የመውጫ ፈተና በእኛ የተጀመረ በእኛ የሚፈጸም አይደለም ። በመካከለኛው ዘመን ዩኒቨርሲቲዎች በአውሮፓ ማበብ ከጀመሩበት ከዛ እሩቅ ዘመን ጀምሮ ነበር ወደፊትም ይኖራል። በሀገራችን የቤተ ክህነት ትምህርትም ከንባብ ጀምሮ ዜማ፣ ቅኔና ትርጓሜ የማስመስከር ወይም የመውጫ ፈተና አላቸው። ከንባብ በኋላም ሌሎች ትምህርቶችን ለመቀጸል የመግቢያ ፈተናም አላቸው። ወደ ተነሳሁበት ሀሳብ ስመለስ በአለማችን የመጀመሪያው የመውጫ ፈተና የፓሪስ ዩኒቨርሲቲ በመካከለኛው ዘመን ትምህርታቸውን አጠናቀው ወደ ተጨማሪ ትምህርት ወይም ወደ ስራው ዓለም ከመቀላቀላቸው በፊት የተሰጠ ነው። ይህ የፈረንሳዩ ዩኒቨርሲቲ ተሞክሮ ወደ ተለያዩ የአውሮፓ ዩኒቨርሲቲዎች ሊስፋፋ እንደቻለ ድርሳናት ያትታሉ።
በአሜሪካ ዩኒቨርሲቲዎች ደግሞ ለተመራቂዎች የመውጫ ፈተና መስጠት የተጀመረው በ19ኛው መክዘ መገባደጃና በ20ኛው መክዘ መባቻ ነው። የሚሰጡትን ትምህርት ደረጃ ለመወሰንና ምሩቃኑ ለስራ ዝግጁ መሆናቸውን ለማረጋገጥ የመውጫ ፈተና መስጠት ተጀምሯል። የመጀመሪያው የአሜሪካ የዩኒቨርሲቲዎች የመውጫ ፈተና የተዘጋጀው በኮሌጅ የመግቢያ ፈተና ቦርድ ነው። በሀገራችንም እንዲህ ገለልተኛ ተቋም ኃላፊነቱን ቢወስድ መልካም ነው። በ20ኛው መክዘ አጋማሽ ላይ አብዛኛዎቹ ዩኒቨርሲቲዎች የየራሳቸውን የመውጫ ፈተና ማዘጋጀት ጀመሩ። የፈተናው ይዘትና ቅርጽ እንደየ ትምህርቱ አይነት ይለያያል። ነገር ግን ሁሉም ተማሪዎቻቸው በመረጡት የትምህርት መስክ የቀሰሙትን እውቀትና የተካኑትን ክህሎት በመውጫ ፈተና መመዘናቸው አንድ ያደርጋቸዋል።
ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ግን የዩኒቨርሲቲዎች የመውጫ ፈተና አወዛጋቢ እየሆነ ነው። በተማሪዎች ላይ አላስፈላጊ ጫና ከመፍጠር ባሻገር ፤ በሰለጠኑበት ትምህርት ምን ያህል ብቃት እንዳላቸውም በትክክል አይመዝንም ሲሉ ሚሞግቱ አሉ። በሀገራችን ደግሞ ከታች ጀምሮ መሠረት ያላሳዝናቸውን ዩኒቨርሲቲ ላይ መፈተን ምን ይሉታል የሚሉ፤ የትምህርት ጥራት ከታች ወይስ ከላይ ነው መጀመር ያለበት በማለት የሚሞግቱ አሉ። ጥያቄዎቹ ውሃ የሚያነሱ ቢሆንም፤ በሙግትና በጉንጭ አልፋ ክርክር ጊዜ የምናጠፋበት ጊዜ ላይ አይደለንም።
የትምህርት ጥራትን የማሻሻል እርምጃዎች ከታች ክፍልም ከዩኒቨርሲቲም መጀመሩ ተገቢ ነው የሚል ዕምነት አለኝ። አሁን እየተሰራ ያለው ከእነ ውስንነቱ በዚህ አግባብ ነው። ይሁንና አብዛኛዎቹ ዩኒቨርሲቲዎች የመውጫ ፈተና የተማሪዎቻችንን የዕውቀትና የክህሎት ብቃት ይመዝናል ብለው ስለሚያምኑ ገፍተውበታል። የመውጫ ፈተና ተማሪዎች ትምህርታቸውን ሲያጠናቅቁ የገበዩትን ዕውቀትና የተካኑትን ክህሎት በትክክል መጨበጣቸውን ለማረጋገጥ የሚሰጥ ፈተና ነው።
በሰለጠኑበት ትምህርት ብቃት አላቸው ወይስ የላቸውም ብሎ በማረጋገጥ መመረቅ አለመመረቃቸውን ለመወሰን ያስችላል። የመውጫ ፈተና ይዘትና ቅርጽ እንደየ ዩኒቨርሲቲውና እንደየ ስልጠና መርሀ ግብሩ ይለያያል። አንዳንድ ዩኒቨርሲቲዎች የቃል ፈተና ሲሰጡ፤ ሌሎች ደግሞ የቃል ወይም የተግባር ፈተና ሊሰጡ ይችላሉ። በነገራችን ላይ ለመውጫ ፈተናው የሚቀመጡ እጩ ምሩቃን ይሁን እንጅ፤ የዩኒቨርሲቲዎች ትምህርትና ስልጠና ምን ያህል ብቃትና ጥራት እንዳለው በተዘዋዋሪ ይለካል። ካስፈተኗቸው ተማሪዎች አብዛኛዎቹ መመዘኛውን በብቃት ካለፉ ይሰጡት የነበረው ትምህርት ጥራት እንደነበረው አንድ ማሳያ ሲሆን፤ በተቃራኒው ከሆነ ደግሞ የዩኒቨርሲቲው ትምህርትና ስልጠና ደካማ እንደሆነ ፍንጭ ሊሰጥ ይችላል። ወደ ሀገራችን ስንመለስ፤
በትምህርት ሚኒስቴር የከፍተኛ ትምህርት ልማት ዘርፍ የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት አገልግሎት ዘርፍ ዳይሬክተር ዶ/ር ኢዮብ አየነው፥ በመጭው ሀምሌ ወር መጀመሪያ ለሚሰጠው የዩኒቨርሲቲዎች የመውጫ ፈተና ዝግጅት እየተደረገ እንደሚገኝ፤ እስካሁን ባለው መረጃ መሰረት ከ240 ሺህ በላይ ተማሪዎች የመውጫ ፈተናውን ለመውሰድ የተመዘገቡ ሲሆን፤ ቁጥሩ ከዚህ በላይ ከፍ እንደሚል ይጠበቃል፡፡
ተማሪዎች ከወሰዷቸው የተለያዩ የትምህርት አይነቶች ውስጥ በአማካኝ ከ10 እስከ 17 የሚሆኑት ተለይተው በመውጫ ፈተናው እንደሚፈተኑ፤ በመንግሥት ዩኒቨርሲቲዎች በበይነ መረብ ለሚሰጠው የመውጫ ፈተናም ከ34 ሺህ በላይ ኮምፒውተሮች መዘጋጀታቸውን፤ የመብራት መቆራረጥ ችግር ቢያጋጥም እንኳን ጀኔሬተር የተዘጋጀ ሲሆን የኢንተርኔት እና ሌሎች ችግሮች እንዳያጋጥሙ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በቅርበት እየተሰራ ይገኛል። ከመጋቢት 15 ቀን ጀምሮ በ210 የትምህርት ፕሮግራሞች እየተዘጋጀ የሚገኘው የመውጫ ፈተናም ሙሉ በሙሉ በሚባል ሁኔታ ወደ መጠናቀቁ መቃረቡንም ዶ/ር ኢዮብ አየነው አንስተዋል።
የትምህርት ተቋማት ለተማሪዎችም የሥነ ልቦና እና የአቅም ግንባታ ስልጠናዎችን እየሰጡ እንደሚገኙ፤ በመመሪያው ላይ ትምህርት ሚኒስቴር በዓመት ሁለት ጊዜ የመውጫ ፈተና የሚሰጥ ሲሆን፤ የተቀመጠውን የመቁረጫ ነጥብ ማምጣት ያልቻሉ ተፈታኝ ተማሪዎችም ዝግጅት ካደረጉ በስድስት ወር ውስጥ ዳግም ተመዝግበው መፈተን ይችላሉ፡፡ ተማሪዎች መታወቂያ ከተሰጣቸው በኋላ በሚፈልጉት ቦታ ተመዝግበው መፈተን የሚችሉ ሲሆን ማንኛውም ተማሪ የመፈተኛ ክፍያ እየከፈለ ያለ ጊዜ ገደብ ይፈተናል ነው ያሉት በትምህርት ሚኒስቴር የከፍተኛ ትምህርት ልማት ዘርፍ የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት አገልግሎት ዘርፍ ዳይሬክተር ዶ/ር ኢዮብ አየነው።
ሚኒስቴሩ በ2010 ዓ.ም በወቅቱ ለነበሩ 36 ዩኒቨርሲቲዎች የመውጫ ፈተናን አስመልክቶ በላከው ደበዳቤ፣ ዩኒቨርሲቲዎች ትምህርታቸውን ተከታትለው ያጠናቀቁ የቅድመ ምረቃ መርሐ ግብር ዕጩ ምሩቃን ከመመረቃቸው በፊት አጠቃላይ ምዘና እንደሚወስዱና ብቃታቸው እንደሚረጋገጥ፣ ይህም ከ2011 ትምህርት ዘመን ጀምሮ በሁሉም የቅድመ ምረቃ ትምህርት መስኮች እንደሚሰጥና ተማሪዎችም አጥጋቢና ከዚያ በላይ ውጤት ማስመዝገብ እንደሚጠበቅባቸው አሳስቦ እንደነበር ይታወሳል፡፡ ይሁንና ከህግና ከሜዲካል ውጭ ፈተናው መሰጠት የሚጀመረው በዘንድሮው የትምህርት ዘመን ነው።
ዘንድሮ ግን 240 ሺህ ለሚደርሱ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች በበይነ-መረብ የመውጫ ፈተና ለመሥጠት መዘጋጀቱን የትምህርት ሚኒስትሩ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ የገለጹ ሲሆን፤ በ2015 ዓ.ም በመጀመሪያ ዲግሪ ፕሮግራም ለሚመረቁ ተማሪዎች የመውጫ ፈተና ለመሥጠት ዕቅድ ወይም ብሉ -ፕሪንት ተዘጋጅቷል፡፡ የመውጫ ፈተና የክፍያ ተመን ረቂቅ መመሪያ መዘጋጀቱንም በዚያ ሰሞን ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባቀረቡት ሪፖርት አብራርተዋል፡፡ የመውጫ ፈተና ስትራቴጂ ማስፈፀሚያ መመሪያ እና የድርጊት መርሐ-ግብር ዝግጅት ተጠናቋል፡፡ በመውጫ ፈተና የሚካተቱ የትምህርት ዓይነቶች ተለይተው በቅድመ-ምረቃ በሚሰጡ በሁሉም የትምህርት መስኮች የፈተና ንድፍ ማሳያ መዘጋጀቱን ማስረዳታቸውንም የምክር ቤቱ መረጃ ያመለክታል፡፡
በመውጫ ፈተናው አስፈላጊነት፣ የፈተና አወጣጥና አፈታተን ዝግጅት፣ በአጠቃላይ የትግበራ ሂደት እና ሊያመጣ በሚችለው ውጤት ዙሪያ ከተለያዩ የመንግስት ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ፕሬዚዳንቶች ጋር በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ምክክር የተደረገ ሲሆን፤ በትምህርት ሚኒስቴር የከፍተኛ ትምህርት ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ሳሙኤል ክፍሌ፤ በሚቀጥሉት አምስት ዓመታት የትምህርት ጥራትን ለማሻሻል ጠንካራ ትግበራና ርምጃዎች ይወሰዳል ባሉት መሠረት የተለያዩ ተግባራት ተከናውነዋል። የትምህርት ጥራትን ይደግፋል ተብሎ የታመነበት ስርዓተ-ትምህርትን መሰረት ያደረገ የመውጫ ፈተና አንዱ መሆኑንም ጠቅሰዋል።
የመውጫ ፈተናው ከሁሉም የመንግስት ዩኒቨርሲቲዎች የሚመረቁ ተማሪዎች በተማሩባቸውና በሰለጠኑባቸው የሙያ ዘርፎች ብቁ መሆናቸውን ለማረጋገጥ የሚያስችል እንደሆነ ገልጸዋል። የመውጫ ፈተናው የሚዘጋጀው፣ የሚተገበረው እና የሚተዳደረው በዩኒቨርሲቲዎች መሆኑን ገልጸው ለዚህም ትግበራ ፖሊሲና ዝርዝር ማስፈፀሚያ መመሪያ መዘጋጀቱን ገልፀዋል። በዚህ ረገድ በሁሉም ዩኒቨርሲቲዎች የሚገኙ ተመራቂዎች የመውጫ ፈተናውን እንዲወስዱ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ጠቁመዋል። በዚህ ሂደት በህግና በህክምና ሙያ የሚሰጠው የመውጫ ፈተና እና የብቃት ማረጋገጫ ፍተሻ እንደ ልምድ ይወሰዳልም ነው የተባለው።
የመንግስት ዩኒቨርሲቲዎች የምክክር መድረክ ፕሬዚዳንት እና የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ፕሮፌሰር ጣሰው ወልደሃና፤ የመውጫ ፈተናው የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ፣ የስራ ገበያን ለማሳደግና ተወዳዳሪ ለመሆን ከፍተኛ እገዛ የሚያደርግ መሆኑን፤ ይህ በየጊዜውም ከዩኒቨርሲቲዎች ተመርቀው የሚወጡ ተማሪዎች ምን ያህል የተግባር፣ የጽንሰ-ሃሳብ እውቀት አላቸው የሚለውን ለመፈተሽ ይረዳል። በምክክር መድረኩ የተገኙት የተለያዩ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንቶች፤ የመውጫ ፈተናው የትምህርት ጥራትን ከማረጋገጥ ባሻገር ምሩቃንን በአግባቡ በመለካት ረገድ ጉልህ ሚና እንደሚኖረው፤ ተማሪዎች በተማሩባቸው የትምህርት መስኮች በአገሪቱ እድገት ላይ የራሳቸውን አስተዋጽኦ ማበርከት እንዲችሉ እገዛ የሚያደርግ መሆኑን ተናግረዋል። በማከልም ዩኒቨርሲቲዎች ለመውጫ ፈተናው አተገባበር ጠንካራ የሆነ የክትትል ስርአት መዘርጋት፤ ውስጣዊ አደረጃጀታቸውን በማጠናከር በእያንዳንዱ የትምህርት ፕሮግራም ውስጥ ባሉ ትምህርቶች ላይ እውቀት፣ ክህሎትና አስተሳሰብ መለካት የሚችል ስርአት መዘርጋት ይኖርባቸዋልም ።
የከፍተኛ ትምህርትን አገራዊ ቅድመ ምረቃ የመውጫ ፈተናን በአግባቡ ለመምራትና ለማስተዳደር የተዘጋጀው የከፍተኛ ትምህርት መውጫ ፈተና ማስፈፀሚያ መመሪያ ጸድቆ ወደስራ ተገብቷል። ከዚህ በፊት መመሪያው በፍትህ ሚኒስቴር መመዝገቡና መጽደቁ ይታወሳል መመሪያው በመውጫ ፈተና ዝግጅት ሊካተቱ ስለሚገባቸው ሀገራዊ ዝቅተኛ የትምህርት ብቃት መመዘኛዎችን፣ የሙያ ሥነምግባር ደምቦችን እና ተቋማት ሊከተሏቸው የሚገቡ የአሠራር ስነ- ስርዓቶችን አካቷል። መመሪያው የትምህርት ጥራትን ለማስጠበቅና ሀገሪቱ የምትፈልገውን የሠለጠነ የሠው ኃይል ለማፍራት ከሚደረጉ ማስፈፀሚያ ስልቶች አንዱ ነው። በመመሪያው ዝግጅት ሂደት ውስጥ በስርዓተ ትምህርት እና ፈተና ዝግጅት ከፍተኛ ልምድ ያካበቱ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ምሁራን፣ የሙያ ማህበራት ተወካዮች እንዲሁም ሌሎች ባለድርሻ አካላት አስፈላጊውን ግብአት መስጠታቸው ይታወሳል።
በ”The Ethiopian Economiat View”ድረ ገጻቸው ቢዝነስ፣ ኢኮኖሚክስና ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ በመጻፍ፤ ማህበራዊ ሚዲያውን በተለይ ፌስቡክን ለበጎ አላማ በማዋል የሚታወቁት የኢኮኖሚክስ ባለሙያው አቶ ዋሲሁን በላይ በፌስ ቡክ ገጻቸው የመውጫ ፈተና ተፈታኝ ከሆናችሁ በቀሪው ጊዜያችሁ እነዚህን አድርጉ ይላሉ፤
1. የመውጫ ፈተናው አስፈላጊ መሆኑን አምኖ መቀበል (ልምድ እንዳላችሁ አለመርሳት ወደ ኮሌጅ እና ዩኒቨርሲቲ ለመግባት ተፈትናችሁ ያለፋችሁ ናችሁ (10ኛ እና 12ኛ ክፍል)፡፡ የመውጫ ፈተናውን በአይምሮ ደረጃ አምኖ አለመቀበል ጊዚያችሁን ይበላል፡፡
2. ለፈተና ይጠቅማል ብላችሁ ያሰባችሁበትን ክፍል ለይታችሁ መከለስ! ያላጣራችሁት ቦታ ካለ በደንብ ለፈተና በሚሆን መልኩ ማንበብ/መከለስ (በእያንዳንዱ የኮሌጅ ቆይታ ወቅት ለፈተና አንብባችሁ ሊሆን ስለሚችል ምን አልባት ክለሳ ማድረግ ሊበቃ ይችላል)፡፡
3. ከፈተናው ሁኔታ (ፎርማት) ጋር ፈጥኖ ለመግባባት መሞከር (ኦን ላይን ከሆነ መልመድ፤ ፈተናው ስለሚዳስሰው ነጥብ ማወቅ፤ ልምምድ ማድረግ፤ ሞዴል ፈተናዎችን በትኩረት መስራት፤ የጥያቄዎቹን ይዘት ለማወቅ መሞከር፡፡
4. የሚዘጋጁ የናሙና ፈተናዎችን በትኩረት መፈተን እና በደንብ መለማመድ የቀደመ የህግ እና የጤና መውጫ ፈተና ይዘቶችን ጠይቆ ልምዶችን መውሰድ፤ ምን አልባት ኦን ላይን ያሉ ናሙናዎችን እንደ መለማመጃ መውሰድ፡፡
5. የጊዜ መርሃ ግብር ማውጣት፤ በአንዴ ብዙ ለመሸፈን መሞከር ትኩረት ስለሚያሳጣ ቀሪ ጊዜያችሁን በጥብቅ ፕሮግራም መምራት (ከማህበራዊ ሚዲያ መቀነስ፤ ከጨዋታ መቀነስ፤ ከእንቅልፍ መቀነስ (በቀሪው ጊዜ ተቸግራችሁ ከቁጭት መዳን ትችላላችሁ) እና ለዚህ ፈተና የመጨረሻ አቅማችሁን መጠቀም፡፡
6. በዚህ ወቅቱ በቡድን ማጥናት፤ ሙከራዎችን መስራት፤ ሊያስረዷችሁ የሚችሉ ሰዎችን መፍጠር ያስፈልጋል፤ በከበዳችሁ ክፍል ላይ ጊዜ በማጥፋት ወደ ተስፋ መቁረጥ ውስጥ እንዳትገቡ የሌሎችን እርዳታ ለመቀበል ክፍት መሆን አስፈላጊ ነው፡፡
7. ከወዲሁ እና በፈተና በሚሰጥባቸው ቀናት ሊፈጠሩ የሚችሉ ስህተቶችን ቀንሱ የኮምፒውተር አጠቃቀም ፣ የማርፈድ ፣ ጥሩ ስሜት ያለመፈጠር፤ የድካም ፣ የመጨናነቅ ፣ ወዘተረፈ ።
ሻሎም ! አሜን ።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)
fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን ሰኔ 18/2015