በአንድ መድረክ ላይ አንድ የዕድሜ ባለጸጋ ንግግር እንዲያደርጉ ተጋበዙ። በአዳራሹ የሚበዙት ወጣቶች ናቸው። ወጣቶች ናቸው ማለት እንግዲህ ምን ማለት እንደሆነ ግልጽ ነው (ኧረ ይሄ ወጣት አሁንስ ወቀሳ በዛበት)።
የተጋበዙት አዛውንት ንግግራቸው በጣም ዘለግ አለ። በእያንዳንዱ ወጣት ልብ ውስጥ ‹‹አይጨርሱም እንዴ!›› የሚል ምኞት ይነበባል። ስልኩን ይነካካል፣ ያፋሽካል፣ ከጎን ያወራል፣ እየወጣ ይሄዳል፤ አዛውንቱ የቀደም ትዝታቸውን እያወሩ ይህን ትውልድም በነገር ወረፍ ያደርጋሉ።
አዛውንቱ ማሳረጊያ የሚመስል ዓረፍተ ነገር ሲናገሩ አዳራሹ በጭብጨባ ይናጣል፤ የሚያጨበጭቡት በተናገሩት ነገር ተደስተው ሳይሆን ‹‹እፎይ ሊጨርሱ ነው›› በሚል ደስታ ነው፤ እግረ መንገድም ይበቃዎታል የሚል መልዕክት መሆኑ ነው። አዛውንቱ የሞቀው ጭብጨባ ቀዝቀዝ ሲል ጠብቀው እንደገና አዲስ ታሪክ ይጀምራሉ፤ ታዳሚውም አዲስ ተስፋ መቁረጥ ይጀምራል። በጭብጨባ በፉጨት አያስቆማቸው ነገር አዛውንት ናቸው፤ በዚህ በኩል ታዳሚው ይመሰገናል።
አሁን ከአዳራሹ እንውጣ ይሄ ነገር ለምን ተፈጠረ? ካልን በሁለት ምክንያት ይሆናል። አንድ፤ በታዳሚው፤ ሁለት ራሳቸው በአዛውንቱ። ታዳሚው ለምን እንዲህ አይነት እውቀት ሰለቸው? አዛውንቱስ የዕድሜ ዘመን ገጠመኛቸው ሁሉ በአንድ መድረክ ያልቅ ይመስል ለምን ነገር ያስረዝማሉ?
መድረክ ላይ አንድ ችግር አለ፤ ጥልቅና ትንታኔ ያላቸው ነገሮች አይወደዱም። የተለመደው የሚያስቅ ነገር ነው። ከዚያ አለፍ ሲልም መንግስትን ወይም የሆነን አካል የሚሳደብና የሚያስጨበጭብ ነገር ነው።
ለነገሩ አሁን አሁን በመድረክ ብቻ ሳይሆን በዋናዎቹ የመገናኛ ብዙኃንም የተለመደው ይሄው ሆኗል። እንዲያውም እኮ መድረክ ሲዘጋጅ ታዳሚን ለማብዛት የሚጠቀሱት ሰዎች አስቂኝ ንግግር ያላቸውን ነው። ጥልቅ ትንታኔ ያላቸው ነገሮች እየጠላን ነው። እንዲያውም አንድ ሌላ ገጠመኝ ትዝ አለኝ። ይሄንን እንኳን ስም እና ቦታ ጠቅሼ ልናገር!
የጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ፍትሕ መጽሔት ወደ ገበያ ልትገባ በብሔራዊ ቴአትር የተዘጋጀ የምርቃት (ማስተዋወቂያ እንበለው) የተዘጋጀ መድረክ ነበር። በአዳራሹ መቆሚያ መቀመጫ እስከሚጠፋ ሰው ሞልቷል፤ አብዛኛው ወጣት ነው። ዝግጅቱን አስመልክቱ አዝናኝም አስተማሪም አጫጭር ነገሮች ቀረቡ።
ፍትሕ መጽሔት ከዚህ በፊት ፍትህ ጋዜጣ ነበረች። እናም ፍትሕ ጋዜጣን የሚዳስስ ጽሑፍ ሊያቀርብ ብርሃኑ ደቦጭ ተጋበዘ። ገና ሲጀምረው የፍትሕን ብቻ ሳይሆን የሌሎችንም ጋዜጦች እያጣቀሰ ጥልቅ ትንታኔ ማቅረብ ጀመረ። በትንታኔው ተመስጬ በጉጉት እያዳመጥኩ ሳለሁ ግን ሊቀጥል አልቻለም። የ‹‹ይበቃሃል›› መልዕክት ያለው ጭብጨባ አስተጋባ። ብርሃኑ ወረቀቱን ጠቅልሎ ወረደ። በግሌ በጣም አፈርኩ፤ በጣም ተናደድኩ! ይህኔ እንቶፈንቶ አሉቧልታና ቀልድ ቢያወራ ኖሮ ጭብጨባው የአድናቆት ይሆን ነበር።
አንዳንድ ሰዎች ለምን ወደ መድረክ እንደሚሄዱ ሁሉ አይገባኝም። ጉዳዩ ስለምን እንደሆነ በግልጽ ተነግሮ እያወቁት ይሄዳሉ። አዳራሹ ውስጥ ሆነው ግን አይከታተሉትም፤ እንዲያውም ሌላም ሰው እንዳይከታተል ነው የሚረብሹት።
ወደ ዕድሜ ባለጸጎች እንመለስ። ከእነዚህ አባቶች የምናገኘው እውቀት የመጀመሪያ ደረጃ መረጃ ነው፤ ያ ማለት ተናጋሪው የአይን እማኝ ናቸው ማለት ነው። ያዩትን የኖሩትን ነው የሚነግሩን፤ ዳሩ ግን እንዲህ አይነቶቹን አንሰማም፤ ቆይ ግን እውነት አንወድም ማለት ነው?
በእርጅና ዕድሜ ላይ ያሉ ሰዎችም በባህሪያቸው ነገር ያስረዝማሉ፤ ምክንያቱ ግን ግልጽ ነው። የሚናገሩበት ዕድል ስለሌላቸው ነው። አንተ ወጣቱ በየገባህበትና በየሄድክበት ታወራዋለህ (መቼም መዞር ነው ሥራህ)፤ አዛውንቱ ግን ብዙ ቦታ አይሄዱም፤ ሲሄዱ ኖረው አሁን ቁጭ ብለው የሚናገሩበት ነበር። (ሰሚ ቢገኝ)
እንዲያውም ልብ ብለን ከሆነ መድረክ ላይ ሲወጡ ብቻ አይደለም ነገር የሚያስረዝሙት። ታክሲ ውስጥም ይሁን የትም ቦታ ባገኛችሁት አጋጣሚ ልብ ብላችኋል? የሆነ ነገር ሲያዩ ወይም ሲሰሙ ዝም አይሉም፤ ይናገራሉ። ባያዩና ባይሰሙ ራሱ ዝም ብለው ይናገራሉ። ይመክራሉ፣ ይቆጣሉ፣ ይገስጻሉ።
መድረክ ላይ ሲወጡ ነገር የሚያስረዝሙበት ምክንያት ይሄው ነው፤ የሚናገሩበት ዕድል ስላልነበራቸው ውስጣቸው ያለውን ለመናገር። በነገራችን ላይ አዛውንቶች መድረክ ብቻ አይደለም ያሉት፤ መንደር ውስጥ ራሱ የሚያወሩበት ዕድል የለም። ምናልባት የእነርሱ ዕድሜ እኩያ የሆኑ ካላገኙ ወጣቶች ከእነርሱ ጋር አያወሩም። እነርሱ ደግሞ መምከርና መገሰጽ የሚፈልጉት ወጣቱን ነበር እንጂ አዛውንት ከአዛውንትማ ታሪካቸውና ገጠመኛቸው ይመሳሰላል።
እነርሱም እንዲህ የሚያወሩበትና የሚሰማቸው ሲያጡ ውስጣቸው የተጠራቀመውን ብሶት ሁሉ መናገር ይፈልጋሉ።
ምናልባት ግን መድረክ ላይ እንደዚያ በረጅሙ ካልተናገሩ ብሎ መፍረድም ይከብዳል። ምክንያቱም መድረክ ማለት የተወሰነ ሰዓት ያለበት ነው፤ ሌሎች ፕሮግራሞችም የተያዙበት ነው። ይህንን ዓውድ ደግሞ እነርሱ አይረዱም።
ከአባቶች እውቀት እንጠቀም ከተባለ ራሱን የቻለ መድረክ ማዘጋጀት፣ ያ እንኳን ባይቻል ቁጭ ብለን ብናዳምጣቸው፣ የመገናኛ ብዙኃን ዕድል ብንሰጣቸው። ደግሞ እኮ ‹‹ተንቀሳቃሽ ቤተ መጽሐፍ›› እያልን እንጠራቸዋለን፤ ግን አልተጠቀምንባቸውም። የአባቶች እውቀት አይባክን!
አዲስ ዘመን ቅዳሜ ግንቦት 3/2011
በዋለልኝ አየለ