ የዘመኑ ሰዎች ድል ያደረጉበት የዘመን አሻራ ነው። በዚህ ጉዳይ መግባባት ላይ መደረስ አለበት። ሁለተኛ ዓድዋ ላይ ድል የመጣው መደማመጥ ስላለ፣ ብሄራዊ ጥቅም ስለቀደመና ድርድር የማይደረግባቸው መስመሮች ስለተፈጠሩ ነው። ዛሬም ቢሆን ብሄራዊ ጥቅምን የማስከበርና የመደማመጥን ባህል በማሳደግ ድርድር የማይደረግባቸው ጉዳዮች ሊኖሩ ይገባል። ሦስተኛው የዓድዋ የማሸነፍ ባህል በብዙ መንገዶች ተተርጉሞ ዛሬም የአሸናፊነት መንፈስ እንድንላበስ ማድረግ አለበት። ከተፈጠረው ታሪክ ከመኩራት ባሻገር በአሁን ወቅት ያሉትን ችግሮች በአሸናፊነት የምንወጣበት የድል መነሻ ተደርጎ መወሰድ አለበት።
በዲላ ዩኒቨርሲቲ የታሪክና የዓለም አቀፍ ጉዳዮች ረዳት ፕሮፌሰር ዶክተር አብዱ መሀመድ አሊ እንደሚናገሩት፤ የዓድዋ ድል በዓል በተወሰነ መንገድ ጥቅም ላይ ውሏል። ዓድዋ ትልቅ አኩሪ ድል እንደመሆኑ የኢትዮጵያ ሳይሆን የመላው አፍሪካ ጥቁር ህዝብ የኩራት ምንጭም ነው። ከዚህ አንፃር ሲታይ ዓድዋ ኢትዮጵያን ከቅኝ አገዛዝ ነፃ ወጥታ እንድትቆይ ያደረገ ታሪካዊና ወታደራዊ ድል በመሆኑ ትልቅ ፋይዳ አለው። በዚህ ረገድ ጥቅም ላይ ውሏል ማለት ይቻላል። ከ124 ዓመት በፊት የመጣው ድል ኢትዮጵያን እንደ አንድ ጥቁር አፍሪካዊ ሉዓላዊ አገር ቆማ እንድትሄድ አድርጓታል። ከዚህ አንፃር ሲታይ ተጠቅመንበታል ተብሎ ይታሰባል።
እንደ ዶክተር አብዱ አባባል፤ አገሪቱ እንደ አገር፤ ህዝቡ እንደ ህዝብ ነፃ ሆነው እንዲኖሩ ያደረገው ዓድዋ ላይ የመጣው ድል ነው። ነገር ግን “የዓድዋን ድል ምን ያክል ተጠቅመንበታል?” የሚለው ነገር ሲታይ እንደየዘመኑ የተለያየ ነው። በዓድዋ ጦርነት ወቅት የነበረው ኢትዮጵያዊ ትውልድ ትልቁን የቤት ሥራ ሠርቶ አልፏል። በወቅቱ መላው አፍሪካ በቅኝ ግዛት ስር የነበረ ሲሆን፤ ኢትዮጵያና ላይቤሪያ ብቻ ነፃ አገር ሆነው ይኖሩ ነበር። ከጦርነቱ ድል የመጀመሪያ ዘመናት፤ በተለይ እስከ ሁለተኛው የኢጣሊያ ወረራ ጊዜ የዓድዋ ድል ጠቀሜታ ከነፃ አገር ስሜት በዘለለ ተሸናፊ ኃይሎች ማለትም ኢጣሊያ፣ እንግሊዝና ሌሎች በምሥራቅ አፍሪካ ቅኝ ተገዝተው የነበሩ አገራት ውድቀት ነበር።
የዓድዋ ድል ከነጭ ህዝብ እኩል የሰለጠነ እና እነሱን ማንበርከክ የሚችል ኃይል እንዳለ ያሳየ የድል ቀን መሆኑን የጠቀሱት ዶክተር አብዱ፤ በዚህ ሁኔታ እስከ ኢጣሊያ ሁለተኛ ወረራ ድረስ በዓድዋ በተገኘው ድል ምክንያት አገሪቱ ነፃ ሆና ቆይታለች። ነገር ግን፤ አገሪቱ ነፃ ሆና በቆየችበት ጊዜ ሁሉ ችግሮች ነበሩ። በዓድዋ ድል ምክንያት ሀበሾች እራሳቸውን በማኩራራት ለእድገት ብዙ አልተጓዙም። ኢጣሊያ በአርባ ዓመት ጊዜ ውስጥ እራሱን በጦር መሳሪያ አደራጅቶ ሲመጣ ኢትዮጵያ ግን በነበረችበት ሁኔታ በመቆየቷ ልትሸነፍ መቻሏን ያመላክታሉ።
የኢትዮጵያ ሽንፈት የሚያሳየው በዓድዋ ድል ኩራት የተሰማው ህዝብ ቢኖርም ሌሎች ጉዳዮች ላይ መዘናጋቶች እንደነበሩ አሳይቷል። በዓድዋ ጦርነትና ድል እና በማይጨው ጦርነት ጊዜ የነበረው ትውልድ አንድ ዓይነት ስነ ልቦና አልነበረውም። በሁለቱ ጦርነቶች መካከል በነበሩ ዘመናት የትውልድ ክፍተት ተፈጥሯል። ከዚህ አንፃር ሲታይ የዓድዋ ድል ነፃነትን በማስከበር ደረጃ ኩራት ያመጣ ቢሆንም፤ በዓድዋ ጊዜ የነበሩት ትውልዶች የሠሩትን የቤት ሥራ ለመድገም ጥረቶች አልተደረጉም። ከዓደዋ ድል በኋላ ክፍተቶች በመፈጠራቸው ማይጨው ላይ ሽንፈት ማጋጠሙን ዶክተር አብዱ አብራርተዋል።
እንደ ዶክተር አብዱ አባባል፤ ለአምስት ዓመት በቆየው የኢጣሊያ ወረራ ወቅት የአርበኞች እንቅስቃሴ የሚያሳየው የዓድዋ ድል ስሜት ሙሉ በሙሉ አለመጥፋቱን ነበር። ነገር ግን፤ ኢትዮጵያ ከኢጣሊያ እኩል ዘመኑን የተከተለች አልነበረችም። በወቅቱ ኢትዮጵያ ዘመናዊ ዴሞክራሲን የተከተለ ስርዓት መገንባት አልቻለችም ነበር። ከድህረ ዓድዋ በኋላ የተገኘው ነገር ቢኖር ፖለቲካዊ ነፃነትና አገራዊ አምባገነንነትን ነው። የቀዳማዊ ኃይለ ስላሴ መንግሥት፤ የደርግ መንግሥትና አሁን ያለው የአገሪቱ አስተዳደር ሲታይ በኢትዮጵያ ለህዝብ የቆመ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት እስከአሁን መገንባት እንዳልተቻለ ነው። አሁን ያለው የኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ከድሮው በይዘት እንጂ በቅርፅ ተመሳሳይ ነው።
“ዘመናዊነት በዳግማዊ ምኒሊክ ይጀመር እንጂ፤ በኃይለሥላሴ ዘመነ መንግሥት እንደ አዲስ ነው የተጀመረው” የሚሉት ዶክተር አብዱ፤ በአምስቱ ዓመት ወረራ ጊዜ የተማሩ የተባሉ ኢትዮጵያውያን እንዲሰደዱና እንዲገደሉ ተደርጓል። በዚህ ምክንያት ዘመናዊነት እንደ አዲስ እንደተጀመረ ይገልፃሉ። የዓድዋ ድል ቀን በየዘመኑና በየዓመቱ እንዲከበር ተደርጓል። ይሁን እንጂ፤ ምን ያክል በታሪክ ትምህርት ውስጥ ገብቶ ትውልድ እንዲያውቀው ተደርጓል የሚለው ነገር ውስንነቶች አሉት።
በየወቅቱ አገሪቱን ሲያስተዳድሩ የነበሩ መንግሥታት እራሳቸውን ለማጉላት ሲሉ ቀደም ብሎ የተሠሩትን ሥራዎች የማሳነስ ነገር እንዳለ ዶክተር አብዱ ያስረዳሉ። እንደዚህ ዓይነት ሁኔታ በሁሉም የአስተዳደር ዘመናት የተከሰተ ጉዳይ ነው። እውቀት በአፍሪካ አገራት በጉልበት ስር የምትገኝ በመሆኑ ጉልበት ያላቸው ኃይሎች እውቀትን የመቆጣጠር መብት አላቸው። ታሪክን ለፖለቲካ ዓላማ ብቻ በማዋል ረገድ በሦስቱም መንግሥታት በርካታ ነገሮች መስተዋላቸውን ያብራራሉ።
በአሁን ወቅት ያለው ትውልድ ዓድዋንና መሰል ታሪካዊ ክስተቶች በአግባቡ እንዲያውቅ አልተደረገም። ይህ ደግሞ ለታሪክ ባይተዋር የሆነ ትውልድ እንዲፈጠር አድርጓል። ለታሪኩ ባይተዋር የሆነ ትውልድ ደግሞ መገለጫው እብሪተኝነት፣ ዘረኝነትና ጨለምተኝነት ነው። በየትኛውም አገር ላይ ለታሪኩ ባይተዋር የሆነ ትውልድ ሦስቱን መገለጫዎች ያሳያል። አሁን የሚታዩት ችግሮች መንስኤያቸው ለታሪኩ ባይተዋር የሆነ ትውልድ በመፈጠሩ የመጣ መሆኑን ይናገራሉ።
የዓድዋ ድል በዓል በየዓመቱ መከበሩ ታሪኩ እንዳይረሳ ቢያደርገውም የድሉን በዓል የቱሪስት መዳረሻ ለማድረግ የተሠራ ሥራ የለም። የዓድዋን ተራሮች በማልማት የቱሪስት መስብህ ማድረግ ይቻላል። ነገር ግን በአሁን ወቅት በዓድዋ ከተማ ውስጥ በወቅቱ የተሰው ጀግኖችን የሚዘክር ሀውልትና ሙዚየም አለመሠራቱን ይጠቅሳሉ። ይሄ የሚያሳየው በፖለቲካ ምክንያት ያለፉት 124 ዓመታት ስልጣን የያዙ ኃይሎች ለዓድዋ ድልና ታሪክ የሰጡት ቦታ የይስሙላ መሆኑን ያሳያል። ከዚህ አንፃር የዓድዋ ድል ምንም ጥቅም ላይ ውሏል ብለው እንደማያምኑ ዶክተር አብዱ ይገልፃሉ።
እንደ ዶክተር አብዱ ገለፃ፤ የተፈጠረ ታሪክ የትናንት ነው ሊቀየር የሚችል አይደለም። ነገር ግን ያለፈው ታሪክ አሁን ላይ የራሱ የሆነ አሻራ ይኖረዋል። ትናንት ሳይታወቅ ዛሬን ማወቅ አይቻልም። የታሪክ ትምህርትም ቢሆን አገሪቱ ውስጥ ታሪክ ፍርድ ቤትና የንትርክ መድረክ እየሆነ ይገኛል። ትውልዱ ማወቅ ያለበት ነገር ቢኖርም ታሪክን ሊቀየር አይችልም። ነገር ግን ትርክቱ እንደየጊዜው ሊቀያየር እንደሚችል ማመን ያስፈልጋል። ስለ ዓድዋ ታሪክ አስር ፀሐፊያን በተለያየ መንገድ ሊፅፉት ቢችሉም ድርጊቱን ሊቀይሩት አይችሉም። በአገሪቱ አሁን ግጭት እየተፈጠረ ያለው በታሪክ ላይ ሳይሆን በትርክቶች ላይ ነው።
አብዛኛው ትርክቶች አንዱን አኮስሰው ሌላኛውን አጀግነው የሚስሉ በመሆናቸው ትውልዱ በፖለቲካ ምክንያት የሚመጡ ታሪኮችና እውነተኛ ታሪኮችን መለየት አልቻለም። መለየትና ማወቅ ግን አለበት። ማንኛውም ሰው አንድ ታሪክ ሲያነብብ “ማን ፃፈው? ለምን ተፃፈ?” ብሎ “ምን ላይ ተመርኩዞ ፃፈ?” የሚለውን መጠየቅ አለበት። በዚህ መልኩ ከሆነ ከታሪክ መማር እንደሚቻል ዶክተር አብዱ ያስረዳሉ።
አዲስ ዘመን የካቲት 23/2012
መርድ ክፍሉ