ባለፉት ዓመታት መንግስት የወጣቶችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተለያዩ ፓኬጆችን ቀርጾ እንቅስቃሴ ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ በ2009 ዓ.ም መግቢያ ላይ ይፋ የተደረገው የወጣቶች ተዘዋዋሪ ብድር ፈንድ ከተቀረጹት ፓኬጆች መካከል ተጠቃሽ ነው፡፡ ይህ የ10 ቢሊዮን ብር ተዘዋዋሪ የብድር ፈንድ ወጣቶችን ተጠቃሚ የማድረግ ዓላማ ያነገበ ነበር፡፡ የገንዘብና ኢኮኖሚ ሚኒስቴር መረጃ እንደሚያመለክተው በአገር አቀፍ ደረጃ እስከ ጥቅምት 2011 ዓ.ም ድረስ 8 ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር ለክልሎች ተሰራጭቷል፡፡ በፈንዱ በርካታ ወጣቶች ተጠቃሚ መሆን ችለዋል፡፡ ሆኖም የተዘዋዋሪ ብድር ፈንዱ አጠቃቀም ላይ በርካታ ችግሮች እንደሚስተዋሉበት ወጣቶች በተደጋጋሚ ሲገልጹ ይስተዋላል፡፡
ወጣት ዮሃንስ ሊሳካ በአዲስ አበባ የአራዳ ክፍለ ከተማ ነዋሪ ነው፡፡ በተዘዋዋሪ የብድር ፈንዱ ጥቂት የማይባሉ ወጣቶች ህይወታቸው መለወጡን ያነሳል፡፡ እርሱ በቅርበት የሚያውቃቸው ጎዳና ላይ ተቀምጠው ይውሉ ከነበሩ ወጣቶች መካከል ጥቂት የማይባሉት ከተዘዋዋሪ ፈንዱ ብድር ወስደው ወደ ስራ ገብተው ራሳቸውን እና ቤተሰባቸውን መጥቀም መጀመራቸውን ይናገራል፡፡ በሌላ በኩል ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተመርቀው ስራ አጥተው ሰፈር ይውሉ የነበሩና ለቤተሰቦቻቸው ሸክም ሆነው የነበሩ በርካታ ወጣቶችም ከተዘዋዋሪ ፈንዱ በመጠቀም ሀገራቸውንና ራሳቸውን እየጠቀሙ ናቸው፡፡ ይህንንም ማየት እንደሚያደስተው ነው የገለጸው፡፡
ነገር ግን ለከተማዋ ወጣቶች የተመደበው ተዘዋዋሪ ብድር ፈንድ በሚፈለገው ልክ ወጣቶችን ተጠቃሚ አድርጓል ብሎ እንደማያምን የሚናገረው ወጣት ዮሃንስ፤ በተለይም ከከተማዋ ስራ አጥ ወጣቶች አንጻር ሲታይ እጅግ አነስተኛ በመሆኑ ከፍላጎት ጋር ሊጣጣም አልቻለም፡፡ ይህም በሚፈለገው ልክ የወጣቶችን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ እንዳይቻል አንዱ ምክንያት ሆኗል የሚል እምነት እንዳለው ይናገራል፡፡
እንደ ወጣት ዮሃንስ ማብራሪያ፤ የገንዘቡ መጠን አነስተኛ ከመሆኑ ባሻገር፤ የተመደበው ፈንድ አጠቃቀም ላይ በሚስተዋሉ ብልሹ አሰራሮች የተነሳ የወጣቱ ተጠቃሚነት በሚፈለገው ደረጃ አልተረጋገጠም፡፡ የብድር አቅራቢ ተቋማት አሰራር የተንዛዛ በመሆኑ ወጣቶች ተስፋ ቆርጠው ተዘዋዋሪ ፈንዱን እንዳይጠቀሙ ምክንያት ሆኗል፡፡
ቢሮክራሲውን ሆነ ብለው በማንዛዛት ወጣቶች ተዘዋዋሪ የብድር ፈንድ እንዳይጠቀሙ የሚያደርጉ ግለሰቦች መኖራቸውን የሚናገረው ወጣት ዮሃንስ፤ እርሱ ራሱ የዚህ ችግር ሰለባ መሆኑን ይናገራል፡፡ ከጓደኞቹ ጋር በመሆን ለአምስት ተደራጅተው ሁሉንም መስፈርቶች አሟልተው ሊበደሩ ቢሄዱም በተንዛዛ ቢሮክራሲ ምክንያት ቡድኑ እንደፈረሰ ተናግሯል፡፡ በውጣ ውረድ ተስፋ እንድንቆርጥ ከተደረገ በኋላ ከማህበሩ አባላት መካከል አንዷ ሴት ከተዘዋዋሪ የብድር ፈንድ መበደሯን ትታ ከፋይናንስ ተቋሙ (ተዘዋዋሪ የብድር ፈንዱን እንዲያስተዳድር የተወከለው አዲስ የብድርና ቁጠባ ተቋም አክሲዮን ማህበር) ብቻዋን መደበኛ ብድር እንድትወስድ ምክር እንደለገሷት ገልጾ፤ ልጅቷ ከቡድኑ ራሷን እንድታገል መደረጉን ለአብነት ይጠቅሳል፡፡
እንደ ወጣት ዮሃንስ ማብራሪያ፤ መንግስት ተዘዋዋሪ ፈንዱን እንዲያስተዳድር ኃላፊነት የሰጠው ተቋም አሰራር መፈተሽ አለበት፡፡ ወጣቶችን ለምሬት እና እንግልት የሚዳርጉ ተቋማት አሰራራቸውን የማያሻሽሉ ከሆኑ መንግስት ተዘዋዋሪ የብድር ፈንዱን በግል እና በመንግስት ባንኮች አማካኝነት ለህዝቡ ተደራሽ የሚያደርግበትን ሁኔታ ሊያመቻች ይገባል፡፡
ለወጣቶቹ ከተዘጋጀው የብድር መጠን ማነስና ብድር አቅራቢ የፋይናንስ ተቋማት ውስጥ ከሚታዩ ብልሹ አሰራሮች በተጨማሪ፤ ወጣቶች ስለ ተዘዋዋሪ የብድር ፈንዱ ያላቸው ግንዛቤ አነስተኛ መሆኑም ወጣቶች ከተዘዋዋሪ ፈንዱ ተጠቃሚ መሆን ባለባቸው ልክ ተጠቃሚ እንዳይሆኑ ጋሬጣ ሆኗል የሚለው ወጣት ዮሃንስ፤ ወጣቶችን ግንዛቤ በማስጨበጥ ረገድ ሰፊ ስራ ሊሰራ እንደሚገባ ተናግሯል፡፡
የፌዴራል የከተማ ምግብ ዋስትናና የስራ እድል ፈጠራ ኤጀንሲ የኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ አሰፋ ፈረደ እንደሚናገሩት፤ መንግስት ለጥቃቅንና አነስተኛ ዘርፍ በሰጠው ትኩረት በስራ እድል ፈጠራ ላይ በመረባረብ የኢንተርፕራይዞችን ተወዳዳሪነት በማሳደግ አምራች ኢንዱስትሪዎችን ለማስፋፋት የማምረቻና መሸጫ ቦታ፣ የብድር አቅርቦት፣ የኢንዱስትሪ ኤክስቴንሽን እና የገበያ ትስስር ድጋፎች ሲደረግ ነበር፡፡ በዚህም መሰረት ሥራ ፈላጊ ወጣቶች በተለይ የከፍተኛ ትምህርት እና የቴክኒክና ሙያ ተቋማት ምሩቃን ጊዜያቸውንና እውቀታቸውን በመጠቀም ሥራ ፈጣሪዎች እንዲሆኑ በተለያየ አደረጃጀት ውስጥ ገብተው እርስ በእርሳቸው በክህሎት ተደጋግፈው ሊሰሩ የሚችሉበት አማራጮች መመቻቸቱን ይናገራሉ፡፡
በመሆኑም በከተሞች የሚገኙ ስራ ፈላጊ ወጣቶች በመረጡት የስራ መስክ መሰማራት እንዲችሉ ለወጣቶች በሁለት መልኩ የገንዘብ ድጋፍ ሲደረግ መቆየቱን ይናገራሉ፡፡ አንደኛው ቁጠባን መሰረት ያደረገ ብድር በማይክሮ ፋይናንሶች አማካኝነት እየቀረበ ሲሆን፤ ከዚሁ ጎን ለጎን መንግስት የወጣቶችን የፋይናንስ ችግር ለመቅረፍ 10 ቢሊዮን ብር በመመደብ የወጣቶች ተዘዋዋሪ የብድር ፈንድ ማቋቋሙን ይናገራሉ፡፡
ተዘዋዋሪ የብድር ፈንዱ ከተቋቋመበት ከ2009 ዓ.ም ጀምሮ እስካሁን ድረስ ከ10 ቢሊዮን ብር ውስጥ 3 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር ለከተማ ወጣቶች መከፋፈሉን የሚያነሱት አቶ አሰፋ፤ ብድሩ ለወጣቶች ሲቀርብ የነበረውም ተገቢው የማጣራት ስራ ከተሰራ በኋላ መሆኑን ይናገራሉ፡፡ ተበዳሪዎቹ ወጣቶችና ስራ አጥ መሆናቸው ሲረጋገጥና ሌሎች ውስን መስፈርቶችን አሟልተው አምስት ሆነው ተደራጅተው ሲመጡ ሲቀርብላቸው እንደነበር አስታውሰዋል፡፡
እንደ አቶ አሰፋ ማብራሪያ፤ በተሰሩ ስራዎች በርካታ ስኬቶችን ማስመዝገብ ተችሏል፡፡ በርካቶች ራሳቸውን ከስራ አጥነት አውጥተው ራሳቸውን እና ሀገራቸውን ጠቅመዋል፡፡ ሆኖም የወጣቶችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚደረገው ጥረት ከችግር የጸደ አይደለም፡፡ በተለይም ለከተማ ወጣቶች የቀረበው የፋይናንስ መጠን አነስተኛ መሆንና ፈንዱን ተጠቃሚ መሆን የሚገባቸው ወጣቶች በሚፈለገው ልክ ተጠቃሚ ሳይሆኑ ተጠቃሚ መሆን የማይገባቸው አካላት ተጠቃሚ የሆኑባቸው አካባቢዎች እንዳሉ ለማወቅ ተችሏል፡፡
በብድሩ ተጠቃሚ መሆን ያለባቸው ወጣቶች ሳይጠቀሙ እንዳይቀሩ እና ተጠቃሚ መሆን የሌለባቸው ተጠቃሚ እንዳይሆኑ የተለያዩ ጥንቃቄዎች ሲደረግ ነበር የሚሉት አቶ አሰፋ፤ በዚህም በርካቶች ያለ አግባብ ተጠቃሚ ሊሆኑ ሲሉ ታግደዋል ብለዋል፡፡ በሌላ ጎን ተጠቃሚ ሳይሆኑ ሊቀሩ የነበሩ ወጣቶች ተጠቃሚ እንዲሆኑ ማድረግ ተችሏል፡፡ ሆኖም ሾልከው የገቡ አንዳንድ አካላት የወጣቶችን እድል በመዝጋት ለወጣቶች የተበጀተውን በጀት ሲሻሙ እንደነበር ከህብረተሰቡ በቀረበው ጥቆማ እና በተደረገው ምልከታ ታውቋል፡፡
እንደ አቶ አሰፋ ማብራሪያ፤ ገንዘቡ ከወጣትነት እድሜ ክልል ውጭ ላሉት እና ለሌሎች አግባብ ባልሆነ መንገድ እንዲታደል ሲደረግ የነበረው አንድም በማወቅ የተወሰነ አካልን ተጠቃሚ ለማድረግ ሆን ተብሎ ሲሆን፤ በሌላ በኩል ሳያውቁ እንዲህ አይነት ተግባር የተፈጸመባቸው አካባቢዎች ነበሩ፡፡ የፌዴራል የከተሞች የሥራ ዕድል ፈጠራ እና የምግብ ዋስትና ኤጀንሲ እርምጃ እንዲወስድ የሚያስችል ስልጣን የለውም፡፡ ችግሩ ሲፈጠር በክልሎች፣ በከተማ አስተዳደሮች እና በወረዳዎች ያሉ አካላት የማስተካከያ እርምጃ እንዲወስዱ ድጋፍ ሲያደረግ ነበር፡፡ አሁንም ይህን ችግር ሲፈጥሩ የነበሩት ተጠያቂ እንዲሆኑ ጫና የመፍጠር ስራው ተጠናክሮ ይቀጥላል፡፡
ከኤጀንሲው የተገኘው መረጃ እንደሚያመ ላክተው፤ በተያዘው በጀት ዓመት 1 ነጥብ 8 ሚሊዮን ለሚሆኑ የከተማ ወጣቶች ቋሚና ጊዜያዊ የስራ እድል ለመፍጠር እቅድ ተይዟል፡፡ ወጣቶቹ ተደራጅተው ከመንግስት አስፈላጊውን ድጋፍ አግኝተው ወደ ስራ እንዲገቡና ራሳቸውን እና ሀገራቸውን እንዲጠቅሙ ለማድረግ የተለያዩ የቅድመ ዝግጅት ስራዎች እየተሰሩ ነው፡፡ በመጀመሪያው ሩብ ዓመት የተለያዩ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠናዎችና የአቅም ግንባታ ስራዎች ተሰርቷል፡፡
አዲስ ዘመን ታህሳስ 28/2011
መላኩ ኤሮሴ