ማዋዣና መንደርደሪያ፤
ሰኔ 22 ቀን 2015 ዓ.ም በታተመው በዚሁ አንጋፋ ጋዜጣ ላይ የአካባቢው ስያሜ በስሙ ደምቆ፤ መታሰቢያው ግን ከቦታው ተነስቶ አስታዋሽ በማጣት ተድበስብሶ ስለቀረው የፑሽኪን ሐውልት ጉዳይ ታሪካቸውንና ታሪካችንን፤ ገጠመኞቻቸውንና ገጠመኛችንን እያዛነቅሁ “አውቀው ለተኙት ይመለከተናል ባዮች” መቀስቀሻ ይሆን ዘንድ ግለሰባዊ ትዝብቴንና ወቀሳዬን አለሳልሼ ማስነበቤ ይታወሳል፡፡
ይህንን ጽሑፍ ያነበቡ ወዳጆቼ “ከ1799 – 1837 ስለኖረው የደም ተዋራሻችን ስለ አሌክሳንደር ሰርጌቪች ፑሽኪን ብቻ ምነው? የእኛዎቹስ መሰል ታሪኮችና ባለታሪኮች ቢታወሱ አይበጅም ወይ?” ብለው ስለጠየቁኝ፤ ከዘላቂ ማረፊያ የቀብር ቦታቸው ላይ ክብር ተነፍጓቸው ስላጎሳቆልናቸው የጥቂት ነፍሰ ሔር አርአያዎቻችንን የመቃብር ሐውልቶችና የአደባባይ ሞገሳቸውን ስለተገፈፉት የታሪካዊ መታሰቢያ ሐውልቶቻችን የትዝብት ቁዘማ ለማድረግ በዚህ ጽሑፍ ዳግም ተመልሻለሁ፡፡
ወደ ዋናው ርዕሰ ጉዳይ ከመግባቴ አስቀድሞ እንደ መንደርደሪያ እንዲያግዘን በታላቁ እንግሊዛዊ ባለቅኔ በዊሊያም ሼክስፒር የመቃብር ሐውልት ላይ የተቀረጸውን መልእክት ላስታውስ፡- “Blessed is the man who spares these stones, and cursed be he who moves my bones.” ተቀራራቢ የአማርኛ አቻ ትርጉሙ እንደሚከተለው ሊነበብ ይችላል፡- “ይህንን ሐውልቴን አክብሮ የሚጠብቅ ብፁእ ነው፤ ለአጽሜ ክብር ባለመስጠት የመቃብሬን መታሰቢያ የሚያፈርስ ሰው ግን የተረገመ ይሁን፡፡”
በመቃብር ላይም ሆነ በአደባባዮች ላይ የሚቆሙ ሐውልቶች የሙታን ስሞች የሚታወሱባቸው ብቻ ሳይሆኑ መልካም ተግባራቸውም ሆነ እኩይ ድርጊታቸው በእኩልነት የሚዘከርበት ስለሆነ በትውልዶች የዘመን ቅብብሎሽ እንደተከበሩ ቢሸጋገሩ፤ የሼክስፒርን አባባል እንዋስና፤ የአስተማሪነት ፋይዳቸው ከፍ ያለ ብቻ ሳይሆን “ብፅእናውም ሆነ እርግማኑ” ለሀገር ታሪክ ጭምር የሚተርፍ እንደሆነ ልብ ሊባል ይገባል፡፡
በመንገድ መስፋት ምክንያት የፈረሰው የደም ተዛማጃችን የአሌክሳንደር ፑሽኪን የመታሰቢያ ሐውልት ብቻ አይደለም፡፡ በእኛው ባለቅኔም ላይ ተመሳሳይ ታሪክ ተፈጽሞበታል፡፡
“አጥንቱን ልልቀመው መቃብር ቆፍሬ፣
ጎበናን ከሸዋ አሉላን ከትግሬ፤
ስመኝ አድሬያለሁ ትላንትና ዛሬ፣
አሉላን ለጥይት ጎበናን ለጭሬ፡፡
ጎበና ሴት ልጁን ሊያስተምር ፈረስ፣
አሉላ ሴት ልጁን ጥይት ሊያስተኩስ፡፡
ሀገሬ ተባብራ ካልረገጠች እርካብ፣
ነገራችን ሁሉ የእምቧይ ካብ የእምቧይ ካብ።
በማለት የተቀኘውና “ኢትዮጵያ ሆይ! ደስ ይበልሽ” የሚለውን የመጀመሪያውን ብሔራዊ መዝሙራችንን የደረሰው፣ አርበኛው፣ የዳግማዊ ምኒልክ ት/ቤት መምህሩ፣ የሕግ መወሰኛ ምክር ቤት ምክትል ፕሬዚዳንትና የበርካታ ቴያትሮችና ግጥሞች ደራሲ የሆነው የባለቅኔው የቀኝ ጌታ ዮፍታሔ ንጉሤ (1887 – 1939 ዓ.ም) ታሪክ በስሱም ቢሆን የፍጻሜው ታሪክ ከፑሽኪን የሐውልት መፍረስ ጋር የሚቀራረብ ይመስለናል፡፡
የፓርላማውንና የጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤትን እየታከከ ከአራት ኪሎ ወደ አዋሬ የሚወስደው መንገድ በግንባታ ምክንያት በሚሰፋበት ወቅት በአካባቢው የነበረውን የበዓለ ወልድ ቤተ ክርስቲያንን መካነ መቃብር በመንካቱ የታላቁ የሀገር ባለውለታ የዮፍታሔ ንጉሤ አጽም በዶዘር ተፈንቅሎ ወጥቶ ነበር፡፡
“አጥንቱን ልልቀመው መቃብር ቆፍሬ…” ብሎ የተቀኘው ባለቅኔ ትንቢቱ በራሱ ላይ በመፈጸሙ አጽሙ እንደ አልባሌ ነገር ተበታትኖ ያስተዋሉት የቤተ ክርስቲያኒቱ አገልጋዮችና ለታሪክ ግድ ባላቸው የአካባቢው መልካም ሰዎች ጥቆማና እሪታ አጽሙ የትም ተበታትኖ እንዳይቀር የሊስትሮ መሣሪያ በምታህል አነስተኛ ሣጥን ውስጥ ተሰብስቦ አጽሙ በቤተ ክርስቲያኑ ታዛ ሥር ተቀምጦ ስናስተውል በርካቶቻችንን ለእንባ ዳርጎን ነበር፡፡
ይህ ጸሐፊ ይህንን ጉዳይ በተመለከተ የዓይን እማኝ ስለነበረ በዚሁ ጋዜጣ ላይ ሐዘኑ እንደከበደበት ሁኔታውን ማስነበቡ ይታወሳል፡፡ ሐምሌ 1 ቀን 2009 ዓ.ም ለዓመታት ተረስቶ የቆየውን አጽሙን በትውልድ ስፍራው በጎጃም ደብረ ኤሊያስ በክብር እንዲያርፍ ላመቻቹ ግለሰቦችና ተቋማት ምሥጋና ማቅረቡ ተገቢ ይሆናል፡፡
ሌላውና መታወስ ያለበት ጉዳይ ከወጋየሁ ንጋቱ እረፍት በኋላ የተፈጸመው አሳዛኝ ክስተት ነው። 30 ያህል የመድረክ፣ 18 የቴሌቪዥን፣ 46 የሬዲዮ በጠቅላላው 94 የሚደርሱ ቴያትሮችን በዘመነ ሕይወቱ የተወነውና የፍቅር እስከ መቃብር መጽሐፍን በአስደናቂ የሬዲዮ ትረካ ያስደመጠን ወጋየሁ ንጋቱ በአጸደ ሥጋ የተለየን ኅዳር 6 ቀን 1982 ዓ.ም ነበር፡፡
በህልፈተ ሕይወቱ ማግሥት አጽሙ ባረፈበት የእንጦጦ ኪዳነ ምህረት ዋና መግቢያ በር ላይ የመታሰቢያ ሐውልት ቆሞለት ነበር፡፡ ነገር ግን ሐውልቱ ከቆመ ከጥቂት ወራት በኋላ ቦታው የከተማ አውቶቡስ ማዞሪያ ነው በሚል ምክንያት ሐውልቱ ፈርሶ ልክ እንደ ዮፍታሔ ንጉሤ አጽም በቤተ ክርስቲያኒቱ መጠለያ ሥር ይወረወራል፡፡ ይህን አሳዘኝ ክስተት ያስተዋሉት ባለቤቱ ወ/ሮ አምሳለ ገነት ይመር ከዚህ ዐምደኛ ቢሮ በመገኘት እንባቸው እንደ ጎርፍ እየወረደ “የወጋየሁ ንጋቱ ውለታ ይሄ ነወይ?” በሚል ቁጭት ብሶታቸውን ገለጹለት፡፡
ይህ ጸሐፊም የወጋየሁ ወዳጅነትና የረዢም ዘመን አገልግሎቱ ግድ ስላለው በወቅቱ የአዲስ ዘመን ጋዜጣ እህት ለነበረችው ለተወዳጇ የዛሬይቱ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ለአቶ ስሜነህ መኮንን ጉዳዩን በማስረዳት የካሜራ ባለሙያ ተመድቦለት ዝርዝር ታሪኩን በዚያው ጋዜጣ ላይ እንዲታተም አድርጓል፡፡
አሳዛኝ ክስተቱ ለሕዝብ ይፋ ከተደረገ በኋላ የፈረሰው ሐውልት በተሻለ ሁኔታ ይሰራል የሚል ተስፋ ከወቅቱ መንግሥት በይፋ የተሰጠ ቢሆንም ትግበራው ከምን እንደደረሰ እርግጠኛ አይደለሁም። ሁለቱን ብቻ ለመጥቀስ ሞከርኩት እንጂ የተወዳጁን የሥነ ጽሑፍ መምህራችንን የደራሲ ደበበ ሰይፉ እና የበርካታ ሌሎች የኪነ ጥበባትና በየሙያ ዘርፋቸው ለሀገራቸው ውለታ የዋሉ ዜጎች የመቃብር ሐውልት በምን ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ጥናት ስላልተደረገ በዝርዝር ለማቅረብ አዳጋች ይሆናል፡፡ ምናልባትም ከላይ የተጠቀሰው የዊሊያም ሼክስፒር ጠንክር ተብሎ የተቀረጸው የመቃብር ሐውልት ማሳሰቢያ ለእኛም ሀገር ይሠራ ከሆነ ደጋግመን ብንጠቅሰው ሳይበጅ የሚቀር አይመስለንም፡፡
“ለማፍረስ መጀገን፤ እንደ ብሔራዊ ኩራት”፤
የቅርብ ዘመናቱ የኢትዮጵያ የሥርዓተ መንግሥታት የሽግግር ታሪክ አብዛኛውን ጊዜ ሲፈጸም የኖረው ጭካኔ በሚስተዋልበት ግብታዊ እርምጃ ቅርሶችን በሚያወድምና በሚያፈርስ አብዮት እየታጀበ ነበር/ነውም፡፡ ይህንን ጥቅል ሃሳብ በስፋት እናብራራው ብንል ከብዙ ሁኔታዎች ጋር ስለሚያነካካን ከጀመርነው የሐውልቶች ጉዳይ ጋር ብቻ አዛምደን ማየቱ የተሻለ ይሆናል፡፡
የደርግ መንግሥት ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴን ከዙፋናቸው ገፍትሮ በጣላቸው ማግሥት ፈጥኖ የተረባረበው ከቻይና የተኮረጀውን “የባህል አብዮት” በማስፈጸም ነበር፡፡ ይህን መሰሉ ታሪክንና ቅርሶችን የማውደም እብሪትና እብደት በደርግ ዘመነ መንግሥት እንደምን ይተገበር እንደነበር በ1992 ዓ.ም “ኤሎሄና ሃሌሉያ” በሚል ርዕስ የተዘጋጀውን የዚህን ጸሐፊ መጽሐፍ አንብቦ መረዳት ይቻላል፡፡
ወታደራዊው ደርግ ለታሪካዊ ሐውልቶችና መታሰቢያዎች ከፍ ያለ ጥላቻ እንደነበረው ለማሳየት በርካታ ማስረጃዎችን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ለምሳሌ፡- በፓርላማው የፊት ለፊት ሕንጻ ላይ በጉልህ ይታዩ የነበሩትን በቅዱስ ጊዮርጊስ ስም ይጠሩ የነበሩ የሞዛይክ ሥዕሎችን ከቦታቸው አስወግዶ ታሪካዊውን ሕንጻ ሌጣ ያደረገው ሥልጣን በያዘ በጥቂት ወራት ውስጥ ነበር፡፡
በአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (ECA) ፊት ለፊት የነበረውን የአንበሳ ሐውልት አፍርሶ የሩሲያዊውን አብዮተኛ፣ የኮሚኒስት ፓርቲ መሥራችና የሶቪዬት ኅብረት ጠቅላይ ሚኒስትር የነበረውንና እ.ኤ.አ በ1924 ዓ.ም የሞተውን የቭላድሚር ሌኒንን ሐውልት በምትኩ በማቆምም የበቀል እርምጃ ውስዶ ነበር፡፡
ሐውልቱ ከነሐስ የተሰራና 20 ቶን ያህል ይመዝን ነበር፡፡ ምስሉ የተቀረጸው በኢትዮጵያዊያንና በኩባዊያን አርቲስቶች ነው እየተባለ ይወራ ነበር፡፡ ወጪውን የሸፈነው ደግሞ የሰሜን ኮሪያ መንግሥት መሆኑ በስፋት ተነግሯል፡፡ ሙሉውን ታሪክ የሚያውቁ ሰዎች ምስክርነት ቢሰጡ ይጠቅም ይመስለናል፡፡
ሌላው አሳፋሪ ታሪክ ሲኒማ አምፒር ፊት ለፊት በኢትዮጵያ ውስጥ በሚኖሩ ሕንዳዊያን የገንዘብ መዋጮ ቆሞ የነበረው ግዙፉ የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ሐውልት የፈረሰው ገና ወታደራዊው ጁንታ ዳዴ ማለት በጀመረበት በ1967 ዓ.ም የመጀመሪያ ወራት አካባቢ ነበር፡፡ በሐውልቱ ላይ የተቀረጸው ጽሑፍ እንዲህ ይነበብ ነበር፡- “በኢትዮጵያ የምንኖር የሕንድ ተወላጆች ሁሉ በሥራችንና በኑሯችን ደስ ስላለን ለግርማዊ ንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ 25ኛው የዘውድ በዓል ኢዮቤልዩ ይህን ሐውልት መታሰቢያ አቅርበናል፤ ጥቅምት 23 ቀን 1948 ዓ.ም”
ወታደራዊው መንግሥት የንጉሠ ነገሥቱን ሥርዓት የሚያስታውሱ ምንም ዓይነት ቅርሶች እንዳይኖሩ ማፈራረስ ብቻ ሳይሆን በምትካቸውም ሥርዓቱ እከተላለሁ የሚለውን የሶሻሊስት አይዲዮሎጂ በሚወክሉ የሌኒን፣ የኤንግልስና የማርክስ ሥዕሎችና ሐውልቶች ሀገሪቱን ከዳር እስከ ዳር ማጥለቅለቁን ዕድሜውን ያደለን ዜጎች ምስክሮች ነን፡፡
ሌላው ቀርቶ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ዋና መግቢያ አናት ላይ እጅግ የገዘፈ የማጭድና ሞዶሻ አርማ ተሰቅሎ እንደነበር የዚያን ዘመኑ ተማሪዎች ልንዘነጋው የምንችለው አይደለም፡፡ በግቢው ፊት ለፊት የቆመው የማርክስ ሐውልትም ዛሬም ድረስ ጺሙ እንደተንዠረገገ ተኮፍሶ እንዳለ ነው፡፡ በግቢው ውስጥ የነበሩ የንጉሡን ሥርዓት አስተዋሽ ምልክቶች በሙሉ እንዲጠፉ መደረጉንም ከአሁን ቀደም ባስነበብኳቸው ጽሑፎች ውስጥ መጠቃቀሴ አይዘነጋም፡፡
በደርግ መቃብር ላይ “ነገሥኩ” ይል በነበረው በኢህአዴግ መራሹ የአስተዳደር ዘመንም ሆን ተብለው የተፈጸሙ በርካታ የታሪካዊ ቅርሶች ውድመት ከትዝታችን ውስጥ ገና አልደበዘዙም፡፡ ጥቂት ወካይ ማሳያዎችን ለማመላከት እንሞክር፡፡
የደርግ መንግሥት “የጣዖት ያህል” ሲያመልከው የነበረው የሌኒን ሐውልት በአዲስ አበባ ሕዝብ ከመሰረቱ ተፈንቅሎ የተገረሰሰው ኢህአዴግ አዲስ አበባን ለመቆጣጠር ሦስት ቀን ሲቀረው ቅዳሜ ግንቦት 17 ቀን 1983 ዓ.ም ነበር፡፡ ድሮውንም ቢሆን የሕዝብ ይሁንታ ያገኘ ስላልነበረ ጊዜና ወቅት ሲፈቅድ የታላቁ ሌኒን ሐውልት በውርደት ተገርስሶ መጨፈሪያ ሊሆን ችሏል፡፡ ተገንድሶ የወደቀው ሐውልት ቀድሞ እሥራኤል ጋራዥ በመባል በሚታወቀው ግቢ ውስጥ ተጥሎ ነበር። ዛሬ እዚያው ቦታ መኖር ስላለመኖሩ በእርግጠኝነት መመስከር አይቻልም፡፡
በቀድሞ ስሙ ማይጨው አደባባይ ይባል የነበረውና ሀገሪቱ መከራ በወደቀባት የፋሽስት ወረራ ዓመታት የሜክሲኮ መንግሥት ያደረገውን ድጋፍ በማስታወስ ከፌዴራል ፖሊስ ዋና መሥሪያ ቤት ፊት ለፊት የሚገኘው አካባቢ “ሜክሲኮ አደባባይ” ተብሎ በመሰየም ባለ ሦስት አውታር የተቀራረቡ ግዙፍ ምልክቶችና ከአንገት በላይ የተቀረጸ የአንድ ወታደር ሐውልት ከአውታሮቹ ዝቅ ተደርጎ ቆሞ ነበር፡፡ እነዚህ የአደባባይ ምልክቶች ለአዲስ አበባ ቀላል ባቡር የመንገድ ግንባታ ሲባል በመፍረሳቸው ዛሬ የቀረው ቅርስ “ሜክሲኮ” የሚለው ስያሜው ብቻ ነው፡፡
የከተማ አስተዳደሩ ዳግም ሐውልቱን ለማቆም ማሰብ ያለማሰቡን በይፋ ቢገልጥ አንድም ሕዝብን ማክበር ነው፤ በሌላ ጎኑም መታሰቢያ የቆመለት ሀገር መንግሥትም “የሀገሬ መታሰቢያ ሐውልት” የት ደረሰ ብሎ ቢጠይቅ መልስ ስለማይኖረን ሰላማዊውን የዲፕሎማሲ ግንኙነት ያጠይም ይመስለናል፡፡
ሌላውና በሐረር ከተማ መሃል ቆሞ የነበረው የራስ መኮንን ሐውልት በደቦ ስለምን እንደፈረሰ የሚያስረዳን አስተዋይ ሰው ብናገኝ ለመማር ዝግጁዎች ነን፡፡ ያ ኤኩዌስትሪያን (ፈረስ ላይ የተቀመጠ ምስለ ሰው ቅርጽ) በመፍረሱ ምን ታሪካዊና ፖለቲካዊ ትርፍ ተገኘበት? ወደፊትስ ለትውልድ የሚያስተላልፈው ውርስ ምንድን ሊሆን ይችላል? ብለን ብንጠይቅ ለጊዜው የምናገኘው መልስ ሊያግባባን ስለማይችል ለጊዜ ጊዜ ሰጥቶ ማለፉ ይበጃል ባይ ነን፡፡
ለመሆኑ ታሪካዊ ይዘት ያላቸውን መታሰቢያዎችና ሐውልቶች በየሥርዓተ መንግሥታቱ እስከ መቼ እያወደምንና እየቀለጣጠምን እንኖራለን? ከአሁን ቀደም ደጋግሜ ለመጥቀስ እንደሞከርኩት “ከታሪክ መሰዊያ ላይ እሳቱን ከመጫር ይልቅ አመዱን እየዛቅን ለመደሰት የምንሞክረውስ እስከ መቼ ይሆን?”
ኢህአዴግ ደርግን እንደረገመና በየክልሉ ቂምና በቀል አስተዋሽ የሆኑ ሐውልቶችን ሲያቆምና ሲመርቅ ኖሮ የሥልጣን ዘመኑ ፀሐይ ስትጠልቅ በተራው በሰፈረው ቁና ተሰፍሮ ዘመነ መንግስቱ አብቅቷል፡፡ መቼ ይሆን ሰከን ብለን የሥርዓተ መንግሥት ሽግግር ባደረግን ቁጥር እኛ ባለሀገሮቹ ደስ ብሎን ዓለምም እያጨበጨበ የሚያመሰግነን? “ልብ ያለው ልብ ያድርግ!” አለ ይባላል፤ ክፉ ቀንን ለመሻገር ብሎ ሚስቱን ለባሪያ ፈንጋዮች ለመሸጥ ያስማማ የተረት ባል፡፡
ትውልድ ሆይ በወቅታዊ ጉዳዮች እየጋምንና እየጋልን ከምንወስዳቸው ክፉ ስሜታዊ ርምጃዎች ምራቃችንን ዋጥ አድርገን በትእግሥት ለማለፍ ጨክነን እንወስን፡፡ የየትኛውም ሀገር ታሪክ የተዋቀረው በብርሃናማ ደማቅ ኮከብ በሚመሰል ታሪክ ብቻ ሳይሆን ሀዘን ያጠላበትን ጀንበር በማለፍ ጭምር እንደሆነ ልብ ብለን እናስብ፡፡ ሰላም ለሀገራችን፤ ለዜጎችም በጎ ፈቃድ፡፡
(በጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን ሰኔ 28/2015