እንደ መግቢያ
በአንድ አገር ውስጥ የሚኖረው እድገትም፣ ውድቀትም በሰው ኃይሉ ላይ ይመሰረታል፡፡ የሰው ኃይሉን በወጉ አስተምሮ ያመራመረ አገር ከችግሮቹ ተሻግሮ ይበለጽጋል። በአንጻሩ ትምህርት የምርምር እና ችግር ፈቺነት አቅም መገንቢያ አውድ መሆን ሳይችል ከቀረ ያ አገር ለፈተናዎች እጁን የሚሰጥ ትውልድ ይፈጥራልና በችግር ውስጥ መዳከር እጣ ፈንታው ይሆናል፡፡ ኢትዮጵያም እንደ አገር ከትናንት ተሻግራ ዛሬ ላይ ስትደርስ፤ ከዛሬም አልፋ ነገን ስታማትር በዚሁ የሰው ኃይሏ አቅምና ተፈጥሮ በለገሳት ሃብቷ ላይ ተማምና ነው፡፡
ከዚህ አኳያ በኢትዮጵያ ዘመናትን ያስቆጠረው የትምህርት ሥርዓት በየጊዜው እየታደሰና እየተሻሻለ ዘልቋል፡፡ ጊዜ በተለወጠና አዳዲስ ክስተቶች በተፈጠሩ ቁጥር አብሮ ሊለወጥ፣ ሁነቶችንና ክስተቶችን ባማከለ መልኩ ሊዘጋጅ የግድ ስለሆነም፤ ከ2010ሩ አገራዊ ለውጥ ማግስት እንዲለወጡና የሪፎርሙ አካል እንዲሆኑ ከተደረጉ ዘርፎች አንዱ የትምህርት ዘርፉና ሥርዓቱ ነው። በዚህም እንደ አገር አዲስ የትምህርት ፍኖተ ካርታ የተዘጋጀ ሲሆን፤ ፎኖተ ካርታውም በ2015 የትምህርት ዘመን ተግባራዊ መደረግ ጀምሯል፡፡
ይህ ፍኖተ ካርታ እንደ አገር የታዩ የትምህርቱ ዘርፍ ዝንፈቶችን ያቀናል፤ ችግሮችን ያርማል፤ ስብራቶችን ይጠግናል፤ በጥቅሉ በዘርፉ ያሉ ዘርፈ ብዙ ችግሮችን ቀርፎ ለአገር ሁለንተናዊ እድገትና ብልጽግና የራሱን አበርክቶ የሚያደርግ ትውልድን በእውቀትም፣ በክህሎትም፣ በአመለካከትና በሥነምግባርም አበልጽጎ ለመፍጠር ያስችላል የሚል እምነት ተጥሎበታል፡፡
አዲሱን የትምህርት ሥርዓት ወደ ተግባር ለማስገባት እሱኑ ማዕከል ያደረገ አደረጃጀትና የመማር ማስተማር አውድን መፍጠር ስለሚያስፈልግ በየደረጃው ይሄው ሲደረግ ቆይቷል፡፡ በዚህም ገሚሱ ዝግጅት ተጠናቅቆ፤ ገሚሱ ደግሞ ከትግበራውም ማግስት በሂደት ላይ ስለመሆኑ ይነገራል፡፡ በሂደት ላይ ካሉ ጉዳዮች እና በአዲሱ የትምህርት ሥርዓት ውጤታማነት ሚናቸው ጉልህ ከሆኑት መካከል ደግሞ የመማሪያ መጻሕፍት ተጠቃሽ ናቸው፡፡
መጻሕፍት፣ በመማር ማስተማር ሂደት ውስጥ ለተማሪዎች ብቻ ሳይሆን ለመምህራንም መሰረታዊ የሆኑ የትምህርት አጋዥ ግብዓቶች ናቸው፡፡ ትምህርትን ያለ መጻሕፍት መማር ማለት፤ እንጀራን ያለ ወጥ እንደመመገብ የሚተናነቅ እውነት ነው፡፡ እንዴት ቢሉ፣ ምንም እንኳን እንጀራ ባማረ መሶብ/ሌማት ቢቀርብም ያለ ወጥ ምሉዕ እንደማይሆን ሁሉ፤ የመማር ማስተማር ሂደትም ትምህርት ቤቶች፣ የመማሪያ ክፍሎች እና ሌሎች ቁሳቁሶች ተውበውና ተሟልተው ቢዘጋጁም ያለመማሪያ መጻህፍት የሚፈለገውን እውቀት ለማስረጽ ፈታኝ ነው የሚሆነው፡፡
ከዚህ አንጻር ሲታይ፣ በ2015 ዓ.ም ወደ ትግበራ የገባው አዲሱ ፍኖተ ካርታ/የትምህርት ሥርዓት፤ እሱን ያገናዘበ መጻሕፍት ተዘጋጅተውለትና ታትመው ለተማሪዎች በማድረስ በኩል ችግር ታይቷል፡፡ የትምህርት ዘመኑም መጻሕፍት በተቀመጠላቸው የጊዜ ሰሌዳ መሰረት ታትመው ለተማሪዎች ያልደረሱበት፤ ተማሪዎች ከመጻሕፍት ጋር ተነፋፍቀው ያሳለፉበት፤ በዚህም የመማር ማስተማሩ ሂደት ከፍ ያለ ችግር ላይ የወደቀበት፤ ተማሪዎች፣ መምህራንና ወላጆች ጭምር እጅጉን የተፈተኑበት ሆኖ ተጠናቅቋል፡፡
የትምህርት ጅማሮው ዝግጅት በኢትዮጵያ ያሉ ትምህርት ቤቶች በኢትዮጵያ የዘመን ቀመር መሰረት መስከረም መጀመሪያው ላይ የመማር ማስተማር ሂደታቸውን እንደሚጀምሩ ይታወቃል፡፡የመማር ማስተማር ሂደታቸውን ሲጀምሩም ከተማሪዎች ምዝገባ ቀጥሎ የሚሆነው ተግባር የመማሪያ መጻሕፍትን ለተማሪዎች ማድረስ ነው፡፡ ይሄ የየዓመቱ የትምህርት ቤቶች ተግባር ቢሆንም የ2015 በጀት ዓመት ግን ከመማሪያ መጻሕፍት አኳያ የተለየ ገጽ ነበረው፡፡
እንዴት? ከተባለም ለዚህ የሚሆኑ አንዳንድ ማሳያዎችን እነሆ፡፡ ዋልታ ኢዜአን ጠቅሶ እና በኦሮሚያ ትምህርት ቢሮ የትምህርት ቤቶች ማሻሻያ ፕሮግራም ዳይሬክተር ወርቅነህ ነጋሳን ዋቢ አድርጎ መስከረም 3 ቀን 2015 ዓ.ም እንደዘገበው፤ በኦሮሚያ ክልል በሁሉም ትምህርት ቤቶች የመማር ማስተማር ስራ ከማስጀመር ባሻገር፤ የመምህራን ዝግጅት፣ የመማሪያ መጻሕፍት ማዘጋጀትና የትምህርት ቤቶች ዝግጅት ስራ ተከናውኗል፡፡
በዝግጅት ምዕራፉ 34 ሺሕ ተጨማሪ የመማሪያ ክፍሎችን የገነባው ክልሉ፤ በትምህርት ዘመኑ በክልሉ 11 ነጥብ 3 ሚሊዮን (በኋላ ላይ ስምንት ሚሊዮን 28 ሺህ 958 ተማሪዎች በክልሉ በትምህርት ላይ ያሉ መሆናቸው መገለጹን ልብ ይሏል) ተማሪዎችን ለመቀበል የሚያስችል ዝግጅም ተጠናቅቋል፡፡
16 ሺሕ የሚጠጉ የመጀመሪያና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች አሉኝ ያለው የኦሮሚያ ክልል፤ በሁሉም የክልሉ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤቶች የሚሰጠው በአዲሱ ሥርዓተ ትምህርት እንደመሆኑ በአዲሱ ሥርዓተ ትምህርት መሰረት የተማሪዎች መማሪያ መጻሕፍት እንደ ቀድሞው የታተሙ መጻሕፍትን ሳይሆን ”ሶፍት ኮፒ”ያቸውን ለሁሉም ትምህርት ቤቶች ማድረሱን አሳውቆ ነበር፡፡
እንደ ኦሮሚያ ትምህርት ቢሮ ሁሉ፣ በትምህርት ዘመኑ ለሰባተኛ እና ለስምንተኛ ክፍል ተማሪዎች 133 ሺህ ያህል መጻሕፍትን በሁለተኛው መንፈቀ ዓመት መገባደጃ ላይ ከማከፋፈል የዘለለ መስራት ያልቻለው የአፋር ክልል ትምህርት ቢሮም፤ ቀሪዎቹ መጻሕፍቶች እስከ ሰኔ መጨረሻ ድረስ ህትመታቸው እንደሚጠናቀቅ ቃል ከመግባት ያለፈ ነገር ማድረግ አልቻለም፡፡ በወቅቱ መጻሕፍትን አትሞ ያላደረሳቸው ከአንደኛ እስከ ስድስተኛ ክፍል ላሉ ተማሪዎች በሶፍት ኮፒ ለማድረስ ነበር ጥረት ሲያደርግ የቆየው፡፡
የዋና ከተማዋ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮም ቢሆን ከዚህ የተለየ አይደለም። ምክንያቱም፣ መስከረም መጀመሪያ ላይ የመማር ማስተማር ስራውን አስጀመርኩ ያለው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ፣ ትምህርት ቤቶች የመማር ማስተማር ስራቸውን ከመጀመራቸው ቀደም ብሎ የቅድመ ዝግጅት ስራዎች ስለመከናወናቸው አሳውቆ ነበር፡፡
ለአብነት፣ ጳጉሜን 2014 ዓ.ም የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት የከተማዋ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ዶክተር ዘላለም ሙላቱን ዋቢ አድርጎ ያወጣው መረጃ እንደሚያሳየው፤ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ስር የሚገኙ በሁሉም ትምህርት ቤቶች የመማር ማስተማር ስራ ከመጀመራቸው በፊት የቅድም ዝግጅት ስራዎች ተከናውነዋል፡፡ በአዲሱ የትምህርት ስርዓት መሰረት
የተዘጋጁ መጻሕፍት ህትመታቸው ተጠናቅቆ እስኪሰራጩም “ሶፍት ኮፒ”ያቸው ለትምህርት ቤቶችን እንዲደርሱ ተደርጓል፡፡
የታተሙ መጽሓፍትን የማድረስ ቃልና ትግበራው የመማሪያ መጽሓፍት ለመማር ማስተማር ሂደት አይተኬ ሚና ያላቸው ቢሆንም፤ በ2015 የትምህርት ዘመን እነዚህ መጽሓፍት ከተማሪዎች ጋር ሳይተዋወቁ ዓመቱ መጠናቀቁ ይታወቃል፡፡ በዚህ ረገድ ዘግይቶም ቢሆን ለተማሪዎች እናደርሳለን ሲሉ የነበሩ የከተማ አስተዳደሮች እና ክልሎች ቢኖሩም፣ በቃላቸው መሰረት መገኘት ሳይችሉ ነው ተማሪና የመማሪያ መጽሓፍት እንደተነፋፈቁ የትምህርት ዘመኑ የተጠናቀቀው፡፡ ለዚህ ማሳያ የሚሆኑ አንድ ሁለት መረጃዎችን ለመጥቀስ ልሞክር፡፡
መስከረም መጀመሪያ ላይ የመማር ማስተማር ስራውን አስጀመርኩ ያለው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ፣ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ስር የሚገኙ በሁሉም ትምህርት ቤቶች የመማር ማስተማር ስራ ከመጀመራቸው በፊት የቅድም ዝግጅት ስራዎች ስለማከናወኑ አሳውቆ ነበር።
ይሄ የቅድመ ዝግጅት ተግባር ደግሞ የትምህርት ቤቶች እድሳትን፣ የአዲሱ ሥርዓተ ትምህርት የመጻሕፍትን ማስተዋወቅ እና የትምህርት ጉባዔ ማካሄድን ያካተተ ነው፡፡ ሆኖም የመጻሕፍት ዝግጅትና ስርጭትን አስመልክቶ የቢሮው ኃላፊ ህዳር 19 ቀን 2015 ዓ.ም ለአዲስ ዘመን ጋዜጣ በሰጡት ማብራሪያ፣ የመጻሕፍቶቹ ሶፍት ኮፒ ለየትምህርት ቤቶቹ ደርሶ የመማር ማስተማር ስራው እንዲጀመር ተደርጓል፡፡ ከዚህ በተጓዳኝም ከተማ አስተዳደሩ መጻሕፍቱን በኮፒ ደረጃ በማዘጋጀት 1 ነጥብ 5 ሚሊየን የሚደርሱትን ለትምህርት ቤቶች አሰራጭቷል፡፡
ይህ እንደተጠበቀ ሆኖ፣ እስከ ህዳር 30 ድረስ የመጻሕፍቱ ህትመት ተጠናቅቆ 80 በመቶ የሚሆነው ስርጭት የሚከናወን ስለመሆኑ የቢሮው ኃላፊ መግለጻቸው ተነግሮ ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ ያለውን ሂደት ግን ከሚዲያዎችም፣ ከትምህርት ቢሮውም ይሄ ነው የሚል መረጃ ሊገኝ አልቻለም፡፡ ሆኖም እንደ ሌሎች ክልሎች ሁሉ በአዲስ አበባም ያሉ ትምህርት ቤቶች እና ተማሪዎች ከመማሪያ መጻሕፍት ጋር እንደተነፋፈቁ የትምህርት ዘመኑን ስለማጠናቃቸው ሌላ ነጋሪ ሳያሻን በየቤታችን ያሉ ተማሪዎችን ቦርሳ መመልከቱ በቂ ማስረጃ ይመስለኛል፡፡
እንደ አዲስ አበባው ሁሉ፣ በአፋር ክልልም ከ730 ሺህ በላይ የመማሪያ መጻሕፍት ህትመት እየተከናወነ ስለመሆኑ የካቲት 8 ቀን 2015 ዓ.ም አዲስ ዘመን ጋዜጣ ይዞት በወጣው ዘገባ አስነብቧል፡፡ ጋዜጣው የአፋር ክልል ትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ አብዱ ሀሰንን ዋቢ አድርጎ እንዳስነበበው፤ በክልሉ ከአንደኛ እስከ ስምንተኛ ክፍል ለሚገኙ ከ186 ሺህ በላይ ተማሪዎች በየትምህርት ዓይነቱ በአዲሱ የትምህርት ፖሊሲ መሰረት የተዘጋጁ 730 ሺህ 633 መጻሕፍት ህትመት እየተከናወነ ነው፡፡
በዚሁ ጋዜጣ ሰኔ 12 ቀን 2015 ዓ.ም በወጣ መረጃ ደግሞ፤ በክልሉ ለሰባተኛ እና ስምንተኛ ክፍል ተማሪዎች 133 ሺህ በላይ መጻሕፍት ህትመት ሙሉ በሙሉ ተጠናቅቆ መሰራጨታቸውን፤ እና ከ730 ሺህ በላይ መጻሕፍት ደግሞ በ150 ሚሊዮን ብር ወጪ ህትመታቸው እየተከናወነ መሆኑ ተዘግቧል፡፡
ከዚህ ዘገባ መረዳት የሚቻለው፣ ክልሉ በሁለተኛው ወሰነ ትምህርት እንኳን ለሰባተኛ እና ስምንተኛ ክፍል ተማሪዎች መጽሓፍትን በጊዜው ማድረስ ካለመቻሉም በላይ፤ ከአንደኛ እስከ ስድስተኛ ክፍል ያሉት መጻሕፍት ህትመት ባለመከናወኑ ተማሪዎች መጽሓፍትን ሳያገኙ ዓመቱን ለማጠናቀቅ ተገድደዋል፡፡
11 ነጥብ 3 ሚሊዮን ተማሪዎችን ለመቀበል ተዘጋጅቻለሁ(ምንም እንኳና በኋላ ላይ በክልሉ ስምንት ሚሊዮን 28 ሺህ 958 ተማሪዎች መኖራቸውን ቢገለጽም)፣ መጻሕፍቶቹንም በሶፍት ኮፒ ለሁሉም ትምህርት ቤቶች አድርሻለው ያለው ኦሮሚያ ክልልም ቢሆን፤ የመጻሕፍት ህትመትና ሥርጭትን ጉዳይ በሁለተኛው መንፈቀ ዓመት እንደጀመረው መረዳት ይቻላል፡፡ ለምሳሌ፣ ጥር 13 ቀን 2015 ዓ.ም የወጣ መረጃ እንደሚያመለክተው፣ በክልሉ በትምህርት ገበታ ላይ ላሉ ተማሪዎች የአንድ ነጥብ ሰባት ሚሊዮን መጻሕፍትን ብቻ ነው ህትመታቸውን ተጠናቅቆ ማሰራጨት የቻለው፡፡
ከዚህ ውጪ ያለው ተማሪ ገና ከመጻሕፍቱ ጋር ያልተዋወቀ ከመሆኑም በላይ፤ 35 ሚሊዮን የሚሆኑ የመማሪያ መጻሕፍት ገና በህትመት ሂደት ላይ ያሉ ናቸው፡፡ ችግሩ መጻሕፍቶቹ ህትመታቸው መዘግየቱ ብቻ አይደለም፤ ይልቁንም እነዚህ መጻሕፍት ቢታተሙ እንኳን ሊያዳርሱ የሚችሉት የክልሉን ግማሽ ያህል ተማሪዎች ብቻ ነው፡፡
የዚህ ማረጋገጫ የሚሆነው ደግሞ በክልሉ ትምህርት ቢሮ በምክትል ቢሮ ኃላፊ ደረጃ የኦሮሚያ ትምህርት ቢሮ አማካሪ አቶ ኤፍሬም ተሰማ ተናገሩት የተባለው ሲሆን፤ ይሄም የአንደኛ ደረጃ ትምህርት የመማሪያ መጻሕፍትን ለሁሉም ተማሪዎች ተደራሽ ለማድረግ በአጠቃላይ 74 ሚሊዮን መጻሕፍት ያስፈልጋሉ ማለታቸው ነው፡፡
የመጻሕፍቱ አለመድረስና ተጽዕኖው በመማር ማስተማር ሂደት ውስጥ የመማሪያ ጻሕፍት ምን ያህል ዋጋ እንዳላቸው ለማወቅ የግድ በትምህርት ዓለም ውስጥ መኖርን አይጠይቅም፡፡ ምክንያቱም ይብዛም ይነስም ሁሉም በዚሁ መስመር አልፎ አይቶታልና። በመሆኑም በ2015 የትምህርት ዘመን በሥራ ላይ እንዲውል የተወሰነውን አዲስ ሥርዓተ ትምህርት ተከትሎ የተዘጋጁ መጻሕፍት ለተማሪዎች አለመድረሳቸው ከፍ ያለ ተጽዕኖ መፍጠራቸው እሙን ነው፡፡ ይሄ ተጽዕኖ ደግሞ የትምህርት ጥራት ችግር አንድ ጉዳይ ተደርጎ የሚወሰድ ነው፡፡
ምናልባት ለመጻሕፍቱ በጊዜ አለመድረስ ትምህርት ሚኒስቴርም ሆነ ቢሮዎች የየራሳቸውን ምክንያት ሊያቀርቡ ይችላሉ፡፡ በርግጥም በተለያዩ ጊዜያት እንደምንሰማው የመማሪያ መጻሕፍት ለተማሪዎች በወቅቱ ታትመው ለተማሪዎች ላለመድረሳቸው ቢሮዎቹ የየራሳቸውን ምክንያት ሲያቀርቡም ነበር፡፡ በዚህም ማተሚያ ቤቶች፣ በጀት፣ የውጭ ምንዛሬ እና የወረቀት ችግር፣ የታተሙ መጻሕፍትን ለማሰራጨት የሚወስደው ጊዜን የመሳሰሉት በ”እናቴ መቀነት አደናቀፈኝ”ነት ምክንያት ሲደረድሩ ተደምጠዋል፡፡
ይሁን እንጂ ይሄ የምክንያት ጋጋታ መጻሕፍት ለተማሪዎች በወቅቱ ተደራሽ ባለማድረጋቸው በመማር ማስተማር ሂደት ላይ የሚፈጠረውን ከፍ ያለ ተጽዕኖ አያስቀረውም፡፡ ምክንያቱም፣ መጻሕፍቱ በወቅቱ ለተማሪዎች ባለመድረሳቸው ተማሪዎች በክፍል ውስጥም ሆነ ከክፍል ውጪ እንዲሰሯቸው የሚሰጧቸውን መልመጃዎችን እንዳይሰሩ መሆናቸው፤ ከመጻሕፍቱ ተጨማሪ ሃሳቦችን አንብበው ለመረዳትና እውቀትን ለማንበር መቸገራቸው፤ መምህራንም ለተማሪዎች ማስታወሻን በጥቁር ሰሌዳ ላይ በመጻፍ የትምህርት ጊዜያቸውን እንዲያባክኑ መገደዳቸው በግልጽ ታይቷል፡፡
የዘርፉ ምሑራን፣ መምህራን፣ ተማሪዎች እና ወላጆች ጭምር ይሄንኑ ሲናገሩ ቆይተዋል፡፡ ካለው ተጨባጭ ሁኔታም ሆነ ከወላጆች፣ ከተማሪዎችና ከመምህራን የዓመት ሙሉ ጥያቄና ቅሬታ መረዳት እንደሚቻለው፤ በአዲሱ ሥርዓተ ትምህርት የተዘጋጁትን መጻሕፍት መምህራን እና ተማሪዎች ባለማግኘታቸው የመማር ማስተማር ሂደቱን ለማሳለጥ ክፍተት መፍጠሩን ነው፡፡
ምክንያቱም እንደ ኢትዮጵያ ባሉ የቴክኖሎጂው መሰረተ ልማት ባልተስፋፋባቸው እና ትምህርት ቤቶቹም ከፍ ያለ የመሰረታዊ መሰረተ ልማት ፈተና ውስጥ ባሉ አገር ቀርቶ፤ የተሻለ አቅም አላቸው በሚባሉትም ቢሆን የመማር ማስተማር ሂደት ከመማሪያ መጻሕፍት ተፋትቶ የተከወነበት አጋጣሚ እምብዛም የሚታወስ አይደለም፡፡
በኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ ደግሞ፣ በአንድ በኩል የኢንተርኔትና ተያያዥ መሰረተ ልማቶች ያልደረሱባቸው አከባቢዎች የበዙ መሆናቸው፤ በሌላም በኩል ከህብረተሰቡ የኑሮ ደረጃ አኳያ የስማርት ስልኮችን፣ ታብሌቶችንና ላፕቶፖችን ከሚጠቀመው ማህበረሰብ አኳያ ሲታይ እነዚህን የመማሪያ መጻሕፍት በሶፍት ኮፒ ጥቅም ላይ ማዋልን አማራጭ አድርጎ ሙሉ የትምህርት ዘመን መጨረስ ጉዳቱን ያጎላዋል፡፡
ለዚህም ነው ወላጆች ለልጆቻቸው ሲጨነቁ፤ መምህራን በማስተማር ሂደቱ ሲባትሉ፤ ተማሪዎችም ከመጽሓፍ ውጪ በሆነው የመማር ማስተማር ሂደት ሲቸገሩ የተስተዋለው፡፡ ይህ ሁኔታም ለትምህርት ጥራት ከሚኖረው ጉዳት አንጻር የዘርፉ ምሑራንም ስለ አሉታዊ ተጽዕኖው ደጋግመው ሲገልጹ የተስተዋለው፡፡
ዘመኑ ከሚጠይቀው የመማር ማስተማር ሥነ-ዘዴ መምህር ተኮር ሳይሆን ተማሪ ተኮር ከመሆኑ አኳያም፤ የመማር ማስተማር ሂደቱ የተማሪዎች ቀድመው ማንበብና ራሳቸውን ለውይይት ማዘጋጀትን የግድ ይላል፡፡ ታዲያ ተማሪዎች መጻሕፍትን አግኝተው ይሄን ማድረግ ካልቻሉ፤ በመማር ማስተማር ሂደቱ የሚፈለገው የውይይትና የእውቀት ሽግግር እውን መሆን አይችልም፡፡
ይሄንን ተጽዕኖ አስመልክቶ ከሰሞኑ በአዲስ ዘመን ጋዜጣ ሃሳባቸውን የገለጹ ምሑራን እንዳሳሰቡትም፤ በአዲሱ ስርዓተ ትምህርት መሰረት የተዘጋጁ መጻሕፍትን በቶሎ ታትመው ለተማሪዎች በማድረስ በኩል ያሉ ክፍተቶች ቶሎ ካልተቀረፉ፤ አንድም ተማሪዎች በአግባቡ አንብበው ተገቢውን እውቀት እንዳይጨብጡ እንቅፋት ይፈጥራል፡፡ ሁለተኛም መምህራን ላይ ጫና በመፍጠር የትምህርት የጥራት መጓደልን ያስከትላል፡፡ ስለሆነም በተቻለ ፍጥነት መጻሕፍቱ ታትመው ለተማሪዎች እንዲደርሱ መሥራት ከሁሉም አካል የሚጠበቅ ትልቅና ቅድሚያ የሚሰጠው የቤት ሥራ መሆን አለበት የሚል ነበር፡፡
በቀጣዩ የትምህርት ዓመት ከመማሪያ መጻህፍት አቅርቦት ጋር በተያያዘ ተማሪዎች እና መጻሕፍት ተራርቀው ያሳለፉበት 2015 የትምህርት ዘመን፤ ቀደም ብሎ ለመጥቀስ እንደተሞከረው በመማር ማስተማር ሂደቱ ላይ ካሳደረው ጫና እንዲሁም በትምህርት ጥራት ላይ ከሚፈጥረው ተጽዕኖ በተጓዳኝ፤ ከፍ ያለ ቅሬታን ይዞ አልፏል፡፡
ይሄ ጫና ሳይቃለል ቅሬታውም መልስ ሳያገኝ ደግሞ የ2016 ትምህርት ዘመን ደረስኩ ደረስኩ እያለ ነው፡፡ ዋናው ጥያቄ ታዲያ ቀጣዩ የትምህርት ዘመን (2016) እንደ አለፈው (2015) ሁሉ ተማሪና መጻሕፍት ተነፋፍቀው የሚያሳልፉበት ይሆናል? ወይስ ከተግባር የተፋታው የትምህርት ቢሮዎች ቃል ታድሶ መጻሕፍትና ተማሪዎች በትምህርት ቤታቸው ለመገናኘት እድል ያገኛሉ? የሚለው ነው፡፡
በዚህ ረገድ ቢሮዎቹ የየራሳቸው ተግባራዊ ምላሽ ሊኖራቸው ቢችልም፤ ቀደም ሲል ከነበረው አፈጻጸማቸውና ብሂላቸው አኳያ ግን አሁንም የሚነሱ ስጋቶች አሉ፡፡ ለምሳሌ፣ በኦሮሚያ ክልል በ2015 ቀድመው ታትመው ለተማሪዎች የተሰራጩ መጻሕፍት ክልላዊ ፈተና የሚወስዱ የስምንተኛ ክፍል ተማሪዎችን ማዕከል ያደረገ ነበር፡፡ በሂደት እየታተሙ በስርጭት ላይ የነበሩት የአንደኛ፣ የሦስተኛ፣ የአምስተኛ እና የሰባተኛ ክፍል መጻሕፍት ናቸው፡፡
የሁለተኛ፣ የአራተኛ እና የስድስተኛ ክፍል ተማሪዎች የመማሪያ መጻሕፍትም እስከ መስከረም ወር ድረስ ሙሉ በሙሉ ታትመው ለ2016 የትምህርት ዓመት ለተማሪዎች እንዲደርሱ የሚደረጉ ናቸው፡፡ በጥቅሉ ሲታይ ግን በሕትመት ላይ የነበሩት 35 ሚሊዮን መጻሕፍትም ለ2015 ሊከናወኑ በእቅድ የተያዙ ናቸው፡፡
ከዚህ አንጻር ሲታይ 2016 የትምህርት ዘመን ተማሪው መጻሕፍትን አግኝቶ ትምህርቱን ለመከታተል የሚችልበት እድል ስለመፈጠሩ እርግጠኛ መሆን ስለማይቻል፤ ከወዲሁ በምክንያት ከመታጠር ወጥቶ መጻሕፍትን አሳትሞ ለ2016 የትምህርት ዘመን ለተማሪዎች የማድረስ ጉዳይ ተገቢው ትኩረት ተሰጥቶት ሊሰራበት ይገባል፡፡
በአፋር ክልልም ቢሆን፣ በሁለተኛው መንፈቀ ዓመት መጻሕፍት እንደደረሳቸው ከተነገረው የሰባተኛ እና ስምንተኛ ክፍል ተማሪዎች ውጪ፤ ከአንደኛ እስከ ስድስተኛ ክፍል ያሉ ተማሪዎች ዛሬም ድረስ ከአዲሶቹ መጻሕፍት ሳይገናኙ የትምህርት ዘመኑን አጠናቅቀዋል፡፡ በሶፍት ኮፒ ማግኘት የቻሉትም ቢሆኑ፤ በክልሉ ካለው የኢንተርኔትና መሰረተ ልማትም ሆነ በሌሎች በበርካታ ምክንያቶች በሚፈለገው ልክ ላይጠቀሙበት ይችላሉ፡፡
ከዚህ አኳያ የክልሉ ትምህርት ቢሮም ችግሩን የተገነዘበው ስለመሆኑ ቀደም ሲል የተጠቀሱት መረጃዎች ያሳያሉ፡፡ በመሆኑም የክልሉ መንግሥት በ2015 የትምህርት ዘመን የታየውን የመማሪያ መጻሕፍት እጥረት በመፍታት በ2016 የትምህርት ዘመን ለእያንዳንዱ ተማሪ የሚያስፈልገውን መጻሕፍት ለማዳረስ እየሰራ ስለመሆኑ ነው የተገለጸው፡፡
ሆኖም ይሄም እንደ 2015 የትምህርት ዘመን ሁሉ ከእቅድነት ያላለፈ ምኞት እንዳይሆን ከወዲሁ በልዩ ትኩረት መስራትና ቃልን በተግባር ማዋል፤ የቀደመውን አካሄድ መቀየር እና ተማሪዎችን ከመጻሕፍት ማገናኘት እጅጉን አስፈላጊ ነው፡፡ ይሄ ማሳሰቢያ፣ በማሳያነት ለተነሱት የኦሮሚያ እና አፋር ክልሎች ብቻ አይደለም። ይልቁንም ለሁለቱም ከተማ አስተዳደሮች እና ለሁሉም ክልሎች ትምህርት ቢሮዎች እንጂ፡፡
ምክንያቱም፣ በመጀመሪያ ሥራው ሁሉን አቀፍ ትኩረት የሚሻ ነው፡፡ ሲቀጥል በምክንያት ተከብቦ ውጤት መጠበቅ ስለማይቻል ነው፡፡ እንዴት ካሉም፣ ምክንያት በመደርደር በተማሪዎች፣ በመምህራንና ወላጆች ላይ የሚፈጥረውን ጫና መቀነስ አይቻልም፤ ምክንያት በመደርደር የመጻሕፍት በወቅቱ ያለመድረስ በትምህርት ጥራት ላይ የሚፈጥረውን አሉታዊ ተጽዕኖ አያስቀርም፤ ምክንያት መደርደር የተሟላ የኢንተርኔት መሰረተ ልማት የማያገኙ እና በኑሮ ደረጃ ምክንያት ላፕቶፕ፣ ታብሌት እና ስማርት ስልክ ማግኘት የማይችሉ ተማሪዎች ከመጻሕፍቱ ሳይተዋወቁ አንድ ዓመት ያሳለፉበትን ሂደት አይቀይርም።
በመሆኑም ቃልን በተግባር ለማዋል ምክንያት ሳይሆን ትጋት እጅጉን አስፈላጊ መሆኑን ተረድቶ፤ ይታተማሉ ወይም እየታተሙ ነው የሚባሉ መጻሕፍት በወቅቱ ትምህርት ቤቶች እንዲደርሱ ማድረግ፤ ትምህርት ቤቶችም ያለመሳቀቅ መጻሕፍቱን ለተማሪዎቻቸው እንዲያድሉ፤ ተማሪዎችና መምህራኑም በመጻሕፍቱ አለመኖር ምክንያት ከሚደርስባቸው ጫና እንዲላቀቁ፤ ወላጆችም ከሚፈጠርባቸው ጭንቀት እንዲድኑ፤ ከዚህም በላይ እንዲያንሰራራ የሚፈለገው የትምህርት ጥራት ከምኞት ያለፈ እውነት እንዲሆን ማድረግ የቀጣዩ የትምህርት ዘመን ተማሪዎች ያለ መጻሕፍት የማይማሩበት ዓመት በማድረግ ውስጥ የሚገለጽ ውጤት ተደርጎ ሊወሰድ የተገባ ነው፡፡
በየኔነው ስሻው
አዲስ ዘመን ሰኔ 20/2015