ኢትዮጵያ በርካታ የማይዳሰሱ ቅርሶች እና የሀገረሰብአዊ ሀብቶች ያሉባት አገር ለመሆኗ ማሳያው ባህላዊ የሙዚቃ መሳሪያዎቻችን መሆናቸው እሙን ነው። እነዚህ መሳሪያዎች እጅ ለእጅ እንዲያያዙ፤ ማህበራዊ ድምፅን በማስተጋባት ለሁሉም እንዲዘምሩ፣ ፍቅርን እንዲሰብኩ፣ በጥላቻ የተሞላ አንጎልን በመፈወስ መንፈሳዊ አርበኛ እንዲሆኑ ያደርጋሉ።
ለሙዚቃ ውበት ሰጪ፣ የግለሰብ ስሜት ቀስቃሽ፣ ከዚያም ልቀው ማህበራዊ ዕውቀት አንሸራሻሪ፣ ግንኙነትን አጠንካሪ እንዲሁም ትምህርታዊ መልዕክቶችን አስተ ላላፊ ናቸው። የአንድን ማህበረሰብ ቋንቋ፣ አመጋገብ፣ ባህል፣ አለባበስ፣ ወግና ልማድ እንዲሁም ማህበራዊ ትስስር ለመረዳትም ሁነኛ መፍትሔ ሰጪ እንደሆኑ ማንም አይክድም። ግለሰቡ ምን ዓይነት ማንነት እንዳለውም በእነርሱ እናውቃለን።
ዘመን አሻጋሪ፣ በዘመናዊ የቅንብር ሥራዎች ውስጥ እንኳን ልዩ ድምፅ አመንጪ የሆኑት እነዚህ መሳሪያዎች፤ የአገሪቷን ባህላዊ እሴቶች በማስተዋወቅም የማይተካ ሚና አላቸው። በሰው ልብ ውስጥ ለመግባትና ለማደርም ቅርብ በመሆናቸው ደግሞ ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦችን አንድ ያደርጋሉ። ኢትዮጵያዊነትን ያሳያሉ።
የብሄረሰቡን አኗኗር፣ የበዓል አከ ባበር፣ የሠርግና የኀዘን እንዲሁም የአለባ በስ ሥርዓት እና አጨፋፈር ስልቶች ማን እንደነሱ ገልጦ የሚያሳይ አለ! እናም ይህንን ሁሉ ታሪክ የያዙት ባህላዊ መሳሪያዎቻችን በየብሔሩ የበዙ ናቸውና መርጦ ማውጋት ግድ ይለናል። ስለዚህ ወደ ደቡብ የአገራችን ክፍል እናምራና ጉዟችንን ከለምለሟ ወላይታ ዞን እናድርግ።
በዚህች ዞን ውስጥ ገብተን የባህላዊ ሙዚቃ መሳሪያቸው እንወቅ። ስለ አንድ አካባቢ ባህላዊ ምንነት በግለሰብ ደረጃ መናገር ከባድ፤ ሃሳቡ ቁንጽል እንዲሁም መሳሳትን ያመጣልና አዋቂዎችን፤ የአ ካባቢው የሙዚቃ አቀንቃኞችን መጠ የቅ ግድ ይለናል። እኛም ስለ ወላይታ ባህላዊ የሙዚቃ መሳሪያ እንዲነግረን በባህላዊ ሙዚቃ ሥራው የሚታወቀውንና የማስታወቂያ ባለሙያ የሆነውን አቶ አክሊሉ አዶሌን ጠየቅን። እንዲህም አለን።
የራሳቸው መገበያያ የነበራቸው ወላይ ታዎች፤ ባህላዊ የሙዚቃ መሳሪያቸውም ከሌላው አካባቢ ለየት ያደርጋቸዋል የሚለው አቶ አክሊሉ፤ የባህላዊ ሙዚቃ ዎቻችን ጎልተው እንዲታዩ የሚሆነው በባህላዊ መሳሪያው ሲታጀቡ እንደሆነ ያነሳል። ባህላዊ መሳሪያዎቹ ልዩ ስበት አላቸው ይላል። ለዚህም አንድ ማሳያ አንስቶ ይዘረዝራል።
ኢትዮጵያውያን ለባህላዊ ዘፈኖች ከሚሰጡት ቦታ ያልተናነሰ ከተለያዩ አገራት ወደ ኢትዮጵያ የሚመጡ የውጭ ዜጎች በአገሪቱ የሙዚቃ ምቶች ውስጥ ራሳቸውን አስገብተው «እስክስታ፣ የተለያዩ ሀገረኛ ጭፈራዎች» ለመልመድ ሲሞክሩና ባህላዊ ጭፈራውን ሲያስነኩትም የምናየው ከልባቸው በመግባቱ የተነሳ መሆኑ በቂ ማስረጃ ነው ይላል።
ኢትዮጵያኑም ቢሆኑ ከዘመናዊ መሳሪያ ይልቅ ባህላዊው መሳሪያ ጨዋታ ላይ ይበልጥ ይመሰጣሉ። በወላይታዎች ዘንድ የባህል ሙዚቃ መሳሪያዎችም የሚሰጠው ዋጋ በቀላሉ የሚገለጽ አይደለም። ባህላዊ የሙዚቃ መሳሪያው ሲወጣ የማህበረሰቡ አለባበስ፣ ደስታና ኀዘንም አብሮ ሊወጣ ይችላል። ከዚያ ድጋፋቸውንና ነቀፌታቸውን፤ ማግኘትና ማጣታቸውን ሲገልጡበት ይውላሉ።
በዚህ አካባቢ ያሉ ባህላዊ የሙዚቃ መሳሪያዎች ብዙ ጊዜ በተግባር ላይ ስለሚውሉ ሙዚቃ በቋንቋ፣ በቀለምና በፖለቲካ አመለካከት ድንበር የታጠረውን የዓለምን ህዝብ አንድ የማድረግ ኃይል ያለው መሆኑን ያሳያሉ። ስሜታቸው ተኮርኩሮ ሲዘሉ ስንመለከት ደግሞ መሳሪያዎቹ ምን ያህል ኃያል የሆነ ድምፅ እንዳላቸው እናስተውላለን። ለመሆኑ እነዚህ ልብ የሚሰርቁ ባህላዊ የሙዚቃ መሳሪያዎች ምን ምን ይባላሉ ካላችሁ አቶ አክሊሉ የነገረንን እናንሳ።
የመጀመሪያው በዓለም ረጅሙ የትንፋሽ መሳሪያ ሲሆን፤ ወላይታዎች «ዲንኪያ» እያሉ ይጠሩታል። በጫፉ እጥፍ ያለ ቀንድ መሳይ ነገር ይቀመጥለትና ከታች እስከ ላይ ያለው ቀርከሃ ክፍት ይሆናል። አጠቃላይ ርዝመቱ ደግሞ ከአራት እስከ አምስት ሜትር እንደሚደርስ ድምፃዊው አክሊሉ ነግሮናል። ዲንኪያ የሚያወጣው ድምፅ የዘመንኛውን ቤዝ ጊታር ዓይነት ሲሆን፤ ድምፁ የሚፈጠረው ደግሞ ቀንዱ ላይ ትንፋሻችን ሲደርስ ነው።
አቶ አክሊሉ እንደሚናገረው፤ ይህ የሙዚቃ መሳሪያ አራት ዓይነት ዜማ አለው። ዜማዎቹም ላሚያ፣ ሄሲያ፣ ማራ፣ ኦይቲያ ይባላሉ። እንደ ቅኝት የሚወሰዱ ሳይሆን ከባቲ፣ አንቺሆዬ፣ አምባሰልና …እንደምንለው የራሳቸው የሆነ ዜማ ያለቸው ናቸው። የወላይታ ባህላዊ የሙ ዚቃ መሳሪያዎች በብዛት የሚሠሩት ከቀርከሃ እንደሆነ የሚናገረው የሙዚቃ ባለሙያው፤ ስለ «ጫቻ ዛይያም» ጥቂት ብሎናል። ጫቻ ዛይያ አራት ዓይነት ድምፀቶች ያሉት የሙዚቃ መሳሪያ ነው። ድምፀቶቹም ዮዳ፣ ኮይሻቷ፣ ቦጊያ፣ ሄቼቺያ እየተባሉ ይጠራሉ። ስለዚህም ተጫዋቾቹ እነዚህን ድምፆች ተከትሎ መጫወት በባህሉ ዘንድ ግዴታ አለበት። እነዚህም ዞሃ፣ ማራ፣ ጊድዎ እየተባሉ የሚጠሩት ናቸው። ይህ ባህላዊ መሳሪያ እንደሁለቱ ባህላዊ ሙዚቃዎች ሁሉ የሚሠራው ከቀርከሃ ነው። ተጫዋቹ የሚጫወተው ፊት ለፊት በመንፋት ሲሆን ድምፁ ከሳክስፎን ጋር እንደሚመሳሰልም አጫውቶናል።
ሌላው የሙዚቃ መሳሪያ «ናጋሪታ» እያሉ የሚጠሩት ሲሆን፤ ነጋሪት እንደማለት ነው። ይሄ መሳሪያ እንደሚታወቀው በአንድ በኩል ሰፋ ብሎ በሌላ በኩል በጣም ጠባብ ተደርጎ ክፍት እንጨት ላይ በቆዳ የተወጠረ ነው። ሆኖን ግን ከከበሮ ቅርጽ ለየት ያለና የሚመታበት ቦታ በጣም ሰፊ ነው። ስለዚህ ነጋሪቱን በመጎሰም ወላይታዎች ጨዋታን ያደምቃሉ። ይህ መሳሪያ በቤተ እምነቶች ውስጥ በስፋት ይታያል። የሚጎሰመውም ለትልቅ ነገር ነው። ወላይታዎች ግን ከመሳሪያቸው ጋር አድርገው ሁልጊዜ ይጫወቱበታል። ውስጥን የሚያነቃቃ ድምፅ በማውጣት ህሊናን ገዝቶ ከማናስበው አዓለም ውስጥ እንዲከተን ያደርጋል።
በባህላዊ ሙዚቃ መሳሪያነት ከሚጠ ቀሱት ውስጥ ሌላው የምናነሳው ደግሞ «ካምባ» የሚለውን ነው። ማንኛውም አካባቢ እንደምናገኘው ዓይነት መሳሪያ ነው። የሚሠራውም ከእንጨትና ቆዳ ነው። ከሁለቱም በኩል በቆዳ ተወጥሮ እኩል ቅርጽ ያለው ከበሮ ይመስላል። ድምፁ እንደከበሮ ድም ድም የሚል ይሆናል። ከዚያማ ከበሮውን ምቺው አርጊው ደንቧ ደንቧ እያሉ እንደወለደች ላም እንቧ እያሉ መጨፈር ነዋ።
ከራቤዬ በመባል የሚጠራ ትንሽ ከበሮም እንዳላቸው የሚናገረው ሙዚቀኛው፤ ይህ ባህላዊ መሳሪያ ቁጭ ተደርጎ የሚመታ ሲሆን፤ የሚሠራው ከሸክላ ነው። ስሜትን የመቀስቀስና ወደ ደስታ የመውሰድ ኃይሉ ከፍተኛ ነው። ምክንያቱም ድምፁ እንደትንሽነቱ ሳይሆን ሳይፈለግ ስሜትን በመቀስቀስ ወደ እንቅስቃሴ ወይም ጭፈራ ውስጥ የሚከት ነው ።
«ኡልዱዱዋ» የሚባለው የሙዚቃ መሳሪያ ደግሞ ከቀንድ የሚሠራ ነው። ግን ለመንፋት ያክል አነስ ያለች አንድ አንጓ ቀርከሃ ይደረግበታል። ሆኖም የድምፁ ባለቤት ግን ቀንዱ እንደሆነ አጫውቶናል። ብዙ ጊዜ የማናየውን ሱጋፎን ድምፅ ያወጣል። ከመለከት ጋርም ድምፁ የሚቀ ራረብበት ሁኔታ እንዳለም ይናገራል የሙዚቃ ባለሙያው አክሊሉ።
ሌላው «ዲታ» እየተባለ የሚጠራው ባህላዊ የሙዚቃ መሳሪያ ሲሆን፤ የክራር ዓይነት ቅርጽና ድምፅ ያለው ነው። እንቢልታም እንዲሁ ልዩ መሳሪያቸው ነው። የራሱ የሆኑ ድምጸቶች ያሉት ሲሆን፤ ሻንቂቷ፣ ባርባዷ፣ ባርኩንዳ፣ ጭርታ፣ አዳርሿና ሶሊንጢያ የሚባሉ መሆናቸውን ይናገራል። አንድ መሳሪያ ተጫዋች እነ ዚህን ስድስት ነገሮች ካላወቀ ሙዚቃው ሙሉ ለሙሉ ይበላሻል። ስለዚህ የባህላዊ ሙዚቃዎቹ አንዱ ከአንዱ የሚነጣጠል ባህሪ ስለሌላቸው በጥንቃቄ መጫወት የሚችል ሰውን ይፈልጋሉ ብሎናል። በተለይም ባህላዊ ክብረ በዓላት ላይ አንዱ ከአንዱ መናበብ ግድ ይሆናል።
ወላይታዎች አዴ ካራቢያ፣ ማልካታ፣ ሱሱሊያ፣ ማዘንቂያ እየተባሉ የሚጠሩም ባህላዊ የሙዚቃ መሳሪያዎች ባለቤቶች ናቸው። ሁሉም መሳሪያዎቻቸውም በአን ድነት ባህላዊ ክዋኔዎች ላይም ይቀርባሉ። በድምፃቸውም ህሊናን ይገዛሉ፤ የሚደሰተውን በማስደሰት፤ ያዘነውን ደግሞ በማጽናናት እንዲሁም ኀዘኑን ከልብ እንዲገልጽ በማድረግ አገልግሎታቸውን ይወጣሉ።
በህይወት አጋጣሚ ፈልግንም ይሁን ሳንፈልግ ሙዚቃ የምናዳምጥበት ሁኔታ አለ። እናም በትክክለኛው ጊዜ ሲደመጥ ደግሞ የሚሰጠው ስሜት የላቀ ነውና እነዚህም መሳሪያዎች ያንን በማድረግ በኩል ሁነኛ መድሃኒት ናቸው።
ማህበራዊ ህፀፅ ሲኖር፣ አለመረጋ ጋትና የፖለቲካ ልዩነት ሲስፋፋ የመንፈስ መረጋጋትን ይፈጥራሉ። አንድነትን እንድናቀነቅን፤ ሰብዓዊና ርህራሄን እን ድንሰብክ ያበረታታሉ። እናም ይህንን ሁሉ ተግባራቸውን እንዲወጡ እናስተዋ ውቃቸው፤ እንጠቀምባቸውም እያልን ለዛሬ በዚህ ቋጨን። ሰላም!
አዲስ ዘመን ሰኔ 16/2011
ጽጌረዳ ጫንያለው