እንደመግቢያ ቢሆነኝ ደግሞም ገላጭ ሆኖ ሳላገኘሁት የጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አህመድ ንግግራቸውን ተዋስኩ። እንዲህ አሉ፤ «ዘመን የሰው ልጆች የታሪክ፣ የማንነት፣የባሕል፣የሥነ ልቡና እና የህልውና መከተብያ፣መሳያ፣መበየኛ፣መንደፍያ እና ማቆያ ትንግርታዊ ሰሌዳ ነው። ይህንን ድንቅ ስራ በመቁጠር፣ በመቀመር፣በማስላት እና በተፈጥሮ ዑደት ውስጥ የሚዘወርበትን ሥርዓት በመዘርጋት የሚጠቀምበት ማኅበረሰብ ደግሞ እርሱ ከዘመን ጋር የማይሄድ ከዘመንም ጋር የማይመጣ በዘመን ገላ ላይ ትናንት በአባቶቹ፤ዛሬ በራሱ እና ነገም በልጆቹ ህያው የሚሆን ታላቅ ሕዝብ ነው። የሲዳማ ሕዝብ ይህን ታላቅ የሥልጣኔ አበርክቶ አጥሮ፣ጠብቆ አቆይቶልናል።»
«ፊቼ ጫምባላላ»በመባል የሚታወቀው የሲዳማዎች ቀመር በከዋክብት ዑደት ላይ የተመሠረተ ነው። ብርሃናቱ ፀሐይና ጨረቃ ከዋክብትም የተፈጠሩት ስለ አራት ነገሮች መሆኑንም ኦሪቱ ያብራራል፤ ለምልክቶችና ለዘመናት፣ ለእለታትና ለዓመታት በማለት። ትውፊታዊውና ኦሪታዊው መጽሐፍ ስለ ብርሃናት ተፈጥሮ ይገልጻል። ቀንና ሌሊትን ይለዩ ዘንድ በሰማያት ብርሃናት ተደረጉ ይለናል።
ታላቁ ብርሃን በቀን እንዲሠለጥን፣ ታናሹ ብርሃን በማታ እንዲገዛ ከዋክብትንም ፈጠረ ሲል ያክልበታል። ምልክቶች ሲል በዓሎቹንና ጾሞችን፤ ዘመናትን ሲል አራቱን ወቅቶች ክረምትና በጋ፣ መፀውና ፀደይን፤ ዕለታትና ዓመታት ሲልም እንደየ ትውፊቱ ያሉትን አቆጣጠሮች ማመልከቱ እንደሆነ የዘርፉ ምሁራን እና ጸሐፍቶች ያስረዳሉ።
ኢትዮጵያ ብዙ ባህል ያላት አገር እንደመሆኗ ከዘመን ቆጠራ አኳያ በየአካባቢው ባሉ ነገሮች፣ ብሔረሰቦች የየራሳቸው መገለጫ የሆኑ ባህላዊ የዘመን አቆጣጠር አላቸው። ከነዚህም መካከል የተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ድርጅት (ዩኔስኮ) በሰው ልጅ ወካይ ቅርስነት የመዘገበው የሲዳማ የዘመን አቆጣጠር ይገኝበታል። እኛም ስለበዓሉ ከመነሻው አስከ አሁን ድረስ ያለውን ጠቅላላ መረጃ የሲዳማ ዞን ህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ገነነ አበራ የነገሩን ይሄው ለንባብ ብለናል።
የፊቼ በዓል በአፈ ታሪክ እንደሚወሳው መጠሪያውን ያገኘው «ፊቾ» ከምትባል የሲዳማ ሴት መሆኑን አቶ ገነነ ነግረውናል። ታሪኩ ደግሞ እንዲህ ነው፤ ፊቾ ዕድሜዋ ለአቅመ ሔዋን ሲደርስ በሲዳማ ብሔር ባህልና ሥርዓት መሠረት ተዳረች። ይህች ሴት በየዓመቱ ለወላጆቿ፣ ወንድሞቿ፣ ለዘመድ አዝማድና ጎረቤት «ቡርሰሜ» (ከእንሰት ላይ የሚፋቅ ቆጮ በእሳት ላይ ተነኩሮ እና ቅቤ በብዛት ተጨምሮበት የሚዘጋጅ ባሕላዊ ምግብ) እና እርጎ በመያዝ በየዓመቱ በሲዳማ ብሔር የዘመን መለወጫ በዓል በሚውልበት ዕለት በቋሚነት ትጠይቃቸው ነበር። በዓሉ የሚውለው በተመሳሳይ «ቃዋዶ» (በሲዳማ ብሔር የቀን አቆጣጠር የሳምንቱ የመጀመርያ ቀን) ሲሆን በአፈ ታሪኩ መሠረት ፊቾ ያመጣችውንም ምግብ በዚሁ ዕለት ምሽት ላይ ዘመድ አዝማድ፣ የአካባቢ ነዋሪ፣ ጎረቤትና ቤተሰብ ተሰባስበው ይመገቡት ነበር።
አባቷና ታዳሚዎች ዘወትር የፊቾን ደግነትና ያመጣችውን ምግብ በማድነቅ ይመርቋታል። ፊቾ ይህንን በተደጋጋሚ ስትፈጽም ቆይታ ከዚህ ዓለም በሞት ስትለይ የአካባቢው ነዋሪዎች ፊቾ በመሞቷ ጥልቅ ሐዘን የተሰማቸው ከመሆኑም በላይ የእርሷ ድግስ ታዳሚ የነበሩ ሰዎች ይህችን ሩህሩህ ደስታ ፈጣሪ ሴት በዘላቂነት ለማስታወስ ቀደም ሲል እርሷ ምግብ ይዛ የምትመጣበትንና ግብዣው የሚካሄድበትን የሲዳማ ብሔር የዘመን መለወጫ ቀን በስሟ ፊቼ ብለው ሰየሙት። የፊቼ በዓል ሁሌም በቃዋዶ ቀን የሚውልበት ምክንያት ቀኑ በብሔሩ የሳምንቱ የመጀመርያውና ታላቅ ቀን ተደርጎ የሚቆጠር በመሆኑ ነው።
አቶ ገነነ ቀጥለው ይናገራሉ፤ በበዓሉ ሁሉም ሰው የሚያርፍበት፤ ከብቱም ሳይቀር የተጣላ ሁሉ በ«ፍቼ ጨምባላላ» ማለትም አዲስ ዓመት ሳይገባ ይቅርታ መጠያየቅ ግዴታው ነው። የተፋቱ ባል እና ሚስት ቢኖሩ እንኳን በዋዜማው ቀን ተጣልታ የወጣችበት ቤት ማለትም የቀድሞ ባሏ ጋር ሄዳ እርቅ ማድረግ ይገባታል። «ምክንያቱም…» ይላሉ አቶ ገነነ «ምክንያቱም በዓሉ የእርቅ ስለሆነ ነው።»
የዘንድሮው ፊቼ ጨምባላላ በዓል ግንቦት 22 ቀን እና 23 ቀን 2011 ዓ.ም በሐዋሳ ከተማና አካባቢ ተከብሯል። እንደ ሕዝብ ግንኙነቱ አቶ ገነነ ገለጻ፤ ዋዜማው «ፊቼ» እና መባቻው «ጫምባላላ» እንዲከበር ያደረጉት የሥነ ከዋክብት ምልከታ ያከናወኑት የከዋክብት ቀማሪዎቹ «አያንቶዎች» ናቸው ብለዋል።
ከደቡብ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ የተገኘ መረጃ እንደሚያመለክተው በዓሉ በሲዳማ ዞን ወረዳዎች ለሁለት ሳምንት በተለያዩ ዝግጀቶች ይከበራል። የፊቼ ጫምባላላ በዓልን በዓለም ቅርስነት ለማስመዝገብ ጥናቱን የሠሩት ባለሙያው አቶ ገዛኸኝ ግርማ እንደገለጹት፤ የፊቼ ጫምባላላ በዓል ከትውልድ ወደ ትውልድ ሲተላለፍ የመጣ በሲዳማ ብሔር አባላት ዘንድ በየዓመቱ በድምቀት የሚከበር ነው።
በዓሉ በቤተሰብና በጎረቤት ደረጃ ተሰባስቦ በማክበር የሚጀምርና ከዚያም እየሰፋ በመሄድ በባህላዊ አደባባይ (ጉዱማሌ) በጋራ የማክበር ሒደትን ያጠቃልላል። እንደ አቶ ገዛኸኝ ትንተና፣ ፊቼ ከዘመን መለወጫ በዓልነት ፋይዳው ባሻገር በርካታ ባህላዊና ማኀበራዊ ፋይዳዎች አሉት፤ሀገር በቀል የሆነ የዘመን አቆጣጠር ዕውቀትን አካትቶ ከመያዙ በሻገር የሲዳማ ብሔር አንኳር የሆኑ ባህላዊ ገጽታዎች የሚንፀባረቁበት ግዙፍነት የሌለው ወይም የማይዳሰስ (ኢንታንጀብል) ቅርስ ነው።
የፊቼ በዓል ሰላም፣ መከባባር፣ መቻቻል እንዲሰፍን፣ ዕርቅ እንዲወርድ እንዲሁም ልማት እንዲፋጠንና ሰብዓዊ መብቶች እንዲከበሩ የጎሳ መሪዎች እና የበቁ አረጋውያን ለኅብረተሰቡ በሰፊው ትምህርት የሚሰጡበት ወቅት ነው።
አቶ ገነነ በበዓሉ የሚከወኑ ተግባራትን እንደዘረዘሩት የሲዳማ ብሔር ዘመን መለወጫ በዓል የሆነው ፊቼ ለሁለት ሳምንታት ያህል በድምቀት የሚከበር ሲሆን አከባበሩም ቅደም ተከተላዊ ሥርዓትና ሒደት ያለው ነው። ከእነዚህ ማኅበራዊ ክንዋኔዎች መካከል የመጀመርያው ምልከታ (ላኦ) ነው። የፊቼ በዓል ሁሌም በብሔሩ የሳምንቱ የመጀመርያው ቀን ማለትም በቃዋዶ ቢውልም ቀኑ በየዓመቱ በተመሳሳይ ቀን ስለማይውል መቼ እንደሚውል ተለይቶ የሚታወቀው በባህላዊ ቀን ቆጠራ ስሌትና የሥነ ክዋክብት ምልከታ እንደሆነ ጠቅሰዋል።
የሥነ ክዋክብት ምልከታውን የሚያከናውኑት አያንቶ የተሰኙ የሥነ ክዋክብት ጠበብቶች ናቸው። አያንቶዎች ቡሳ የተሰኙ ኅብረ ክዋክብት ከጨረቃ አቀማመጥ ጋር ያላቸውን ግንኙነት በማገናዘብ የክዋክብቱ ከጨረቃ የመቅደምና ወደ ኋላ የመቅረት ሁኔታ በትኩረት በመከታተል በተለይ ከክዋክብቱ መካከል አውራ የሆነችው ኮከብ ከጨረቃ መቅደሟን ሲያረጋግጡ፤ ፊቼ በቀጣይ ቀናት ውስጥ ባለው የቃዋዶ ዕለት እንደሚውል እንደሚወስኑ አቶ ገነነ ይናገራሉ።
ከዚያም የሥነ ከዋክብት ምልከታውን የሚያከናውኑት አያንቶዎች የፊቼ በዓል የሚውልበትን ቀን ለጎሳ መሪዎች (ገሮ) ያሳውቃሉ። አያንቶዎች ባቀረቡት ሐሳብ ላይ ተመሥርተው የጎሳ መሪዎች የበቁ አረጋውያን (ከጪሜሳዎች ) ጋር የአዛውንቶች ስብሰባ (ሶንጎ ) በማድረግ በጉዳዩ ላይ ከተወያዩ በኋላ ቀኑ በአዋጅ ለኅብረተሰቡ እንዲገለጽ ከስምምነት ይደርሳሉ።
የጎሳ መሪዎችም በየአካባቢያቸው በሚገኙ የገበያ ሥፍራዎች የበግ ቆዳ ረዥም ዘንግ ላይ ሰቅለው በመያዝ ለኅብረተሰቡ የፊቼ በዓል የሚውልበትን ቀን ያውጃሉ ወይም «ላላዋ» ያደርጋሉ። ከላላዋ በኋላ የመጀመርያው ባህላዊ ጭፈራ (ሳፎቴ ቄጣላ) ይቀጥላል። ዩኔስኮ ፊቼ ጨምባላላን በሰው ልጆች የማይዳሰሱ ወካይ ቅርሶች ውስጥ የተመዘገበው በ2008 ዓ.ም. ኅዳር ወር ላይ መሆኑ ይታወሳል። እኛም ዘመን መለወጫው የሰላም፣ የይቅርታ፣ የፍቅር እና የአንድነት እንዲሆን እንመኛለን። አይዴ ጨምባላላ !
አዲስ ዘመን ግንቦት 25/2011
አብርሃም ተወልደ