«በኢትዮጵያ እጅግ ያማሩ ደመግቡ፣ ቆንጆዎችና ውብ ሰዎች አሉባት። ርህራሔ ያላቸውም እንደ እግዚአብሔር ነው። በመንገድ ለሚያልፍ የሚሆን ሰው ድግስ ያዘጋጃሉ። ምንም ቢሆን መንገደኛ የሚበላውን አያጣም። በዕድሜያቸው ከመቶ እስከ መቶ እስከ መቶ ሃያም እስከ መቶ ሰላሳም ይኖራሉ። ነውርና ክፉ ነገር በራሳችው የተጠላ ነው። የጤና ምንጮች የሆኑ የውሃ ወንዞች አሏቸው። በጠጧቸው ጊዜም ሰውነታቸው ይታደሳል፤ በሀብትም እጅግ የበለጸጉ ናቸው»
– ስለ ትናንታችን ሔሮዶቶስ በአንድ
ወቅት ያለው ።
እውነት ብሏል፤ ሥጋዊ ውበትና ደምግባት ከኑሮ (ከማዕድ) ይመጣል። ለራስ ተርፎ ለመንገደኛም የሚበላውን ደግሶ ማዘጋጀት ከልብ ደግነትና የሚሰጡትን ካለማጣት ይገኛል። የሀገሩን ማለት የሕዝብን ኑሮ ‹‹ በሀብት እጅግ የበለጸጉ ናቸው›› ሲል ምን ያህል ዘመኑ ፍትሐዊ እንደነበር ያሳያል። በዛ ዘመን ሕዝቡ በርህራሔ የተሞላና ነውርና ክፉ ነገርም በኑሮ ዕሴቱ የተጠላበት ሲል ለዛሬ ማንነታችን ትልቅ ማስተማሪያ ነው። በጊዜው ሌብነት/ ሙስና/ የተጨማለቀ ዘመን ቢሆን አይደለም ለሌላ ሕዝብ ለራስን አይተረፍም ነበር። ሀገር ከሙስና ሲጸዳ ሕዝብ ሔሮዶቱስ በገለጸው ይዘት ይገኛል።
ዛሬ ላይ ሙስና በሀገር ላይ ስለገነነ፤ በዕድገትና በሥልጣኔ ለጎረቤት ሀገሮች ምሳሌ መሆን አይደለም የሕዝቡ ኑሮ ሙሾው ዕለት ተዕለት መራር ዜማ ሆነ። በዚህ ሀገር ላይ ሙስናን በመዋጋት ህልውናውን ከስሩ መንግሎ መጣል ወይም በማሽመድመድ መፍትሔ ማምጣት በራሱ ብዙ ሜጋ ፕሮጀክቶችን የማሳካት ያህል ያስቆጥራል። ሌብነትን እንደባሕል ለማሳደግ የምንለማመድበት፤ የሰረቀን ጠላት የገደለ ያህል የሚወደስበት፤ ሌቦችና ግብራበሮቻቸው በስራቸው የሚኮሩትን የምናበረታታ እንመስላለን። ሰርቶ ከማግኘት፤ ነግዶ ከማትረፍ ይልቅ በቁም ገድሎ ከትውልድ የሀገር ሀብት የሰበሰቡትን ምድር ላይ ከሚኖሩበት ተርፎ ለሰማይ ቤታቸው የሚስፈልግ የሚመስላቸው ሙሰኞች ሞልተውናል።
ይህ የመሰለ የሌብነት ሥርዓት በዚህ ሀገር ላይ የተፈጠረው በብዙ ምክንያት ነው። ለምሳሌ ሥልጣን ሀገርና ሕዝብን በቅን ልቡና ከማገልገል ውጭ የሀብት ምንጭ ሲሆን፤ በዝባዥ የሆኑ ባለሀብቶች ሀገርን ለከፍተኛ ብልጽግናቸው መሠረት ሲያደርጓት፤ ምሁራኑ በጥበባቸው የሀገር ችግር ከመፍታት ይልቅ የገንዘብ ማግኛ መሳሪያ ሲያደርጉ ነው። የሀገሬ ሰው አንድ ትልቅ ብሒል አለው። ‹‹ባዶ ቂጡን ያደገ ሱሪ ሲገዛ ይኖራል።›› ይላል። በዚህ መንገድ መጥቶ በሙስና የተዘፈቀ ሰው በአንድ ጣት ለሚቆጠር ዕድሜው ያለውንና የመጪውን የትውልድ ሀብት በየሰው ሀገር ካዝና የሚያከማች አለ። እንደባለተረቱ የትናት ድኅነቱን አብዝቶ ስለሚፈራ ነው። ለዚህም እንደነብር ጅራት ከያዘ አለቅ የሚለው።
እንዲህ ዓይነቱ ሰው የትናንት ድኅነቱን ስለሚፈራ ዛሬ በእጁ ያለውን ከበቂ በላይ ሀብት እንኳ ቢይዝም አይጠግብም። ፍርሃቱ ደግሞ ልክ እንደአህያዋ ነው። ‹ አህያዋ በለስ ቀንቷት አንጀቷን ዘርግፎ ራት የሚያደርጋት ጅብ አንገቱን ነክሳ ብትገደለው እንኳ መንከሷን አታቆምም አሉ። ታዲያ አሳዳሪዋ ብረት (ጉጠት) አግሎ አፏን አስነክቶ በማስለቀቅና የሞተውን ጅብ አርቆ ጥሎ ነው ነጻ የሚያወጣት። አልያ ጅቡ ተነስቶ የሚበላት ነው የሚመስላት። በዚህች ሀገርም ብዙ ሙሰኞች እንዲህ ስለሚመስሉ መስረቅ ቢያቆሙ ድኅነታቸው እንደጅቡ ዞሮ የሚዘነጥላቸው ስለሚመስላቸው የገንዘብና የንብረት ጥም አልቆርጥ የሚል የሙስና ሱስ ውስጥ ይዘፈቃሉ። በዚህ አካሄዳችን ከቀጠልን ነገ የሙስና ማገገሚያ /እንደሱስ ማገገሚያ ሳያስከፍትልን አይቀርም።
ሙሰኛ ሰው በሀገሩ ለምን ተፈጠረ ቢሉ ሃይማኖተ ቢስና የሰውነት ደረጃ ላይ ያልደረሰ ሰብዕናን ገንዘብ ያደረገ በመሆኑ ነው ማለት ይቻላል። ሰውነት ከሌለ ደግሞ ሙትነት ይነግሳል። ለዚህ እኮ ነው ሊቃውንቱ ‹ሙስና መሞት፣ መበስበስ ነው› የሚሉት። በሙስና ሰበብ ለሚንገላታ፣ ለሚራብ፣ ለሚታረዝ፣ ለሚሰደድ— ሕዝብ ድርሻውን በመስጠት ከእርኩሰት መንጻት ይቻላል። ሙስና የግለሰብንና የሀገርን ሀብት የሚነጥቅ እንጂ የሚለግስ እጅ የለውምና የባለሙሰኞች እጅ እንዲሰበስቡ ማድረግ ሀገርን ከድህነትና ከጥፋት መታደግ ይቻላል። አልያ የሙስና ሀገር ማሕጸኗ ሰፊ በመሆኑ በቃኝን ስለማታውቅ ለዕድገትና ለብልጽግና የሚደረግ መንገድ አይኖርም።
ይህ ክፉ ግብር መግታት የሚቻለው ደግሞ በሕግና በሕግ ብቻ ነው። ያለ ሕግ ፍትሕ አይመጣም። ያለ ሕግ በሥርዓት መኖር አይቻልም። ምክንያቱም ገነት እንኳን በአንዲት በለስ የታጠረች ነበረች። አምላክ ፍትሓዊ በመሆኑ ለአንድ አዳምና ለአንድ ሔዋን ሕግ ስለተላለፉ ቅጣት ወስኖባቸዋል። ዓለምም ሚዛን ጠብቃ የምትኖረው በሥርዓትና በሕግ ብቻ ነው። ሕግ ሲጣስ ሥርዓት ሲዛባ የዓለም መልክ ይቀየራል። በሀገርም ሕግ እስካልተተገበረና እስካልተከበረ ድረስ ሌቦች ፈት ሆነው ሀገርን ወደመቀመቅ ያወርዷታል። በየተቋሙ ሌብነት ሲደራ በየሰፈሩ እንኳን ዘራፊ ይበረታል። በዚህም ሕዝብ በሁለት ሰይፍ ይመተራል።
ሀገር የምትድነው ፍትሐዊ በሆነ ሕግ ብቻ ነው። በተግባር ያጠፋን በመቅጣት፤ የሰራን በመሸለም ነው። በፍጥረት ውስጥ ደግሞ እንደ ሰው ሕግ የሚሽር የለም። ሌሎቹ በጥንተ ደመነፍሳዊ ሕጋቸው እስከዛሬ አሉ። የሰው ልጅ ግን ሕግ የሚሽርና ሥርዓት የሚያፈርስ ብቸኛው ፍጥረት ነው። መስመር የሚይዘው ደግሞ በየብዙኃኑ መገናኛ ለይስሙላ ትምህርት በመስጠት፣ የግንዛቤ ማስፋፊያ በማቅረብ የሚሆን አይደለም። ምክንያቱም በሙስና ባሕር ውስጥ የሚዋኘው ሌላው ትምህርቱ የሚሰጠው ለተሰረቀው ሕዝብ መሆኑ ማሰብ በጣም ያበሳጫል። ያማልም። ያለጥርጥር ፈር ማሲያዝ የሚቻለው የሕዝብ፣ የሀገርን ሀብትና የግለሰብን ድርሻ የዘረፈን የዘረፈውን በመንሳትና ላጠፋውም ተመጣጣኝ ቅጣት በመቅጣት ነው።
በዚህ ዓለም ላይ ማንም የማንንም ድርሻ ሊነሳ አልተፈጠረም። ለዚህም ምንም ዓይነት መብት አልተሰጠም። ሁሉም ዜጋ የድርሻውን፣ የልኩን፣ የድካሙን ዋጋ ሰርቶ የሚከፈለው፣ ነግዶ የሚያተርፈው፣ ዘርቶ ምርት የሚሰበስበው፣ አልምቶ የሚቆጥረው ለላቡ ልክ አለው። ሁሉም የድካሙን ቢወስድ ሁሉም በደረጃው ያድጋል። በአንጻሩ በየፈርጁ ሀገር ሲያድግም አብሮ ይታደጋል።
ዛሬ በሀገሩ የዝና፣ የስኬት፣ የስም….. መለኪያው ገንዘብና ገንዘብ ብቻ ሆነ። መታፈር፣ መከበር በገንዘብ ሆነ። እምነት፣ ጥበብ፣ ፍልስፍና፣ ክህሎት፣ ዕውቀት…. ዋጋ የማያወጡ የሆኑ መሰለ። ይህ መንገድ ከቀጠለ ምን አይነት ትውልድ ልናፈራ ነው? ምን አይነት ሀገር ልንሰራ ነው? ምን አይነት እሴት ልንገነባ ነው? ታምኖ መስራትና ተግቶ ማትረፍ ካልተወደደ የባንዲራ አከል ከፍ አድርገን የምናከብራቸው በዘረፋ፣ በማጭበርበር እንዲሁም በጉልበትና በሥልጣን ሀገር ያደኸየውን ከሆነ፤ ሰርቶ በማትረፍ መክበርና መኩራት መች ይመጣ ይሆን? ሰው መሆን ማለት እኮ ከልክ ያለፈ የሀብት ባሕር ውስጥ በመዘፈቅ ብ ቻ አይደለም የሚሰምረው።
በዚህ ሀገር ላይ ደግሞ ብዙኃኑ ሕዝብ የሚፈልገው በቀዬው በሰላም መኖርና ለኑሮው መሠረታዊ ፍላጎቱ እንደሀገሯ ዕድገት ማግኘት እንጂ የቀን ሕልሙን ሕዝብ በጋራ አይጠብቅም። ዛሬ የብዙ ችግሮች ምንጭ የሕዝብ መሠረታዊ ፍላጎት ያልተሟላበት ምክንያት ደግሞ የሕዝብ ሀብትና ድርሻ በጥቂቶቹ ሙሰኞች ስለተሰበሰበ ነው።
መንግሥት ማለት የተቋማትና የክልል መንግሥታት ስብስብ ነው። ሁሉም ደግሞ በተዋረዳቸው መሪዎች ናቸው። ራዕይ ያላቸው፣ በሥልጣን የማይባልጉ፣ ሕዝብ የሚያገለግሉ፣ በሀገር ዕድገት ላይ በጎ የሚያስቡ፣ ከጊዜያዊ ጥቅምና ዝና ይልቅ ለሀገርና ለሕዝብ ዘመናት የሚያሻገር ሥራ የሚሰሩ ጥሩ አመራሮች በመሪነት ዘመናቸው የሙስናን ሰንኮፍ ከሥሩ መንግለው መጣል አለባቸው።
ሁሉም ባለድርሻ አካል በተቋሞቻቸው ውስጥና ከተቋሞቻቸው ውጭ በሚፈጠሩ የሌብነት ስራዎችን በአብነት በመታገልና በማታገል ከሆነ ብቻ ነው ለውጥ ሊመጣ የሚችለው። ለዚህ ደግሞ ቁርጠኝነትን ይጠይቃል። በክፍያቸውና በተገቢ ጥቅማጥቅማቸው የሚያገለግሉ አመራር ሆነው ሌብነትን ንቀውና ተጸይፈው ሁሉም በዘመናቸው ያደገች ሀገር ተገንብታ ለማየት የናፈቁ ከሆኑ ከወዲሁ የሌቦችን እግር መግታት እጆቻቸውንም ማሳጠር አለባቸው።
በዚህ ሀገር ሙስና /ሌብነት/ ጠፍቶ፣ ፍትሕ ነግሶ፣ ልማት ተስፋፍቶ፣ ሀገረ አድጎ ለማየት በብዙዎች ተጽፏል። ለምሳሌ ከመቶ ዓመት በፊት የነበሩ ነጋድራስ ገብረ ሕይወት ባይከዳኝ በዚህ ዘመን እስካሉ የምጣኔ ሀብት ባለሙያዎችና የፖለቲካ አመራሮች ብዙ ቢሉም ዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ በዘመናቸውም ድንቅ ሐሳብ አምጥተው እንደታገሉበት ታሪክ ይነግረናል።
ዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ ለሀገር ባደረጉት ውለታ በብዙ የሚጠቀስ ምግባራት ያሏቸው ንጉሠ ነገሥት ናቸው። ለሀገር አንድነት የደከሙ፣ የመንፈስ ጥንካሬያቸውን ያጋቡ፣ በጋፋት ድካማቸውን ማየት ይቻላል። ፕላውዴን እንደመሰከረላቸውም ‹‹ ከሚገባው በላይ ለጋስና ለወርቅም ሆነ ለገንዘብ የማይሳሱ ናቸው ›› ሲላቸው፤ አውሮፓውያኑም ‹‹ጫማ አልባው ንጉሥ›› ይሏቸዋል። ሀገር በእጃቸው ሆኖ የወርቅ ጫማ መጫማት፤ የወርቅ ልቡጥ ልብስ መልበስ ሲችሉ ሀገር ለማቅናት ደፋ ቀና ሲሉ ብዙውን ሕይወታቸው ከተራ ልብስ ያልወጡ ነበሩ። በአንድ ወቅት ይህን መልዕክት አስተላልፈውም ነበር፤
“በቴዎድሮስ ዘመን ሠራተኛው በሥራው ይኩራ፤ ሌባ ለእጁ ይፍራ፤ ቀማኛ ለአንገቱ ይፍራ፤ ጉቦ የሚበላ ፍርድ የሚያዳላ ወዮውለት፤ እንኳን ከቴዎድሮስ ጋር ከእናቱ ጋር አይኖርም። መኖሪያ ቤቱ መቃብር ይሆናል። ከተራ እስከ ራስ፤ ሠራዊቴ በሙሉ እንደማዕረጉ በሚሰጠው ደሞዝ ይተዳደራል። ሁሉም ሰው እንደአቅሙ በነፍስ ወከፍ ለንጉሥ ይገብራል። ንጉሡም ከነሠራዊቱ ያንጓ እንደ ድርሻው ተከፋፍሎ ይተዳደራል‘ብለው ነበር።
እዚህ አንቀጽ ውስጥ የሚደንቁ ሐሳቦች አሉ። ሰው መኩራት ያለበት በስራው መሆኑን ይጠቁማል። ይህ ማለት ሠራተኛው በተገቢው ክፍያ የሚኖርበት፤ ለሙስና ለሌብነት እጁን የማይዘረጋበት፤ ሌባ ለእጁ ቀማኛ ለአንገቱ ይፍራ ሲሉም ያጠፋ በጊዜው የሚቀጣበትና ምንም ከለላ የማያገኝበት ተሰርቶ እንጂ ተሰርቆ መብላት የሚያስቀጣበት መሆኑን የሚያሳይ ነው። ዛሬ ላይ ግን ሌብነት በአደባባይ ወጥቶ ፀሐይ ሲሞቅ የማይታፈርበት ያልሰረቀ የማይከበርበት ዘመን መስሏል፤ ጉቦ የሚበላና ፍርድ የሚያዳላ አይቀጡ ቅጣት እንደሚቀጣና እንኳንስ ከንጉሡ ከእናቱ ጋር አይኖርም ሲሉ ሌባ መደበቂያ እንደሌለው ያሳዩበት ጭምር ነው።
ሌብነት ከነገሰ ሀገር ወደፊት መጓዝ አይቻላትም። በሀገር ላይ ሙስና ካልተስፋፋ በቀር ሥር የሰደደ ድህነት አይፈጠርም። ሙስና ከከሰመ ደግሞ ዜጎች የሀገር ሀብትን በተገቢ ተጠቃሚ ይሆናሉ። ሀገር ያፈራውን የዜግነት ድርሻቸውን ሕዝብ ሊቀማ፣ ሊነጠቅ አይገባም። ከምንም በላይ ዜጎች በሀገራቸው ውስጥ ሲኖሩ ዳቦና ውሃ የሰው እጅ አይተው መኖር አይገባቸውም። ዛሬ በዚህ ሀገር ውድ የሆነው መሠረታዊ ፍላጎቶቻችን ናቸው። ግን በፍትሕ መዛባትና በሙስና ማየል ምክንያት የሕዝብ ሀብት ለጥቂቶቹ በመዋሉ ችግሩ የከፋ ሆኗል።
ሁሌም ለጤናማ የኑሮ ዘይቤ ሰርቶ በአቅም መኖር፣ በተመጣጣኝ ዋጋ ሸምቶ መብላት፣ በሀገር ያለንን ሀብት በተገቢ መጠቀም የኑሮ ሥርዓቶች በሀገሩ መስፈን አለበት። ዳቦና ውሃ፤ መጠለያና አልባስ ማግኘት አለመቻል ራስን እስከማጣት የሚያስመስል ስጋት በዜጎች ልቦና ላይ መፈጠር የለበትም። በየትኛውም ሥነ አመክንዮ ቢታይ የሕዝብ ኑሮ ቤት ውስጥ ቢሆን ሥነ ልቦናዊ ፋይዳው የጎላ ነው የሚሆነው።
የሰውን እጅ በሕይወት፣ በኑሮ ውስጥ ማየት መቼም አያኮራም። መሠረታዊ ፍላጎቶቻችንን በሰው እጅ በልግስና መቀበል በራሱ ለተመጽዋቹ ከባድ ነው። የተለየ ምክንያት ካልተፈጠረ በስተቀር ዜጎች በልግስና መሠረታዊ ፍላጎቶቻቸውን ማሟላት አይገባቸውም። ለሥራና ለኑሮ ትግል ሰንፈው ካልፈቀዱ በቀር።
በሀገሪቱ ውስጥ ድሆች ሳይሆኑ የድሃ ድሃ እየበዙ በመጡበት ሁኔታ ትንንሽ ነገሮችን በመደጎም ሥር የሰደደ ድኅነት አይቀረፍም። በእርግጥ ለጋሾች በሰው ዘንድ ተመራቂዎችና በፈጣሪ ዘንድም የበረከት ተቋዳሾች ናቸው። ማንም ቢሆን በመለገሱ አይወቀስም። ድሃ ለባለጸጋ እንኳ ካለው ቢሰጥ ይወደሳል እንጂ አይተችም። መስጠት መጠን የለውም፤ ልብ እንጂ ኪስ አይሰጥምና። ልግስና የሰብዓዊነት ሚዛን መጠበቂያ አንዱ ዕሴትም ነው።
በሀገሪቱ የተለያዩ የመንግሥት አካላት፤ ድርጅቶችና ቡድኖች አልያ በግለሰብና በየሃይማኖታዊ ባሕላት ላይ ለምሳሌ በክርስትና ሃይማኖታዊ ባሕላት ላይ ጾም ማስያዝና ማስፈሰክ፤ በእስልምና ሃይማኖታዊ ባሕላት ላይ ማስፈጠርና መለገስ እንዲሁም የተለያዩ ቁሶችን፣ አልባሳትንና የምግብ ውጤቶች ሸምቶ በልግስና ማቅረብ እየተለመደ መጥቷል። ይህ ተግባር በየጎዳናው፣ በየተቋማትና እስከ ቤት ለቤት ድረስ የሚተገበር በጎ ምግባር ነው።
አንዳንዴ ደግሞ የዚህ ዕድል ተቋዳሾች በዝና ሰማይ የገነኑ፣ በሕይወት ወይም በኑሮ መሬት ያሉትን ጭምር በእናስታውሳቸው መርሃ ግብር በየባሕሉ የጎጆአቸውን በር የሚቀበቅቡ ለጋሾች አልጠፉም። የመኝታ ፍራሽ፣ ገንዘብ፣ በግ አንዳንዴም የበዓል ዳቦ ወይም ኬክ ተጨማሪ በማዘጋጀት ዐውድ ዓመትን ያከብሩላቸዋል። ይህ በራሱ የሰናፍጭ ቅንጣት ታክል ክፋት የለውም። ክፋቱ ሀገር በማገልገል ለሰማይ ለምድር የከበዱ የነበሩ ዜጎች ቤት ባፈራው ባሕልን በቤታቸው ማክበር ሲሳናቸው ማየት ነው። ግን እስከ መቼ ይህ ዓይነቱ መንገድ ያዛልቃል። በተለይ ሀገርን በተሰጥኦዋቸው ሙያ ሲያገለግሉ ኖረው የማታ ማታ የሰው እጅ የሚያዩ አንጋፎችን ማሰብ በጣም ያሳዝናል።
በአንድ ሀገር ተፈጥሮ ካመጣው ድርቅና በሌሎች አደጋዎች ሰበብ ምክንያት የሚመጣ መራብና መታረዝ የሰው ልጆች የጋራ ጉዳይ ሆኖ እየታሰበ መጥቷል። ማንም ሀገር ቢሆን በተፈጥሮ አደጋ ሰውና እንስሳት ሲጎዱ እንኳን በሀገር ውስጥ ያለ ሕዝብ አይደለም በሌላ ክፍላተ አህጉራት ያሉ ሰዎች ሞራላዊ ግዴታቸው ሆኖ የመከራውን ባሕር ያሻግራሉ።
ይህ ዓይነት የሰብዓዊነት ትብብር ባለበት ዓለም በሀገር ውስጥ ደግሞ የተለያዩ ምክንያቶች የኑሮ መወደድ፣ ከፍትሕ መዛባት የተመረተው እንኳን የአቅርቦት ስርጭት ማነስ፣ ሕዝብን በዝባዥና አቆርቋዥ የንግድ ሥርዓት መፍጠርና በየመስኩ የሌብነት/ የሙስና ማበብ ተንሰራፍቶ ዜጎች ችግር ውስጥ ከወደቁ ችግሩ በዋናነት የሚነቃው ከአስተዳደር መናጠብ ነው የሚሆነው። ለዚህ ደግሞ ከማንም በላይ ሙስናን ለመከላከል የሚደረግ ጥረት ከምንም በላይ መቅደም አለበት።
በአንድም በሆነ በሌላ መንገድ የጎዳና ተዳዳሪ፤ የመንገድ ላይ ነዲያን፤ በየቤታቸው ያሉ ተረጂዎች፤ በአረጋውያን መርጂያ ያሉና በሌሎችም ተቋማት ያሉ….የድኅነታቸው ዐብይ ምክንያት በሙስና /በሌብነት ድርሻቸው በተለየ መንገድ ተወስዶ እንጂ እንደዜጋ ዳቦና ውሃ፤ እራፊ ጨርቅና ትንሽ መጠለያ… ማጣት አልነበረባቸውም። አንድ ሀገር ሕዝቧ በምግብና በሌሎች መሠረታዊ ፍላጎቶች ራሳቸውን ችለው ለሀገሪቷም ዕድገትና ብልጽግና የሚያመጡ ነገሮች ለማየት አንዱ ሙስናን በመዋጋት ዜጎች ድርሻቸውን እንዲያገኙ በማድረግ ነው።
ኢትዮጵያ ባላት የሰው ኃይል ሀብት፤ የተፈጥሮና የታሪክ ሀብት በመጠቀም በአጭር ጊዜ ውስጥ ራሷን ችላ ለሌሎች ጎረቤት ሀገራትም የምትተርፍ ማድረግ ያን ያህል ከባድ አይደለም። ለዚህም ዘላቂ ሰላም በማስፈን ፍትሐዊ የሀብት ክፍፍል በማድረግና ከሌብነት በጸዳ ለሁሉም ሕዝብ ጠንካራ የሥራ ባሕል በመፍጠር ዕድገት፤ ብልጽግናንና ሥልጣኔን ማምጣት ይቻላል። ምንም ያህል ወደተለያዩ የሥራ ዘርፎች ሕዝብን ብናሰማራ የሌብነትን መረብ በጣጥሰን መጣል ካልቻልን የሀገርን ሀብት ጥቂት ግለሰቦች አስግረው ሀብታቸውን ማካበት የዘለለ አይሆንም።
በሀገር ላይ ሙስናን እንደ ሕዝብ ለመታገል ከትንሹ መጀመር እንችላለን። ሙስና ወይም ሌብነት የሰውን መውሰድ ከሆነ በዕለት ተዕለት ሕይወታችን የሚያጋጥሙን የሌብነት ልምምዶችን መዋጋት አለብን። ለምሳሌ ያህል በትራንስፖርት በታሪፍ ዋጋ መገልገል፤ በሸቀጦች ላይ ያለ ምክንያት የሚጨምርቱን ዋጋ ላይ ቁጥጥር ማድረግ፤ በዳቦ፤ በጤፍ፤ በሥጋና በተለያዩ ቅመማ ቅመሞች ላይ በየባሕላቱ እያስታከኩ ዋጋ የሚያንሩትን ስግብግብ ነጋዴዎችን ገበያ ያወጡትን ባለመሸመት ሁሉ መቅጣት ይገባል።
በተለይ መንፈሳዊ በዓላትን በሥጋና በቅቤ ብቻ መከበር የለበትም በመንፈሳዊ ባሕሉ መወጣት ተገቢ ነው። በባሕላት ደስታ የሚያስፈልግ ቢሆንም ሁሌ በኑሮ እየተጨነቅን መሆን የለበትም። እንደ ሕዝብ የዕለት ተዕለት መሠረታዊ ፍላጎቶቻችን ላይ ቅጥ ያጣ የዋጋ ንረት በጸጋ መቀበል ተገቢ አይደለም። ዛሬ በሀገሪቱ ውስጥ የተፈጠረው ከባድ የኑሮ ውድነት ሽክም ውጭ ያለው ዓለም ተጽዕኖ ይልቅ በሀገር ውስጥ ያለው የሙስና ጫና ይበልጥ ወገብ ያጎብጣል። ሀገርን እያደኸዩ ካላት ላይ ከመዝገን ሀገርን አሳድጎ ለሁሉም የማይጎድል የሀብት ምንጭ መፍጠር ይቻላል።
በአጠቃላይ እያደር የሚያድጉ፤ እያደርም የሚደኸዩ ሀገራት ይኖራሉ። ማደግም መደኽየትም ያለው በሕዝብ፤ በምሁራን፤ በነጋዴዎችና በመሪዎች ተሳትፎ ነው። ለዕድገትና ለሥልጣኔና ለብልጽግና ሁሉም ድርሻቸው የጎላ ነው። ሕዝብ የሀገር ሀብት ሲዘረፍ ሲያይና ሲሰማ ድምጹን ማሰማት አለበት። ምሁራን በአንድ ወገን በዕውቀታቸው የሀገሪቱን የዕድገት መስመር ማመላከት ሲሆን በሌላ መልክ ደግሞ ዕውቀታቸውን የሙስና መሳሪያ ባለማድረግ መከላከል ነው።
ነጋዴዎች ማለትም በትልልቅ ኢንቨስትመንት ውስጥ ያሉ ባለሀብቶች የገንዘብ ጉልበታቸውን በመጠቀም የሀገሪቱንና የሕዝቡን ሀብት ለመመዝበር የሚቋምጡትን የሀገር ውስጥ፤ ውጭ ባለሀብቶችንና መንግሥታት ስር ሀገር እንዳትወድቅ ሥርዓት ባለው መልክ በሀገር ላይ ንዋያቸውን አፍስሰው ራሳቸውንና ሀገርን ሲጠቀሙ ነው። እንዲሁም በተለያዩ እርከን ያሉ የመንግሥት አመራሮች ሙስናን በሀገር ውስጥ እንዳይስፋፋ ሕግ በማስከበርና ፍትሕን በማስፈን ሀገርን ከድኅነት መታደግ ይቻላል። ሙስና ሥራ ስላልሆነ አሽመድምደነው ሰርቶ መክበር እንደሚቻል ምስክር የምትሆን ሀገር በጋራ ፈጥሮ ማሳየት ከሁሉም ይጠበቃል።
በመኩሪያ አለማየሁ
አዲስ ዘመን ሰኔ 24/2015