ባለፉት አራት ዓመታት ውስጥ መንግሥት ትኩረት ሰጥቷቸው እየተሰሩ ካሉ አበይት ሀገራዊ ክንዋኔዎች መካከል የአረንጓዴ አሻራ /ሀገርን አረንጓዴ የማልበሱ ርብርብ ተጠቃሽ ነው። እስካሁንም በሀገር አቀፍ ደረጃ ሁሉንም ማህበረሰብ ባሳተፈ መልኩ 25 ቢሊዮን ችግኞችን መትከል ተችሏል፡፡
ዘንድሮም በተመሳሳይ መልኩ ኢትዮጵያን በአረንጓዴ የመሸፈን ተግባሩ ‹ነገን ዛሬ እንትከል› በሚል መሪ ቃል በጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ ፊታውራሪነት በሁሉም የሀገራችን ክፍል ተጀምሯል። በዚህ ሀገራዊ ንቅናቄ ላይ እንዳለፈው ጊዜ ሁሉም የማህበረሰብ ክፍል በበረታ ተነሳሽነት የራሱን አሻራ በማሳረፍ ይሁንታ እያሳየ ነው፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብርን በተመለከተ በተለያዩ ጊዜ የተለያዩ ንግግሮችን አድርገዋል። ካለፈው ጊዜ ተነስተን ወደ ዘንድሮው መሪ ቃል ስንመጣ የሚከተለውን እናገኛለን። ባሳለፍነው 2013 ግንቦት ወር መጨረሻ ላይ የችግኝ ተከላ መርሀ ግብሩን ባስጀመሩበት ወቅት የተናገሩት ንግግር የመርሀ ግብሩን አላማ በግልጽ ያሳየ እንደነበረ ይታወሳል፡፡
‹የችግኝ ተከላ መርሀ ግብሩ የአካባቢ ብክለትንና የአየር ንብረት ለውጥ የሚያስከትላቸውን ሀገራዊና ማህበራዊ ችግሮች ለመቅረፍና ለመመከት የወጣው የአራት አመት እቅድ አካል እንደሆነ በመጥቀስ በሚቀጥሉት ጊዜአትም ቀጣይነት እንደሚኖረው መናገራቸውን ማስታወስ እንችላለን፡፡
ቀጥሎ ባለው 2014 ዓ.ም ተመሳሳይ ንግግሮችን አድርገዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር እንደ አለም የተደቀነብንን የህልውና አደጋ የምንወጣበት ብቸኛ መንገድ እንደሆነ ከንግግራቸው ይዘት መረዳት ችለናል። ዘንድሮም ‹ነገን ዛሬ እንትከል› በሚለው የንቅናቄ ትግበራ ላይ የትናንቱን መሰል ንግግሮችን አድምጠናል፡፡
የአረንጓዴ አሻራ አላማ በየትኛውም ሀገርና ማህበረሰብ አንድ አይነት አላማ ያለው ነው።ሞትና ጉስቁልና ስጋቱ ለሆነው የአየር ለውጥ ለየትኛውም የሰው ልጅ እውቀትና መረዳት ተመሳሳይ ግንዛቤ ነው ያለው።አላማው ሁልጊዜም የሰው ልጅን ከአየርን ብረት ለውጥና ተያይዞ ከሚመጣው የህልውና አደጋ መታደግ ነው፡፡
ለዚህ ደግሞ አስተማማኙና ሁነኛው መፍትሄ በአረንጓዴ አሻራ አረንጓዴ ምድር መፍጠር ነው።የአረንጓዴ አሻራን ጥቅም ከአየር ንብረት ለውጥ ጋር ብቻ አያያዘን የምንጨርሰው ጉዳይ አይደለም። በየትኛውም የሰው ልጅ ጉዳይ ውስጥ ከፊት ተሰለፎ የምናገኘው ነው፡፡
የአረንጓዴ አሻራ እሳቤ የለውጥና የተሀድሶ ከዚህ ከፍ ካለው የጤናና የደስተኝነት ሰንደቅ እንደሆነ መረዳት ያሻል። አእምሮ ህልውናውን የሚያገኘው ከአካባቢው እውነታ ተነስቶ ነው። አካባቢ ስንል ደግሞ ከፍተኛውን ድርሻ የምንሰጠው በዙሪያችን ላለው ተፈጥሮና ሰው ሰራሽ መስተጋብር ነው፡፡
ይሄ መስተጋብር ለአእምሮ ምቹና ተስማሚ ካልሆነ አደጋው ብዙ ነው። ይሄን አይነቱን ችግር ለመቅረፍ በአረንጓዴ ልማት እሳቤ ውስጥ መቆም አማራጭ የሌለው ግዴታ ይሆናል። ከዚህ እውነት በመነሳት መንግሥት ለአየር ንብረት ለውጥ የሰጠው ቦታ ምን ያክል እንደሆነ ከትግበራው መረዳት ይቻላል፡፡
ከጉዳዩ አሳሳቢነት አንጻር መንግሥት ለአካባቢ ጥበቃ ትኩረት ሰጥቶ መንቀሳቀሱን ያለፉትን ሶስት አመታት ጨምሮ የዘንድሮውን ትግበራ ከነውጤታቸው ማየት ይቻላል። ከዚህ ቀደም መንግስት የጎረቤት ሀገራት ጉዳይ የኢትዮጵያ ጉዳይ እንደሆነ በመቀበል የችግኝ ተከላው መርሀ ግብር ከሀገር አልፎ ጎረቤት ሀገራት የደረሰ እንደነበር አይዘነጋም።
ችግኝ ተከላን በተመለከተ አብዛኛውን ጊዜ የምንታማበት አንድ ነገር አለ እርሱም ምንድነው ለመትከል የተነሳሳነውን ያክል ለእንክብካቤ አለመነሳታችን ነው።ከዚህ በፊት ብዙ ጊዜ ተክለን ከእንክብካቤና ከክትትል ማነስ ብዙ ችግኞች እንደደረቁብን እንሰማለን። ይህ የአሁኑ ህዝባዊ መነሳሳት ግን ከዚህ በፊት እንደነበረው አይደለም፡፡
ሁሉም ሰው የተከለውን ችግኝ እስኪጸድቅ ድረስ እንዲንከባከብና ኃላፊነቱን ወስዶ እንዲከታተል በሚያስችል ልክ የተገነባ ህዝባዊ እንቅስቃሴ በመሆኑ ብዙም ስጋት አለው ተብሎ አይታሰብም። እርግጥ ነው የተከልንውን ያክል ጸድቆልን አያውቅም።ያለፉት ሶስት አመታት የትግበራ አቅጣጫ ግን መትከልን ከመጽደቅ ጋር ያቆራኘ ሂደት ነበር፡፡
ከዚህ ባለፈ መንግሥት ከእቅዶቹ አንዱ በማድረግ ብዙ ኃይልና ገንዘብ መድቦ በኃላፊነት የሚያንቀሳቅሰው ስለሆነ በብዙ ኃላፊነት የታጀበ እንደሆነ ማረጋገጡ ተዐማኚነት ይሰጣል። ያለፉትን አመታት ብናይ እንኳን በሀገር አቀፍ ደረጃ ከተተከሉ ችግኞች ውስጥ አብዛኞቹ የጸደቁ ሲሆን ይሄም ማለት በመቶኛ ሲሰላ 87 ከመቶ የሚሆኑት ችግኞች በጥሩ ሁኔታ ላይ እንዳሉ በመንግሥት ደረጃ የተገለጸበት ሁኔታ እንደነበር ማስታወስ ተገቢ ነው፡፡
ከዚህ አኳያ የምንለፋው እና የምንደክመው ለለውጥ እና ለተሻለ እምርታ እንደሆነ በመረዳት ወደ ፊት መቀጠሉ አዋጭነት አለው። የአረንጓዴ አሻራ እሳቤ ዓለም አቀፍ እውቅና ያለው እሳቤ ነው። አለም በአየር ንብረት ለውጥ የመጣውንና ወደፊትም የሚመጣውን የህልውና ጥያቄ ለመቆጣጠር እንደዋና አማራጭ የያዘችው የችግኝ ተከላ ንቅናቄን ነው፡፡
በየአመቱ የክረምት ወርን ጠብቆ መንግሥት ችግኝ መትከልን እንደ ትልቅ ሀገራዊ አጀንዳ ይዞ በመንቀሳቀስ ላይ ያለው ከዚህ እውነታ በመነሳት ነው። ከፍ ብዬ ለመግለጥ እንደሞከርኩት የአረንጓዴ አሻራ እውነታ የአየር ንብረት ለውጥን በመከላከል ብቻ የሚያበቃ አይደለም ብዙ ትሩፋቶች ያሉት እሳቤ ጭምር ነው። እንዲህ አይነቱ ለጋራ ጥቅም የጋራ ተሳትፎን የሚሻ ልማት ደግሞ በመንግሥት ትከሻ ላይ የሚጣል ብቻ ሳይሆን የዜጎችም ይሁንታ ሊኖርበት የሚገባ ነው፡፡
አረንጓዴ አሻራ የአየር ንብረት ለውጥን ከመከላከል ጎን ለጎን ያለውን ሀገራዊ በረከት በሌላም መልኩ ሊገለጽ ይችላል ፤ኢትዮጵያ ሀገራችን በታላቁ የህዳሴ ግድብ ተስፋና ትንሳኤን በአንድነት ይዛ ለሌሎች ግድቦችም በመሰናዳት ላይ ያለች ተስፈኛ ሀገር ናት።
እየገነባነው ላለነውና ወደ ፊትም ሊገነቡ እቅድ ለተያዘላቸው ትልልቅ ኤሌክትሪክ ማመንጫ ግድቦች ዛሬ ላይ ችግኝ መትከላችን የውሃ እጥረትን ከመከላከል ባለፈ ጤናማና የተስተካከለ አካባቢ እንድናገኝ ይረዳናል። ጥቅሙ በዚህ የሚያበቃ አይደለም ድርቅና በርሃማነትን በመከላከል፣ ወቅቱን የጠበቀ ዝናብ በመስጠት ህልውናችንን የሚያረጋግጥልን ነው። በጸሀይ ጨረር የሚመጡ እንደ ካንሰርና የቆዳ በሽታዎችን ከመከላከል አኳያ አረንጓዴ አሻራ የጎላ ድርሻ አለው፡፡
ወደ ችግሩ ስንመጣ ደግሞ በአሁኑ ሰዓት የዓለም ትልቁ ስጋት የአየር ንብረት ለውጥ ስጋት እንደሆነ እንደርስበታለን። ጥናቶች እንደሚያሳዩት ከሆነ ደግሞ በአብዛኛው የዚህ ገፈት ቀማሽ ከሆኑ ሀገራት መካከል ድሀ ሀገራት ቀዳሚውን ስፍራ ይይዛሉ። ይህ ማለት ሀገራችን ኢትዮጵያን ጨምሮ መሰል ታዳጊ ሀገራት የገፈቱ ግንባር ቀደም ተጠቂዎች ናቸው ማለት ነው። ችግሩ ይሄ ብቻ አይደለም ከአየር ንብረቱ ለውጥ ጋር ተያይዘው የሚመጡ በርካታ ሀገራዊ ችግሮችም አሉ፡፡
እንደ በረከቱ ሁሉ የዝናብ እጥረትን በማስከተል ድርቅና መሰል ኢኮኖሚያዊ እንቅፋቶችን በመፍጠር በሀገርና ህዝብ ላይ የሚያሳድረው አሉታዊ ተጽዕኖ የት የሌሌ ነው። ተለምዶአዊ የአካባቢ ምህዳርን በመዛባት በሰው ልጅ ላይ እና ህይወት ባላቸው ማናቸውም ፍጡራን ላይ መጥፎ አሻራውን በማሳረፍ ህልውና አደጋ ላይ ይከታል፡፡
እንደነዚህ አይነት ተጨማሪ እንከኖች ታክለውብን ይቅርና ወትሮም ኑሯችን በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ ነው።ኃላፊነት እንደሚሰማው ዜጋ ግን ከመንግሥት ጎን በመቆም በአረንጓዴ አሻራው ላይ የበኩላችንን አስተዋጽኦ ብናደርግ አንድም ለራሳችን አንድም ለሀገራችን መትረፍ እንችላለን፡፡
ክረምቱ ሳያልፈን፣ ወቅቱም ሳይሄድብን መንግሥት በጀመረው በዚህ የአረንጓዴ መርሀ ግብር ላይ የነቃ ተሳትፎ በማድረግ ነጋችንን ብሩህ ማድረግ ከእያንዳንዳችን ይጠበቃል። የኢትዮጵያ አረንጓዴ መልበስ እንደመሪ ቃሉ ነገን ዛሬ መትከል ነው። ነገን ዛሬ መስራት ነው። ችግሮቻችንን ከወዲሁ መርታት ነው። ዛሬ ላይ የምንተክላት እና የምንከባከባት አንድ ችግኝ ነገ ላይ ለኔና ለእናንተ ብሎም ለልጆቻችን የህይወት ዋስትና ሆና መምጣቷ የማይቀር ነው፡፡
ከዚህ ጋር አያይዤ አንድ ገጠመኜን ላውጋችሁ። ከሰሞኑ አምስት ኪሎ ከሚገኘው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ሙዚየም ጎራ ብዬ ነበር። ግድግዳው ላይ ሌላ ዓለም፣ ሌላ ሰማይና ምድር የሚመስል ፍጹም የሚደንቅ አረንጓዴ የለበሰ አንድ ፎቶግራፍ ግድግዳው ላይ ተሰቅሎ ተመለከትኩ፡፡
ቀርቤ አየሁት..ከስሩ ያለውን ጽሁፍ ሳነበው ለካ ከሚሊዮን አመት በፊት የነበረችው የኛ ምድር ፎቶግራፍ ነበር። ከጎኑ በበርሀ የተዋጠችው አሁናዊ የምድራችን ገጽታ አለ። የሁለቱን ልዩነት በአግራሞት ነበር ያየሁት። ለመጪው ትውልድ የተራቆተችን ሀገር ማስረከብ የለብንም። ተባብረን ኢትዮጵያን አረንጓዴ ማልበስ አለብን። አረንጓዴ መሬት፣ አረንጓዴ ምድር ያስፈልገናል። በዚህ የተቀናጀ ልማት ውስጥ አረንጓዴ ምድር ብቻ ሳይሆን አረንጓዴ እሳቤም አብረን መፍጠር እንችላለን፡፡
የአየር ንብረት ለውጥ ሁሉንም ማህበረሰብ የሚያጠቃ የአለም በሽታ ነው። ዋናውና ብቸኛው መከላከያ መንገድ ዛፍ መትከል፣ ችግኞችን መንከባከብ ብቻ ነው። መንግሥት በያዘው የአረንጓዴ ልማት መርሀ ግብር ላይ በመሳተፍ ኢትዮጵያንና ምድሯን ከበርሀማነት መታደግ ለነገ የማንለው፣ ለማንም ሳይሆን ለራሳችን የምንውለው ቀዳሚ ውለታ ነው፡፡
ችግኝ በመትከል የአየር ንብረት ለውጥን ከመከላከል ጎን ለጎን መንግሥት ማህበረሰቡ ለምግብ የሚሆኑ ፍራፍሬዎችንና አትክልቶችንም እንዲተክልና ራሱን በምግብ እንዲችል እያደረገ ያለውም ጥረት የሚደነቅ ነው።አሁን ላይ ከችግኝ ተከላው እኩል ሁሉም በየደጁና በየጓሮው በከተማ ግብርና ራሱን ከወጪ ተከላክሎ ከጓሮው ቀጥፎ የሚበላበት ሁኔታ እየተፈጠረ ያለበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡
አዲስ አበባን ጨምሮ በርካቶች በዚህ የመንግሥት መርሀ ግብር ውስጥ በመሳተፍ በጓሮአችውና በግቢያቸው ውስጥ ለምግብ የሚሆኑ አትክልቶችን በመትከል ራሳቸውን በመደጎም ላይ እንደሆኑ በተለያየ ሚዲያ ላይ ምስክርነታቸውን ሲሰጡ እየተደመጠ ነው።በቀላል መንገድ፣ በትንሽ ቦታ ላይ ራስን ከወጪ መታደግ ዘመናዊነት ነው፡፡
ይሄ ተግባር በስፋት ተሰርቶበት ማህበረሰቡ ከጓሮው ቀጥፎ መብላትን ልምድ እንዲያደርግና ድህነትን አሸንፎ እንዲወጣ መንግሥት በያዘው በጎ መንገድ መቀጠል አለበት።በአንድ ድንጋይ ሁለት ወፍ ማለት ይሄ ነው።የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል ችግኝ እየተከሉ በዛውም ለህይወት አስፈላጊ የሆኑ ፍራፍሬና አትክልቶችን በመትከል ራስን በምግብ መቻል፡፡
ይህ ተግባር መንግሥትን እንደ መንግሥት ሲያስመሰግነው ማህበረሰቡን ደግሞ ከመጠበቅና ከልመና ወጥቶ በህይወት ለመኖር የተለያዩ አማራጮችን እንዲፈልግ መንገድ ይጠቁመዋል። ህይወት በብዙ አማራጮች የተከበበች ናት። ከመጠበቅ ወጥተን ለመኖር የሚያስችለንን ቀላልና አዋጪ ዘዴ ማየት ይኖርብናል፡፡
ገንዘብ አውጥተን መርካቶና አትክልት ተራ ድረስ ሄደን ጊዜና ጉልበታችንን ከምናባክን በአንድ እጃችን የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል ችግኝ እየተከልን በአንዱ ደግሞ ርሀባችንን የምናስታግስበትን አትክልትና ፍራፍሬ መትከልን ባህል ማድረግ ይኖርብናል። ገንዘብ ስላለን ብቻ መግዛት ሳይሆን በአቅማችን ማድረግ የምንችለውንም መሞከር ብልህነት ነው፡፡
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ሰኞ ሰኔ 19 ቀን 2015 ዓ.ም