ታሪካዊ ዳራ፤
ሄኒሪ ጆን ቴምፕል (1784 – 1865) ታላቋን እንግሊዝ ለአሥር ዓመታት በጠቅላይ ሚኒስትርነት በመምራት ታሪካቸውን በደማቁ ያጻፉ የፖለቲካ ሰው ነበሩ። የሌበር ፓርቲን ከምሥረታ እስከ ተጽእኖ ፈጣሪነት በማድረስ አንቱታን ያተረፉት እኚህ የእንግሊዝ ፖለቲከኛ የአመራር ዘመናቸው የተሳካና ዛሬም ድረስ የሚጠቀስላቸውን በርካታ ውጤታማ አሻራ አሳርፈው እንዳለፉ የሀገራቸው የታሪክ ዘርፍ ምሁራን በየመጻሕፍታቸው አዘውትረው ይጠቅሷቸዋል።
ሚ/ር ቴምፕል ሀገራቸውን በመራሄ መንግሥት ዘመነ ሥልጣን በመሩባቸው ዓመታት የሚደነቁትና የሚወደሱት ባስመዘገቧቸው ስኬቶች ብቻ ሳይሆን በዘመን ተሻጋሪ አባባላቸው ጭምር ነው። እንዲህ ነበር ያሉት፡- “We have no eternal allies, and we have no perpetual enemies. Our interests are eternal and perpetual.”
አባባላቸው በተቀራራቢ ትርጉም ወደ ቋንቋችን ሲሸጋገር እንዲህ የሚል ፍቺ ይሰጠናል። “እኛ ዘለዓለማዊ የምንለው ጠላትም ሆነ ወዳጅ የለንም። ዘላቂና ዘለዓለማዊ የምንለው የግል ጥቅማችንን ብቻ ነው።”
እጅግ በርካታ የዓለም ሀገራት ፖለቲከኞችና ዲፕሎማቶች ይህንን አባባል ዛሬም ድረስ የንግግራቸው መክፈቻ፣ የድርድራቸው አጀንዳና የዕቅዳቸው ግብ በማድረግ ጭምር ሲናገሩትና ሲተገብሩት የኖሩት መርህ ነው። ለብሔራዊ ጥቅማቸው ማስተግበሪያም እንደ ዋነኛ ፖሊሲ በመቀበል “የእንካ በእንካ” ስምምነቶችንና ውሎችን ይፈጽሙበታል።
ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት ተፋላሚ አገራት ተቀዳሚ ተዋንያን መካከል፡-
“በቸርችል ጎዳና በአንቺ አረማመድ፣
እንዴት ይዘለቃል ይህ ሁሉ መንገድ”
ተብሎ ይደነቅ የነበረውና ዛሬም ሞገሱ ያልደበዘዘው የከተማችን ዋና ጎዳና በስማቸው የተሰየመላቸውና ጠቢቡ የአገሬ ሸማኔ በአንድ ወቅት “ቸርችል ጎዳና” የሚል የወይዛዝርት የጥበብ ዓይት በስማቸው የሰየመላቸው፣ “የወዳጅ አገር መሪ” እና “ፀሐይ በግዛቴ አትጠልቅም” ባዩዋ የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር የነበሩት ዊንስተን ቸርችል የቀዳሚ መሪያቸውን የሚ/ር ቴምፕልን ጥልቅ አባባል እጅግ አግዝፈው በማስታወስ እንዲህ በማለት የወቅቱን የአገራቸውን ፖሊሲ ለዓለም ማህበረሰብ አስታውቀው ነበር።
“I am ready to put my hands in the hands of the devil for the progress of my country.” ውርስ ትርጉም፡- “ለአገሬ ዕድገት የሚበጅ መሆኑን ካረጋገጥሁ፤ ከሰይጣንም ጋር ቢሆን እጅ ለእጅ ተጨባብጬ ወዳጅነት ለመፍጠር አላመነታም።” አባባሉን በተመለከተ ብዙዎች ጠቅላይ ሚኒስትሩን የተቹም ያሞገሱም አልታጡም። አንዳንዶችም “ሥነ ምግባር የጎደለው ንግግር ነው” ብለው አምርረው ቢቃወሙም እውነታውን ስንፈትሽ ግን ከዓለም የፖለቲካ እውነታ ጋር በሚገባ እንደሚጎዳኝ እንገነዘባለን። ለምን ቢሉ ለአገራት የፖለቲካና የዲፕሎማሲ ትርፍ ሲባል ምን የማይደረግ ነገር ይኖራል?
በቸርችል አባባል እውነታነት የሚስማሙ ደጋፊዎች ዋነኛ የመከራከሪያ ነጥባቸውን እንዲህ በማለት ጮክ ባለ ድምጽ ለማስረዳት ይሞክራሉ፡- “Politics is an art and the techniques of distinguishing different situations to make the best use of them for national interests” የዚህ አባባል አስኳል ሃሳብ “የፖለቲካ ጨዋታ በጥበብ የተቃኘ ነው። የአሸናፊነቱ ምሥጢር የሚለካውም ለአገር የሚጠቅም አንዳች ነገር ማውጣት ሲቻል ነው” የሚል ይሆናል።
ከመቶ ሰላሳ ዓመታት በላይ ያስቆጠረውን የጠቅላይ ሚኒስትር ቴምፕል አባባል እየጠቀሱ ለአገራቸው ጥቅም ሽንጣቸውን ገትረው ሲከራከሩ የኖሩና እየተከራከሩ ያሉ የዓለማችን ፖለቲከኞችና ዲፕሎማቶች ቁጥር በቀላሉ የሚገመት አይደለም። የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የነበሩት ሄኒሪ ኪሲንጀርም ያንን ዘመን ተሻጋሪ ጥቅስ እንዳለ ቃል በቃል በመዋስ በተለያዩ መድረኮች ይጠቀሙበት እንደነበር ግለ ታሪካቸው ይመሰክራል። “እኛ አሜሪካኖች ቋሚ ወዳጅም ሆነ ቋሚ ጠላት ብለን የምንፈርጀው የለንም። ቋሚና የማይናወጠው መርሃችን የአሜሪካንን ፍላጎት ማስጠበቅ ብቻ ነው።”
“ወዳጅ ወዳጁን አይከዳም፤ ከጅብ ወዲያ ሆዳም” የሚለው አገርኛ ብሂል አበው በዓለማችን የፖለቲካ ጨዋታ ውስጥ የሚሠራ መርህ አይደለም። ኢየሱስ ክርስቶስ የብሉይ ኪዳንን አሠርቱን ትዕዛዛት በጥቂት ቃላት ወስኖ ለአዲስ ኪዳን ደቀ መዛሙርቱና ስሙን ለሚሸከሙ ምእመናን በሙሉ “ወንድምህን እንደ ራስህ ውደድ” ብሎ ያስተማረው ወርቃማ ትምህርት ከፖለቲካ አካሄድ ጋር ፍጹም ጠበኛ ነው።
በፖለቲካ መርህ መሠረት ትናንት በወዳጅነት እፍ ባለ ፍቅር ያበዱና የከነፉ መንግሥታት የየግላቸው ጥቅም የተነካ ሲመስላቸው ወይንም ጥቅም አልባ ሲሆንባቸው “እሣት ለብሰውና እሣት ጎርሰው” የፍልሚያ ሸማ ከመጣጣል አይመለሱም። የራስ ጥቅም ካልሆነ በስተቀር “ለአንተ እንዲደረግልህ የምትፈልገውን ለወንድምህም እንዲሁ አድርግለት” የሚለው የጽድቅ ምክር ከፖለቲከኞች ጆሮ የሚደርስ፤ ለትግበራም የሚጣደፉበት ዓይነት ግብረ ገብ አይደለም።
በዲፕሎማሲውም ሆነ በፖለቲካው ዐውደ-ሠፈር ምን ይሉኝና ርህራሄ እጅግም ዋጋ እንደሌለው ካረጋገጡ የዓለማችን መሪዎች መካከል “ብረቷ እንስት” የመሰኘት አድናቆት ያተረፉት የእንግሊዟ ጠቅላይ ሚኒስትር ማርጋሬት ታቸር በዚህ የአገርን ጥቅም የማስቀደም ተቀዳሚ ጉዳይ ሁነኛ ማሳያ ተደርጎ የሚጠቀስላቸው አባባላቸው እንዲህ የሚል ነበር፤፡- “There are no personal sympathies in politics.” – “ግለሰባዊ ርህራሄ ከፖለቲካ ጋር የተፋታ ነው።”
ሲያሻቸው እርስ በእርስ ጠላቶች የሚሆኑትና ፍቅራቸው የጠና ሲመስላቸው ደግሞ “ቆሎ ካልተጓረስን” የሚሉት ድራጎኖቹ ቻይናዊያን፣ ድብ ነን ባዮቹ ሩሲያዊያንና በንሥር ከፍታ እንበራለን ብለው የሚመጻደቁት አሜሪካዊያን የሚያራምዱትን የፖለቲካ አካሄድ ሰከን ብለን ብንመረምር ወዳጅነትንና ጠላትነት በእነርሱ የፖለቲካ አይዲዮሎጂ ምን ያህል እንደ ገበቴ ውሃ እንደሚያዋልል ማስተዋል አይገድም።
እኛስ? ፡- “ልካስ ያለ ታግሶ፤ እጸድቅ ያለ መንኩሶ”
በአግባቡና በወጉ የመስካሪዎችን የታሪክ ገጽ ተነፈግን እንጂ እኛም ለሉዓላዊነታችን ክብር ስንል “ከሰይጣን ጋር ተጨባብጦ” ከማሸነፍ ይልቅ “ሆድ ከአገር ይሰፋል” በሚል የትዕግስት መርህ የበርካታ መንግሥታትን ሤራና ተንኮል ተቋቁመን ታሪካችንን ያስቀጠልንባቸው አጋጣሚዎች እጅግ በርካቶች ናቸው። ጥቂት የነበር አብነቶችን እናስታውስ።
በሚያዝያ ወር 1911 ዓ.ም የመጀመሪያውን የዓለም ጦርነት በድል ለተወጡ የአውሮፓ መንግሥታት “የእንኳን ደስ ያላችሁ መልእክት” ለማድረስ አገሬ በሦስት የተለያዩ አገራት የዲፕሎማሲ መልእክተኞችን ልካ ነበር። ወደ እንግሊዝ አገር በደጃዝማች ናደው አባወሎ መሪነት ከንቲባ ገብሩና ብላቴን ጌታ ሕሩይ ወልደ ሥላሴ ያሉበት የልዑካን ቡድን ተሰማርቶ ነበር። በደጃዝማች ወልደ ገብርኤል በሻህ የሚመራው ቡድን ደግሞ ደጃዝማች ሺበሺ በየነንና አቶ ዘውገ ኃይሉን አካቶ ወደ ፈረንሳይ አቅንቶ ነበር። ለጣሊያን መንግሥት የተወከሉት ደግሞ ደጃዝማች ጌታቸው አባተ ሊቀ መኳስ መንገሻ ውቤ እና አዛዥ ደግፌ ነበሩ። (ምንጭ፡- ከቀዳማዊ እስከ ቀዳማዊ፤ አንድ ሺህ አንድ ጥያቄዎች፤ ገጽ 377-378)።
የአገሬን የእንኳን ደስ አላችሁ መልእክት የተቀበሉት እነዚህ አገራት ከአሥራ አምስት ዓመታት በኋላ የኢጣሊያ ሠራዊት በግፍ በወረረን ወቅት አሜሪካንን በአባሪነት ከጎናቸው በማሰለፍ ውለታችንን “አመድ አፋሽ” በማድረግ ወራሪው ጦር ሕዝባችንን የፈጀበትን የመርዝ ጋዝና የጦር መሣሪያ ድጋፍ አዥጎድጉደውለት ነበር።
ከላይ በጠቀስኩት መጽሐፍ ውስጥ ዝርዝራቸው እንደሚከተለው ተመዝግቧል። የአሜሪካ መንግሥት የመርዝ ጭስ (ሙስታርድ ጋዝ) እና ታንኮችን፤ የእንግሊዝ መንግሥት ቦንብ ጣይ፣ የመርዝ ጋዙን የሚረጩና መትረየስ የሚተኮስባቸው 100 ሮል ሮየስ የተባሉ ተዋጊ አውሮፕላኖችን፤ የፈረንሳይ መንግሥት ታንክ፣ መድፍና መትረየሶች።
እነዚሁ አገራት ለፋሽስቱ ጦር ከረዱት የጦር መሣሪያዎች በተጨማሪ በሊግ ኦፍ ኔሽን ስብሰባ ላይ የጣሊያን መንግሥትን ወረራ በመደገፍ ኢትዮጵያን በብዙ መልኩ ጎድተዋል። አሜሪካና የጃፓን መንግሥት የመንግሥታቱ ጉባኤ በጣሊያን ላይ ጥሎት የነበረውን የኢኮኖሚ እገዳ በመጣስ ለወራሪው የፋሽስት መንግሥት ነዳጅ ይሸጡ ነበር።
አሜሪካ በግሏ ለኢትዮጵያ ምንም ዓይነት የጦር መሣሪያ እንዳይሸጥና በተለያዩ መንገዶች የተገኙትም ወደ አገር ውስጥ እንዳይገቡ ክልከላ ጥላ ነበር። ይህቺው “ታላቅ ተብዬዋ አሜሪካ” የዚያድ ባሬ ጦር በ1969 ዓ.ም አገራችንን በወረረ ጊዜ በንጉሡ ዘመን የታዘዙት የጦር መሣሪያዎች እንዳይላኩ እግድ መጣሏ አይዘነጋም።
እጅግ የሚገርመው “የፖለቲካ ተውኔት” የተፈጸመው ደግሞ ጀግኖቹ አባቶቻችን ወራሪውን የፋሽስት ጦር ድል አድርገው ባንበረከኩ ማግሥት ቀድመው ደስታቸውን የገለጹት እነዚሁ “ቋሚ ጠላትም ሆነ ቋሚ ወዳጅ የለም” ለሚል ፍልስፍና የገበሩ አገራት ነበሩ። ንጉሠ ነገሥቱን ከስደት አጅበው የገቡት እንግሊዞች መሆናቸውን ስናስብና አሜሪካም የቃኘው ሻለቃን የጦር ሠፈር በአስመራ ለመገንባት እንደምን እንደተሽቀዳደመች እነርሱ ቢክዱም ታሪካችን በሚገባ ይመሰክርልናል።
ፈረንሳይም ብትሆን የአገሪቱ ዘመናዊ ትምህርት ፈረንሳይኛ እንዲሆን ያላደረገችው ጥረት አልነበረም። በ1930ዎቹ መጨረሻ በአዲስ አበባ የተከፈተው ሊሴ ት/ቤት መታሰቢያ ያደረገው ከፋሽስቶች ጋር ትንቅንቅ በማድረግ ለወደቁት ለጀግናው ገብረ ማሪያም ጋሪ ነበር። እንዴት ሆነ ቢባል አውሮፓዊያንም ሆኑ አሜሪካኖች ፍልስፍናቸው “Politics is an art…” የሚል ስለሆነ “የጉልበታቸውን ብርታት ታናናሽ በሚሏቸው መንግሥታት ላይ ለዘመናት ሲፈትሹ የኖሩት” የፖለቲካ ድራማ እየተወኑ ስለመሆኑ ጥሩ ማሳያ ይሆናል። የአገሬ ብሂለኛ፡- “ወግቶ ይማርህ” እንደሚለው መሆኑ ነው።
ዛሬም በኢትዮጵያ ላይ ሲያሻቸው የዲፕሎማሲ ጫና፣ ሲፈልጉ የእርዳታ እህል እቀባ፣ በሉ ሲላቸውም በመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ላይ የጉዞ ማዕቀብ፣ ጠንከር ሲልም የእርዳታና የብድር ገንዘብ የሚነፍጉን “እንደ እስስት የሚለዋወጠው” የፖለቲካና የዲፕሎማሲ መርሃቸው ግድ ስለሚላቸው ነው።
“ጠላት ሲነሳብህ ወዳጆችን አበርክት” እንዲል ብሂላችን፤ አገሬ ሁልጊዜ የእነርሱን ፊትና እጅ ከመጠበቅ አንድም የውስጧን ችግሮች በቤቷ ጨርሳ እፎይ በማለት ሙሉ ኃይሏን ወደ ልማት ብታዞር፣ አንድም አሁን እየተስተዋለ እንደሚታየው በጥበብ የተቃኘ የዲፕሎማሲ አካሄዷን አጠናክራ የምዕራባዊያኑን ሚዛን በሚያስጠብቅ አማራጭ መጓዙን ብትገፋበት ይበጅ ይመስለናል። የሚ/ር ቴምፕልን ግማሽ አባባል እንዋስና “Our interests are eternal and perpetual” ብለን ሃሳባችንን እንደምድም። ሰላም ለሕዝባችን፤ ለዜጎችም በጎ ፈቃድ።
(በጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን ሰኔ 17/2015