ሙሉ እና ጎዶሎ ቁጥሮች በስያሜዎች ላይ የሚያመጡት ውጤት ምን ያህል ከባድ እንደሆነ ብዙዎች ልብ አንለውም። ነገሩ ልማድ ወይም ባህል ነው ብለን የምንተወውም ጥቂቶች ላንሆን እንችላለን። ነገር ግን ሙሉና ጎዶሎ ቁጥር ትልቅ ኃይል ያለው ተግባርን ይከውናል። ለዚህም በአብነት የምናነሳው የ13 ቁጥርን ዋጋ ነው። ብዙዎች በተለይም አውሮፓውያን ይህንን ቁጥር ገደቢስ፤ መጥፎ ዕድል መገለጫ ያደርጉታል። ስለዚህ በዚህ ቁጥር የሚሰየም ማንኛውም ነገር በአውሮፓውያኑ ዘንድ የተጠላ ይሆናል። እኛ ግን የአገራችን መለያ አድርገን የ13 ወር ጸጋ እያልን ስንጠቀምበት ቆይተናል። ምክንያቱም ለእኛ ደግሞ ምክንያት አለውና።
በየትኛውም ቦታ 13 ወር ሙሉ ፀሐይ የሚታይበት አገር የለም። ስለዚህም የ13 ወር ጸጋ ባለቤቶች መሆናችንን ለማሳየት ሲባል ይህ መለያ አድርገነው ስንጠቀምበት ቆይተናል። ሆኖም ግን በስያሜው ያጣነውን ለማግኘት እና የኢትዮጵያን ማንነት በይበልጥ መግለጽ የሚችል ስያሜ በማግኘታችን መለያ ስያሜያችንን «ምድረ ቀደምት» ወደሚለው ለውጠናል።
ምድረ ቀደምት የሚለው መለያ ለሀገራችን ያንሳት እንደሆነ እንጂ አይበዛባትም የሚሉ ብዘዎች ናቸው። ለአብነት በአንድ ወቅት የተባበሩት መንግሥታት የዓለም ቱሪዝም ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ታሊብ ራፋይን የተናገሩትን እናስታውሳለን። «እርግጥ ነው ‘ምድረ ቀደምት’ ተብላለች፤ ይህንን መለያ እያደነቅሁ ግን ደግሞ ኢትዮጵያ ከዚያም በላይ መሆኗን እመሰክራለሁ:: የቀደመው የሰው ልጅ መገኛ ብቻ ሳትሆን የደጋጎች፣ የሳቂታዎች፣ የጀግኖች፣ የአዋቂዎች፣ …ምድር ነች፡፡ ኢትዮጵያ ምድረ ቀደምት መባል የሚያንሳት ልዩ የመስህብ ሀገርም ነች።» ብለዋል። እውነት ይህን ያስባላቸው ምን ይሆን ካላችሁ ደግሞ መሰረታዊ ነጥቦችን እንጥቀስ።
የመጀመሪያው ጎንደርን በጎበኙበት ወቅት የኪነ ሕንፃ መሀንዲስ መሆናቸው በጎንደር አብያተ መንግሥታት የኪነ-ሕንፃ ጥበብ በእጅጉ መደመማቸው ነው። በዚህም እንዲህ ብለው ነበር «የፋሲል አብያተ መንግሥታት ኪነ-ሕንፃዎች እያንዳንዷ ጠጠር በምክንያት የተቀመጠችበት፣ የነገሥታቱንና የባለሙያዎቻቸውን የዕውቀት ደረጃ የሚመሰክሩ ናቸው።» ለመሆኑ በአገሪቱ ነባራዊ ሁኔታ ቀደምት የሚያሰኛት ምን ምን ነገሮች ይገኛሉ ካሉ መልሱ እንዲህ ነው። ከሰዓት አቆጣጠራችን እንነሳ። ኢትዮጵያ አንድ ብለን ነው የምንቆጥረው ሌሎች አገራት ግን ምንም እንኳን የቁጥር መጀመሪያ አንድ ቢሆንም ከሰባት ይነሳሉ። እንደውም በንግግራቸው «ጠዋት ሰባት ሰዓት እንገናኝ» ይላሉ።
«ጠዋትና ሰባት ሰዓት በምን መልኩ ይቀራረባሉ» ሲሉ ትችታቸውን የሚያቀርቡት በቱሪዝም ኢትዮጵያ በአገር አቀፍ ደረጃ የቱሪዝም መለያን በድጋሚ ለማስተዋወቅ የተጠናውን ጥናት ያቀረቡት በቱሪዝም ኢትዮጵያ የማርኬቲንግ ዳይሬክተር አቶ ወልደገብረኤል በርሄ ናቸው። እርሳቸው እንደሚናገሩት፤ ጠዋት መጀመሪያ ነው። አንድ ቀን ጨርሰን ሌላኛውን የምንጀምርበትም ነው። አዲስ ቀን እየጀመርን ግን ሰባት ሰዓት መባሉ ትርጉም አይሰጥም። ስለዚህም ትክክለኛውንና ቀዳሚ የሆነውን ሃሳብ ያመነጨችው ወይም እየተጠቀመችበት ያለችው ኢትዮጵያ ነች። ፀሐይ ስትወጣ አዲስ ቀን መሆኑን ተገንዝባ አንድ ብላ ትጀምራለች። ስለዚህ ይህ ጉዳይ ቀደምትነቷን ያረጋግጥላታል።
ሌላው የምድረቀደምትነቷ ምሳሌ ቡናን ለዓለም ያበረከተች መሆኗ ነው። አሁን በዓለም ደረጃ ሁለት ነጥብ 25 ቢሊየን ሲኒ ቡና በየቀኑ ይጠጣል። በአሜሪካ ብቻ በቀን አራት መቶ ሚሊዬን ስኒ ቡና ጥቅም ላይ ይውላል። ይህ ደግሞ ኢትዮጵያ ለዓለም ያበረከተችው ምርት ምን ያህል ዋጋ እንዳለው የሚያስረዳ መሆኑን ይናገራሉ። በመሆኑም ይህንን የሚጠቀሙ ሰዎች ኢትዮጵያ የምርቱ መሰረትና ምንጭ መሆኗን በመንገር ምድረ ቀደምትነቷን ተቀብለው ጎብኚዎች ወደ አገር እንዲመጡ ማድረግ ይገባል ይላሉ።
ኢትዮጵያ የሰው ዘር ብቻ ሳይሆን የብዙ ፍጥረታትም መገኛ ናት የሚሉት አቶ ወልደገብርኤል፤ አንድ ነገር ለመግዛት ስንሄድ «ኦርጅናል ነወይ» ብለን የምንጠይቀው ያለምክንያት አይደለም። ስለዚህም ኦርጅን የሚለውም ይህንን ኃይል ያሳያል፤ ያልተበረዘ መሆኑን ይገልጻል። በዚህም የሰው ዘር መገኛ መሆኗን እንናገራለን። ይህ ግን ያለምክንያት አይደለም የሚሉት አቶ ወልደገብርኤል፤ በዓለም አቀፍ ደረጃ የሰው ዘር አመጣጥን በተሻለ መልኩ ሊገልጹ ይችላሉ ተብለው ከተገኙ ቅሪት አካሎች 14 ከፍተኛ ዕድሜ ያለውና 12ቱን የያዘው ኢትዮጵያ የተገኘው መሆኑን ይናገራሉ። ይህ ደግሞ የሰው ልጅ ወደራሱ ታሪክ እንዲመጣ የሚያስችል ጠንካራ መሰረት ያለው መሆኑን ያስረዳሉ።
ሌላው ምድረቀደምት ያስባላት የአባይ ወንዝና ሸለቆ መፍለቂያና የስልጣኔ ጀማሪ መሆኗ ሲሆን፤ የአብዛኞቹ አገራት ስልጣኔ ምንጭ ወንዞች መሆናቸው ይጠቀሳል። በዚህም ኢትዮጵያም የአባይ ወንዝ መፍለቂያ ናት። ይህ ደግሞ ለአፍሪካ ሁሉ የሚደርስ በመሆኑ አፍሪካውያን ስልጣኔያቸውን ያገኙት ከኢትዮጵያ መሆኑን ይነግረናል። ምክንያቱም አባይ በርዝማኔው ብቻ ሳይሆን የተለያዩ ሰለጠኑ የምንላቸው አፍሪካውያን ህልውና ወስኗል ይላሉ።
ጥንታዊ የሙዚቃ ኖታዎች ባለቤት መሆኗም አንዱ ቀደምትነቷን የሚነግረን ነው የሚሉት ዳይሬክተሩ፤ በአውሮፓ ወይም በተለያዩ ዓለማት የሙዚቃ ኖታ የተጀመረው በ18ኛው ክፍለ ዘመን እንደሆነ ቢታወቅም አሻሽለውት ግን 1025 ዓ.ም እንደተጀመረ ይናገራሉ። ይሁን እንጂ ይህም ቢሆን በኢትዮጵያ በቅዱስ ያሬድ አማካኝነት በ540ዓ.ም ነው የተጀመረው። ስለዚህ ምድረቀደምት በሙዚቃ ኖታም ኢትዮጵያ መሆኗን ይገልጻሉ።
ዓለም የሳይንስና ቴክኖሎጂ ደረጃውን ከፍ እንዲያደርግ መሰረቱ ኢትዮጵያ መሆኗም ይናገራል። ለመጀመሪያ ጊዜ የሰው ልጅ ከእጁ ውጪ ሌላ መሳሪያን መጠቀም እንዲችል ያሳየች ነች። እነዚህ መሳሪያዎችም ስለት ያላቸው ድንጋዮች ሲሆኑ፤ ከ2 ነጥብ 6 ሚሊየን ዓመት በፊት በአፋር አካባቢ የተገኘ መረጃ ያረጋገጣቸው መሆናቸውን ይናገራሉ። ኢትዮጵያዊያን መሳሪያ ያስፈልገናል ብለው ባይጀምሩት ኖሮ ሳይንሱ የት ላይ እንደሚቆም መገመት አያዳግትም። ስለዚህ የቴክኖሎጂ ጀማሪ መሆናችን ቀደምትነታችንን ያረጋግጣል ባይ ናቸው።
ሌላው ምሳሌ የአፍሪካ ነፃነት ተምሳሌት መሆኗ ሲሆን፤ አፍሪካ በቅኝ ግዛት ሥር ስትሆን ነፃነቷን አስከብራ የቆየች ብቸኛ አገር ነች። ከዚያም አልፎ አፍሪካውያን ከባርነት ቀንበር እንዲላቀቁ መንገድ ከፍታለች። ማሸነፍና ነፃ መሆንን አስተምራለች። ለዚህም ማንዴላ ይህንን ሲሉ ተናግረዋል። «ፈረንሳይ፣እንግሊዝና አሜሪካን ከመጎብኘት ይልቅ ኢትዮጵያን መጎብኘት እመርጣለሁ። ምክንያቱም ወደ ራሴ ታሪክ፣ ወደራሴ ዘር፣ ወደራሴ አፍሪካዊነት እየተመለስኩ እንደሆነ አድርጌ ነው የማስበው።»
የመጀመሪያ ሄጅራ ከመካ ወደ መዲና ሳይሆን ከመካ ወደ ኢትዮጵያ እንደነበር ይናገራሉ። ለዚህም በምክንያትነት የሚያነሱት የነብዩ መሀመድን ጉዞ ነው። የነብዩ የቅርብ ቤተሰቦች ወደ ኢትዮጵያ ባይመጡ ወይም ኢትዮጵያ ባትቀበላቸው የእስልምና ሃይማኖት ዕጣ ፋንታ ያከትም ነበር። ምክንያቱም በወቅቱ ስደተኛ መቀበል ብዙ ዋጋ ያስከፍላል። ይሁንና አገሪቱ ሸሻጊ፣ እንግዳን ተቀባይና መልካም መስተንግዶ አድራጊ በመሆኗ ነብዩ መሀመድን ተቀብላ አስተናግዳቸዋለች። በዚህም የእስልምና ሃይማኖት ቀጣይነቱን ማረጋገጥ ችሏል።
የብሔር ብሔረሰቦች መገኛ፤ ውብና ማራኪ የመልከአምድር አቀማመጥ ያላት፤ ማለትም ህይወት ለሌላቸውና ላላቸው ምቹ የሆነች አገር ነች። የእንሰትና ጤፍ ምንጭ፤ የተዋቂ አትሌቶች መፍለቂያ ፤ የራሷ የሆነ ፊደል፣ ቀን አቆጣጠርና ቁጥር ያላት ብቸኛ አገር ነች። ይህ ደግሞ በሚገባ ምድረቀደምትነቷን ያስረዳል ብለዋል። ታዲያ ይህንን ሁሉ በቀደምትነት የያዘች አገር ስያሜው ያንስባት እንደሆን እንጂ አይበዛባትም።
ኢትዮጵያን ስለራሳችን ምን እናስባለን? ሲባል በጥናቱ የተገኘው « ኢትዮጵያ የብዙ ነገሮች መነሻ የሆነች፣ የሰው ዘር መገኛ፣ የቀደምት ስልጣኔ ባለቤት፣ ብዝሃነትን የሚያስተናግድ መቻቻልና ጠንካራ አንድነት ያለባት፣ የውብና ድንቅ መልከአምድር ባለቤት ነች።» ይህ ደግሞ መሬት ላይ ያለ ግን ያልተተዋወቀ መሆኑን አቶ ወልደገብርኤል ይናገራሉ።
«የብዙ ነገሮች መሰረት ነች፤ በአፈታሪክና እውነትነት ባላቸው ትንግርቶች የበለጸገች ነች፤ ታሪካዊና የጊዜ ፈተና ያልበገረው ባህል፣ ጥንታዊ የመሬት ገጽታዎች የሚታይበት ድንቅ የሆነ መልከአምድር ባለቤት ነች” ሲሉም ውጭ ሀገራትም መስክረውላታል። በጀብድ / አድቬንቸር/ መዳረሻ ቦታ የሆነች፤ እንግዳ ተቀባይ ያላቸውን የሚያካፍሉ ህዝቦች ባለቤት» ሲሉ አድናቆታቸውን ሰጥተዋታል። አዎ! ከዚህም በላይ በተለያየ ጊዜ የሚመጡ የውጭ ዜጎች ከዚህ በላይ ሊሉ ይችላሉ። ግን ማስተዋወቅና የተባለውን መንገር ስላልተቻለ ገና አልታወቀችም ይላሉ አቶ ወልደገብርኤል።
የኢትዮጵያ ምድረቀደምትነት የመጣው፣ ከሌላው ዓለም የሚለያትና በቱሪዝም ሀብቷ ተጠቃሚና ተወዳዳሪ የሚያደርጓት ሦስት አበይት ነገሮች ስላሏት እንደሆነ የሚናገሩት አቶ ወልደገብረኤል፤ የመጀመሪያው የመልከአምድሩ አቀማመጥና በውስጡ የሚገኙ ህይወት ያላቸው ነገሮችም ናቸው። ሌላው የረጅም ታሪክ ባለቤት መሆኗ ሲሆን፤ በሦስተኛ ደረጃ የሚነሳው ደግሞ የብሔር ብሔረሰቦች መገኛና ልዩነትን እንደጸጋ ቆጥሮ የሚኖርባት ምድር እንዲሁም የተለያዩ ባህሎች ባለቤት በመሆኗ ነው። ነገር ግን ብዙ መሥራት ይጠበቃልና እያንዳንዱ ዜጋ ለራሱ ሲል አገሩን ያስተዋውቅ መልዕክታቸው ነው። እኛም ይህንን ሁሉ ቀደምትነትን የያዘች አገር ይዘን እንሻገር አልን። ሰላም!
አዲስ ዘመን ሀምሌ 14/2011
ጽጌረዳ ጫንያለው