አንድ ሀገር ሁለንተናዊ እድገትን በማምጣት የሕዝቦቿን ኑሮ ማሳደግ የምትችለው በሚኖራት የሰው ኃይል አቅም ነው፡፡ ስኬትና ኪሳራን የምታወራርደው ባለመችው፣ እልምታም ባበቃችው ትውልድ ነው። ትምህርት ደግሞ ይሕን ትውልድ እውን ለማድረግና ለአንድ አገር እድገት መሰረት፣ ዋልታና ማገር ነው።
ስለ ትምህርት ሲነሳ ብዙዎች እንደ ማሳያ የሚጠቀሙበት የደቡብ አፍሪካ የነፃነት ምልክት ኔልሰን ማንዴላ ‹‹ትምህርት ዓለምን ለመለወጥ ልትጠቀምበት የምትችለው በጣም ኃይለኛ መሣሪያ ነው ” የሚለው ንግግራቸው ሁሌም ተጠቃሽ ነው፡፡
አገር በትምህርት ውስጥ የሚያልፉ ዜጎቿ በጨመሩ ቁጥር፣ ምክንያታዊ ትውልድን እያፈራች እድገትና ልማቷን የማፋጠን እድሏ እየጨመረ ይሄዳል። እነዚህ ዜጎቿ ችግሯን የሚሸሹ፣ ሲከፋም ችግር የሚፈጥሩባት ሳይሆን በቅርብ ሆነው መፍትሄ የሚሰጡና የችግርን መፍቻ ቁልፍ የታጠቁ ናቸው። ይህ ሳይሆን ሲቀር ግን ዜጎች ለአገር ሸክም ይሆናሉ። የተሠራን የሚያጠፋና የሚያወድም ትውልድም ይፈጠራል። ለዚህ ታዲያ ቁልፍ መሠረቱ የትምህርት ሥርዓት ነው።
በዓለም አቀፍ ደረጃም በርካታ አገራት ለትምህርት ዘርፍ በሠጡት ትኩረት የድካማቸውን ፍሬ መልቀም ችለዋል፡፡ ለትምህርት ዘርፍ ትኩረት በመስጠት ረገድ በተለይ ጥራትን ማስጠበቅና የተደራሽነቱን ማስፋትም የአገርን እድገት አንድ እርምጃ ወደፊት ለማስቀጠል እጅግ አስፈላጊ መሆኑ አያጠያይቅም።
ኢትዮጵያም ከትላንት እስዛሬ የትምህርት ፋይዳ የገባት ‹‹መማር ያስከብራል፤ አገርን ያኮራል›› የሚለው ብሂል፤ ትምህርት ለግል አእምሮአዊ እድገት ብቻ ሳይሆን ለአገርም ምን ያህል ፋይዳ እንዳለው የሚገለፅባት ከፍ ሲል የሚዘመርባት አገር ናት፡፡
በኢትዮጵያ በቀደሙት ዓመታትም በመንግሥት ትልቅ ትኩረት ከሚሰጣቸው ዘርፎች መካከል ትምህርት በግንባር ቀደምነት ይጠቀሳል፡፡ በሁሉም ደረጃ የትምህርት ተደራሽነቱን ላይ በጎና ሰፊ ስራ ተሰርቷል። ይሑንናን ብዛት ሳይሆን ጥራት ሲጠየቅ መልሱ ቀላል አልነበረም፡፡
የትምህርት ተደራሽነትን ለማስፋት በሚል በሚከናወኑ ተግባራት የትምህርት አቅርቦቱ ሊያድግ ይችላል፡፡ ይሁን እንጂ ከዚህ ጎን ለጎን የጥራቱን ጉዳይ ታሳቢ ያደረገ መንገድ ካልተከተሉ ዞሮ ዞሮ አተርፍ ባይ አጉዳይ ሆኖ መቅረት የማይቀር ነው፡፡
ኢትዮጵያ የትምህርት ስርዓቱ ብዛትን ተከትሎ የጥራትን መንገድ በመሳቱ፤ በብርቱ ሲታመም እና ሲሰቃይ ቆይቷል፡፡ በየትምህርት ስርዓት ላይ ለሚታየው ስብራት በርካታ ምክንያቶች ይጠቀሳሉ፡፡ በቀደሙት ዓመታት ለትምህርት ስርአቱ ሞት በተለይም ለጥራቱ ዝቅጠት ግንባር ቀደም መንስኤዎች ተብለው ከተለዩት ምክንያቶች አንዱም የፈተና ሂደት ከዝግጅት እስከ ስርጭት ደካማ መሆን በቀዳሚነት ይነሳል፡፡
እንደሚታወቀው ትምህርት የነገ የአገር ተስፋ የሆኑ ተማሪዎችን በእውቀት፣ አመለካከትና ሥነምግባር ቀርጾ የማውጣት ቁልፍ ሲሆን ፈተና ደግሞ የዕውቀት መለኪያ ነው። ፈተና ተማሪዎች በትምህርት ወቅት በገበዩአቸው እውቀቶች ልክ የሚፈተሹበትና የሚለኩበት ሚዛን ነው።
በኢትዮጵያ ነባራዊ ሁኔታ በፈተና አሰጣጥ ሂደት በሚስተዋሉ ድክመቶች ተማሪዎች በተደራጀ ሁኔታ ኩረጃ ላይ ሲተጉ ይስተዋላል። ኩረጃ በዕለት ተዕለት የትምህርት ስርዓት ወቅት የሚያጋጥም ቢሆንም በተለይ በብሔራዊ ፈተናዎች ላይ የሚከወንበት መንገድ ዘመን ባመጣው ቴክኖሎጂ የተደፈገ መሆኑ ኪሳራውን ከፍ አድርጎታል።
ኩረጃው በተማሪዎች ብቻ ሳይሆን በፈተና ጣቢያ አስተባባሪዎች፣ በፈታኝ መምህራን፣ በመስተዳድር ኃላፊዎች፣ በትምህርት ቤቶች፣ በተለይም ስማቸውን በመሸጥ ጥሩ ገቢ ለማግኘት በሚጥሩ ትምህርት ቤቶችም ጭምር መቀነባበሩም የኢትዮጵያን የትምህርት ስርአት ተአማኒነት ጥያቄ ውስጥ እንዲገባ አድርጎት ቆይቷል። በመንግስት በኩል ችግሩን ለመከላከል ለተከታታይ ዓመታት የተለያዩ ተግባራት ቢከናወኑም ውጤታማ መሆን ግን አልተቻለም።
ይህም ድክመትም እንደ አገር የትምህርት ስርአቱን አከራካሪ ሲሰባብረው ቆይቷል፡፡ ችግሩም በተማሪዎች ከራስ ጥረትና ልፋት ይልቅ በሌሎች ትከሻ ወረቀትን ለማግኘት እንዲተጉ፣ እውቀትን ከመሸመት ይልቅ ኩረጃን እንደ አቋራጭ መንገድ መጠቀምን ቀዳሚ ምርጫ እንዲያደርጉም ምክንያት ሆኖ ታይቷል፡፡
ከመጀመሪያ እስከ ሁለተኛ ደረጃ ባሉት የትምህርት እርከኖች ተማሪዎች ‹‹ባናጠናም እናልፋለን›› የሚል አስተሳሰብ እንዲዳብርና ሳይዘጋጁ ለፈተና መቅረብ የተለመደ እንዲሆን አድርጎትም ቆይቷል፡፡ የፈተናው አሰጣጥና ውጤት ጥራት ደካማ በመሆኑም በተለይ የመሰናዶ ተማሪዎች በሙሉ ለሙሉ በሚባል መልኩ ወደ ዩኒቨርሲቲ የሚገቡበት አሳፋሪ ሁኔታን ፈጥሯል።
እውቀት፣ ክህሎት፣ የስራ አመለካከት በበቂ ሁኔታ ይዞ ከመገኘት ይልቅ ቆብ መጫንና ምስክር ወረቀትን መያዝ ቀዳሚ ምርጫ ያደረገ ትውልድ እንዲሁም ከጥራት ይልቅ ብቃትን በማስቀደም በርካቶችም‹‹ ማስመረቅ››ቻልኩኝ በሚል የሚኮፈሱ የትምህርት ተቋማት እንዲበራከት አድርጓል፡፡ የአገሪቱ የትምህርት ዘርፍ የገባበትን ገደል ጥልቀት ለመረዳት ደግሞ ብዙ ርቀትን መመለስ ሳይፈልግ የቅርቡን የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ ፈተና አስደንጋጭ ውጤት ማስታወስ በቂ ነው፡፡
የወቅቱ መንግስትም ይህን የትምህርት ዘርፍ ስብራት በመረዳት የዘርፉን ችግር ያስቀራል የተባሉት ማሻሻያዎችን ባለፉት ሁለትና ሦስት ዓመታት ሲከውን ቆይቷል፡፡ የትምህርትና የሥልጠና ፍኖተ ካርታ ከማዘጋጀት ጀምሮ አዳዲስ አሠራሮችን አስተዋውቋል፡፡ አዳዲስ አሰራሮች ከተተገበሩባቸው መካከል ደግሞ የፈተና አሰጣጥ በቀዳሚነት ይጠቀሳል። ባለፉት ጊዜያትም የፈተና አሰጣጥ ሥርዓቱን ከማሻሻል ጀምሮ ሌሎች አቋራጭ መንገዶችን ለመዝጋት የሚያስችሉ ሥራዎች በመከናወን ላይ ናቸው፡፡ ከእነዚህ ተግባራት አንዱም የመውጫ ፈተና ነው፡፡
በአዲስ ፍኖተ ካርታም ወደ ተቋማቱ የሚገቡትን ብቻ ሳይሆን አጠናቀው የሚወጡትም የሥራ ገበያውን ከመቀላቀላቸው በፊት ብቃታቸው መፈተሽ አስፈላጊ መሆኑ ታምኖበታል፡፡ ትምህርት ሚኒስቴርም ከአንድ ዓመት በፊት የዩኒቨርሲቲ የመውጫ ፈተና በሁሉም የመንግስትና የግል ዩኒቨርሲቲዎች እንደሚሰጥ ውሳኔን አሳልፋል፡፡ የዩኒቨርሲቲ መውጫ ፈተናውንም ከቀናት በኋላ መሰጠቱ እርግጥ ሆኗል።
በአሁን ወቅትም ሁሉም በየፊናው ለፈተናው ስኬትና ያማረ ውጤት እየተጋ ይገኛል፡፡ የተለያዩ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትም ተማሪዎቻቸው ለመውጫ ፈተናው ብቁ እንዲሆኑ እየተጉ ናቸው፡፡ የመንግስትን ውሳኔ በመቀበል የሚፈለገውን ውጤት ለማምጣት በልዩ ትኩረት ተማሪዎችን ከማብቃትና ከማዘጋጀት አንፃር ሰፊ ስራዎች እየሰሩም ናቸው፡፡
የዚህ ፅሁፍ አዘጋጅ ከሰሞኑ ለስራ በተንቀሳቀሰባቸው ዩኒቨርሲቲዎች፣ ፈተናው በትምህርት ጥራት እንዲሁም ብቁና ተወዳዳሪ የሰው ኃይል ከማፍራት አንፃር ያለውን ሁለንተናዊ ፋይዳ ታሳቢ ባደረገ መልኩም ከተማሪዎች፣ ከመምህራን፣ ከአመራሮችና ጉዳዩ ከሚመለከታቸው የዩኒቨርሲቲው ማህበረሰብ አባላት ጋር በቅርበት እየሰሩ መሆኑን መታዘብ ችላል፡፡ ስለ ፈተናዉ መረጃና ግንዛቤ የመስጠት፣ ልዩ ድጋፍ የሚፈልጉ ተማሪዎችን የመለየት፣ ቲቶሪያል ትምህርት የመስጠትና ለዘርፉ አጋዥ የሆኑ ሞጁሎችን እና መጽሐፍቶችን እንዲሁም ሞዴል ፈተናዎችን የማዘጋጀት ተግባራት በስፋት እየተከናወነ ይገኛል፡፡
በእርግጥ የትምህርት ጥራትን የሚያረጋግጠው የመውጫ ፈተና ብቻ አይደለም፡፡ ይሑንና የመውጫ ፈተና ወደ ትምህርት ጥራት የሚደረገውን ጉዞ ምቹ ከሚያደርጉ መደላድሎች በዋነኛነት ሊጠቀስ የሚችል ነው፡፡ የመንግስት የለውጥ ጉዞ እርምጃውም ኢትዮጵያ በቂ የተማረ እና ለውጥ የሚያመጣ ትውልድን እንድታገኝ ትልቅ አቅም የሚሰጥ ነው፡፡ መሰል አሰራር በስርቆት መተማመንም ሙሉ በሙሉ ያስቀራል፡፡ ከስርቆት ይልቅ በራሱ አቅም የሚተማመንና በእውቀት የላቀ ትውልድን ለመፍጠር አቅም ይፈጥራል፡፡
የመውጫ ፈተናው ቀጥታ ውጤት የተማሪው ሊሆን ይችላል፡፡ በተዘዋዋሪ ግን የመምህሩ፣ የትምህርት ክፍሉ፣ የኮሌጁና የዩኒቨርሲቲው አጠቃላይ ውጤት ነው፡፡ የመውጫ ፈተናው በተለይ በአገሪቱ ትምህርት ጥራት ላይ የሚኖረው አስተዋፅኦ ነጋሪ አያሻውም፡፡ ይሕ ማለት ግን ውጤቱ ወዲያው ይታያል ማለት አይደለም፡፡ ፈተናው መኖሩ በመታወቁ ብቻ ከዚህ በኋላ ሁሉም ዩኒቨርሲቲም፣ አስተማሪም ሆነ ተማሪ መማር ማስተማርን በልዩ ትኩረትና ጥንቃቁ እንዲመለከቱ ያስገድዳል፡፡
መውጫ ፈተና በተለይም ለዩኒቨርሲቲዎች የህልውና ጉዳይ ነው፡፡ ለዩኒቨርሲቲዎች ሁለት እድልን ሰጥቶ ያልፋል፡፡ በርካታ ተማሪዎች ማሳለፍ ያልቻለ ዩኒቨርሲቲ ራሱን እንዲፈትሽ እንዲሁም በሚመለከታቸው አካላት ፍተሻ እንዲደረግበት ያስችላል፡፡
ተማሪዎቹም ለሀገር አቀፋዊ ፈተናው የሚሆን ዝግጅት እያደረጉ ናቸው፡፡ መምህራኖቻቸውም የተመረጡ የትኩረት መስኮች ዙሪያ የተለያዩ ግንዛቤን በማስጨበጥና ትቶሪያል ትምህርቶችን በመስጠት እገዛ ማድረጋቸው አላቋረጡም፡፡ ይሑንና በአንዳንድ ተማሪዎች ዘንድ የመውጫ ፈተና አቅሎም፣ አክብዶም የመመልከት እሳቤ ማስተዋል ተችሏል፡፡
ዩኒቨርሲቲዎቹም የመውጫ ፈተናውን በስኬት ለመወጣት ተማሪዎች ከመሰል የተሳሳተ እሳቤ እንዲታረሙ በተለይ ስነ ልቦና ዝግጁነት ላይ ሰፊ የምክርና ድጋፍ ስራዎች ሲያከናውኑ ቆይተዋል፡፡ መውጫ ፈተና እንደሚሰጥ ከተነገራቸው ግዜ ጀምሮ አስፈላጊውን ሁሉ ዝግጅት ሲያደርጉ የቆዩ ተማሪዎች ቢሆን ከየዩኒቨርሲቲዎቻቸው ባገኙት ድጋፍ እጅጉን ደስተኛ ስለመሆናቸው በተግባራቸው ብቻ ሳይሆን በአንደበታቸው ሲመሰክሩም መታዘብ ችለናል፡፡
የሚያጠግብ እንጀራ ከምጣዱ…. እንደሚባለው የተከናወኑ ተግባራት ፈተናው ውጤታማ ለማድረግ አቅም የሚፈጥሩ መሆናቸውም የሚያጠራጥር አይደለም፡፡ ተፈታኝ ተማሪዎችም ስለ መውጫ ፈተናው አዎንታዊ እንጂ አሉታዊ አመለካከት እንደማይኖራቸው፣ ፈናውን በብቃት እንደሚወጡ በልበ ሙሉነት የሚናገሩ እንጂ ፍርሃት ያሽመደመዳቸው ማግኘት ከባድ መሆኑም እርግጥ ነው፡፡
ምንም እንኳን ባለፉት ወራት በተከናወኑ ተግባራት የመውጫ ፈተናውን ውጤታማ በሆነ መልኩ መወጣት እንደሚቻል ቢታመንም የፈተናው ሂደት ሙሉ በሙሉ ከስጋት ነፃ ነው ማለት ግን አይደለም፡፡ በተለይ የኔትወርክና የመብራት መቆራረጥ ችግር የፈተናው አሰጣጡ ሂደት ላይ እክል እንዳይፈጥር ያሰጋል፡፡ መሰል ችግሮች ለአንድና ሁለት ዩኒቨርሲቲዎች ብቻ ሳይሆን ለበርካቶች ስጋት ሊሆኑ ስለሚችሉ ከወዲሁ የሚመለከታቸው አካላት መፍትሄው ላይ መስራት ይኖርባቸዋል፡፡
የዚህ ፅሁፍ አዘጋጅ ከሰሞኑ ለስራ በተንቀሳቀሰባቸው ዩኒቨርሲቲዎች ምንም እንኳን ተማሪዎች በዝግጅትም ሆነ በስነልቦና ጠንካራ ሆነው መውጣት ቢችሉም አንዳንዶች በአንጻሩ ፈተናውን የተመለከቱበት የፍርሃት መነፅር አሁንም ድረስ አለመጠረጉ በግልፅ ማስተዋል ችሏል፡፡ የመውጫው ፈተናው ውጤት የተማሪዎቹን ቀጣይ ሕይወት የሚወስን እንደመሆኑ ስነልቦናዊ ጫና እንደፈጠረባቸው በገፅታቸው ላይ የሚነበብ ብቻ አይደለም፡፡ በአንደበታቸው ጭምር የሚገልፅ ነው፡፡ ማናቸውም ተማሪዎች ዘንድ የሚስተዋል ጭንቀት እና ስጋት ደግሞ ምናልባትም ከፍ ሲል ነገሮች ባልተፈለገ አቅጣጫ ሊወስዳቸው የሚችልበት እድል የለም ለማለት አያስደፍርም፡፡
በተለይ በቂ ዝግጅት ያላደረጉ ተማሪዎች ውዥንብር በመፍጠር ፈተናውን ለማደናቀፍ ያልተገባ ሙከራ ሊያደርጉ ይችላሉ፡፡ ይህንን ታሳቢ ያደረገ ዝግጅትም አስፈላጊ ስለመሆኑ ይሰማኛል። የመውጫ ፈተናውን ውጤታማ በሆነ መልኩ ብቻም ሳይሆን ሰላማዊ በሆነ መልኩ እንዲጠናቀቅ ማድረግ እጅጉን ወሳኝ ነው፡፡
ለትምህርት ጥራት የሚገቡትን ብቻም ሳይሆን የሚወጡትንም ለማጥራት የሚከናወኑ ተግባራት በሚፈለገው ልክ ውጤታማ ለመሆን ተማሪዎችም የመውጫ ፈተናውን ሁለንተናዊ ጥቅም ጠንቅቀው መረዳት ይኖርባቸዋል፡፡ በተዛባ አስተሳሰብ ራሳቸውን ሳያስጨንቁና ሳይረብሹ በተረጋጋ መንፈስ ፈተናው ላይ ብቻ ትኩረት ሊያደርጉም ይገባል፡፡
ዩኒቨርሲቲውንም ሆነ ራሳቸውን በውጤታማነትን ብሎም በሰላማዊነት ማስጠራትን ቀዳሚ ምርጫ ማድረግም ይኖርባቸዋል፡፡ መሰል ለትምህርት ጥራት ወወደ ዩንቨርሲቲ የሚገቡትን ብቻ ሳይሆን የሚወጡትንም የማጥራት ተግባር፤ ሀገር ለማዳን ከሚከፈል መስዋዕትነት እኩል ሊታዩ የሚገባው፤ የትምህርት ስርአቱ ከወደቀበት ለማንሳት ትልቅ አቅም የሚሆን ነው። ከዚህ የተነሳ ለመውጫ ፈተናው ውጤታማነት ሁሉም ኃላፊነት ሊወጣ ይገባል፡፡
ታምራት ተስፋዬ
አዲስ ዘመን ሐምሌ 1/2015