ፈላስፋ ፣ ባለቅኔ ፣ ጸሐፊ ተውኔት ፣ ደራሲና ጋዜጠኛ ክቡር ዶክተር ከበደ ሚካኤል የተወለዱት ከ103 ዓመታት በፊት በዚህ ሳምንት ጥቅምት 23 ቀን 1909 ዓ.ም ነበር።
ጽድቅና ኩነኔ ቢኖርም ባይኖርም
ከክፋት ደግነት ሳይሻል አይቀርም።
የዚህ ተወዳጅ መንቶ ግጥም ደራሲ ከበደ ሚካኤል በሰሜን ሸዋ ደብረ ብርሃን ከተማ አካባቢ ገርም ገብርኤል በተባለ ቦታ ጥቅምት 23 ቀን 1909 ዓ.ም ተወለዱ። እናታቸው ወይዘሮ አጸደ ሚካኤል ባህላዊውን የግዕዝ ትምህርት በቅጡ እንዲማሩ እንዳደረጓቸው ይነገራል። ከበደ በ1918 ዓ.ም ወደ አዲስ አበባ መጥተው በእናታቸው ወንድም በአቶ ሰይፉ ሚካኤል ልዩ ድጋፍ በአሊያንስ ፍራንሴስ በፈረንሳይኛ ቋንቋ የአንደኛ ደረጃ ትምህርታቸውን መከታተል ጀመሩ።
በመሃሉ በአሊያንስ ፍራንሲስ ትምህርት ቤት የነበሩ መምህራን ግርፊያ ያበዙ ስለነበር በዚህ ተማርረው ወደ ላዘሪስት ሚሲዮን ትምህርት ቤት ተዘዋወሩ። ቆይቶ ግን ሁኔታዎች በመሻሻላቸው ወደ አሊያንስ ፍራንሲስ ትምህርት ቤት ተመልሰው ጥቂት ዓመታት እንደተማሩ የሊባኖስ ዜግነት የነበራቸው የትምህርት ቤቱ ርዕሠ መምህር የልቦለድ ድርሰት ፀሐፊ ስለነበሩ ይህንኑ ሙያ ለመረጧቸው ስድስት ተማሪዎቻቸው ለማሳወቅ በግል መኖሪያቸው ማስተማር በጀመሩ ጊዜ ከበደ ሚካኤል አንዱ ሆነው ተፈጥሮ ያስታጠቀቻቸውን ጸጋቸውን መግራት ቻሉ።
በኋላም ጣሊያን ኢትዮጵያ ውስጥ በቆየባቸው አምስት ዓመታት ቤተ መጽሐፍት ውስጥ ብዙ የማንበብ ዕድል ገጠማቸው። በንባባቸው በዘመናቸው ቀደምት ታዋቂ ኢትዮጵያውያን ምሁራን የነበሩትን የአለቃ አጽመ ጊዮርጊስን ፣ የአለቃ ኪዳነወልድ ክፍሌን ፣ የነጋድራስ አፈወርቅ ገብረ ኢየሱስን ፣ የነጋድራስ ገብረ ሕይወት ባይከዳኝንና የቀኝ ጌታ ዮፍታሄ ንጉሴን አዳዲስ አስተሳሰቦች ቀስመዋል። ከንባቡ ጐን ለጐንም የጣሊያንኛ ቋንቋን በሚገባ ተምረዋል።
በቋንቋ በኩል ከበደ ሚካኤል ልሣነ ብዙ ከሚባሉ ደራሲዎች አንዱ ናቸው። ከአገራቸው አማርኛና ግዕዝ ቋንቋዎችን ከውጭ ደግሞ ፈረንሣይኛ ፣ ጣሊያንኛና እንግሊዘኛ ቋንቋዎችን ጠንቅቀው ያውቁ ነበር። ታዲያ በሁሉም ቋንቋዎች የሚያገኙትን መጽሐፍትን ለማንበብ አያመነቱም።
ከበደ ለምን ወደ ሥነ ጽሑፍ ዓለም እንዳዘነበሉ “የቅኔ ውበት” ብለው በሰየሙት የብዙ ሥራዎቻቸው መድብል በሆነው መጽሐፋቸው መቅድም ውስጥ እንደሚከተለው ገልጸዋል። “ገና በልጅነቴ በትምህርት ቤት ሳለሁ መጽሐፍ ልጽፍ ብዙ እመኝ ነበር። በዚህ ምኞቴ የተነሣ ባነበብኳቸው የውጭ አገር መጻሕፍት ውስጥ አልፎ አልፎ ደስ የሚያሰኝ ፍሬ ያለው ቃል ባገኘሁ ጊዜ በየብጣሹ ወረቀት ላይ ሲጽፉ ከዚህ መካከል የሚበልጠው እየጠፋብኝ የተረፈውን በአማርኛ እየገለበጥኩ ካጠራቀምኩ በኋላ እያንዳንዱን ቃል በግጥም አድርጌ በእርሳስ እየጻፍኩ ለማስተካከልና ግጥሙን ለማሳመር የተቻለኝን ያህል አምስትና ስድስት ጊዜ እየለዋወጥኩ ስጽፍ በኋላም እንደገና መልሼ በሐሳቤ ውስጥ ሳይረሱኝ የቆዩትን ቃሎች ስጽፍ፣ ሳጠፋ፣ ሳስተካክል በብዙ ጊዜ ይህንን መጽሐፍ ልጨርሰው በቃሁ …”
የከበደ ሚካኤል የመጀመሪያ ድርሰት “ብርሃነ ህሊና” የተሰኘው መጽሐፍ ሲሆን፤ የተጻፈው በጣሊያን ዘመን ነው። በኋላ የቅኔ ውበት በተባለው መጽሐፋቸው ከተካተቱት ስብስቦች አንደኛው በመሆን በተደጋጋሚ ታትሟል። ከበደ ሚካኤል ጠላት ከተባረረም በኋላ የድርሰት ሙያን አላቋረጡም። ከ1933 እስከ 1966 ዓ.ም. በጋዜጠኝነት ፣ በትምህርት ሚኒስቴር ውስጥ በኢንስፔክተርነትና በምክትል ዳይሬክተርነት ፣ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤት በተርጓሚነትና በፀሐፊነት፣ በብሄራዊ ቤተመጽሐፍት ወመዘክር በዳይሬ ክተርነት ፣ እንደገና በትምህርት ሚኒስቴር በዳይሬክተርነት ፣ በንጉሠ ነገሥቱ ካቢኔ በምክትል ሚኒስትርነት ማዕረግ የዜና ማደራጃ ኃላፊ እና በኋላም ሚኒስትር ሆነው ባገለገሉባቸው አጋጣሚዎች ሁሉ በደራሲነት ቀጥለዋል:: በነዚህ የሥራ ዘመናት በጠቅላላው 26 መጽሐፍትን አሳትመዋል::
በተለይ ደግሞ ዘመናዊ ትምህርት በአገ ራችን በስፋት ሲዘረጋ የአማርኛም ቋንቋ የሥርዓተ ትምህርቱ አንድ ክፍል ሆኖ እንዲሰጥ ተወስኖ ነበር። ሆኖም በየደረጃው የተዘጋጀ የመማሪያ የማስተማሪያ መጽሐፍ አልነበረም። በዚህ ጊዜ ከበደ ሚካኤል “ታሪክና ምሳሌ 1ኛ መጽሐፍ” በሚል ርዕስ በ1934 ዓ.ም ያቀረቡት መጽሐፍ በወቅቱ በትምህርት ገበታ ላይ ለነበሩ ወጣቶች መማሪያ ተደርጓል።
ከዚህ ጊዜ ጀምሮ የከበደ ሚካኤል ሥራዎች ለአማርኛ ቋንቋ ማስተማሪያነት ለሚዘጋጁ መጽሐፍት ሁነኛ ግብዓት በመሆን እንደ ፋኖስና ብርጭቆ ፣ ጽጌሬዳና ደመና፣ ብረት ድስትና ሸክላ ድስት ያሉ ሥራዎቻቸው አስካለንበት ዘመን ድረስ መዝለቅ የቻሉ በታዳጊ ተማሪዎች የሚወደዱ የበርካቶች ትዝታዎች መሆን ችለዋል።
ፍልስፍና ፣ ሥነ መለኮት ፣ ሥነ ትምህርት ፣ ሥነምግባር ፣ ሳይንስ ፣ ስነጥበብ ሌሎች ዘርፎችን የሚዳስሱ ወጥ ድርሰቶች ፣ ትርጉሞች ፣ ተውኔቶችና ግጥሞች የተካተቱባቸው ሥራዎቻቸው አሁንም ድረስ ተወዳጆች ናቸው። ከተወዳጅ ድርሰቶቻቸው መካከል ሮሚዎና ዡልዬት (ተውኔት) ፣ በላይነህ /ቅጣት ማዕበል (ተውኔት) ፣ የትንቢት ቀጠሮ (ተውኔት) ፣ ብርሃነ ህሊና ፣ የቅኔ ውበት ፣ ታላላቅ ሰዎች ፣ ታሪክና ምሣሌ አንደኛ መጽሐፍ ፣ ታሪክና ምሣሌ ሁለተኛ መጽሐፍ ፣ ትልቁ እስክንድር ፣ አኒባል (ተውኔት) ፣ ከይቅርታ በላይ ፣ ካሌብ ፣ የሥልጣኔ አየር ፣ የልዑል መኮንን ታሪክና መታሰቢያ በሥዕል ፣ ጂፓን እንዴት ስለጠነች ፣ ትንሣኤ ፣ ግርማዊነታቸው በአሜሪካን አገር ፣ የቅኔ አዝመራ ፣ የዓለም ታሪክና የእውቀት ብልጭታ የተሰኙት ይገኙባቸዋል።
ዶክተር አምሳሉ አክሊሉ በ1992 ዓ.ም በወጣው ጦቢያ መፅሔት ቅጽ 7 ቁጥር 4 እትም ስለከበደ ሚካኤል ተከታዩን ምስክርነት ሲሠጡ፡- “የከበደ ሚካኤል የአማርኛ ቋንቋ ችሎታ እንደ ታላቁና ስመ ጥር ደራሲ እንደ ኅሩይ ወልደሥላሴ አማርኛ ፤ አፈወርቅ ገብረየሱስ አማርኛ መሆን ይገባዋል እንደሚሉት ‹ገጥ ያለ፣ ቅልጥፍ ያለ፤ ላንደበት የተስማማ፤ ለጆሮ ያልገለማ፤ ላንባቢ የሚመች፤ ለሰሚ የማይሰለች› ዓይነት ነው። በድርሰቶቻቸው ውስጥ አልፎ አልፎ ረጃጅም ዓረፍተ ነገሮች ቢታዩም የሰዋሰውን ሥርዓት ልብ አድርጎ ከመጠበቅ የተነሣ ፍሰቱ የማይጎረብጥ፤ አንባቢን የማያንገላታ፤ በምንባብ ጎዳና ላይ የማያንገጫግጭና አቅፎ ደግፎ እስከ ዐረፍተ ነገሩ መጨረሻ ድረስ የሚያዘልቅ ነው። ሐረጋት በተገቢዎቹ መቀናበሪያ ንዑሳን ቃላት ስለሚያያዙ ከአንዱ ሐሳብ ወደ ሌላው ሐሳብ ስንሸጋገር የሚያደናቅፈን ቦታ ከቶ አናገኝም›› ።
“ስለ ደራሲ ከበደ ሚካኤል ከፍተኛ የቋንቋ ችሎታ ካነሣን ዘንድ የሚከተለውን መጨመር ተገቢ ይመስለኛል። በአንዳንድ ደራስያን ዘንድ የሚታየው ሚዛን ሊያነሣ የማይችለውን ሐሳብ ለአማርኛ እንግዳ በሆኑ ቃላትና ሐረጋት ጀቧቡኖ የማቅረብ አዝማሚያ በከበደ ሚካኤል የብዕር ሥራዎች ውስጥ ፈጽሞ አያጋጥመንም። አቀራረባቸው ግልጽ በመሆኑ ሊያስተላልፉት የፈለጉት መልዕክት ለአንባብያን ፍንትው ብሎ ይታያል። የታላላቅ ደራስያን አንዱ መታወቂያ ባህሪያቸው ይህ ነው።
ከደራሲ ከበደ ሚካኤል ድርሰቶች ጋር ስንተዋወቅ ለእኒህ ትልቅ የሥነ ጽሑፍ ሰው እግዚአብሔር ብዙ ዓይነት የድርሰት ተውህቦ የለገሳቸው መሆኑን እንረዳለን። ከሰፊው ንባባቸው የተነሣ በልዩ ልዩ አርእስት ልዩ ልዩ ጉዳዮችን በአማርኛ ከሽነው አሳምረውና አጣፍጠው አቅርበውልናል። ከነዚህም ሥራዎቻቸው ከበደ ሚካኤል ተመራማሪ፤ ተንታኝ፤ ለወገንና ለሀገር ቀናኢና ተቆርቋሪ፤ አስተማሪ፤ ትውልድን ገሣጭና ወቃሽ፣ በፈጣሪ ጽኑእ አማኝ መሆናቸውን እንገነዘባለን።ብለው ነበር››
ከበደ ሚካኤል ከ1966 ዓ.ም ለውጥ በኋላ የወታደራዊ ደርግ ባለስልጣናት በደራሲነት ለአገራቸው ያበረከቱትን አስተዋጽኦ ከመመልከት ይልቅ የወደቀው ስርዓት ግብረአበር አድርገው ስለቆጠሯቸው ብዙ ችግሮች ደርሰውባቸዋል:: የሰሩትን ቤት በቀበሌ ታጣቂዎች ተነጥቀው አብዛኛውን ኑሯቸውን የገፉት አውራሪስ እና ቱሪስት በተባሉ ሆቴሎች ውስጥ ነው:: “አእምሮቸው ንክ ሆኗል” እያሉ በሚያስወሩባቸው ወገኖች ምክንያትም የመገለል ችግር አጋጥሟቸው እንደ ነበር ይነገራል::
ከደርግ ውድቀት በኋላ ግን ትውልድን ለመቅረጽ ባበረከቱት አስተዋጽኦ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጥቅምት 26 ቀን 1990 ዓ.ም በስነጽሁፍ የክብር ዶክትሬት ዲግሪ ሰጥቷቸዋል።
በ1957 ዓ.ም የቀ.ኃ.ስ የስነጽሑፍ ሽልማትን ለመጀመሪያ ጊዜ የተቀበሉ ታላቁ ብዕረኛ በአማርኛ ፣ ፈረንሳይኛ ፣ እንግሊዘኛና ጣሊያንኛ ቋንቋዎች ከ90 በላይ በታተሙና ከ200 በላይ ባልታተሙ ወጥና ትርጉም ድርሰቶቻቸው የኢትዮጵያን የስነጽሁፍ አድማስ ስለማስፋታቸው ‹‹ኢትዮሪደርስ ዶት ኮም›› በተሰኘው የኢትዮጵያዊ ጸሐፍትን ታሪክና ሥራዎቻቸውን በያዘው ድረገጽ ላይ ሰፍሯል። ከአይቀሪው ጉዞ የሚቀር የለምና ከ 11 ዓመታት በፊት ኅዳር 3 ቀን 1991 ዓ.ም በ82 ዓመታቸው አርፈው የቀብር ስነስርዓታቸው በጴጥሮስ ወጳውሎስ ቤተ ክርስቲያን ተፈጽሟል::
አዲስ ዘመን ጥቅምት 19/2012
የትናየት ፈሩ