ኢትዮጵያውያን ከ99.9 በመቶ በላይ አማኞች ናቸው የሚል የጨረተ Clichy እውነት አለ። የክርስትና፣ የእስልምና፣ የይሁዲ ወይም የሌላ ዕምነት ተከታዮች ናቸው። ጥያቄው እኔን ጨምሮ ይሄን እምነታቸውን በተግባር ይኖሩታል የሚለው ነው። አዎ! አብዛኛዎቹ ዕምነታቸውን በሕይወታቸው ገልጠው ይኖራሉ። ቁጥሩ ቀላል የማይሆን አማኒ ግን ከዕምነቱ አስተምህሮና ቀኖና በተቃራኒው መቆሙ ፀሐይ የሞቀው የአደባባይ ሀቅ ከሆነ ውሎ አድሯል።
ቁጥራችን ቀላል ያልሆነ ይሄን እምነታችንን በሕይወታችን ስለማንኖረውና ስለማንገልጠው ዛሬም ሆነ ትናንት ሀገራችን ፈተና ላይ ወድቃለች። ልዩነት፣ ጥላቻና መጠራጠር መልካውን ተቆጣጥሮታል። ሀገራችንና ሕዝባችን እረፍት አጥተዋል። ይቅርታ ይደረግልኝና አሁን አሁን ከእኛ ይልቅ እንስሳት ሳይበልጡን ይቀራል። አዎ እኛማ ከሰውነት ተራ ወጥተን አውሬ ሆነናል ። ሃይማኖታችንና ዕምነታችን ወደ ሰውነት ተራ መመለስ ተስኗቸዋል ። ከራሳችንም ከአምላክም ተጣልተናል ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በዓላት በመጡ በሄዱ ቁጥር ከራሳችን ፣ ከአምላካችንና ከዕምነታችን ጋር ሰላምና ዕርቅ እንድናወርድ ያለ መታከት መልዕክት ያስተላልፋሉ። እኛ ግን አሻፈረኝ ያልን ይመስላል ። በዓላትን በነቂስ ወጥተን አክብረን ወደየቤታችን ስንመለስ ልዩነታችንን፣ ጥላቻችንንና መጠራጠራችንና አጠቃላይ ፖለቲካችን የቱ ጋ ነበር ያቆምነው ብለን እንደ እሪያ ወደ ትፋታችን እንመለሳለን ።
የጥላቻንና የልዩነትን ፍላጻ ወደ ሚያንበለብሉት ማህበራዊና መደበኛ ሚዲያዎች ጎራ እንቀላቀላለን። ውጊያውን እንመራለን። እስኪ በዚህ ድንግዝግዝ ሆነን ዓይናችንና ልቦናችን ቢከፈትልን ጮራ የሚፈነጥቀውንና የተለመደውን የጠቅላይ ሚኒስትሩን መልዕክት በጥሞና እንከታተል። ሃይማኖታችንንና ዕምነታችንን በአንድነት ወደሚገልጸው ባህላዊ ወረቶቻችን እንመለሳለን።
ሙስሊሞች የዒድ አል አድሃን በአንድነትና በፍቅር እንደሚያከብሩት ሁሉ ኢትዮጵያ ከምንም ነገር በላይ ዛሬ የምትፈልገው፣ መከባበርን እና መፋቀርን ነው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ መግለጻቸውንና ለ1444ኛው የዒድ አል አድሃ የእንኳን አደረሳችሁ የሚል መልዕክት ባለፈው ረቡዕ አስተላልፈዋል። የአረፋ ኮረብታ ከመላው ዓለም የተሰባሰቡ ሙስሊሞች የዒድ አል አድሃን በአንድነት ያከብራሉ። ዜግነታቸውና ማንነታቸው የተለያየ ቢሆንም፣ ሁሉም የሚያስቡት ሙስሊም መሆናቸውን ብቻ ነው። የተለያዩበትን ረስተው የተገናኙበትን፣ የተሳሰሩበትን እያሰቡ ፣ አንድ ይሆናሉ ።
እኛም ለምንለያይበት ሳይሆን ለምንገናኝበት፣ ለምንገፋፋበት ሳይሆን ለምንሳሳብበት፣ ለምንሻኮትበት ሳይሆን ለምንተባበርበት ቅድሚያ ሰጥተን፣ አንድ ትልቅ ሕዝብ እንሁን ። ከልዩ ልዩ ቦታ ብንመጣም፣ ልዩ ልዩ ማንነት ቢኖረንም፣ የተለያየ ቋንቋ ብንናገርም፣ የተለያየ ሃይማኖት ብንከተልም፣ ኢትዮጵያ ሲባል አንድ እንሁን ብለዋል ። ይህ መንደር ይህ ሠፈር የእኔ ነው ማለትን ትተን፣ ኢትዮጵያ የእኛ ናት የምንል ዜጎች እንድንሆን አደራ እላለሁ ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ሁሉንም አካባቢ ለሁላችንም እንዲበቃ አድርገን ልናለማው፣ ልናበለጽገው እንችላለን።
ከነካነው ያልነካነው ሀብታችን ይበልጣል፤ ከሠራነው ያልሠራነው ይበዛል ብለዋል። ልጆቿ ተደማምጠው እና ተከባብረው፣ በሰላም እና በፍቅር የሚኖሩባትን ሀገር፣ በጋራ እንድንገነባ ሙስሊሞችን ብቻ ሳይሆን፣ የሁሉንም እምነት ተከታዮች በአክብሮት የሚጠይቁ መሆኑን አመልክተው፤ ኢትዮጵያ ከምንም ነገር በላይ ዛሬ የምትፈልገው፣ መከባበርን እና መፋቀርን መሆኑን አስገንዝበዋል። ልብ ማለት በጀ ማለት ተሳነን እንጂ።
ከገባንበት ሁለንተናዊ ቀውስ ለማገገምም ሆነ በሀገራችን ዘላቂ ሰላምና አንድነት ለማረጋገጥ የጣልናቸውንና የረሳናቸውን ዕምነቶች ፣ ሃይማኖቶች ባህላዊ ወረቶች እንዲያንሰራሩና መልሰው እንዲያቆጠቁጡ ሌት ተቀን መሥራት ይጠበቅብናል። ጎን ለጎን መንግሥት ልዩነትንና ጥላቻን የሚጎነቁሉ መዋቅሮችን ፣ ተቋሞችንና አስተሳሰቦችን ከስር ከስር የማስወገድ ኃላፊነት አለበት። በየባዕላቱ የሚገልጽልንን መሻትና ምኞት ይበልጥ በተግባር ሊያሳየን ይገባል ።
ይህን ማድረግ ካልቻልን ከገባንበት ፈተና መውጣት አይቻልም ። ለመሆኑ ለሀገራችንና ለተቋማት ሰራ አካላት ጤንነት የልብ ትርታ የሆነው ባህላዊ ወረት ምንድን ነው፤ ከዚያ በፊት ባህል ፣ ባህላዊ ወረትስ ምንድን ነው የሚለውን ለመግባቢያ ያህል እንመለከታለን ። ባህል ሁሉንም የሚያስማማ የሚያግባባ ወጥ የሆነ ትርጉም ብያኔ ባይኖረውም የአንድ ማኅበረሰብ ወይም ሕዝብ ዕምነት፣ ልማድ ፣ ወግ በኪነ ጥበብ እና በሥነ ጥበብ ተዳውሮ ፣ ተሸምኖ ፣ ተንሰላስሎ የመገኘት ፣ የመገለጥ ዥጉርጉር ሕብራዊ ቀለም ነው።
በደስታ ፣ በኀዘን ፣ በሥራ ፣ በሃይማኖት ፣ በትምህርት፣ ወዘተ . የሕይወት አንጓዎች ይገለጻል። በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ቋንቋዎች ጥናትና ምርምር ማዕከል የተዘጋጀው የአማርኛ መዝገበ ቃላት ባህልን ፦ የኅብረተሰብ የአኗኗር ዘዴ ፣ ወግ ፣ ልማድ፣ እምነት ፣ …። በማለት ሲተረጉመው። የደስታ ተክለ ወልድ የአማርኛ መዝገበ ቃላት በበኩሉ ባህል ፦ ልማድ ፣ ደንብ ሲል ይፈታዋል ።
ባህላዊ ወረት ( cultural capital ) የሚለው ሀረግ ፔሬ ቦርዴው በተባለ በ20ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ማብቂያ ላይ የተነሳ የሥነ ኅብረተሰብ ተመራማሪ እንደተፈጠረ የተለያዩ የዘርፉ ድርሳናት ያትታሉ ። ባህላዊ ንብረት በማኅበረሰብ ውስጥ ያለን ተቀባይነት ቦታ ከፍ ለማድረግ ዕውቀትን፣ ፀባይና ክህሎትን የማሳደግ የማካበት ሂደት ነው ። ባህላዊ ንብረት በግለሰብ ፣ በማኅበረሰብ ከፍ ሲልም በሕዝብ በሀገር ይሰላል ።
የበለፀገ ባህላዊ ንብረት ያካበተ ግለሰብ በማኅበረሰቡ ዘንድ ያለውን ተቀባይነት ከፍ እንደሚያደርገው ሁሉ ያደገ የለማ ባህላዊ ንብረት ያለው ማኅበረሰብ ሕዝብ በተመሳሳይ ሁኔታ ከፍ ያለ ተቀባይነት ይኖረዋል። ባህል ማለትም የኅብረተሰብ የአኗኗር ዘዴ ፣ ወግ ፣ ልማድ ፣ እምነት ፣ ወዘተ . በሂደት በዕውቀትና በክህሎት እየበለፀገ፣ እየዳበረ ሲሄድ ለሀገር ሰላም ፣ አንድነት ከፍ ሲልም እድገት የላቀ አስተዋጽኦ ይኖረዋል ።
በተቃራኒው ባህል በዕውቀት ፣ በክህሎት ካልበለፀገ አይደለም ለሀገር ሰላምና ዕድገት መዋል ይቅርና የማኅበረሰቡን እሴቶች ጠብቆ ማቆየት ካለማስቻሉ ባሻገር የዕለት ተዕለት ችግሮችን እንኳ መፍታት የሚሳነው ይሆናል። ባህላዊ ወረት እንደ ኢኮኖሚያዊ ወረት ማለትም ገንዘብ በአግባቡ ኢንቨስት ተደርጎ ሰላምን ፣ ፍቅርን፣ እርቅን ፣ መነጋገርን ፣ መቀባበልን ፣ መከባበርን ፣ መተባበርን፣ አንድነትን ፣ ወዘተ . እውን ማድረግ ካልቻለ እንደባከነ እንደከሰረ ሊቆጠር ይችላል ።
ሀገርን ሕዝብን ከግጭት ፣ ከቀውስ ፣ ከመፈናቀል፣ ከመጠራጠር ፣ ከጥላቻ ፣ ከበቀል ፣ ወዘተ . መታደግ አልቻለማ። እስኪ ለአንድ አፍታ ባህሎቻችንን እምነቶቻችንን ወይም ባህላዊ ወረቶቻችንን ከዚህ አኳይ እንመዝናቸው ። ባክነዋል ወይስ በአግባቡ ሥራ ላይ ውለዋል ! ? አሁን ከምንገኝበት ሀገራዊ ቁመና አንጻር ባክነዋል ቢባል የሚያስኬድ ይሆናል። ታዲያ እነዚህን ባህላዊ ወረቶቻችንን እንደ ጦር ዕቃ ለብሶ እንደ ጥሩር ደፍቶ መውጣት መግባት ፣ መመላለስ ለምን ተሳነን ! ? መልሱ ቀላል ነው ።
ላይ ላዩን እንከውናቸዋለን እንጂ አንኖራቸውም። በቃል እናነበንባቸዋለን እንጂ በልባችን አላተምናቸውም። ባልንጀራህን፣ ጎረቤትህን እንደ ራስህ ውደድ የሚሉ አብርሀማዊ እምነቶችን ማለትም ክርስትናን ፣ እስልምናንና አይሁድን እየተከተልን እንዴት በጥል ግድግዳ ተለያየን ! ? በአንድ አምላክ በዋቄ ፈና እያመን ኢ ሬቻን በየአመቱ እያከበርን እየከወን ይቅር መባባል ለምን ተሳነን !? መልሱን ለማግኘት ምስጢሩን ለማወቅ ሞራ ማስገለጥ ወይም ኮከብ ማስቆጠር አያሻም ።
መልሱ ቀላል ነው ። እሱም ባህላዊ ወረቶቻችንን በካዝና ቆልፈን አስቀመጥን እንጂ ሥራ ላይ ስላላዋልናቸው ( ኢንቨስት ) ስላላደረግናቸው ነው። የሰላም ስምምነቱን ሆነ ሀገራዊ ሰላምና አንድነት በዘላቂነት እውን ለማድረግ የተቆለፈባቸውን ባህላዊ ንብረቶች ከካዘና አውጥቶ በእያንዳንዱ ዜጋ ላይ በፍጥነት ማፍሰስ ኢንቨስት ማድረግ ይጠይቃል ።
በኢኮኖሚክስ አስተምህሮ ባህል ከተፈጥሮ ፣ ከሰውና ከአካላዊ ፣ ቁስ አካላዊ ( physical ) ቀጥሎ 4ኛው ንብረት ሆኖ መጠናት ፣ መተንተን ከጀመረ ከራርሟል ። በአግባቡ ጥቅም ላይ ከዋለ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ለሀገር ዕድገትና ለዘላቂ ሰላም አስተዋጽኦ ያበረክታል ። ሰላም በሌለበት ኢኮኖሚያዊ ዕድገትም ሆነ ብልፅግና ሊታሰብ አይችልምና ።
ለሀገር ግንባታ በአዎንታዊም ሆነ በአሉታዊ ወሳኝ ሚና ከሚጫወተው ፖለቲካዊና አስተዳደራዊ ሥርዓት በተጨማሪ ለዘመናት እንደ ሕዝብ ፣ እንደሀገር አጋምዶ ያቆየን ባህላዊ ወረታችን ነው ። ሁነቱን ፣ ክዋኔውን ፣ መንፈሱን ጠብቆ ተንከባክቦና አልምቶ ከትውልድ ወደ ትውልድ ማስተላለፍ ፣ ማስቀጠል ፣ ማክበርና ማስተዋወቅ ትልቅ ኃላፊነትም አደራም ነው። ሆኖም የመጨረሻ ግብ ሆኖ ግን ሊወሰድ አይገባም ። ቱባነቱን እንደጠበቀ ማደግ ዘመንና ትውልድ መዋጀት ይጠበቅበታል ።
አዎ ! የትውልዱንና የዘመኑን ህፀፅ የሚያርም ለምፅ የሚያነጻ ፣ የሚዋጅ መሆን አለበት። ዘረኝነትን፣ ጥላቻን ፣ ቂም በቀልን ፣ ደባን ፣ መከፋፈልን ፣ ወዘተ. መቤዥ ፣ መዋጀት አለበት። ባህላዊ ወረታችንን ይበልጥ በማጎልበት፣ በማልማትና በማስፋት ለመጻኢ እድላችን ፣ ለነገ ተስፋችን፣ ለእርቅ ፣ ለሰላም፣ ለአንድነት ፣ ለሁለንተናዊ ብልፅግና ፣ ወዘተ. ልናውለው ይገባል። ስኬቶቻችንን የምናወድስበት፣ ፈተናዎቻችንን የምንሻገርበት ነገአችንን የምንተልምበት ጭምር አድርጎ ስለመጠቀም አብክረን ማሰብ ያስፈልጋል ።
የፍቅር ፣ የእርቅ ፣ የሰላም ፣ የአብሮነት ፣ የማካፈል ፣ የመተባበር ፣ የመተጋገዝ ፣ የመረዳዳት፣ የምስጋና ፣ ወዘተ. ባህሎች፣ ልማዶች ፣ ዕምነቶች፣ ሃይማኖቶች ከፍ ሲልም ድምር ባህላዊ ወረቶች ባለቤት እንዲሁም የጥንታዊት ሀገር ባለቤት ሆነን አንድነትን በመከፋፈል ከሰዋን ፣ ፍቅር ከጎደለን ፣ እርቅ ከገፋን ፣ ሰላም ከራቀን ፣ አብሮነትን በቀዬአዊት ከተካን ፣ ማካፈልን በስስት ከቀየርን፣ መተባበርን በመለያየት ከለወጥን ፣ ምስጋናን በእርግማን ከተካን፣ ወዘተ . ምኑን ሙሉኡ ሆነው !? ባለፉት አራትና አምስት አመታት ያለፍንባቸው ሀገራዊ ውጣ ውረዶች ፣ አሳፋሪ ድርጊቶች እውነት የእነዚህ ሁሉ መንፈሳዊና ባህላዊ ፀጋዎች ባለቤት ስለመሆናችን የሚመሰክሩ ናቸው ።
እስኪ ሌሎችን አቆይተን ከአዲሱ አመት ወዲህ እንዲሁም ወደፊት በተለያዩ የሀገራችን ክፍሎች የሚከበሩ መንፈሳዊና ባህላዊ ሁነቶች የተሸከሙትን ግዙፍ መልዕክቶችና አንድምታዎች አለፍ አለፍ ብለን እየተመልከትን ሒሳብ እናወራርድ ። ፍቼ ጨምበለላ፣ ቡሔ ፣ ሻደይ ፣ አሸንዳ ፣ ሶለል አይነ ዋሬ ፣ እንቁጣጣሽ ፣ መስቀል ፣ መስቀላዮ ፣ አጋመ ፣ ጊፋታ፣ ኢ ሬቻን ፣ ጋሮ ፣ ቺሜሪ ፣ ወዘተ . በአንድም በሌላ በኩል በተለያዩ የሀገራችን ማህበረሰቦች የሚከበሩ ሃይማኖታዊ ወይም ባህላዊ ክዋኔዎች ናቸው ።
ሁሉም ማለት ይቻላል ተስፋን ፣ ፍቅርን ፣ ነፃነትን፣ አብሮነትን ፣ ምስጋናን ፣ እርቅን ፣ ይቅርታን ፣ ወዘተ . የሚያውጁ ፣ የሚለፍፉ ናቸው ። ግን በነቂስ ወጥተን ለዘመናት በየአመቱ በአደባባይ የምናከብራቸው የምንዘክራቸውን ያህል በዕለት ተዕለት ኑሮአችን አንኖራቸውም ። አንለማመዳቸውም ።
ይሁንና ከገጠሙን ቀውሶች ፣ ፈተናዎች መውጣት ማገገምና ማንሰራራት የቻልነው በቀሩን ሽርፍራፌ እንጥፍጣፌ በባህላዊ ንብረቶቻችን መሆኑን ልብ ይሏል ። በተለይ ባለፉት 30 አመታት ቀን ከሌት እንደ ተሰበከው ልዩነት ፣ ጥላቻና ዘርኝነት ቢሆን ኑሮ እርስ በእርስ ተበላልተናል ። ተጨራርሰናል ። ለዚህ ነው መዳኛችን፣ ማገገሚያችንና ማንሰራሪያችን የሆነውን ባህላዊ ወረት ወደሙላቱ መመለስ ለነገ የሚባል ጉዳይ የማይሆነው ።
ባህላዊ ንብረታችን ለበጎ አላማ ሲውል ሀገርን ከጥፋት ከእልቂት እሳት እንደሚታደግ በጋሞ ሀገር ሽማግሌዎች ተመልክተናል ። የጋሞ የሀገር ሽማግሌዎች እሳት ጎርሶ እሳት ለብሶ ለበቀል ተነስቶ የነበረውን የአርባ ምንጭና የአካባቢውን ወጣት ለምለም ሳር ይዘው ተንበርክከው በመለመን ቁጣውን አብርደው መልሰውታል ። ይህን የሀገር ሽማግሌዎች ገድል በጥሞና ለተረዳው የአርባ ምንጩን እሳት ብቻ አይደለም ያጠፉት የአርባ ምንጩን ጥፋት ተከትሎ በመላ ሀገሪቱ ሊዛመት የነበረውን የበቀል ሰደድ እሳት ጭምር እንጂ ። ቁጣ አብራጁ ይህ የጋሞ አባቶች ልመና ( ጋሞ ወጋ ) እየጠፋ ፣ ትኩረት እየተነፈገው ያለው ባህላዊ ንብረታችን ተጠብቆ ለትውልድ ሲተላለፍ ሀገርን እንዴት ማዳን እንደሚችል ጥሩ ማሳያ ነው ።
የጋሞ አባቶች የ2011 ዓ.ም ልዩ የበጎ ሰው ተሸላሚ መሆናቸው በሁሉም ኢትዮጵያዊ ዘንድ ያለ አንዳንች ልዩነት ዳር እስከዳር አድናቆትን ተቀባይነትን ያተረፈው በዚህ እሳቤ ነው ። ሰላምን ፣ ፍቅርን፣ ይቅርታን ለማነፅ ፣ ለመገንባት ከምንሰጠው ትኩረት ባልተናነሰ በየአካባቢው እንደ ጋሞ ወጋ ዓይነት የሽምግልና ፣ የእርቅ ባህላዊ ካፒታሎቻችንን ላይም መሥራት ይጠበቅብናል ። ከዚህ መሳ ለመሳ የአክራሪነት አዝማሚያ ፣ እኩይ አስተሳሰብ እንዲገታ ብሎም ተሸንፎ ከሰላምና ከእርቅ መንገድ ገለል፣ ዘወር እንዲል ድልብ የሆኑ ባህላዊ ወረቶቻችን ጥንስስ ፣ እርሾ የማይተካ ሚና አላቸው ። ሁሉም ኢትዮጵያውያን የተለያዩ ባህላዊ ንብረቶች ባለፀጋ ስለሆኑ የየራሳቸውን መዋጮ ማበርከትና ወደ ሥራ መግባት ይጠበቅባቸዋል።
በየአካባቢያችን፣ በየቀዬአችን የምናንፀው፣ የምናቀነቅነው ከባቢያዊ ብሔርተኝነት ወደ አክራሪነት፣ ፅንፈኝነት የሚያንደረድር ወደገደል አፋፍ የሚገፋ ስለሆነ እነዚህን ባህላዊ ወረቶች በመጠቀም መግታት ያስፈልጋል። የዜጎች ማንነት እሴት እንደተከበረ ወደ ኢትዮጵያዊ ብሔርተኝነት የሚያደርሰንን ቀና መንገድ በቅንነት መቀላቀል ፣ መያያዝ ይገባል ።
ሻሎም ! አሜን ።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)
አዲስ ዘመን ሰኔ 27/2015