ጠለፋ በኢትዮጵያ በተለያዩ ክልሎች በሚገኙ ባሕላዊ ልማዶች ላይ ተመሥርቶ ከጥንት ጀምሮ ስር የሰደደ ባሕል ሆኖ ቆይቷል፤ አሁንም በአንዳንድ የሀገሪቱ ክልሎች ተንሰራፍቶ ይገኛል። ተግባሩ ሴቶችን እና ልጃገረዶችን ያለ ፈቃዳቸው ለትዳር፣ ለፆታዊ ብዝበዛ ወይም ሌሎች ምክንያቶች ከፍላጎታቸው ውጪ በኃይል ማፈንን የሚያካትት ፆታን መሠረት ያደረገ ጥቃት ነው። በኢትዮጵያ የሴቶችን እና ልጃገረዶችን ደህንነት የሚጎዳ ተግባር የሰብዓዊ መብት ጥሰት ተደርጎ ይወሰዳል።
ይህም ሆኖ ግን አሁንም ባለው ተጨባጭ ሀገራዊ እውነታ የጠለፋ ተግባር በብዙ ውግዘት ውስጥ ቢሆንም ሙሉ በሙሉ መከላከል አልተቻለም ። እንዲያውም አሁን አሁን የዕለት ዜና አካል እየሆነ የመጣበት እውነታ እየተከሰተ ነው ። በዚህም ለአቅመ ሔዋን ያልደረሱና የደረሱ ልጃገረዶች ተጋላጭ እየሆኑ ነው ።
በቀደምት ጊዜያት ጠለፋን የሚፈጽሙት አልተማሩም፣ እውቀት የላቸውም የሚባሉና በገጠሩ ክፍል በሚኖሩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ቢሆኑም አሁን አሁን ግን ችግሩ ወደ ከተማ ገብቶ በጉዳዩ ላይ የተሻለ ግንዛቤ አለው በሚባል የማኅበረሰብ ክፍልም እየተስተዋለ ነው።
ቀደም ሲል /ድሮ/ የጠለፋ ተግባራት ይፈጸሙ የነበረው አንድም ከግንዛቤ ማነስ ሌላው ኅብረተሰቡ ለጠለፋ ከሚሰጠው የተሳሳተ ዋጋ እንደነበር ለመገንዘብ አይከብድም። ዛሬ ላይ ከችግሩ አስከፊነትና ሊያስከትል ከሚችለው ዝብርቅርቅ የተነሳ በዚህ ተግባር ላይ መሳተፍ የሕግ ተጠያቂነት ማስከተሉ የማይቀር ነው ።
ለመሆኑ ይሄን አሳሳቢ የሆነ ጉዳይ በእንጭጩ ለማስቀረት ከመንግሥት፣ ከሃይማኖት ተቋማት፣ ከሰብዓዊ መብት ተቋማት፣ ከሚዲያ? የጉዳዩ ባለቤት ከሆነው ሕዝብ ምን ይጠበቃል?
በነዚህ አካላት ለጉዳዩ አሳሳቢነት የተሰጠው ትኩረት ምን ይመስላል? ምን አይነት አስተማሪ እርምጃ ሊወሰድ ይገባል? መፍትሔው ምን ይሁን? ችግሩ እንዳይከሰት ቀድመን ምን እንሥራ? ለሚሉና ለመሳሰሉ ጥያቄዎች ተገቢውን ምላሽ ፈጥኖ መስጠት ይገባል።
ለጽሑፌ መነሻ ይሆነኝ ዘንድ ከሰሞኑ በሀገራችን ሴቶችንና ሕጻናትን ያለፍላጎታቸው በማፈን የጠለፋ ተግባራትን በመፈጸም የመገናኛ ብዙኃንና የማኅበራዊ ሚዲያ (ፌስ ቡክ) መነጋገሪያ ሆኖ የቆዩትን ክስተቶች ላንሳ ።
ጠላፊዎቹ የተለያዩ ስልቶችን በመጠቀም ለአቅመ ጋብቻና ፆታዊ ግንኙነት ያልደረሰችን ታዳጊ ጨምሮ እጮኛ ያላትንና የጋብቻ ቀኗን በጉጉት የምትጠብቀውን ወይዘሪት በማን አለብኝነት በጉልበት አግተው ለሳምንታት በማቆየት አካላዊና ስነ ልቦናዊና ጉዳት አድርሰዋል።
ዘመናዊዎቹ ጠላፊዎች እንደ ዱሮዎቹ ጠላፊዎች ሴቶቹን በማስገደድ በፍቃዳቸው እንደሆነና እንዳልተጠለፉ በማስመሰል ሽምግልና የመላክና በሕግ እንዳይጠየቁ ጥረት ሲያደርጉ ተስተውሏል። ምንም እንኳን አጀንዳው ብዙ ያነጋገረ ቢሆንም የጉዳዩን ክብደት ያክል ትኩረት የተሰጠው አይመስለኝም ።
ከዚያ ይልቅ በየማኅበራዊ ሚዲያው ለሚገኙ የወሬያለህ ለሚሉ መቀለጃና የገንዘብ መሥሪያ እንደሆነ ይሰማኛል። ጉዳዩ የሁሉም ሕመም ከመሆኑ አንጻር፤ በክስተቶቹ ዙሪያ አስተያየት ሲሠጥ የነበረው ሁሉ በርግጥ ሕመሙ ተሰምቶት ነው ለማለት የሚያስደፍር አይደለም።
የጠለፋ ተግባር ሴቶች እና ልጃገረዶች ላይ፤ አካላዊና ሥነልቦናዊ ችግሮችን ያስከትላል፤ የልብ ስብራትንና በሕይወት ተስፋ መቁረጥን እንዲሁም ማኅበራዊ መገለልን ያመጣል። ከሁሉም በላይ ደግሞ በተለይም ለአቅመ ሔዋን ያልደረሰችን ልጅ ጠልፎ ለቀናት ማቆየትና በዚህም መካከል አለፍቃዷ ፆታዊ ግንኙነት እንድታደርግ ማስገደድ የአስገድዶ መድፈር ወንጀል ነው።
ብዙ ታዳጊ ሴቶች አካላቸው ሳይጠና በሚመጣ ፆታዊ ግንኙነት አልፎም እርግዝናና ወሊድ እንደ ፌስቱላ ላሉ አሰቃቂ ሕመሞች የመዳረጋቸው ዕድልም በእጥፍ የጨመረ ነው። ይህንን ማኅበራዊ እርግማን ለመከላከል ሁሉም ዜጋ ኃላፊነት አለበት። አሁን ላይ ማንኛችንም የዚህ ማኅበራዊ እርግማን ሰለባ ስላለመሆናችን መተማመኛ የለንም፤ ይህ ችግር የልጆቻችንን ነገ እንደማይበላሽ ማረጋገጫም ስለሌለን ዛሬውኑ ሳይቃጠል በቅጠል ይሉት አይነት እርምጃችንን መጀመር ይገባናል።
የሃይማኖት ተቋማት፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ የሚዲያ ተቋማት፣ የሰብዓዊ መብት ተቋማት የሕግ አካላትና መንግሥት ችግሩ አድጎ የሀገር ፈተና ከመሆኑ በፊት ሊረባረቡ ያስፈልጋል። አሁን ላይ ሴቶች ከወንዶች እኩል ናቸው እያልን እነሱም ከእኩልነት አልፈው በትልልቅ ማኅበራዊ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ላይ የነቃ ተሳትፎን ከማድረግ ጀምሮ እስከ ውሳኔ ሰጪነት ድረስ ሚናቸው እያሳዩን ባለበት ወቅት በወረደና ዘመኑን ባልመጠነ ድርጊት ከሕልማቸው መጨናገፍ የለባቸውም ልዩ ትኩረት ልንሰጠውም ይገባል።
በርግጥ በሀገራችን የሴቶች እና ልጃገረዶች አፈና ጠለፋ ባሕል ሳይሆን የወንጀል ድርጊት ነው በማለት የኢትዮጵያ የወንጀለኛ መቅጫ ሕግ ጠለፋ፣ አስገድዶ መድፈር፣ የግዳጅ ጋብቻ እና ሌሎች ፆታን መሠረት ያደረጉ ጥቃቶችን ወንጀል አድርጎ ያስቀምጣል።
ይሁን እንጂ የእነዚህ ሕጎች አፈፃፀም ደካማ በመሆኑ የተፈለገውን ያህል ውጤት አስገኝቷል ለማለት አያስደፍርም። በተለይም በገጠር አካባቢዎች ባሕላዊ ልምድ ሆኖ ስለሚቆጠርና ሴቶቹም የሚሰማቸው አግኝተው ከችግሩ በቀላሉ መውጣት የሚችሉበት መንገድ ስለሌለ በሚፈለገው ልክ ውጤት ያመጣ ሥራን ማየት አልተቻለም። አሁን ላይ ግን ባልተለመደና ይሆናል ተብሎ በማይታሰብ መልኩ በከተሞች ላይ በመበራከት ይኸው ችግር የወለደው እንደሚሆን ለመገመት የሚከብድ አይደለም ።
ስለሴቶች መብትና እኩልነት በቂ ግንዛቤና ትምህርት ባለመሰጠቱ ብዙ ሴቶች እና ልጃገረዶች ስለመብቶቻቸው በቂ ግንዛቤ የላቸውም ይህ ደግሞ ድርጊቱን ለመቃወም እና ለማውገዝ አቅመቢስ አድርጓቸዋል። በወንዶች ላይ ያለው የኢኮኖሚ ጥገኝነትም የጠለፋ ተጋላጭነት እንዲጨምር ምክንያት እንደሚሆንም ይታመናል።
መንግሥት በተለያየ ጊዜ የአፈና እና ሌሎች ፆታን መሠረት ያደረጉ ጥቃቶችን ለመፍታት እርምጃ ከመውሰድ ጀምሮ በሥርዓተ-ፆታ ላይ የተመሠረቱ ጥቃቶችን መከላከል በተለያዩ ጊዜያት በሥርዓተ-ፆታ ላይ የተመሠረቱ ሀገራዊ የድርጊት መርሐ ግብሮችን አጽድቋል።
ስለ ሴቶች መብት ግንዛቤ የማስጨበጥ እና ኅብረተሰቡን በፀረ-ጠለፋ ትግል ላይ ለማሳተፍ በተለያዩ ወቅቶች ንቅናቄ ፈጥሯል። ሆኖም ችግሩ ከመሻገር አልያም ባለበት ከመቆም ይልቅ እየተስፋፋ ዛሬ ዛሬ ደግሞ ጭራሽ በዋና ዋና ከተሞች ላይ እየተሰማና እየተስተዋለ መሆኑ ዘርፉ ላይ ብዙ መሥራት ያለባቸው ነገሮች እንዳሉ ያመላክታል።
የሕግ አስከባሪዎችን በተለይም ጉዳዩን በቅድሚያ የሚይዙትን ፖሊሶች አቅም ማጠናከር ስለ ችግሩ አሳሳቢነት በቂ እውቀት እንዲኖራቸው ማስቻል፣ ተጠቂዎችም ከአንድ ቀን ያለፈ ምስከርነትን እንዲሰጡና ጉዳያቸውን በነፃነት እስከመጨረሻው ድረስ እንዲከታተሉ ድጋፍ እና ጥበቃ ማድረግ የሚያስፈልግ ሲሆን ሁሉም የኅብረተሰብ ክፍል ስለሴቶች መብት እና እኩልነት ግንዛቤው እንዲሰፋ የትምህርት አሰጣጥ ዘዴያችንን ቀላልን ሁሉንም ያማከለ ማድረግ፣ በአጥፊዎች ላይም አስተማሪ የሆኑ እርምጃዎችን መውሰድ ያስፈልጋል።
በሴቶችና ልጃገረዶች ላይ የሚደርሰው ጠለፋና አፈና ከፍተኛ የሆነ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ከመሆኑ አንጻር ዛሬም በመንግሥት፣ በሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች እና ማኅበረሰቡ ድርጊቱን ለመከላከል የሚያደርጉት ጥረት ከፍ ባለ ትብብርና ትስስር ሊመራ ይገባዋል።
ዓለማየሁ ግዛው
አዲስ ዘመን ሰኔ 18/2015