የዴሞክራሲ ሥርዓትን ለመገንባትም ሆነ የሕግ የበላይነትን ለማስፈን ተቋማት የማይተካ ሚና አላቸው። ተቋማት ሲባሉ በተለምዶ ቀድመው ወደ አእምሯቸው የሚመጡት የመንግስት አካላት ማለትም ሕግ አውጭው፣ ተርጓሚዊና አስፈጻሚው የስልጣን ክፍፍል/ሴፓሬሽን ኦፍ ፓወር/፣ የዳኝነትና የፍትሕ ተቋማት፣ የምርጫ ቦርድ፣ የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን፣ የሕዝብ እንባ ጠባቂ ተቋም ፣ የሚዲያ፣ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች፣ ወዘተረፈ ናቸው።
እነዚህ ተቋማት የተጣለባቸውን ኃላፊነት በአግባቡ እንዲወጡ ደግሞ ጤናማ የፋይናንስ አጠቃቀምና የክዋኔ ኦዲት ያስፈልጋቸዋል። ለዚህ ደግሞ ጠንካራና ገለልተኛ የፌዴራል ዋና ኦዲተር እና በየደረጃው ተመሳሳይ ተቋማት ያስፈልጋሉ። ጤናማ የፋይናንሽያልና የክዋኔ የኦዲት አፈጻጸም የሌለው ተቋም አይደለም ዴሞክራሲያዊ ሥርዓትን ለማስፈንና የሕግ የበላይነትን ለማረጋገጥ ይቅርና ህልውናውን ማስቀጠል ይሳነዋል።
በሙስና እና በብልሹ አሰራር የተተበተበ አስፈጻሚ፣ ሕግ አውጭና ተርጓሚ፣ ሚዲያ፣ የዳኝነት፣ የፍትሕ ተቋም፣ የምርጫ ቦርድ፣ የሲቪል ሰርቪስ ድርጅት የዴሞክራሲያዊ ሥርዓትን መገንባትንና የሕግ የበላይነትን ማስፈን ይቅርና የሀገርን ህልውናን ለባሰ አደጋ ይደርጋል። ስለሆነም እርስ በርስ ከሚያደርጉት ቁጥጥርና ክትትል በተጨማሪ ጠንካራ የውስጥና የውጭ ኦዲተር ምርመራ ሊደርግባቸው ይገባል። ለዚህ ደግሞ ጠንካራ የኦዲት ተቋም መመስረት ያሻል።
ከተመሠረተ በኋላ የሚሰራቸው ሥራዎች ወይም የምርመራ ግኝቱ፣ የመውጫ ዘገባውና ምክረ ሀሳብ ውጤታማ እንዲሆኑ ሚዲያው፣ የፍትሕ ተቋማት፣ ጸረ ሙስና ኮሚሽንና የሚመለከታቸው አካላት ተገቢውን ድጋፍ ሊያደርጉና ኃላፊነታቸውን ሊወጡ ይገባል። ዝቅ ብሎ እንደተገለጸው የፀረ ሙስና ኮሚሽን ለሌሎች አርዓያና የልህቀት ማዕከል መሆን ሲገባው በዋና ኦዲተር ሪፖርት መካተቱ ገና ብዙ ሥራ እንደሚጠበቅብን ያሳጣል።
ሌሎችን ተቋማት እናቆያቸውና ሚዲያውን እንታዘብ። እስኪ የትኛው ሚዲያ ነው የፌዴራል ዋና ኦዲተር የምርመራ ግኝትንና ምክረ ሀሳብን ተከትሎ ተከታታይ ዘገባዎችን የሰራው። ግኝቱን ተንትኖና ተርጉሞ ለሕዝብ ያስረዳ፤ ከእነ ነጠላ ዜናው እንኳ ተሸፋፍኖና ተድባብሶ የሚያልፍና የኦዲት ግኝቶችን አልቦና አድክሞ የሚዘግብ ነው ። በዚህ አኳኋን ሚዲያው ኃላፊነቱን ሊወጣ አይችልም።
ለዚህ ይመስላል የፌዴራል ዋና ኦዲተር መሠረት ዳምጤ በዚያ ሰሞን፤ የኦዲት ተደራጊ ተቋማትን የኦዲት ግኝት ማስተካከያ ርምጃዎችን ሂደት ከመከታተልና የደረሱበትን ውጤት ለሕዝብ ተደራሽ ከማድረግ አንጻር የሚዲያ አካላት ሚና ከፍተኛ መሆኑን የገለጹት፡፡ ሚዲያና የሒሳብ ምርመራ ምንና ምን ናቸው የሚሉትን አጠር አርገን ከተመለከትን በኋላ ወደ ዋና ኦዲተሯ መግለጫ እንመለሳለን።
ብዙኃን መገናኛዎች የኦዲት ሪፖርትንና ግኝትን መነሻ በማድረግ ቀጣይነትና ተከታታይነት ያለው ሽፋን በመስጠት ግልጽነትን፣ ተጠያቂነትን፣ ክትትልና ቁጥጥርን ለማድረግ የማይተካ ሚና አላቸው ሲሉ በዘርፉ የተጻፉ ድርሳናት ያብራራሉ። በኦዲት ሒደት ሚዲያ የኦዲት ግኝትን ለሕዝብ በማሳወቅ፤ የምርመራ ጋዜጠኝነትን በማካሄድ ሙስናንና ብልሹ አሰራሮችን ለማጋለጥ፤ የሕዝብን ግንዛቤ ለማሳደግና ለማስተማር፤ ሙሰኞችንና ብልሹ አሰራሮችን በሚስጥር ለሚጠቁሙ ሕጋዊ ጥበቃ ለመስጠት ወይም ለ Whistle blower Protection፤ የቁጥጥር አሰራሮች እንዲሰፍኑ ለመወትወት ግንባር ቀደም አስተዋጽኦ አላቸው።
ኦዲተሩ ብልሹ አሰራርን፣ ማጭበርበርንና ዘረፋን በምርመራ ሲደርስበት ለሕዝቡ፣ ለባለአክሲዮኖችና ለባለድርሻዎች በማሳወቅ ጥፋተኞችን ተጠያቂ ለማድረግና ግልጽነትን ለማስፈን ያግዛል። እንዲሁም የኦዲት ሪፖርቱን መነሻ በማድረግ የምርመራ ጋዜጠኞች ጥልቅ ምርመራ በማካሄድ ብልሹ አሰራሩንና ሙስናውን እንዲደርሱበት ፍንጭ ይሰጣል። እንዲሁም ኢ ሥነ- ምግባራዊ አካሄዶችን፣ የጥቅም ግጭት፣ የመመሪያና የሕግ ጥሰት ካለም በማጋለጥ የክትትልና የቁጥጥር ሥርዓቱ እንዲጠናከርና ክስ እንዲመሠረት ያግዛል።
የኦዲት ግኝቶች የሚዲያ ሽፋን ሲያገኙ ሕዝቡ ስለ የፋይናንስ ሪፖርትና ስለ ሒሳብ ምርመራ ወይም ኦዲቲንግ ግንዛቤ እንዲኖራቸው ያደርጋል። ይህ ደግሞ ሕዝብ በእውቀት ላይ የተመሠረተ ውሳኔ እንዲያሳልፍ ይረዳዋል። ሙስናን፣ ማጭበርበርንና ዘረፋን በሚስጥር ለሚጠቁሙ ሰዎች ማንነታቸውን ሳይገልጽ ድምጽ በመሆን ሚዲያው ወሳኝ ድርሻ አለው። ሌላው ሚዲያ ለኦዲት ግኝቶች ሰፊ ሽፋን የሚሰጥ ከሆነ ሕዝብ አጀንዳ አድርጎ በስፋት እንዲነጋገርባቸው በማድረግ፤ ሕዝቡ እርምጃ እንዲወሰድ በሚመለከተው አካል ላይ ግፊትና ጫና እንዲፈጥር ያነሳሳል።
በዘላቂነትም የክትትልና የቁጥጥር አሰራሮች እንዲሻሻሉ፤ ተጠያቂነት፣ ግልጽነትና የኦዲት ሥራ ውጤታማ እንዲሆን የላቀ ድርሻ አለው። ጋዜጠኞች የኦዲት ግኝትን ሲዘግቡ ሙያዊ ሥነ ምግባሩን አክብረውና በትክክል፣ ያለ አድልዎ ሊሆን ግድ ይላል። ለመንደርደሪያ ያህል ስለሚዲያና የኦዲት ግኝት ይህን ያህል ካነሳሁ ወደ ዋና ኦዲተሯ መልዕክት ልመለስ።
የፌዴራል ዋና ኦዲተር ወ/ሮ መሠረት በዓለም አቀፍ ደረጃ ከሚታወቁት ሦስት የኦዲት አሠራርና አወቃቀር ሞዴሎች ውስጥ ፓርላሜንታዊ ሥርዓት የሚከተሉ ሀገራት የሚተገብሩትን የ“Westminster” የኦዲት ሥርዓት ሞዴል የሚከተልና ስልጣንና ኃላፊነቱም በተለያዩ ተቋማት ላይ ያከናወናቸውን የተለያዩ ኦዲቶች መሠረት ያደረጉ ግኝቶች ሪፖርቶችን ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ማቅረብ መሆኑን አብራርተዋል፡፡
የኦዲት ግኝቶቹን መሠረት ያደረጉ ደረጃቸውን የጠበቁ ርምጃዎችን የመውሰድና ተጠያቂነትን የማስፈን ህጋዊ ስልጣን የም/ቤቱ መሆኑን፤ በዓለም አቀፉ የኦዲት አሠራር መመሪያ መሠረት በሜክሲኮ “ዴክላሬሽን” የተጠቀሱ ስምንት ዓለም አቀፋዊ የኦዲት ተቋማት መመሪያዎችን ለፌደራል ዋና ኦዲተር በሕግ መንግስቱና በአዋጅ ከተሰጡት ስልጣንና ተግባራት ጋር በማሳለጥ የሚተገብር ነው ብለዋል፡፡
ከ2008 ዓ.ም ጀምሮ እስከ 2014 ዓ.ም ድረስ በተለያዩ ተቋማት ላይ ያካሄዳቸውን የተለያዩ ኦዲቶች መሰረት ያደረጉ ዋና ዋና ግኝቶችን በዝርዝር የገለጹት ዋና ኦዲተሯ በእነዚህ ዓመታት ውስጥ ከተለያዩ ግኝቶች አንጻር ነቀፌታ የሌለበት አስተያየት የተሰጠባቸውን፤ ከጥቂት ጉድለቶች በስተቀር አጠቃላይ አጥጋቢ ውጤት የታየባቸውን፤ አስተያየት ለመስጠት ያልተቻለባቸውን እና ተቀባይነት የሚያሳጣ የኦዲት ግኝት የታየባቸውን በመለየት በአኃዛዊ መረጃ አቅርበዋል፡፡
ከዓለም አቀፍ ተሞክሮ አንጻር የሀገሪቱን የኦዲት ሥራ አወቃቀር፤ ኦዲታቸው በልዩ ኦዲት ስለሚከናወን ተቋማት፤ ከኦዲት ግኝት በኋላ በአጥፊዎች ላይ መወሰድ ስለሚገባው ርምጃና ተጠያቂነት፤ በኦዲት ሂደት ላይ ሊኖር ስለሚገባው የሚዲያዎች ሚና፤ ከክልል ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤቶች ጋር ስላለው ግንኙነት እና ሌሎች ተዛማጅ ጉዳዮች ጥያቄ አቅርበው ዋና ኦዲተሯ ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል፡፡
ሀገሪቱ የፓርላሜንታዊ ሥርዓት ተከታይ እንደመሆኗ እንደሌሎች ይህንን ሥርዓት እንደሚከተሉ ሀገራት ዋና ኦዲተር ተቋማት ሁሉ የኢፌዴሪ ዋና ኦዲተርም በእቅድ የያዛቸውን ተቋማት ኦዲት የማድረግና ግኝቶችንም ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በሪፖርት ማቅረብ፤ በፌደራሉና በክልል ዋና ኦዲተሮች መካከል ይስተዋል የነበረውን የኦዲት ሥራ ድግግሞሽ
ቁምላቸው አበበ በአማራ ባህል፣ ቱሪዝምና ማስታወቂያ ቢሮ፤ በኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት፤ በደቡብ መገናኛ ብዙኀን፤ በጋዜጠኝነትና በታሪክ ባለሙያነት ያገለገሉ ሲሆን፤ የደቡብ ኤፍ ኤምን ከባልደረቦቻቸው ጋር በመሆንም አቋቁመዋል። በፌዴራል ውሃ ስራዎች ኮንስትራክሽን ድርጅትና በአለ በጅምላ በኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክተርነት አገልግለዋል። ከአአዩ በቋንቋና ታሪክ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን የሰሩ ሲሆን፤ በዚሁ ዩኒቨርሲቲ በጋዜጠኝነትና ኮሙዩኒኬሽን ሁለተኛ ዲግሪያቸውን በማጠናቀቅ ላይ እያሉ ባጋጠማቸው ድንገተኛ ህመም ተስተጓጉሏል። ጥልቅ ሀሳብ ያዘሉ ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ የሚያተኩሩ ፁሑፎችን በማህበራዊ ሚዲያና በተለያዩ ጋዜጦች በማውጣት ይታወቃሉ።
ክፍተት ለማስቀረት በአዋጅ የተደገፈ ተግባር መከናወኑን፤ የክልል ዋና ኦዲተሮች ዓለም አቀፋዊ የኦዲት አሠራር እንዲከተሉ ለማድረግ በሰው ኃይል አቅም ግንባታም ሆነ በቁሳቁስ ለመደገፍ ከፍተኛ ሥራ እየተሰራ ይገኛል፡፡
በኦዲት ግኝቶች ላይ የማስተካከያ ርምጃዎች ሊወሰዱና በአጥፊዎች ላይ የተጠያቂነት አሠራርም ተጠናክሮ መቀጠል እንደሚገባው፤ ለዚህ ተግባር ውጤታማነትም የሚዲያ አካላት የኦዲት ግኝቶች በተመዘገቡባቸው የኦዲት ተደራጊ ተቋማት ላይ በመስራትና ውጤቱን ለሕዝብ ይፋ በማድረግ የድርሻቸውን ሊወጡ ይገባል፡፡
የፌዴራል ዋና ኦዲተር መሠረት ዳምጤ የ2014 በጀት ዓመት የኦዲት አፈጻጸሙን ለኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባለፈው ባቀረቡበት ሪፖርት፤ በኦዲት ግኝቶቹ መሠረት ለኦዲት ተደራጊ ተቋማቱ በተሰጡ የማሻሻያ ርምጃ አስተያየቶች መሰረት በርካታ የማሻሻያ ርምጃዎች መወሰዳቸውን፤ በተለይም ተሰብሳቢ ሂሳቦችን በተመለከተ የተሰበሰቡና ያልተሰበሰቡ ገንዘቦች በሪፖርቱ በዝርዝር ቀርበዋል፡፡
በተጨማሪም ሕግን ያልተከተሉ ወጪዎች ፣ ሕግና መመሪያን ያልተከተሉ ክፍያዎች፣ አሠራርን ያልተከተሉ የሂሳብ አመዘጋገቦች፣ በጊዜያቸው መከፈል የነበረባቸውና ያልተከፈሉ ሂሳቦች፣ የአጠቃቀም ችግር ያለባቸው በጀቶች እና ሕገ ወጥ ግዥዎች እንዲሁም በርካታ የንብረት አስተዳደር ጉድለቶች በተለያዩ ተቋማት ላይ በኦዲቱ መታየታቸውና ለእነዚህም ግኝቶች የኦዲት ማስተካከያ አስተያቶች መሰጠታቸው በሪፖርቱ ተመልክቶል፡፡
ከዚህም ሌላ በበጀት ዓመቱ ያካሄዳቸው የክዋኔ ኦዲቶች በሪፖርቱ በዝርዝር የቀረቡ ሲሆን ለኦዲት ግኝቶቹም ተገቢ የኦዲት ማስተካከያ አስተያየቶች መሰጠታቸው ተገልጿል፡፡ ከሪፖርቱ በኋላ ከምክር ቤት አባላት የተለያዩ አስተያየቶችና ጥያቄዎች ቀርበው በዋና ኦዲተር ወ/ሮ መሠረት ምላሽና ማብራሪያ የተሰጠባቸው ሲሆን በሪፖርቱ መሠረት የተለያዩ ጉድለቶች በታዩባቸው ተቋማት እና አካላት ላይ ተጠያቂነትን በማስፈን ም/ቤቱም ሆነ ሌሎች የሚመለከታቸው የመንግስት አካላት አስፈላጊውን የማስተካከያ ርምጃ እንዲወስዱ ዋና ኦዲተሯ ጠይቀዋል፡፡
የፌዴራል ዋና ኦዲተር ወ/ሮ መሠረት ዳምጤ የ2014 በጀት ዓመት የፌዴራል መንግሥት መሥሪያ ቤቶች የፋይናንስና ሕጋዊነት ኦዲትን በተመለከተ ተቋማቸው ያካሄደውን የኦዲት ሪፖርት፤ ማክሰኞ ሰኔ 20 ቀን 2015 ዓ.ም ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አቅርበዋል፡፡ በተደረገው የኦዲት ሥራ ስድስት ተቋማት አስተያየት ለመስጠት ያልተቻለባቸው ሲሆኑ፤ 19 ተቋማት ደግሞ የጎላ ችግር ያላባቸው ሆነው በመገኘታቸው ተቀባይነት የሚያሳጣ አስተያየት ተሰጥቶባቸዋል፡፡
ሒሳባቸው የጎላ ችግር ያለበት በመሆኑ ተቀባይነት የሚያሳጣ አስተያየት ከተሰጠባቸው ተቋማት መካከል የፌዴራል ሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን፤ የኢትዮጵያ ፖሊስ ዩኒቨርሲቲ፣ የኢንፎርሜሽንና መረብ ደኅንነት አገልግሎትና የፌዴራል ፖሊስ ይገኙበታል፡፡ እንዲሁም ሚዛን ቴፒ ፣ ጂንካ ፣ ደብረ ብርሃን ፣ ጋምቤላ ፣ ወላይታ ሶዶ ፣ አዲስ አበባ ፣ ቦሌ ሆራና የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲዎች ይገኙበታል፡፡
የፌዴራል ዋና ኦዲተር አስተያየት ለመስጠት አልቻልኩባቸውም ካላቸው ተቋማት መካከል የሪፐብሊኩ የጥበቃ ኃይል፣ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ፣ ብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት፣ የቀድሞው የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት፣ የአደጋ ሥጋትና ሥራ አመራር ኮሚሽንና የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር ይገኙበታል፡፡
ከአንድ ዓመት እስከ ስድስት ዓመት ዕድሜ ያለውና ለመንግሥት ገቢ መደረግ የነበረበት 13.4 ቢሊዮን ብር ውዝፍ የጉምሩክ ቀረጥና ታክስ ዕዳ መኖሩ በሪፖርቱ ተመላክቷል። የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ 124 ሚሊዮን ብር፣ የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር 65 ሚሊዮን ብር፣ የአደጋ ሥጋትና ሥራ አመራር ኮሚሽን 64 ሚሊዮን ብር፣ የሰመራ ጉምሩክ ቅርንጫፍ 7.9 ሚሊዮን ብር፣ የሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን 5.6 ሚሊዮን ብር ፣ ወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ 4.8 ሚሊዮን ብር ፣ በድምሩ 307.5 ሚሊዮን ብር የተሟላ ወጪ ሳይቀርብ በወጪ መዝግበው የተገኙ መሥሪያ ቤቶች ናቸው፡፡
በሌላ በኩል ከደንብና ከመመሪያ ውጭ ያላግባብ ክፍያ ከፈጸሙ ተቋማት መካከል የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ 30 ሚሊዮን ብር ፣ የኢትዮጵያ ፖሊስ ዩኒቨርሲቲ 22 ሚሊዮን ብር ፣ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጤና ሳይንስ ኮሌጅ 11.8 ሚሊዮን ብር፣ የመንግሥት ግዥና ንብረት ባለሥልጣን 7.6 ሚሊዮን ብር፣ የቤተ መንግሥት አስተዳደር 6.5 ሚሊዮን ብር፣ አርሲ ዩኒቨርሲቲ 6.1 ሚሊዮን ብር፣ በድምሩ 134.2 ሚሊዮን ብር ተጠቃሽ ናቸው፡፡
የመንግሥት የግዥ አዋጅ ደንብና መመሪያ ያልተከተሉ ግዥዎችን የፈጸሙ 82 ተቋማት በሪፖርቱ የተጠቀሱ ሲሆን፣ ከእነዚህ መሥሪያ ቤቶች የተገኘው የግዥን ሕግ የጣሰ ክፍያ 592.4 ሚሊዮን ብር ነው። ተቋማቱ ጉምሩክ ኮሚሽን፣ ጂንካ ዩኒቨርሲቲ፣ ሰላሌ ዩኒቨርሲቲ፣ የኢንፎርሜሽን መረብና ደኅንነት አገልግሎት፣ የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚና ቡሌሆራ ዩኒቨርሲቲ ናቸው፡፡
የፌዴራል ዋና ኦዲተር ወ/ሮ መሠረት በተከፋይ ሒሳብ ተመዝግበው የተገኙ ነገር ግን ዝርዝር ማስረጃ ባለማቅረቡ የሒሳቡን ትክክለኛነት ለማረጋገጥ እንዳልቻለ ያቀረቡ ሲሆን ፣ ከእነዚህ ተቋማት መካከል የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት አንድ ቢሊዮን ብር፣ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት 583 ሚሊዮን ብር፣ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር 131.8 ሚሊዮን ብርና ጉምሩክ ኮሚሽን 96.5 ሚሊዮን ብር ይገኙበታል፡፡
ከተደለደለላቸው በጀት በላይ የተጠቀሙ መሥሪያ ቤቶችም በሪፖርቱ የተጠቀሱ ሲሆን፣ ከእነዚህ መካከል ወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ 358.9 ሚሊዮን ብር፣ ዲላ ዩኒቨርሲቲ 125 ሚሊዮን ብር፣ ሚዛን ቴፒ ዩኒቨርሲቲ 139.9 ሚሊዮን ብር፣ ዋቻሞ ዩኒቨርሲቲ 166.7 ሚሊዮን ብር፣ እንዲሁም አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ 113 ሚሊዮን ብር ናቸው፡፡
የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች በ2014 ዓ.ም የተፈቀደላቸውን በጀት መጠቀም ሲገባቸው ባለመጠቀማቸው የተገኘው አጠቃላይ ገንዘብ 35 ቢሊዮን ብር መሆኑ በሪፖርቱ ተጠቅሷል፡፡ በጀት ሥራ ላይ ካላዋሉ መሥሪያ ቤቶች የመስኖና ቆላማ ሚኒስቴር 8.9 ቢሊዮን ብር፣ የገንዘብ ሚኒስቴር 6.3 ቢሊዮን ብር፣ የጤና ሚኒስቴር ሦስት ቢሊዮን ብር፣ ፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን 1.2 ቢሊዮን ብር፣ የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር አንድ ቢሊዮን ብር፣ የትምህርት ሚኒስቴር 915 ሚሊዮን ብር፣ እንዲሁም የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር 599 ሚሊዮን ብር ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡ ዋና ኦዲተሯ በጀት ከተፈቀደ በኋላ አለመጠቀም የታቀዱ ሥራዎች ሳይከናወኑ ሊቀሩ ስለሚችሉና ተቋማትም ዓላማቸውን እንዳያሳኩ ስለሚያደርጋቸው፣ የበጀት ዝግጅትና የአጠቃቀም ጥንቃቄ እንዲደረግ አሳስበዋል፡፡
የተሽከርካሪ አጠቃቀምና አያያዝን በተመለከተ በሚያብራራው የኦዲት ሪፖርት በመንግሥት ተቋማት ውስጥ 188 ተሽከርካዎች ሊብሬ ያልቀረበባቸው ናቸው፡፡ 694 ተሽከርካሪዎችና 56 ሞተር ብስክሌቶች ያለ አገልግሎት ወይም በብልሽት የቆሙ ሲሆኑ፣ የባለቤትነት መታወቂያ ደብተራቸው በሌሎች መሥሪያ ቤቶችና ድርጅቶች ስም የሆኑ 275 ተሽከርካሪዎች፣ የነዳጅ መቆጣጠሪያ (ጌጅ) የሌላቸው 44 ተሽከርካሪዎች፣ የመድን ዋስትና የሌላቸው ወይም ያልተገባላቸው አሥር መኪኖች ይገኙበታል ተብሎ በሪፖርቱ ተገልጿል፡፡
የኦዲት ሪፖርቱ ከተሰጠ በኋላ የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የፓርላማ አባል አቶ ሙሉቀን አሰፋ፣ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ አስተባባሪነት በሚመሩ የሜጋ ፕሮጀክቶች ጉዳይ የገንዘብ አሰባሰብና አወጣጥን በተመለከተ የመንግሥት የፋይናንስን አዋጅ ደንብና መመሪያ ተከትሎ እየተሠራ ስለመሆኑ ኦዲት አድርጋችሁ ከሆነ የኦዲት ሪፖርቱ ቢገለጽልን፣ ካላደረጋችሁ ደግሞ ኦዲት ላለማድረግ ምክንያታችሁ ምንድነው?›› በማለት ጥያቄ አቅርበዋል፡፡
የፌዴራል ዋና ኦዲተሯ ወ/ሮ መሠረት ለተነሳው ጥያቄ በሰጡት ምላሽ፣ “ኦዲት አላደረግንም፣ ያላደረግንበት ምክንያት ምንድነው? የፌዴራል ዋና ኦዲተር ተግባርና ኃላፊነት የመጀመሪያው በተከበረው ምክር ቤት የፀደቀውን በጀት የክዋኔ ኦዲት ማድረግ፤” ነው ብለዋል፡፡ በተጨማሪ ደግሞ የመንግሥት ተቋማትም ይሁኑ የልማት ድርጅቶች በአዋጅ በተሰጣቸው ሥልጣንና ኃላፊነት መሠረት የክዋኔ ኦዲት እንደሚደረግና ሪፖርት እንደሚቀርብ ተናግረዋል፡፡ “ስለዚህ ቅድሚያ በተሰጠን ሥልጣንና ኃላፊነት መሠረት እንሄዳለን፡፡ አሁንም ግን እነዚህን ፕሮጀክቶች በተመለከተ የተመዘበረና የጠፋ ነገር ካለ በኦዲት የሚታለፍ ተቋም ስለሌለ፣ የፕሮጀክቶቹ ስምና የጎደለው ገንዘብ በግልጽ ከቀረበልን ለማየት ዝግጁ ነን፤” ማለታቸውን የሪፖርተር ዘገባ ያመለክታል፡፡
ሻሎም ! አሜን ።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን