በቅርቡ አንድ ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ነበርኩ። በመግለጫው አንድ ሦስት ያህል ፈረንጆች ነበሩና ንግግሮች ሁሉ በእንግሊዝኛ ነበሩ። መግለጫውም በእንግሊዝኛ ተደረገ። ለጋዜጠኞች የጥያቄ ዕድል ሲሰጥ፣ መግለጫው በእንግሊዝኛ ነበርና ጋዜጠኞችም ጥያቄያቸውን በእንግሊዝኛ አደረጉ። ከአንድ የቴሌቪዥን ጣቢያ የመጣ ጋዜጠኛ ፈረንጆችን ይመለከታል ያለውን አንድ ጥያቄ በእንግሊዝኛ ከጠየቀ በኋላ ሌሎች ጥያቄዎቹን በአማርኛ አደረገ። ምክንያቱም እነዚያ ጥያቄዎች የሚመለከቱት በቀጥታ መግለጫ ሰጪውን (ኢትዮጵያዊውን ማለት ነው) ነበር።
ይሄ አይደለም የገረመኝ! መግለ ጫውም፣ ጥያቄና መልሱም ሙሉውን በእንግሊዝኛ ሆኖ ረጅም ሰዓት ያስወራው ግን የአማርኛው መግለጫ ነበር። የዚያን መግለጫ የመገናኛ ብዙኃን ሽፋን እንደተከታተልኩትም፤ የአብዛኞቹ ‹‹አን ግል›› በአማርኛው ጥያቄ እና በአማርኛው ማብራሪያ ላይ ነበር።
ለምን ይሄ ሆነ?
መቼም እንግሊዝኛውን ስላልተረዱት ነው የሚል የዋህነት አይኖርም። የቱንም ያህል እንግሊዝኛ የሚቸግረው ሰው ቢሆን ለዚያ መግለጫ የሚሆን እንግሊዝኛ አያጣም! አስቸገረ ቢባል እንኳን የራሳቸው የፈረንጆች እንግሊዝኛ እንጂ ኢትዮጵያዊ የሚያወራው እንግሊዝኛ ለማንም አያስቸግርም። ችግሩ ያ አልነበረም!
ብዙ ጊዜ ልብ ብላችሁ ከሆነ በእንግሊዝኛ ውይይት የሚደረግባቸው መድረኮች ላይ ሃሳቡ ጥልቀት የለውም። የሚነገረው ጉዳይ ቀጥታ በማስታወሻ የተያዘውን ወይም መናገር የፈለጉትን ብቻ ነው። መናገር ያልፈለጉትን ነገር መዘባረቅ አለባቸው እያልኩ አይደለም፤ ዳሩ ግን ውይይት ወይም ገለጻ ማለት አስበው የመጡትን ብቻ አይደለም። ነገርን ነገር ሲያነሳው ከሁኔታዎች ተነስቶ አዳዲስ ነገርም ይወራል።
በእንግሊዝኛ የሚደረጉ ንግግሮች ላይ አካባቢያዊ ነገሮችን፣ ተረትና ምሳሌዎችን፣ ገጠመኞችን እያጣቀሱ ነገሩን ሲያሰፉት አይታይም። በአንጻሩ በአፍ መፍቻ ቋንቋ ንግግር በሚደረግበት ጊዜ ደግሞ አዳዲስ ሃሳቦች ይወጣሉ። ንግግሮች ለዛ ያላቸውና የማያሰለቹ የተዋዙ ይሆናሉ። በእንግሊዝኛ ንግግሮች ግን ይሄ አይስተዋልም።
በመማር ማስተማር ሂደት ውስጥ የክፍል ውስጥ ገለጻን ልብ ብላችኋል? የዩኒቨርሲቲ ተማሪ እያለሁ አንድ የማስታውሰው ነገር ነበር። የምርመራ ጋዜጠኝነት ኮርስ የሚሰጠን መምህር አማርኛ ክፍል ውስጥ አያወራም ነበር። አማርኛ የማይችል ሆኖ እንዳይመስላችሁ! መምህሩ ከክፍል ውጪ በብዙ አጋጣሚ እናውቀዋለን፤ ከአማርኛ ውጪ ሌላ ቋንቋ ሲናገር ሰምተነው አናውቅም።
የመምህሩ ሃሳብ ሌላ ሳይሆን የዩኒቨርሲቲ ማስተማሪያ ቋንቋ እንግሊዝኛ ስለሆነ ህግ ማክበሩ ነው። በሌላ በኩል ያለን የእንግሊዝኛ ቋንቋ ችሎታ አነስተኛ ስለሆነበት ልምዳችንን እንድናዳብር በማሰብ ነው። እንዲያውም አንድ ቀን ሥራዬ ብሎ ስለዚህ ጉዳይ ብቻ ለረጅም ሰዓት መክሮናል። የመምህሩ ትክክልነት እንዳለ ሆኖ ችግሮቹን ግን እንመልከት።
የዩኒቨርሲቲ ተማሪ ማለት ከ12 ዓመት በላይ በትምህርት የቆየ ነው። እንግሊዝኛ መቻል ካለበት እስከአሁን ነው። ዩኒቨርሲቲ መመራመሪያና በአንድ ሙያ ላይ ብቁ የሚሆኑበትን ክህሎት የሚያዳብሩበት እንጂ ገና ቋንቋ የሚለማመዱበት አይደለም። እርግጥ ነው የቋንቋም ሆነ የየትኛውም ትምህርት አያልቅም፤ በሥራ ላይ እያለም ቢሆን ቋንቋ ሊለምድ ይችላል፤ ግን ዩኒቨርሲቲ ውስጥ ትኩረት መደረግ ያለበት ሃሳብ ላይ ነው ወይስ ገና የእንግሊዝኛ ቋንቋ ልምምድ ላይ?
በክፍል ውስጥ ስንማር አንዳንድ አካባቢያዊ ነገሮችን በአፍ መፍቻ ቋንቋችን እናወራ ነበር። በዚህም ጥልቅ ውይይትና ክርክር ነበር የምናደርግ። በእንግሊዝኛ ሲሆን ግን ቀጥታ አካዳሚያዊ ጉዳዩን ብቻ ነበር የምናወራው። በእንግሊዝኛ ከፍተኛ ልምድ አለኝ የሚለው መምህሩም ቢሆን እንደዚያው ነበር። በአማርኛ የሚያወራን እና በእንግሊዝኛ የሚያወራን ይለያያል። በእንግሊዝኛ የሚያወራን ቀጥታ መጽሐፉ ላይ ያለውን ነው፤ ኢንተርኔት ላይ የምናገኘውን ነው። ከዚህ አለፍ ካለም የውጭ አገር ገጠመኞችንና ማሳያዎችን ነው።
በአማርኛ በምናወራበት ጊዜ ግን ከአካዳሚያዊ ኮርሱ ወጣ ይል ነበር። ማሳያዎቹና የሚጠቀሱት ምሳሌዎች ሰፋ ያሉ ይሆናሉ። የአገር ውስጥ የመገናኛ ብዙኃን ፕሮግራሞችን ምሳሌ እያነሳን ስናወራ ውይይቱ የጠለቀ ይሆን ነበር።
እዚህ ላይ አንድ መከራከሪያ ሊነሳ ይችላል። መምህሩም ሆነ ተማሪዎች የእንግሊዝኛ ቋንቋ ችግር ስላለባቸው እንጂ በእንግሊዝኛ ጥልቅ ውይይት ቢደረግ ምን ችግር አለው? የአገር ውስጥ መገናኛ ብዙኃን ፕሮግራሞችም ሆኑ ተረትና ምሳሌዎች ለምን በእንግሊዝኛ አይቀርቡም? የእሳት ዳር ጨዋታዎች ለምን በእንግሊዝኛ አይወሩም? ብሎ መከራከር ያስኬዳል፤ ግን አይቻልም! የቱንም ያህል ጎበዝ እንግሊዝኛ ተናጋሪ ቢሆን ሁለተኛ ቋንቋ እንደ መጀመሪያ ቋንቋ ሊሆን አይችልም። የውጭ አገር ቋንቋ በአካባቢ ያደግንበትን ባህልና ወግ ሊገልጽ አይችልም።
ለዚያውም እኮ ደግሞ ይሄ አካዳሚያዊ ነው፤ ይሄ ማለት ለእንግሊዝኛ ቋንቋ ቅርብ ነው ማለት ነው። መማሪያ መጽሐፉም በእንግሊዝኛ ስለሆነ መምህሩም ተማሪዎችም ይላመዱታል።
በማህበራዊ፣ ፖለቲካዊና አካባቢያዊ ውይይቶች ላይ ግን የተፈለገውን ያህል አያስኬድም። ማንም ሰው በሁለተኛ ቋንቋው የአፍ መፍቻ ቋንቋውን ያህል ሃሳቡን በትክክል ሊገልጽ አይችልም።
ልብ ብዬ የታዘብኩት ጋዜጣዊ መግለጫዎች ላይ ነው። ጋዜጠኞች ደግሞ ለየት ያለ አንግል ይፈልጋሉ። ያ ለየት ያለ አንግል የሚገኘው በአማርኛ በሚደረገው ገለጻ ነው። በእንግሊዝኛ የሚያደርጉት ገለጻ የተለመደና ጠቅላላ እውነታ ነው። ወይም ደግሞ አሃዛዊ መረጃ እና የተቋሙ የአፈጻጸም ሪፖርት ብቻ ነው። ለማስረዳት የሚጠቀሙት አገላለጽ ለየት ያለ ሃሳብ አይወጣውም።
ይሄ ነገር የሚያጋጥመው አንድ ወይም ሁለት ፈረንጆች ባሉበት ቦታ ነው። አንድ የማንፈርድበት ምክንያት አለ። ስንትም ይሁኑ ስንት እነዚያ ፈረንጆች በማያውቁት ቋንቋ የሚደረግን ገለጻ ቁጭ ብለው መከታተል አይችሉም። ስብሰባ እንኳን በማያውቁት ቋንቋ በራስ ቋንቋም ይሰለቻል። እንግሊዝኛ ደግሞ ሁሉንም ስለሚያግባባ በእንግሊዝኛ መሆኑ ችግር የለውም። ግን እነዚያ የጠቀስኳቸው ችግሮች እያጋጠሙ ነው።
እኔ ደግሞ አንድ አስተያየት አለኝ። ፈረንጆች ባሉበት መድረክ ውስጥ በአማርኛ ቋንቋ ሲወራ ‹‹ለካ እንዲህ የራሳቸው ቋንቋ አላቸው›› የሚሉ ይመስለኛል። ‹‹ነፃነታችንን፣ ማንም በቅኝ ገዝቶ ያልቀየረብን፣ የራሳችን ቋንቋና ባህል እንዳለን ይወቁት እስኪ›› እላለሁ በውስጤ! በእንዲህ ዓይነት አጋጣሚ ካላዩት ታዲያ የራሳችን ቋንቋ እንዳለን በምን ያውቃሉ? እስኪ እነርሱም እየተተረጎመላቸው ይስሙ!
ለማንኛውም እንደሁኔታው ነው መሆን ያለበት። የግድ በእንግሊዝኛ ቋንቋ ማድረግ ካስፈለገ ይደረግ፤ ዳሩ ግን በቂ ዝርዝር ወሬ ይኑረው። በተለይም በጋዜጣዊ መግለጫ ጊዜ ደግሞ ለአገር ውስጥ መገናኛ ብዙኃን በሚያሰራጩበት ቋንቋ መሰጠት አለበት። አንድ ኢትዮጵያዊ በእንግሊዝኛ እየተናገረ ሲተረጎም ደግ ነው እንዴ?
በአንድ ገጠመኝ ሃሳቤን ልደምድም!
በመስከረም ወር ነው (ዓመት ሊሆነው ቀናት ናቸው የቀሩት)። የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት በባህ ርዳር ያዘጋጀው አንድ የውይይት መድረክ ነበር። ጥናቶች ሁሉ የተዘጋጁት በእንግሊዝኛ ቋንቋ ነው። ውይይቱ ከመጀመሩ በፊት የተለመደው በኃላፊነት ላይ ያሉ ሰዎች ንግግር ሊደረግ ነው። የተዘጋጁት የፕሮግራም ቅጾች፣ የተለጠፉ ማስታወቂያዎች ሁሉ በእንግሊዝኛ ናቸው። መድረክ አስተዋዋቂውም በእንግ ሊዝኛ ጀመረ፤ ለንግግር የሚጠራቸው ሰዎችም በእንግሊዝኛ ሲያወሩ ቆዩ።
በመጨረሻ ከአማራ ክልል ጤና ጥበቃ ቢሮ በኃላፊነት ላይ ያሉ ሰው ለንግግር ተጠሩ። መድረኩ ላይ ወጥተው ቃኘት ቃኘት አደረጉና እንዲህ አሉ። ‹‹እዚህ አዳራሽ ውስጥ ፈረንጅ እየፈለኩ ነበር፤ አንድም የለም፤ ንግግሬን በአማርኛ ባደርግ ችግር አለው?›› ብለው ሲጠይቁ የአዳራሹ ታዳሚ በሙሉ በሳቅና በጭብጨባ አደበላለቀው።
በአማርኛ መናገር እንዲህ ናፍቋቸው ከነበር ለምን ይሆን ያን ያህል ሲቸገሩ የቆዩ?
አዲስ ዘመን ነሀሴ 11/2011
ዋለልኝ አየለ