የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ፈታኝ ቅድመ ዝግጅቶችን አጠናቆ ሀገራዊ ምክክሩን ለማስጀመር ከጫፍ ስለደረሰ አንዳንድ ነጥቦችን ማነሳሳት ወደድሁ። ሀገራዊ ምክክር የተለያዩ አንጃዎችንና አማጽያንን ወይም በማህበረሰቡ ውስጥ ተቃቅረው ወይም ተከፋፍለው የነበሩን የማነጋገርና የማቀራረብ ሒደት ነው። ያሉብንን ኅልቆ መሳፍርት የሌላቸውን ችግሮች ሁሉ በአንድ ጀምበር የሚፈታ ግን አይደለም። አቀራርቦ የሚያነጋግርና ወደ ጋራ ዘላቂ መፍትሔ የሚያመራ እንጂ።
ይህ እንዲሆን ደግሞ የሁላችንን ቅንና ንጹሕ ልቦና የሚሻ ተሳትፎና የባለቤትነት መንፈስ ይጠይቃል። ከጸሐይ በታች ያሉብንን ችግሮች ሁሉ ይፈታል ብሎ መነሁለልና መጃጃልም አያሻም። ሒደቱ የሚሳካው በሰጠነውና በተቀበልነው ልክ ነው። ለዚህ ልብን ከፍቶ መጠበቅ ይጠይቃል። ጥበቃችን our expectation በልክ ሊሆን ይገባል። ሀገራዊ ምክክር ፖለቲካዊና ማህበራዊ ግጭቶችን ተቀራርቦና ተመካክሮ በመፍታት መረጋጋትንና አንድነትን የሚፈጥር ነው። የዚህ ታላቅ ግብ ስኬትም ሆነ ውድቀት በሁላችንም መዳፍ ስር ነው። ይሄን ታሪካዊ ዕድል ሳናባክን በማስተዋልና በጥበብ በመጠቀም ከታሪክና ከትውልድ ተጠያቂነት ለመዳን ዝግጁ መሆን አለብን።
ሀገራዊ ምክክር በተለያየ ቅርጽና ይዘት ጥቅም ላይ እየዋለ ክፍለ ዘመናትን እንዳሳለፈ በዘርፉ የተሰነዱ ድርሳናት ያትታሉ። በቅርብ አመታት ደግሞ የደቡብ አፍሪካ፣ የሩዋንዳ፣ የሰሜን አየርላንድ፣ የጀርመንና የካናዳ ሀገራዊ ምክክሮች በአብነት ይነሳሉ። የየሀገራቱ ሀገራዊ ምክክሮች እንደየነባራዊ ሁኔታቸው የተለያየ ቢሆንም መዳረሻ ግባቸው ግን ተመሳሳይ ነው። የሁሉም ግብ ይቅር መባባል፣ ተበዳይ ከደረሰበት ጉዳት እንዲያገግምና በመጨረሻም እንዲፈወስ ማገዝ፤ ሀገራዊ መግባባትና አንድነት መፍጠር ነው። ይህ እውን እንዲሆን ምክክሩ ላለፉ በደሎች እውቅና መስጠት፣ ተጠያቂነትን ማስፈን፣ ቁስሎች እንዲያጠግጉ፣ እንባዎች እንዲታበሱና በመጨረሻም ዘላቂና የማይቀለበስ ወይም መልሶ የማያገረሽ ልባዊ ይቅር መባባልን መተግበርን ይጠይቃል። በሀገራዊ ምክክሩ ተሳታፊዎች ዘንድም ቀጣይነት ያለው ቁርጠኝነትና የሕዝቡ የማይነጥፍ ድጋፍ ሒደቱን ለማጽናት ያግዛል።
ሀገራዊ ምክክር ውስብስብና ፈታኝ ሒደት ስለሆነ፤ ነገሮች ሁሉ አልጋ በአልጋ ይሆናሉ ተብሎ አይጠበቁም። ስር የሰደደ ልዩነት የመጀመሪያው ተግዳሮት ነው። በሀገራችን ቢያንስ ለግማሽ ክፍለ ዘመን ያህል ተቋማዊና መዋቅራዊ ሆኖ የተዘራው ልዩነትና ጥላቻ በጎሳ፣ በሃይማኖትና በፖለቲካዊ አስተሳሰቦች ላይ ምሽግ የያዘው ልዩነት ቀዳሚው ፈተና ነው። ሁለተኛው ተግዳሮት ደግሞ የፖለቲካዊ ፈቃደኝነት ማነስ ነው። ሀገራዊ ምክክር እንዲሳካ የፖለቲካ መሪዎች ቁርጠኝነትና ድጋፍ የማይተካ ሚና አለው። የፖለቲካ መሪዎች ለሒደቱ በቅንነት ጊዜያቸውን፣ እውቀታቸውንና ልባቸውን ያለስስት ካላፈሰሱ ሀገራዊ ምክክሩ ሊሳካ አይችልምና የፖለቲካ መሪዎች አበክረው ለዚህ ሊዘጋጁ ይገባል።
ሶስተኛው ተግዳሮት ሕዝብ ሀገራዊ ምክክሩን ባይቀበለውና ቢቃወመው የሚል ነው። ከዚህ አንጻር ኢትዮጵያውያን ችግር እንደሌለባቸው አፍን ሞልቶ መናገር ይቻላል። እኔን ጨምሮ የብዙዎቻችን ችግር ካለንበት ተጨባጭ ሁኔታ አንጻር ምክክሩ ቶሎ እንዲካሄድ ከመጓጓትና ከምክክሩ ብዙ የመጠበቅ አባዜ እንጂ ተቃውሞ የለንም። አራተኛው ተግዳሮት ደግሞ የሀብት ውስንነት ነው። ሀገራዊ ምክክር እጅግ ውድ ሒደት ነው። ያለ በቂ ሀብት ሊሳካ አይችልም። ስለሆነም በቂ ሀብት ስለመያዙ እርግጠኛ መሆን ያሻል። አምስተኛውና ከሀገራችን ተጨባጭ ሁኔታ አንጻር ፈታኙ ተግዳሮት ብጥብጥ፣ ሁከትና ግጭት ሙሉ በሙሉ ሳይወገድ ወደ ሀገራዊ ምክክር መግባታችን ነው። ይህ ባልተፈታበት መተማመንንም ሆነ መግባባትን ማሳካት አዳጋች ስለሆነ በዚህ ረገድ መንግስት ኃላፊነቱን ሊወጣ ይገባል።
ብጥብጦችንና ግጭቶችን ነገ ዛሬ ሳይል በማስወገድ ለሀገራዊ ምክክሩ ምቹ መደላድል ሊፈጥር ይገባል። ስድስተኛውና የመጨረሻው ፈተና ታሪካዊ ቁርሾቻችን ናቸው። እነሱ ላይ እየቆዘምንና እየተብሰከሰክን ሀቀኛ ሀገራዊ ምክክርን ማረጋገጥ ስለማንችል ከታሪክ እስረኝነት ክፉ አባዜ ራሳችንን ነጻ አድርገን መዘጋጀት አለብን። እነዚህን ተግዳሮቶች ተሻግሮ በስስትና በጉጉት የምንጠብቀውን ሀገራዊ ምክክር ለማሳካት የሁላችንን ቀጣይነት ያለው ቁርጠኝነትና ያላለሰለሰ ጥረት ይሻል። ከዚህ በተጨማሪ የሀገራችንን ነባራዊ ሁኔታ ከግምት ያስገባ ፈጠራዊ እይታና አዳዲስ ስትራቴጂዎችን ስራ ላይ ስለማዋል ማንሰላሰልም ያስፈልጋል።
ስለ እውነተኛ እርቅ በተወሳ ቁጥር ከልዑል ፈጣሪ ለጥቆ መቼም ወደ አይነ ፣ እዝነ ህሊናችን ግዙፍ ነስቶ የሚመጣው ፣ በግርማ ጮሆ የሚሰማን ኔልሰን ማንዴላ /ማዲባ/ ነው፡፡ የአፍሪካ ናሽናል ኮንግረስ፣ ደቡብ አፍሪካ ፣ አፓርታይድ ፣ ኤፍ ደብሊው ዴክለርክ ፣ …፤ ከዚያ ይከተላሉ ፡፡ ስለ እርቅ ሲነሳ ማዲባ አብሮ ስሙ ይወሳል፡፡ ማዲባ ሲወሳ እርቅ አብሮ ይነሳል፡፡ የእርቅ ምልክት ነው፡፡ በገዘፈው ሰብዕናው ገልጦ በተግባር አሳይቶናል፡፡ ኑሮታል። መስክሮታል፡፡ እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ1998 የእውነትና እርቅ ኮሚሽን ያጠናቀረውን ሪፖርት ማዲባ ከሊቀ መንበሩ ቀሲስ ዴዝሞንድ ቱቱ ከተረከበ በኋላ ባስተላለፈው መልዕክት፤
“በሕገ መንግስታችን የተደነገገውን ዴሞክራሲና ሰብዓዊነት ለመጠበቅ እርቅ ያስፈልገናል፡፡” ብሎ ነበር፡፡ አዎ ! ተቀራርቦ መነጋገር፣ እርቅና መግባባት ከሌለ ሰላም ሊሰፍን አይችልም፡፡ ሰላም ከሌለ አይደለም ሰብዓዊነት፣ ዴሞክራሲ፤ የሀገር ህልውና ላይ አደጋ መደቀኑ አይቀርም፡፡ እንደኛ በውጥረት፣ ውሉ በጠፋ ትብታብ እና ፅንፍ በረገጠ አቋም ላይ ለምትገኝና ለምትጠራወዝ ሀገር ተቀራርቦ መነጋገር፣ መግባባትና መታረቅ የግድ ነው፡፡ ሀገራችንን ትናንትም ሆነ ዛሬ ቁም ስቅሏን እያሳያት ያለው በፖለቲካዊ ልሒቁና በጭፍራው የሚጎነቆለው ልዩነትና ጥላቻ ከፍ ሲልም ዋልታ ረገጥነትና የፈጠራ ትርክት ነውና ፖለቲካዊ ዕርቅ በብርቱ ያሻናል።
ለመሆኑ ፖለቲካዊ እርቅ Political Reconciliation ሲባል ምን ማለት ነው ?
ኮሊን መርፊ “ THE FORGIVENESS MODEL OF RECONCILIATION “ በሚል ርዕስ ለንባብ ባበቃው ጹሑፉ ፤ “ፖለቲካዊ እርቅን የተሰበረ ግንኙነት የመጠገን ሂደት ነው፡፡ “ በታሪክ ምርኮኝነት፣ ሆን ተብሎ ለፖለቲካዊ ጥቅም ሲባል በተነዛ የፈጠራ ትርክት ፣ በማንነት ላይ በተዋቀረው ፖለቲካ፣ በግራ ዘመም አይዶሎጂ እና በሕዝበኝነት populism በተካረረ ልዩነት፣ ቁጭት መፍጠር እንደማታገያ ስልት በመወሰዱ፣ በሴራ ኀልዮት በተጎነቆለ ጥላቻ፣ ስልጣን ላይ ለመቆየት ሲባል በሕዝቦች መካከል በተዘራ ልዩነት፣ አንድን ሕዝብና ሃይማኖት በመለየት እንደጠላት መፈረጅ እና በሌሎች ገፊ ምክንያቶች የተነሳ በፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል ያለው ግንኙነት እጅግ ሻክሯል፡፡ በዚህ የተነሳ የአንዳንድ ፓርቲዎች አመራሮች አይደለም ቁጭ ብሎ ለመነጋገር አይን ለአይን እንኳ ለመተያየት ፍቃደኞች አይደሉም፡፡
ኮሊን ፖለቲካዊ እርቅ ሶስት ንጣፎች ወይም ንብርብር layers እንዳሉት ያትታል፡፡ የላይኛው የፖለቲካ ፓርቲዎች ግንኙነት እንዲበላሽ ያደረጉ መግፍኤዎችን መለየት፤ እነዚህን ምክንያቶች ከፍ ብዬ ለማሳየት የሞከርሁ ሲሆን የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ ግን ይበልጥ ዘርዝሮ ሊተነትናቸው ይችላል፡፡ መካከለኛው በፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል ከሚፈጠር እርቅ የሚጠበቀውን ግብ ለይቶ ማስቀመጥ ነው፡፡ የተቀመጠው ግብ ውስን ሊሆን ይገባል፡፡ በፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል ያሉ ልዩነቶችን ከማባባስ መቆጠብ ሊሆን ይችላል፡፡ እንደ ብሔራዊ እርቅ ያሉ ጉዳዮች ግን ከፓርቲዎች አልፈው ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ የሚያተኩሩና ተዋናዮቹም በርካታ ስለሆኑ በዚህ የእርቅ ሒደት የሚካተቱ አይደሉም፡፡ የታችኛው ንጣፍ እርቁ የሚሳካበትን ስልት መንደፍ ነው፡፡
ከፍ ሲል የተነሱትን ሁለቱ የፖለቲካዊ እርቅ ንጣፎችን በጥንቃቄ መተግበር የእርቅ ሂደቱን ውጤታማ ያደርገዋል ተብሎ ይታመናል፡፡ ኮሊን መርፊ በማስከተል፤ “ፖለቲካዊ እርቅ የሕግ የበላይነትን በስምምነት በጋራ የማረጋገጥ እንጂ ይቅር የመባባል ጉዳይ ብቻ ተደርጎ መወሰድ የለበትም፡፡ በእርቅ ሂደቱ ምንም አይነት ቅድመ ሁኔታ መቀመጥ የለበትም፡፡ …” የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ በፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል ሊያካሂደው ያቀደውን እርቅ ከምንም አይነት ቅድመ ሁኔታ ጋር ሊያያይዘው አይገባም፡፡
ሁላችንም ልብ እንደምንለው የዴስቲኒ ኢትዮጵያ አባላት የሄዱበት መንገድ ለዚህ ጥሩ አብነት ነው፡፡ ሆኖም ስለ ሰላምና ስለ ይቅርታ መነጋገር የራሱ የሆነ ሂደትና ቅደም ተከተል እንዳለው አበክሮ ማጤን ያሻል፡፡ እዚህ ላይ የሰላም፣ የእርቅ፣ የሽምግልና ዓለማቀፍ ረቡኒው እና በአሜሪካ በሀሪሰንበርግ በሚገኘው ኢስተርን መኖናይት ዩኒቨርሲቲ የዓለማቀፍ ግልግልና ዕርቅ ፕሮፌሰር የሆኑት፤ ሕዝቅያስ አሰፋ፤ “የሰላምና እርቅ ትርጉምና መንገዶች፤ “በሚለው መጽሐፋቸው፤ ያነሷቸውን ቁም ነገሮች፤ ሰላም፣ ዕርቅ የራሱ መንገድ እና አካሄድ እንዳለው ያሳያሉ፡፡
“…ሰላም ለግጭቶች መነሻ የሆኑትን ልዩነቶች በሚገባ ከለየና ከመረመረ በኋላ ልዩነቶችን ለፈጠሩት ችግሮች ሁሉን ወገኖች የሚበጁ መፍትሔዎች መፈለግ ማለት ነው፡፡ …፤ “ ገፅ 26 – 33 ፤ ሲሉ ሰላምን ይበይኑታል፡፡ ሰላም ግጭትን ማስወገድ አይደለም፡፡ በኢህአዴግ እንደሆነው በደህንነት፣ በፀጥታ ኃይሉና በካንጋሮ ፍርድ ቤቶች ግጭትን ማስወገድ ይቻል ይሆናል እውነተኛውን ሰላም ግን አያረጋግጥም፡፡ የአስቸኳይ ጊዜ አውጆ ግጭትን ተቃውሞን ፀጥ ለጥ ማረግ ይቻል ይሆናል ዘላቂ ሰላምን ግን ማስፈን አይቻልም፡፡ ለዚህ ነው ፕሮፌሰር ሰላም ለግጭቶች መነሻ የሆኑትን መርምሮ ለሁሉም ወገኖች የሚበጅ መፍትሔ መፈለግ ነው ያሉት፡፡ አሁን በሀገራችን የሚከሰቱ ግጭቶች ከዚህ አንጻር ማየትን ይጠይቃል፡፡ ፕሮፌሰር ከላይ በጠቀስሁት መጽሐፋቸው የሰላም ስራ የራሱ እሴቶችና መርሆዎች እንዳሉት ያመላክታሉ፡፡
ሀ . መሰረታዊ የግጭት መንስኤዎችን መርምሮ የአመለካከት አድማስን ማስፋት፤
ለ . ፍትሕ፦ ዘላቂ ሰላም ያለፍትሕ ሊገኝ አይችልም፡፡ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካው ፍትሕ ባልተረጋገጠበት ሰላምን ማምጣት አይቻልም፡፡ ለዚህ ነው የለውጥ ኃይሉ ተቋማት ላይ እየሰራ ያለው፡፡
ሐ . መግባባት፦ ፕሮፌሰር መግባባትን ሲበይኑት፤ አንዱ ሌላው ውስጥ ሲገባና ሌላውም መጀመሪያው ውስጥ ሲገባ ነው ይላሉ፤ ዘላቂ ሰላም ለማረጋገጥ መግባባትን መፍጠር የማዕዘን ድንጋይ ነው፡፡ በግጭቶች ተሳታፊ በሆኑ ኃይላት መካከል መግባባትን ለመፍጠር ደግሞ፤ መጀመሪያ የግጭቱ አካላት፣ የሚጋጩባቸው ምክንያቶች እና መፍትሔዎች ላይ መግባባት ይጠይቃል፡፡
መ . የሕይወት መተሳሰር mutuality
ዘላቂ ሰላም እንዲፈጠር የሰዎች ሕይወት የተሳሰረ መሆኑን በጥልቀት መገንዘብ፣ መረዳት ይጠይቃል፡፡ የሰው ልጆች መሰረታዊ ፍላጎቶች ተመሳሳይ፣ ተቀራራቢ መሆናቸውን መገንዘብ ማለት ነው፡፡ ሰው መከበርን፣ መወደድን፣ መደመጥን፣ ከፍ ከፍ ማለትን እንደሚሻ ሁሉ በተቃራኒው ውርደትን፣ መገፋትን፣ መጠላትን፣ መናቅን፣ መቆርቆዝን፣ …፤ ማስወገድ ነው፡፡ ፕሮፌሰር ሕዝቅያስ በዚሁ መጽሐፋቸው ስለ እርቅ ምንነትና መሰረታዊ አላባውያን fundamental elements እንደሚከተለው ይተነትናሉ ፡፡
“እርቅ ማለት በከባድ ጠብና ይህም ባስከተለው መጎዳዳት፣ ጥላቻና መፈራራት ምክንያት ተለያይተው፣ ተራርቀው፣ ተቆራርጠው የነበሩ ሰዎች የወደመውን የጋራ ኑሮአቸውን እንደገና ለመገንባት የሚጓዙበት ሂደት ነው፡፡ እርቅ ጥልቅ የሰላም ግንባታ ዘዴና አላማ ነው፡፡ የእርቅ ሂደት የሚከተሉትን እርምጃዎች ያካትታል፡፡”
፩ኛ . በግጭቱ ተካፋይ የነበሩ ወገኖች በሌላው ላይ የፈፀሙትን በደልና ጉዳት በሀቀኝነት ማመን፤
፪ኛ . በተፈፀመው በደል እውነተኛ ፀፀትን መግለፅ፤
፫ኛ . የተበደለውን አካል ከልብ ይቅርታ መጠየቅ፤
፬ኛ . የተበደለው አካል ከልብ ይቅርታውን በመቀበል ይቅር ማለት፤
፭ኛ . ተበዳዩን ጉዳት ከመድረሱ በፊት ወደ ነበረበት ሁኔታ መመለስ፤
፮ኛ . በደሉ እንደገና እንደማይፈፀም አስተማማኝ የሆነ ማረጋገጫ መስጠት፤
፯ኛ . ከግጭቱና ካስከተለው ጉዳት በመማር የሁለቱንም ወገኖች ጥልቅ ፍላጎትና ጥቅም የሚያራምድ፣ የሚያጎላምስና የሚያስተሳስር አዳዲስ ግንኙነቶችን መመስረትና ዕቅዶችን መንደፍ፤
ፈጣሪ ለእውነተኛ ሀገራዊ ምክክር፣ እርቅና ይቅር ባይነት ያብቃን !!!
አሜን ፡፡
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)
fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን ሰኔ 25/2015