በመላው ዓለም ዙሪያ በሚገኙ የእስልምና ሃይማኖት ተከታዮች ዘንድ በድምቀት ከሚከበሩ በዓላት መካከል አንዱ የሆነው የኢድ አል-አደሃ በዓል መከበር ምክንያቱና ታሪካዊ ዳራው ምን ይመስላል? «የዒድ አል-አድሃ ታሪካዊ ዳራ ነቢዩ ኢብራሂም/ዐሰ/ልጃቸውን ለአላህ ለመሰዋት ያደረጉት ቁርጠኝነት የተመላበት ውሳኔ እና ለመስዋዕትነት የቀረበው ልጅ ያሳየው የተለየ ጽናት ነው። ነቢዩ ኢብራሂም/ዐሰ/የአላህ ደግ ሰው ከ120 ዓመታት የመካንነት ሕይወት በኋላ የበኩር ልጃቸው የሆነውን ኢስማዔልን በእርጅና ዘመናቸው አላህ በፍቃዱ ቸራቸው።
ታላቅ ሚስታቸው ሳራ ለፍሬ ባለመብቃቷ። «ያ አላህ ያለ ዘር አታስቀረኝ፤ እኔን የሚተካ ሷሊህ የሆነ ልጅ ስጠኝ» በማለት ዱዓ አደረጉ፤ በዚሁ መሠረት በሳራ ፈቃደኝነት ሐጀራ የምትባለውን የቤት ሠራተኛቸውን አገቡ። ሐጀራም ዒስማኢል የተባለ ልጃቸውን ወለደችላቸው። ይህ ልጅ በአላህ ፈቃድ በመካ ከተማ እንዲያድግ የተወሰነ ስለነበረ ኢብራሂም ሐጀራን እና ዒስማኢልን ወደ ዐረቢያ ከተማ ወሰዷቸው። ዒስማኢል ካደገ በኋላ ደግሞ አላህ «ልጅህን እንድትሰዋ ታዘሃል» የሚል ትዕይንት በህልማቸው አሳያቸው። የነቢያት ህልም ደግሞ ከራዕይ የሚቆጠር ነው። ስለዚህ ኢብራሂም በህልማቸው ያዩትን ትዕዛዝ በዝምታ አላለፉትም። በወቅቱ የሆነውን ቅዱስ ቁርኣን እንዲህ ይተርካል።
«ከርሱ ጋር ለሥራ በደረሰ ጊዜም» ልጄ ሆይ! እኔ በህልሜ የማርድህ ሆኜ አይቻለሁ፤ (እስቲ አንተም ነገሩን) ተመልከት። «ምን ይታይሃል»?አሉት፡ ፡(ልጁም) አባቴ ሆይ! የታዘዝከውን ፈጽም፤ አላህ ቢሻ ከታጋሾቹ ሆኜ ታገኘኛለህ አለ» (ሱረቱ-ሷፍፋት፤102)። አባትና ልጅ በዚህ መንገድ ከአላህ የተላለፈውን ትዕዛዝ ሊፈጽሙ ተነሱ፤ ነቢዩ ኢብራሂም/ዐሰ/ ልጃቸውን እንዲሰዉ የታዘዙት ከዐረፋት መሬት ብዙም ባልራቀ ቦታ ላይ ስለነበረ ወደዚያው ጉዞ ጀመሩ። በመንገዳቸው ግን ኢብሊስ (ሰይጣን) በሰው ተመስሎ በጣም ተፈታተናቸው፤ ሦስት ጊዜ ያህል እየወጣ «ከስንት ዓመት በኋላ ያገኘኸውን አንድዬ ልጅህን ስትሰዋ ምንም አይጸጽትህም?…እንዴት ጅል ትሆናለህ»? እያለ ሞገታቸው።
ከአላህ ትዕዛዝ ፍንክች የማይሉት ነብዩ ኢብራሂም ግን ድንጋይ ከመሬት በማንሳት «አዑዙቢላሂ ሚነ-ሸይጣኒ ረጂም» እያሉ ኢብሊስን ወገሩት። ነብዩ ኢብራሂም ብቸኛ ልጃቸውን ዒስማኢልን ሊያርዱት አጋደሙት። ልጁም ምንም ሳያንገራግር ከመሬቱ ላይ ተኛ። ነብዩ ኢብራሂም ልጁን ሊያርዱት ሲሞክሩ ግን ቢላዋው አላርድ አላቸው። ኢብራሂም እንደገና ቢላዋውን ገዘገዙት/ሣሉት/፤ነገር ግን ፈጽሞ ዶለዶመ። ታዛዡ ልጅ የሆነው ነገር አልገባውም። አባቱ ቶሎ ስላላረዱት ተገረመና «አባዬ!፣ምናልባት የአባትነት ፍቅር ይዞህ ይሆናል በቶሎ ያላረድከኝ፤እስቲ ዐይኔን በጨርቅ ሸፍነውና እርዱን ሞክር» የሚል አስተያየት ሰጠ።
በዚህን ጊዜ ግን ከወደ ሰማይ ጥሪ መጣ። የአላህ መልዓክ «ኢብራሂም ታላቅነትህን አስመስክረሃልና እርዱን አቆየው»በማለት አወጀ። በምትኩም መልዓኩ ከገነት ያመጣውን በግ እንዲያርዱና ልጁን ወደ ቤት እንዲመልሱት ነገራቸው። በዚህም መሠረት በጉ ታረደ። ኢብራሂምና ዒስማኢልም ወደ መካ ከተማ ተመለሱ። ሁለቱ ሰዎች ለፈጣሪ መታዘዝን በግልጽ ያሳዩባት ያቺ ዕለት የዒድ አል-አድሓ በዓል ሆና እንድትከበርም ተወሰነ። ዒስማኢል ለመስዋዕትነት የቀረበበት ድርጊት ደግሞ በዚሁ ዕለት የሚታረደው ከብት ወይም ግመል «ኡድሂያ» መነሻ ሆነ። ይህን ታሪክ መነሻ በማድረግ ኢድ አል-አደሃ ይከበራል።
በዓሉ የመስዋዕት፣ የእርድ በዓል ነው። በተለይም የሐጅ ጸሎት የሚፈጽም ሰው በዚህ ቀን ከብት የማረድ ግዴታ አለበት። የተቀረውም ሙስሊም ዕለቱን አቅሙ በፈቀደ ሁኔታ ከብት በማረድ ከቤተሰብና ዘመድ አዝማድ ጋር ያሳልፈዋል። ለኢድ አል አድሃ አንድ ሰው ከሚያርደው ከብት ሲሶውን ብቻ እንዲወስድ ነው ደንቡ። የተቀረው ሲሶው ለዘመድ አዝማድ፣ ሲሶው ደግሞ አቅም ለሌለው ደሃ እንዲከፋፈል እስልምና ያዛል። ከዚህ የተነሳም የአረፋ በዓል በእስልምና ኃይማኖት ተከታዮች ዘንድ ታላቅ በዓል ነው።
የእስልምና እምነት እንደሚያስተምረው ዐረፋ የሚለው ቃል በዐረብኛ «አወቀ» እንደማለት ነው። ይህም ታሪክ አለው። አዳምና ሔዋን ወይንም አደምና ሃዋ ከጀነት ወደ ምድር ከወረዱ በኋላ ለብዙ ዘመናት ተጠፋፍተው ነበር። ለረጅም ጊዜ ሲፈላለጉ ከቆዩ በኋላ በዚህ ዕለት በሳዑዲ ዐረቢያ ባለው የአረፋ ተራራ ላይ ተገናኙ። እዚያም«ዐረፍቱከ…ዐረፍቱኪ»ተባባሉ።«አወቅኩህ! አወቅኩሽ»ማለታቸው ነው።ይህንን ታሪክ ለመዘከር ሲባል ነው የዐረፋን በዓል ማክበር የተጀመረው። ይህ በዙልሂጃ ዘጠነኛው ቀን የሚከበር በዓል ነው።
ሀገራችን ኢትዮጵያ ከቀደምት የእስልምና ሃይማኖት ተቀባዮች አንዷ ናት። የእስልምና ታሪክ ሲነሰ የኢትዮጵያም ስም አብሮ ይነሳል። የነብዩ መሐመድን (ሰዐወ)የቅርብ ቤተሰቦችና ተከታዮችን ተቀብላ ያስተናገደች ሀገር ናት። ኢትዮጵያ፣ የመጀመሪያው ሙዕዓዝን(አዛን አድራጊ)ወይም የሰላት ጥሪ አቅራቢ ቢላል ኢብን ረባህም ኢትዮጵያዊ ነው። የነብዩ መሐመድን (ሰዐወ) እንግዶች ተቀብሎ ያስተናገደው ንጉሥ ነጃሺ በእስልምና እምነት ተከታዮች ዘንድ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው ነው።
መሐመድ ዓሊ የተባሉ ምሁር(ፒ.ኤች.ዲ)አንድ ወቅት እንደገለጹት፣ «በንጉሥ ነጃሺ፣ በአጠቃላይም በሃበሻ አማካኝነት ሃበሾችን መሠረት ያደረጉ ከ23 በላይ የቁረአን አንቀጾች፣ በሃበሾች ቋንቋም ከ30 በላይ የቁረአን አንቀጾች እንዲወርዱ፤ በተጨማሪም በነብዩ መሐመድ/ሰዐወ/ሰበብ ስለ ሃበሾች ክብር ከ27 ያላነሱ ነብያዊ ሃዲሶች እንዲነገሩ ምክንያት እንደሆኑ ይነገራል። ከነዚህ የቁረአን አንቀጾችና ነብያዊ ሃዲሶች ለማሳያ ያህል አንድ ሦስቱን እሴቶች ባጭሩ እናውሳቸው።
ሀ) ሶላተል ገይብ፦(አስክሬን በሌለበት የሩቅ ስግደት)። ነብዩ መሐመድ/ሰዐወ/የነጃሺ ሞት መርዶ በጅብሪል አማካኝነት ደረሳቸውና ምዕመኖቻቸውን አስከትለው ሶላተል ገይብ(አስክሬን/ጀናዛ/በሌለበት ስግደት)አሰገዱ። ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ይህ የሶላተል ገይብ የሙስሊሞች ባህል ሆኖ ቀጠለ።
ለ) የውክልና ጋብቻ፦ወደ ሃበሻ ከተሰደዱ ሴቶች መካከል ረምላ ቢንት አቡ ሱፊያን ነበረች። ረምላ ከባሏ ጋር በሃበሻ ስትኖር ባለቤቷ ኡቤይደላ ቢን ጃህሽ ከዚህ ዓለም በሞት ይለያታል። ረምላ፣ ቢባ ከምትባል ሕፃን ልጅዋ ጋር በብቸኝነት ስትኖር በአላህ ፈቃድ በንጉሥ ነጃሺ ውክልና ነብዩ መሐመድን/ሰዐወ/ለማግባት በቃች። የረምላም ወኪል የቅርብ ዘመዷ የነበረው ኻሊድ ቢንሰኢድ ነበር። በአጠቃላይ የጋብቻ ሥርዓቱ በውክልና ጋብቻ የተፈጸመበት፣ ራምላ ከማግባቷ በፊት አራት ወር ከአስር ቀን እንደሞላት የተረጋገጠበት፣ ጥሎሽ የተሰጠበት፣ የሰርግ ግብዣ የተደረገበት፣ ጋብቻው በምስክሮች ፊት የተፈጸመበት፣ ስለአፈጻጸሙም በቃዲ ትምህርት የተሰጠበት ወ.ዘ.ተ ነበር።
ከዚያ ጊዜ ጀምሮ ይህ በነብዩና በራምላ የተፈጸመ የጋብቻ ዓይነት የእስላማዊ ጋብቻ መሠረትና መመሪያ ሆኖ ይገኛል።
ሐ) የውርስ ሕግ፦በእስልምና ታሪክ የውርስ ሕግ አጀማመር ከሃበሻ ጋር ግንኙነት እንዳለው ይታመናል። ለዚህም ወደ ሃበሻ ከተሰደዱ ሰዎች መካከል አዴይ ቢን ነዲላ የሚባል ይገኝበት ነበር። ይህ ሰው በስደት ሃበሻ እንዳለ በመሞቱ ነብዩ መሐመድ ንብረቱን ቤተሰቦቹ እንዲወርሱ በማዘዛቸውና ልጁ አማን በመውረሱ፣ ከዚህ ጊዜ ጀምሮ እስላማዊ የውርስ ሥርዓት እንደተጀመረ ይታመናል።
መ) ዘንግ፦ነጃሺ ለነብዩ መሐመድ/ሰዐወ/ሦስት ዘንጎችን ልከውላቸው ነበር ይባላል። እሳቸውም አንዱን ለአቡበከር፣ ሁለተኛውን ለዓሊና ሦስተኛውን ለቢላል ሰጥተው በተለያዩ የበዓል ጊዜያት ዘንጉን ይዞ ሶላቱን ይመራበት ነበር፤ በአሁኑ ወቅትም በየመስጊዱ የጁምዓ ኹጥባ(ድስኩር)ኢማሞች የሚይዙት ዘንግ ከዚህ ተያይዞ እንደመጣ ይነገራል።
የዓለም ሀገራት የኢድ አል – አድሃ/አረፋ/በዓልን እንዴት ያከብሩታል?
በዓለም ዙሪያ የእስልምና ሃይማኖት ተከታዮች ዘንድ በድምቀት ከሚከበሩ በዓላት መካከል አንዱ ነው። የኢድ አል አድሃ(አረፋ)በዓሉ የእርድ ወይም የመስዋእትነት በዓል በመባል ይታወቃል። የአላህ/ሱወ/ ደግ ሰው ነብዩ ኢብራሂም/ዐሰ/ከ120 ዓመታት የመካንነት ሕይወት በኋላ በአላህ ፈቃድ ወንድ ልጅ ተቸራቸው። ልጃቸው ኢስማኤል ለአባቱ ታዛዥ እንደነበርም ይነገራል።
ነብዩ ኢብራሂም በደስታቸው ማግስት የእምነታቸው ጽናት የሚፈተንበት ወቅት ተፈጠረ። የሰባት ዓመት አንድያ ልጃቸውን መስዋእት ያደርጉ ዘንድ ከፈጣሪ ታዘዙ። የልጃቸው ፍቅር ቢያስጨንቃቸውም ትዕዛዙ የአላህ ነውና ሊፈጽሙ ከመካ ወደ አረፋ ተራራ ወጡ። ነብዩ ኢብራሂም ልጃቸውን ሊሰው ሲዘጋጁ ከሰማይ በኢስማኤል ምትክ መስዋእት የሚሆን በግ ወረደላቸው። በዓሉም ኢድ አል አድሃ(አረፋ)እየተባለ በየዓመቱ ለመከበሩ ምክንያት ሆነ።
በዓለም ሀገራት የአረፋ በዓል አከባበርን ለአብነት ያህል
በሕንድ
ሕንዳውያን በሂጅራ የዘመን ቀመር በ12ኛው ወር በ10ኛው ቀን የሚያከብሩትን የኢድ አል አድሃ በዓል «ታላቁ ኢድ» ሲሉ ይጠሩታል። ኢድ ኩርባን ወይም ኩርባን ባያራሚ ሲሉ እንደሚጠሩትም መረጃዎች ያመላክታሉ። የነብዩ ኢስማኤልን ለመስዋእትነት መመረጥ እና መታዘዝ ታሳቢ በማድረግም ጠቦት፣ ጥጃ፣ ግመል ወይም ሌሎች ለእርድ የተፈቀዱ እንስሳት በቀኑ ይታረዳሉ። የታረደው ስጋም ለቤተሰብ፣ ለጓደኛ እና ማረድ ለማይችሉ ወገኖች ለሦስት እኩል ይከፋፈላል።
ሕንዳውያን በዓሉን ከሃይማኖታዊ ትሩፋቱ ባለፈ የቤተሰባዊ እሴት ማጠናከሪያ እና መሰባሰቢያ በዓል አድርገው ስለሚያዩት በተለያየ ምክንያት ተለያይተው የሚኖሩ ቤተሰቦች ይሰባሰቡበታል። በዓለም ዙሪያ የሚገኙ ሀገራት እና ሙስሊሞች በዓሉን የሚያከብሩበት ሂደት ከባሕል እና ከእሴት ልዩነት ጋር በተያያዘ የሚያከብሩበት አውድ ከቦታ ቦታም ይለያያል። ኢድ አል_አድሃ(አረፋ)ከኢድ አልፈጥር በተለየ መልኩ በዓሉ የሚከበርበት ቀን የጨረቃን መታየት መሠረት አያደርግም።
የተባበሩት አረብ ኤምሪትስ
የተባበሩት አረብ ኤምሪትስ ደግሞ ኢድ አል አድሃ (አረፋ)ን ለማክበር ሦስት ተከታታይ ቀናትን ይጠቀማሉ። ከኢድ አል አድሃ በዓል ቀድማ ያለችዋን ቀን በልዩ ትኩረት ሲያከብሯት ስያሜዋንም «አረፋ» ይሏታል። ከዋዜማው ቀን ጀምረው «ኢድ ሙባረክ» በመባባል የደስታ መልዕክት ይለዋወጣሉ።
ሕፃናት በበዓል አልባሳት ደምቀው የኢድ ስጦታ ለጎረቤቶቻቸው በማበርከት ያሳልፋሉ። እናቶች መኖሪያ ቤቶቻቸውን በኢድ አርማ ያሳምራሉ፤ ተወዳጅ እና ጣፋጭ ምግቦች በተለየ ሁኔታ ለቤተሰቡ ይዘጋጃሉ።
በቱርክ
በቱርክ በመጀመሪያው የኢድ አል አድሃ ቀን ወንዶች ለተለየ ሃይማኖታዊ ሥርዓት ወደ መስጂድ በጠዋት ይሄዳሉ። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በቱርክ ለመስዋዕት የሚቀርበውን ገንዘብ እና እንስሳ ለበጎ አድራጎት ተቋማት ይሰጣል። ቱርካውያን በኢድ አል አድሃ ወቅት ለበዓሉ በሚመጥን አልባሳት ደምቀው ቤተ ዘመድ ይጎበኛሉ፤ ጥሪ አድርገው በቤታቸው ይጋብዛሉ፤ እንዲሁም የሀብት አቅም ለሌላቸው ወገኖች ድጋፍ ያደርጋሉ። ወጣቶች በጎረቤቶቻቸው ቤት በጠዋት እየሄዱ እንኳን አደረሳችሁ!!በማለት እጆቻቸውን በመሳም ይዘይራሉ። አንዳንድ ቱርካውያን ዓመታዊ እረፍታቸውንም በኢድ አል አድሃ አካባቢ ያደርጋሉ።
በሞሮኮ፣ ቱኒዚያ፣ ግብጽ፣ ኢትዮጵያ፣ ሱዳን እና በሌሎችም በርካታ የአፍሪካ እና የዓለም ሀገራት ኢድ አል አድሃ(አረፋ)በእስልምና ሃይማኖት ተከታዮች ዘንድ በተለያዩ ዓለም አቀፋዊ ድባቦች፣ በሰፊ ውብ ዝግጅቶች፣ በከፍተኛ ድምቀት ይከበራል።
ሁሉም የኢትዮጵያ ሕዝብ በቅርበት እንደሚያውቀው በኢትዮጵያ የእስልምና ሃይማኖት ተከታዮች በጠዋት ተነስተው፣ በሃይማኖታዊ ንፁህ አልባሳት ደምቀው እና አምረው ወደ መስገጃ አደባባይ እና ወደ መስጂዶች በረድፍ ሲያመሩ ሲታዩ የጎላ ውበት፣ አስደማሚ አንድነት ይንፀባረቃል። ሶላታቸውን በጋራ ሰግደው እና በአንድ ዓይነት መንፈሳዊ ቋንቋ አላህን አመስግነው፣ እርስ በእርሳቸው የመልካም ምኞት መግለጫ ተለዋውጠው፣ ከልብ የመነጨ ፈገግታ ተመጋግበው፣ አብረን ወደ ቤት እንግባ፣ አብረን እንዋል እያሉ ሲገባበዙ፣ በአክብሮት ሲጠራሩ ማዳመጥ፣ በተግባር መመልከት የተለመደ ነው።
ሲለያዩም በታላቅ ትህትና፣ በልዩ መተናነስ ታጅበው በመጡበት አኳኋን ወይም መንገድ ቀይረው ለፈጣሪ ምስጋና እያቀረቡ ወደ ቤታቸው ይመለሳሉ። ይሄ በኢትዮጵያዊ ጨዋነት የተሞላው መርሃ ግብር በሌላ እምነት ተከታይ ጓደኞች፣ የሥራ ባልደረቦች፣ ጎረቤቶች ዘንድ የማይረሳ የወዳጅነት ትዕይንት፣ የማይዘነጋ የአብሮነት እውነት እንደመሆኑ ከአደባባይ ሶላት በኋላ ደግሞ የእርድ ሥርዓት በየቤታቸው/በየሰፈራቸው/ይኖራል። ቤተሰብ ተሰብስቦ በጋራ ያከብራል፤ ያለው ለሌለው ያካፍላል፤ እንዲሁም ከጎረቤቶቻቸው ጋር በመጠራራት ይገባበዛሉ።
ለጥንቃቄ ሲባል ከእርድ ሥርዓት ቀደም ተብሎ የሌላ ሃይማኖት ተከታይ ወዳጆች፣ ጎረቤቶች ተጠርተው እና ተጋብዘው፣ በጥልቅ የፍቅር ነፃ መንፈስ ተጫውተው«ኢድ ሙባረክ»እየተባባሉ፣ በሰላም፣ በጤና ዘልቀው ቀጣዩን ዓመት ሳይለያዩ በደስታ፣ በጋራ እንዲያከብሩ መልካም ምኞታቸውን እየተገላለፁ፣ ከልብ እየተመራረቁ በፍፁም ኢትዮጵያዊ ለዛ ይገባሉ፣ ይወጣሉ።
መቼም ኢትዮጵያዊነት ይለያል አይደል?
እኛም ለመላው የእስልምና ሃይማኖት ተከታዮች
«ኢድ ሙባረክ» ብለናል!!
የአሰላው ኃይረዲን ከድር/ከአዲስ አበባ/
አዲስ ዘመን ሰኔ 21/2015