ትምህርት ሚኒስቴር በ2012 ዓ.ም የትምህርት ጊዜ እንዳይስተጓጎል ጠንካራ ሥራ ሰርቻለሁ ብሏል። በዩኒቨርሲቲዎች ህግና ሥርዓት በጥብቅ እንዲተገበሩ የሥነ ምግባር መመሪያና ደንቦችን አዘጋጅቻለሁ ብሏል፤ መመሪያና ደንቦቹን ተግባራዊ አለማድረግ ምን ዋጋ ያስከፍላል? ተቋማቱስ ለዚህ ምን ያህል ዝግጁ ሆነዋል?
የአክሱም ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶክተር ፀሐዬ አስመላሽ በ2012 ዓ.ም በዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ የሚታየውን የሥነምግባር ችግር ለመፍታት የተዘጋጀው መመሪያና ደንብ ከሁሉም ባለድርሻ አካላት
ጋር በመነጋገር ሰላማዊ የመማር ማስተማር አውድ ለመፍጠር ዝግጅት ማድረጋቸውን ይገልፃሉ። የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ከሚገበዩት ዕውቀት ጎን ለጎን ሙሉ ስብዕናቸው መቅረጽ አለበት የሚሉት ፕሬዚዳንቱ ወደፊት ማህበረሰቡን ሲቀላቀሉ ኃላፊነትን መሸከም የሚያስችል ቁመና ሊኖራቸው ይገባል ብለዋል።
ባለፉት ዓመታት ከነበረው ልምድ መረዳት እንደሚቻለው ተማሪዎቻችን መብታቸውን ብቻ የሚያቀነቅኑ እንጂ ግዴታቸውንና በእነሱ ኃላፊነት መወጣት የሚገባቸውን ነገር ብዙም ሲወጡ አልታዩም የሚሉት ደግሞ የዲላ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶክተር ችሮታው አየለ ናቸው ። በአንድ አቅጣጫ ብቻ መብታቸው በመለጠጡም ወዳልተፈለገ ሁኔታ እንዲነጉዱ ምክንያት ሆኗል ሲሉ ያስታውሳሉ። የወጣው ህግና ደንብም ዩኒቨርሲቲዎች ሰላማዊ የመማር ማስተማር ሂደት እንዲከናወንባቸው የሚያግዝ መሆኑን አመልክተዋል።
የዲላ ዩኒቨርሲቲ ምንም እንኳን ባለፈው ዓመት በፍጹም ጸጥታ ያሳለፈ ቢሆንም ከዚህ በፊት በደቡብ ክልል ውስጥ የረብሻ ማዕከል እንደነበር ዶክተር ችሮታው አስታውሰዋል። የሰላም መሻሻል የታየውም በዩኒቨርሲቲው የተቋቋመው የሰላም ፎረም ከወትሮው በተለየ ተማሪዎች የራሳቸውን ሰላም የሚጠብቁበትን አደረጃጀት በመዘርጋቱ ነው። የሥነምግባር ደንብና መመሪያውም ይህንኑ የሚያጠናክር መሆኑንም ገልጸዋል።
የጂንካ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ፕሮፌሰር ገብሬ ይትንሶ በበኩላቸው መንግሥት የሀገሪቱን ሰላም ለማረጋገጥ እየወሰደ ባለው ቁራጥ አቋም ለዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችና መምህራን ይፋ ያደረገው የሥነምግባር ደንብ ከአሁን በፊት የነበረውን ገጽታ እንደሚቀይረው ተስፋ አድርገዋል። የዲስፕሊን ጉዳይ ትኩረት ማግኘቱ ሰላማዊ የመማር ማስተማር ስርዓት እንዲፈጠር ከማስቻሉም በላይ አጠቃላይ የሀገሪቱን ሰላም ለማስፈን አጋዥ ነው ብለዋል።
የጂንካ ዩኒቨርሲቲ የተማሪዎችን ዲስፕሊን በተመለከት ቀደም ሲልም የራሱን መንገድ በመከተል ውጤታማ ሥራ እንደሠራ አስታውሰው ባለፉት ሁለት ዓመታት የመማር ማስተማሩን ሂደት ያደናቀፈ ችግር አለመታየቱን በተሞክሮነት ገልጸዋል። ተማሪዎች በመኖሪያ ቦታቸው እያሉ በሚሄዱበት ዩኒቨርሲቲ ምንም ዓይነት ሁከት ላለመፍጠር ውል ገብተው እንዲመጡ መደረጉም ለዩኒቨርሲቲዎች ሰላማዊነት የተሰጠውን ትኩረት የሚያሳይ እንደሆነ ፕሮፌሰሩ ተናግረዋል ።
እንደ ዶክተር ችሮታው ገለፃ ከሁሉ በላይ የሰላሙ ተጠቃሚ እራሱ ተማሪው ነው። የሰላም አለመኖር ተማሪዎች ተገቢውን ዕውቀትና ክህሎት ይዘው እንዲወጡ ስለማያደርጋቸው በአካዳሚክ ብቃታቸውና በቀጣይ ህይወታቸው ላይ ተጽዕኖ እንዳይፈጥርባቸው እግር በእግር እየተከታተሉ ግንዛቤ ማስጨበጥ ይገባል።
ከ2012 ዓ.ም ጀምሮ በሥራ ላይ ሊውል የታሰበው መመሪያና ደንብ በተማሪዎች አለባበስ ፣ጸጉር አቆራረጥ ንብረት አጠባበቅና በመሳሰሉ ልዩ ልዩ የሥነምግባር ደንቦች ላይ ያተኮረ መሆኑ በዩኒቨርሲቲዎች ሰላማዊ የመማር ማስተማር ተግባር እንዲከናወን የሚያደርግ ብቻ ሳይሆን ማንነታቸውንም እንዲጠብቁ የሚያነቃ ነው።
ዶክተር ፀሐዬ ይህንኑ ሀሳብ ሲያጠናክሩ ተማሪዎች ለራሳቸውና ለሀገራቸው ጠቃሚ እንዲሆኑ ቆንጠጥ አድርጎ በመያዝ ባህሪያቸውን ማረቅ ይገባል ይላሉ። የነገ ሀገር ተረካቢ ዜጎችን የሚያፈሩ ዩኒቨርሲቲዎች በተማሪዎች የሥነ ምግባር ግንባታ ላይ ትኩረት ሰጥተው ለመስራት መዘጋጀታቸውም የሚያበረታታ ነው።
በሀገሪቱ ካሉ ዩኒቨርሲቲዎች በአንዱ ሁለት ተማሪዎች ሲጋጩ ጉዳዩ የብሄር መልክ ይዞ የሁሉም ዩኒቨርሲቲዎች ሰላም ሲታወክ እንደነበር ያስታወሱት ፕሬዚዳንቱ የአንዱ ዩኒቨርሲቲ ችግር ለሌላውም እንዳይተርፈው ሁሉም በተመሳሳይ መልክ የወጣውን መመሪያና ደንብ ተግባራዊ ማድረግ እንደሚገባቸውም ዶክተር ፀሐዬ አሳስበዋል።
ይህ መመሪያና ደንብ የመምህራንን የሥነምግባር ግድፈትም የሚመለከት መሆኑ ከመማር ማስተማር ተግባራቸው ውጭ የፖለቲካ ጉዳዮችን የሚያራምዱ መምህራንን አደብ ለማስገዛት ጥቅም እንዳለው ዶክተር ችሮታው አስረድተዋል። ከዚህ በፊት በዲላ ዩኒቨርሲቲ ችግር በፈጠሩ መምህራን ላይ እርምጃ መወሰዱን ያስታወሱት ፕሬዚዳንቱ አሁንም ተግባራዊ የሚደረገው ህግ ተማሪዎችን ተጠቅመው የፖለቲካ ትኩሳቱን ለማባባስ በሚፈልጉ መምህራን ላይ እርምጃ ለመውሰድ የሚያስችል ነው ብለዋል።
ዶክተር ፀሐዬ በበኩላቸው መምህራንን በተመለከት የወጣው የስነ ምግባር መመሪያና ደንብም አስፈላጊ መሆኑ ባያጠራጥርም አክሱም ዩኒቨርሲቲ ግን ሁልጊዜ ሥራ ከመጀመሩ በፊት ከመምህራን ጋር በዩኒቨርሲቲው ሰላማዊ የመማር ማስተማር ሂደት እየተመካከረ የመሥራት ልምድ አለው ብለዋል። በመምህራን በኩል ምንም ዓይነት ችግር እንደሌለና ይልቁንም የሚፈጠሩ ችግሮችን ለመፍታትና ተማሪዎችን ለማረጋጋት ግንባር ቀደም ሚና የሚጫወቱት መምህራን መሆናቸውን ገልጸዋል።
ዶክተር ፀሐዬ በዩኒቨርሲቲዎች የሚስተዋለው አለመረጋጋትና የተማሪዎች የእርስ በእርስ ግጭት መነሻው የሀገሪቱ ፖለቲካ ሁኔታ እንደሆነ ገልጸው ችግሮች እንዳይባባሱ ከማድረግ አንጻር የወጣው መመሪያና ደንብ ለተማሪውም ይሁን ለዩኒቨርሲቲው ደህንነት ጠቃሚ ነው ብለዋል።
ዩኒቨርሲቲው ህብረተሰቡ ውስጥ ያለ እንደመሆኑ ከውጭ የሚከሰተው ችግር ዩኒቨርሲቲ ውስጥ እየገባ ሌላ ችግር ሲፈጥር እንደነበርም ፕሮፌሰር ገብሬ አስታውሰዋል። ዩኒቨርሲቲዎች በአንድ ላይ የተሰባሰቡና በወጣትነት የዕድሜ ክልል ውስጥ ያሉ ተማሪዎች መገኛ እንደመሆናቸው ይህንን ስብስብ ለፖለቲካ አጀንዳ ማስፈጸሚያነት የሚጠቀሙ ኃይሎች መኖራቸውም መታሰብ ይኖርበታል ብለዋል።
የከፍተኛ ትምህርት ተቋም ተማሪዎች በሚሊዮኖች ከሚቆጠሩ ተማሪዎች ነጥረው የወጡና በእውቀት በአስተሳሰቡና በክህሎት የተሻሉ መሆናቸውን የተናገሩት ዶክተር ችሮታው በበኩላቸው በሀገሪቱ ከፍተኛ በጀት የሚፈሰው ለትምህርት ዘርፍ በይበልጥም ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማት መሆኑን ጠቅሰዋል። ስለሆነም ተማሪዎች በርካታ የህዝብ ሀብት እንደሚፈስባቸውም ተረድተው የህዝባቸውንና የሀገራቸውን ውለታ ለመመለስ መዘጋጀት አለባቸው ብለዋል። ተማሪዎች ሰላማቸውን በማስጠበቅ፣ በትርፍ ጊዜያቸው የተቸገሩትን በመደገፍና በማስተማር ለተተኪዎቻቸው ምሳሌ መሆን እንደሚገባቸውም አስረድተዋል።
ፕሮፌሰር ገብሬ ወደ ዩኒቨርሲቲ የሚመጡ ተማሪዎች የተለያየ ማህበራዊ ዳራ እንዳላቸው ተረድተው እንደ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች አስፍተው በማሰብ ተከባብረው ተቻችለውና ተመካክረው ሊኖሩ እንደሚገባቸው መክረዋል። ለሀገራችን ልማትና እድገት ዋናው የስልጣኔ መንገድ ትምህርት ነው ያሉት ፕሬዚዳንቱ ተማሪዎች ዩኒቨርሲቲ ገብተው በሰላማዊ መንገድ መማር ከቻሉ የታሰበውን ስልጣኔ ማምጣት ይቻላል ብለዋል። ፖለቲከኞችም ወጣቶች የትምህርት ጊዜያቸውን በአግባቡ እንዲጠቀሙ ዕድል ሊሰጧቸው እንደሚገባ ተናግረዋል።
የዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንቶቹ እንዳስታወቁት መንግሥት የሀገሪቱን ሰላም ወደ ነበረበት ለመመለስ እያደረገ ያለው ሀገራዊ ንቅናቄ የሚደገፍ ነው። ዩኒቨርሲቲዎችም የዚህ ንቅናቄ አንድ አካል በመሆን ትኩረት ማግኘታቸው ተገቢ እንደሆነ ገልጸዋል። የወጡት መመሪያና ደንቦች ተግባራዊ መሆን ሲችሉም ከዚህ በፊት ይታዩ የነበሩ ግርግሮችን በማስወገድ ሰላማዊ የመማር ማስተማር ሥርዓት ለማስፈን እንደሚያስችል ይጠበቃል።
አዲስ ዘመን መስከረም 8/2012
ኢያሱ መሰለ