ግብር/ታክስ፣ በአንድ ሀገር የተረጋጋ መንግስታዊ ስርዓት እንዲኖር፣ ዜጎች ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተግባሮቻቸውን በሰላማዊ መንገድ እንዲያከናውኑ እና ከመንግስት ማግኘት የሚፈልጓቸውን አገልግሎቶች ማግኘት እንዲችሉ የመንግስት ዋነኛው አቅምና መሳሪያ ሆኖ የሚያገለግል ነው። በመሆኑም መንግስት መንግስታዊ ኃላፊነቱን ለመወጣት፤ ለዜጎችም ሰላምና ደህንነት መረጋገጥ፤ ልማትና የመሰረታዊ ፍላጎቶቻቸው ጥያቄዎች መመለስ፣ መንግስት ግብር የመሰብሰብ ሥልጣን፤ ዜጎችም ግብር የመክፈል ግዴታ አለባቸው።
ምክንያቱም ግብር መክፈል መንግስት ለሕዝቦች ጥያቄ መልስ መስጠት የሚያስችለውን የልማትና ተያያዥ ተግባራትን ለመከወን ብቻ ሳይሆን፤ ከዚህም ከፍ ያለ አገራዊ ክብር (የደህንነት እና ሉዓላዊነት ጥያቄን የመመለስ) አስጠብቆ የመዝለቅ አለመዝለቅን ሁኔታ የሚመለከት ነው። በመሆኑም ግብር/ታክስ መክፈል የአንድ አገር ዜጎች በቅድመ ሁኔታ ያልታጠረ ግዴታ ሲሆን፤ ይሄን ግዴታን መወጣት ደግሞ ከፍ ያለ የስልጣኔ፣ የአገርና ሕዝብ ወዳድነት መገለጫ ባህሪ ነው።
የግብር/ታክስ ዓላማዎች
የዘርፉ ባለሙያዎች እንደሚያስረዱት፣ በአንድ አገር ውስጥ መንግስት በዋነኛነት በሁለት መንገድ ገቢን ይሰበስባል። አንዱ በግብር እና በታክስ አማካኝነት፤ ሁለተኛው በእቃ እና አገልግሎት ክፍያ አማካኝነት። እነዚህ ገቢዎችም የየራሳቸው ዓላማ ኖሯቸው የሚሰበሰቡ ናቸው።
ለምሳሌ፣ በግብር አማካኝነት የሚሰበሰበው ገቢ ሕዝቦች ተጠቃሚ የሚሆኑባቸው የመሰረተ ልማት አቅርቦቶች ወጪ መሸፈኛ የሚውል ነው። በዚህም እንደ መንገድ፣ ውሃና መብራት የመሳሰሉ ማንኛውም ዜጋ በወል የሚጠቀምባቸው መሰረተ ልማቶችን ለዜጎች (ታክስ ከፈለም አልከፈለም) ተደራሽ የሚደረግበት ነው።
በአንጻሩ ከእቃ እና አገልግሎት ክፍያ የሚሰበስበው ገንዘብ፣ የእቃው ወይም የአገልግሎቱ ተጠቃሚ እና የሚጠቀመውም መጠን ተለይቶ የሚታወቅበት ነው። በመሆኑም በዚህ መልኩ ከግብር እና ታክስ እንዲሁም ከእቃ እና አገልግሎት የሚሰበሰበው ገቢ ዋነኛ ዓላማ መንግስት ለስራ የሚያስፈልገውን ገቢ እንዲያገኝ ማስቻል ነው።
ሁለተኛው የግብር ዓላማ፣ ኢኮኖሚን ወይም ካፒታልን የመምራት ሲሆን፤ የንግዱ ማህበረሰብ ተቀዳሚ ዓላማው ትርፍ ማግኘት እንደመሆኑ የተሻለ ትርፍ በሚያስገኝለት የስራ መስክ ላይ መሰማራት ይፈልጋል። መንግስት ደግሞ የሕዝቦችን ኑሮ ለማሻሻል እና ለህዝቡ የመሰረተ ልማት አቅርቦቱን በተገቢው ሁኔታ እንዲዳረስ ለማድረግ ቅድሚያ የሚሰጣቸው ዘርፎች ይኖራሉ። በመሆኑም ባለሃብቱ በእነዚህ መስኮች ቢሰማራ ውጤታማ የሚሆንበትን አነስተኛ ግብር ማስከፈልን የመሳሰሉ ርምጃዎችን ይወስዳል። በመሆኑም በዚህ መልኩ የሚሰበሰብ ግብር እና ታክስ የሃብት ስምሪቱን/ኢኮኖሚውን የመምራት አቅም ይፈ ጥርለታል።
በሌላ በኩል፣ መንግስት ታክስና ግብርን የሕዝቡን ጤና እና የሕዝቡን ማህበራዊ ኑሮ ለመጠበቅ ይጠቀምበታል። ለምሳሌ፣ ሲጋራ፣ የአልኮል መጠጦች እና ሌሎችም ምርቶች የሕዝቡን ጤና ይጎዳሉ፤ የሕዝቡን ማህበራዊ ኑሮ ያናጋሉ፤ ቤተሰብን ይበትናሉ። ስለዚህ ሕብረተሰቡ እነኚህን ምርቶች እንዳይጠቀም ዋጋቸው ከፍ እንዲል በማድረግ ገቢውንም ያሳድጋል፤ የሕብረተሰቡንም ጤና ለመጠበቅ ያስችለዋል።
ከእነዚህ ዓላማዎች በተጓዳኝ፣ ግብር እና ታክስ መንግስት የአገር ውስጥ ኢንዱስትሪን እንዲያስፋፋ የሚያግዙት ሲሆን፤ በተለይ ወደ አገር ውስጥ የሚገቡ እቃዎች ላይ ከፍተኛ ቀረጥ በመጣል እንዲሁም ለአገር ውስጥ አምራቾች ማበረታቻ በማድረግ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ለማገዝ አቅም ይፈጥርለታል።
በዜጎች መካከል ፍትሃዊ የሃብት ክፍፍል (ዌልዝ ዲስትሪቡሽን) እንዲኖር ለማድረግም ታክስ ጉልህ ሚና ያለው ሲሆን፤ በዚህም መንግስት ትልቅ ገቢ ያላቸው እና ቅንጡ ኑሮን የሚኖሩ የሕብረተሰብ ክፍሎች ከፍ ያለ ታክስ ከፍለው ድሃው ሕዝብ የሚደጎምበትን እድል ለመፍጠር ያስችለዋል።
በኢትዮጵያም እነዚህን ዓላማዎች ማዕከል ያደረጉ የግብር እና ታክስ አሰራር ስርዓቶች ተዘርግተው ዘርፈ ብዙ ተግባራት እየተከናወኑ ሲሆን፤ ለእነዚህ አሰራሮች የሚሆኑ የሕግ ማዕቀፎች ተቀርጸው እና አደረጃጀቶችም ተፈጥረው ነው እየተሰራ ያለው። ለምሳሌ፣ ገቢዎች ሚኒስቴር አጠቃላይ ከገቢ እና ግብር ጋር ያሉ ጉዳዮችን ይዞ የሚሰራ ተቋም ሲሆን፤ ጉሙሩክ ኮሚሽንም የገቢና ወጪ ምርቶችን የማሳለጥ፣ የቀረጥና መሰል ጉዳዮችን የሚከውን ነው። ለዚህም የሚሆን አደረጃጀት፣ በጀትና የሕግ ማዕቀፎች ተዘጋጅተው ነው እየተከናወነ ያለው።
ግብር እና ታክስ በኢትዮጵያ
መረጃዎች እንደሚያመለክቱት፤ በኢትዮጵያ የግብር እና ታክስ ስርዓት ከአክሱም ዘመን ጀምሮ ሲተገበር የቆየ ሲሆን፤ በዘመን ጅረት ውስጥ የተለዋወጡ መንግስታትም ይሄንኑ የግብር እና የታክስ ሂደትን የመንግስት አቅም አድርገው ተጠቅመውበታል። አገርና ሕዝብንም በሁሉም መስክ መርተው ማሻገር ችለዋል።
ቀደም ሲል እንዳነሳሁት ደግሞ ከግብር እና ታክስ መሰረታዊ ዓላማዎች አንዱና ቀዳሚው የመንግስትን ዓመታዊ የገንዘብ/ሃብት ፍላጎት የሚያሟላ ገቢ መሰብሰብ ነው። ከዚህ አኳያ ተልዕኮ ተሰጥቶት ግብር እና ታክስን እየሰበሰበ ያለው የገቢዎች ሚኒስቴር ሲሆን፤ በክልሎች እና ከተማ አስተዳደሮችም ለዚሁ ፍላጎቶቻቸው ማሳኪያ የሚሆን ሃብት የሚያሰባስቡ ቢሮዎች ተደራጅተዋል። በዚህ ረገድ በተለይ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ እያደገ የመጣውን የመንግስትን የበጀት ፍላጎት ተከትሎ ተቋማቱ ይሄንን ፍላጎት ባማከለ መልኩ ግብርን የመሰብሰብ ከፍ ያለ ኃላፊነት ወስደው እየሰሩ ይገኛል።
ይሁን እንጂ ካለው አቅም አንጻር በሚፈለገው ልክ ሃብት መሰብሰብ እንዳልተቻለ ግን የዘርፉ ምሑራን ይገልጻሉ። ለዚህ እንደማሳያ የሚያቀርቡትም፣ የአገር ውስጥ አጠቃላይ ምርት (ጂ.ዲ.ፒ) እና የሚሰበሰበው ታክስ መካከል ያለው ግንኙነት ባለፉት ዓመታት እየቀነሰ መምጣቱን ነው። ይሄ ደግሞ በአንድ በኩል፣ ህብረተሰቡ የግብር ግዴታውን በተገቢው መንገድ እየተወጣ አለመሆኑን፤ በሌላ በኩል መንግስት ኢኮኖሚው ከሚያመነጨው ሃብት ተገቢውን ድርሻ እያገኘ አለመሆኑን አመላካች ስለመሆኑ ነው የሚያስረዱት።
ይሄ ደግሞ ኢኮኖሚው ከሚያመነጨው ሃብት ለመንግስት መሰብሰብ የሚገባውን ገቢ በመሰብሰብ ረገድ ትልቅ ክፍተት መኖሩን አመላካች ነው። ይሄ ደግሞ እንደ ተቋምም እንደ አገርም የሚታይ ድክመት ሲሆን፤ ይሄንን ለማሻሻል በየጊዜው የተወሰዱ ርምጃዎች እና የተገኙ ውጤቶች ቢኖሩም አሁንም ድረስ በጅምር ደረጃ የሚወሰዱ እንጂ አጥጋቢ የሆነ ውጤት ተገኝቷል ለማለት አያስችልም።
ይሄንን ለመረዳት አገራዊ የበጀት እድገቱን፣ የገቢ ፍላጎቱን፣ ከአገር ውስጥ ገቢ የሚጠበቀውን ሃብት፣ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የሚይዘውን ዓመታዊ የገቢ ስብሰባ እቅድ እንዲሁም አፈጻጸሙን መመልከቱ ተገቢነት ይኖረዋል። ለምሳሌ፣ የገቢዎች ሚኒስቴር በ2014 በጀት ዓመት 360 ቢሊዮን ብር ሊሰበስብ እቅድ ይዞ፤ ከዚህ ውስጥ 336 ነጥብ ሰባት ቢሊዮን ብር በመሰብሰብ የእቅዱን 93 ነጥብ 53 በመቶ ነው ማሳካት የቻለው። በተመሳሳይ መልኩ በ2015 ዓ.ም 450 ቢሊዮን ብር (266 ነጥብ 95 ቢሊዮን ብር ከአገር ውስጥ ታክስ እንዲሁም 183 ነጥብ 34 ቢሊዮን ብር ከወጪ ንግድ፣ ቀረጥና ታክስ) ለመሰብሰብ ነው እቅድ የያዘው።
ይሄንን እቅዱን ማሳካት አለማሳካቱ በበጀት ዓመቱ መጨረሻ ላይ የሚታወቅ ቢሆንም፤ ሚኒስቴር መስሪያቤቱን የሚከታተለው ቋሚ ኮሚቴ አባላት ግን፤ በአሥር ዓመቱ መሪ የልማት ዕቅድ መሠረት ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ በ2015 ዓ.ም ማቀድ የነበረበት አጠቃላይ ገቢ 497 ቢሊዮን ብር ሊሆን ይገባው እንደነበር መግለጻቸው የሚታወቅ ነው።
ይሄም የሚያሳየው ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ምንም እንኳን በእቅድ አፈጻጸም ረገድ ውጤታማ ነኝ ቢልም፤ በአንድ በኩል ሊያሳካ ያቀደውን እንኳን ሙሉ በሙሉ አለማሳካቱን፤ በሌላ በኩል አገራዊ የገቢ ፍላጎቱንና መሪ እቅዱን ማዕከል አድርጎ አለማቀዱን (በቋሚ ኮሚቴው አቅጣጫ መሰረት የ2015 ብቻ የ47 ቢሊዮን ብር ልዩነት ማሳየቱን ልብ ይሏል) ነው መረዳት የሚቻለው።
የታክስ ሥርዓቱ ፈተናዎች እና መፍትሄዎች
በኢትዮጵያ የታክስ እና ግብር ሥርዓቱን ውጤታማ ለማድረግ በአደረጃጀትም፣ በሕግ ማዕቀፍም የተለያዩ ማሻሻያዎች እየተወሰዱ፣ መጠነኛ ለውጥም እየታየ ቢሆንም፤ ዛሬም ድረስ የግብር አስተዳደር ሥርዓቱን እየፈተኑ የዘለቁ በርካታ ችግሮች አሉ። በዚህ ረገድ ተቋማዊ ጉዳዮች፣ የሕግና አሰራር፣ የግብር ከፋዩ አመለካከትና የሞራል ደረጃ፣ የሕብረተሰቡ የባለቤትነት መንፈስ እንዲሁም ከሰላምና ፀጥታ ጋር ተያይዘው የሚነሱ አንኳር ጉዳዮች ተጠቃሽ ናቸው።
ለምሳሌ፣ ከተቋም እንዲሁም ከሕግ እና አሰራር ጋር በተያያዘ የሚነሱ ችግሮች አሉ። እነዚህ አንድም በተቋማት ያለው የሰው ኃይል በእውቀት፣ ክህሎት እና ሥነምግባር ጋር የሚያያዝ ሲሆን፤ በዚህም ግብር ሰብሳቢውም ሆነ አጋር አካላት የታቀደውን ገቢ እንዲሰበሰብ ከማድረግ አኳያ ከሰው ኃይላቸው አሰራር አንጻር በሚገለጽ ችግር ሲያጋጥማቸው ይታያል። ይሄም አሰራሩን በውል ተገንዝቦ ካለመተግበር ጀምሮ ይሁነኝ ተብሎ ከአሰራሩ ባፈነገጠ መንገድ የተሰጣቸውን ኃላፊነት ለብልሹ አሰራርና ላልተገባ ጥቅም ማካበቻ የሚያደርጉበት ሂደት ነው።
በሌላ በኩል የሚነሳው የግብር ከፋዩ የሕግ ተገዢነት እና የሞራል ሁኔታ ሲሆን፤ በዚህም በአንድ በኩል ግብር ከፋዩ አካል ለሕግ እና ለሞራል እሴቶች ተገዢ ከመሆን ይልቅ፣ በግብር ስወራና ማጭበርበር ላይ ተሰማርቶ መገኘቱ፤ በሌላ በኩል፣ የሕግ ክፍተቶችን እንደ መልካም አጋጣሚ በመጠቀም መክፈል የሚገባውን ታክስና ግብር ላለመክፈል ሲተጋ መታየቱ ነው።
በሕብረተሰቡ ውስጥ ያለው የያገባኛል ስሜት አናሳ መሆን እና ከሕግ ማስከበር ርምጃዎች ደካማነት ጋር ተያይዘው የሚነሱ ጉዳዮችም ተደማሪ የታክስ ሥርዓቱ ፈተናዎች ናቸው። ለዚህም አንድም ሕብረተሰቡ የግብር ጉዳይ የሰላሜ፣ የልማቴ፣ የሉዓላዊነትና ብልጽግናዬ መሰረት ነው ብሎ ያለማሰብ፤ ሁለተኛም፣ የሚሰበሰበው ግብር ለሚፈለገው ዓላማ አይውልም ብሎ እምነት የማጣት ጉዳይ ይነሳል።
ይሄ ደግሞ በአንድ በኩል ግንዛቤ ያለመፍጠር ክፍተት የወለደው ሲሆን፤ በሌላ በኩል ግን ሕብረተሰቡን እምነት እንዳይኖረው የሚያደርጉ የሕግ ጥሰቶች ሲፈጠሩ አስተማሪ እና ሕዝቡ “አጥፊዎች እንዲህ ከተቀጡ እኔም ግብር ሰዋሪዎችን የማጋለጥ ኃላፊነቴን ልወጣ” የሚል መንፈስን እንዳይሰንቅ የሚያደርገው ነው። በመሆኑም የግንዛቤ ክፍተት እና የሕግ ማስከበር አሰራሩ መላላት ህብረተሰቡ የዚህ ተግባር ንቁ ተዋናይ እንዳይሆን አድርጎታል ማለት ይቻላል።
ሌላው፣ ኮንትሮባንድ እና ሕገወጥ ንግድ ነው። ኮንትሮባንድን በመከላከል ረገድ በተለይም በጉሙሩክ ኮሚሽን እና ባለድርሻ ተቋማት በኩል ዘርፈ ብዙ ተግባራት እየተከናወኑ ናቸው። በዚህም አበረታች የሚባል ውጤት እየተገኘ ቢሆንም፤ ችግሩን በሚፈለገው ደረጃ መቅረፍ ባለመቻሉ ጠንካራ እና አስተማሪ ርምጃዎችን በመውሰድ የታገዘ ስራን መከወን ይጠይቃል።
ምክንያቱም፣ ዛሬ ላይ ኮንትሮባንድ እና ሕገወጥ ንግድ፣ ገቢን መሰወር፣ የሕግ ተገዢነት ማነስ፣ የግብር መክፈል ሞራላዊ ልምሻ፣ የአሰራርና ቴክኖሎጂ ውስንነቶችን የመሳሰሉ ችግሮች የገቢ አሰባሰብ ሥርዓቱ ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ ሲያሳድሩ ተስተውሏል። ከዚህ በተጓዳኝ ከሰላምና ጸጥታ ጋር በተያያዘ በየጊዜው የሚስተዋሉ ችግሮች በርካታ ግብር ከፋዮች ከግብር ሥርዓቱ ውጪ ሆነው እንዲቆዩ በማድረግ የገቢ አሰባሰብ ሂደቱ ላይ ጥላ ማጥላታቸው አልቀረም።
በመሆኑም ችግሩን ከመቅረፍ እና ገቢን ከማሳደግ አኳያ የሰው ኃይሉን፣ ተቋማዊ አደረጃጀትን እና የቴክኖሎጂ አቅምን ማጎልበት፤ የሰላምና ጸጥታ ጉዳዮችን ሰላማዊ እልባት መስጠት፤ የሕብረተሰቡን የባለቤትነት መንፈስ በማሳደግ እና ተሳታፊ ማድረግ፤ የሕግ ተገዢነትን እና ተጠያቂነትን ማስፈን የመሳሰሉ ርምጃዎችን መውሰድ አስፈላጊም፣ ተገቢና የግድም ነው።
በተለይ የታክስ እና ግብር አሰባሰብ ሂደቱን ውጤታማ ከማድረግ (የኮንትሮባንድ እና ሕገ ወጥ ንግድ፣ የገቢ መሰወር፣ የደረሰኝ አለመቁረጥ እና ተየያዥ ችግሮችን ከማቃለል) አኳያ በቴክኖሎጂ መታገዝ ካልተቻለ፤ የታክስ አስተዳደሩ የሚፈለገውን አይነት ውጤት ሊያመጣ አይችልም። ምክንያቱም ቴክኖሎጂው ሥራን በጥራትና በቅልጥፍና ከመከወን ባሻገር ከአሰራር ብልሹነት ጋር የሚፈጠሩ ችግሮችን ፈር ለማስያዝ ያስችላል።
ከዚህ ጎን ለጎን የሕብረተሰቡን የታክስ ንቃተ ሕሊና ማሳደግ ይገባል። ይህ ሲሆን በአንድ በኩል ግብር ለምን እና ለማን እንደሚከፍል፣ የሚከፍለው ግብር ለምን ዓላማ እንደሚውል እንዲገነዘብና ግብርን በኃላፊነት እንዲከፍል ያስችለዋል። በሌላ በኩል የንግዱ ማህበረሰብ ዘንድ ከደረሰኝ አለመስጠት ጋር ለተያያዘው ችግር መፈታት አጋዥ አቅም እንዲሆን ያስችላል። ከዚህ በተጓዳኝ ከታክስ ፖሊሲው ጋር የተያያዙ ችግሮችን የማሻሻል፤ በታክስ አስተዳደሩም ላይ ያሉ ችግሮችን የማስወገድ ርምጃዎችን መውሰድ ይገባል።
የመንግስት የበጀት ወጪና ገቢ ፍላጎቶች ምልከታ
ወደ ጉዳዩ ለመዝለቅ ያመቸን ዘንድ ቀደም ያሉትን ሦስት እና አራት ዓመታት የመንግስትን የበጀትና የገቢ ሁኔታ ለመዳሰስ ልሞክር። ለምሳሌ፣ ከ2011 እስከ 2013 በጀት ዓመት ጠቅላላ የመንግስት ገቢ 18 ነጥብ 6 በመቶ ዓመታዊ ዕድገት ያስመዘገበ ሲሆን፤ ከዚህ ውስጥ የታክስ ገቢ ዓመታዊ ዕድገት 18 ነጥብ 3 በመቶ እንደነበር ነው የገንዘብ ሚኒስቴር መጋቢት/2014 ዓ.ም ያወጣው የመካከለኛ ዘመን /2015-2019/ የማይክሮ ኢኮኖሚ እና ፊሲካል ማዕቀፍ ሰነድ ያመለክታል።
በዚህ ሰነድም ሆነ የኢፌዴሪ የ2015 በጀት ዓመት የተደገፈ በጀት ሰነድ ላይ እንደተመላከተው፤ በእነዚህ ሦስት ዓመታት የታክስ ገቢ በአማካይ 79 ነጥብ 3 በመቶ በመሆን ከአጠቃላይ የመንግስት ገቢ ውስጥ ከፍተኛውን ድርሻ የያዘ ቢሆንም፤ ከአጠቃላይ የአገር ውስጥ ምርት ያለው ድርሻ ግን በ2010 ከነበረበት 10 ነጥብ 7 በመቶ በማሽቆልቆል በ2013 ዘጠኝ በመቶ ሆኗል።
ይሄንን ለማሻሻል በታክስ ፖሊሲና በታክስ አስተዳደር ላይ የተደረጉ በርካታ ማሻሻያዎች ኢኮኖሚው ከገጠመው ተግዳሮት ጋር ተያይዞ ውጤት ሊያሳዩ እንዳልቻሉም ነው መረጃዎቹ የሚያመለክቱት። የውጪ እርዳታም ቢሆን ቅናሽ የታየበት ነበር።
በሌላ በኩል፣ በእነዚህ ሦስት ዓመታት ጠቅላላ የመንግስት ወጪ በየዓመቱ የ19 በመቶ ዕድገት ያሳየ ሲሆን፤ የመደበኛ ወጪ የ20 በመቶ እና የካፒታል ወጪዎች የ18 በመቶ ዓመታዊ አማካይ ዕድገት አስመዝግበዋል።
የ2014 በጀት ዓመትን በተመለከተም፤ የፌዴራል መንግስት ወጪ ለመሸፈን 436 ቢሊዮን ብር ከታክስና ታክስ ካልሆኑ ገቢ እና ከውጭ ዕርዳታ ለማግኘት፤ 106 ቢሊዮን ብር የሚሆነውን የበጀት ጉድለት ደግሞ 38 ቢሊዮን የውጭ እና 68 ቢሊዮን የአገር ውስጥ የተጣራ ብድር በመውሰድ መሸፈንን ታላሚ ያደረገ ነበር። በሰሜኑ ኢትዮጵያ የተከሰተው ጦርነት ያደረሰው ከፍተኛ የሰብዓዊና የኢኮኖሚ ጉዳት በመንግስት ላይ ተጨማሪ የወጪ ፍላጎት መጠየቁ ይታወቃል።
786 ነጥብ 61 ቢሊዮን ብር የተያዘለት የ2015ም ከታክስ ገቢ፣ ታክስ ያልሆኑ ገቢዎች እና የውጭ ዕርዳታ የገቢ ምንጮችን በመተማመን የተዘጋጀ ሲሆን፤ በእቅድ የተቀመጠው የ477 ነጥብ 78 ቢሊዮን ብር ገቢ እና የ786 ነጥብ 61 የመንግስት ወጪ መካከል የ308 ነጥብ 83 ቢሊዮን ብር (የአገር ውስጥ ምርት 3 ነጥብ 4 በመቶ ድርሻ ያለው ነው) የበጀት ጉድለት መኖሩን ነው የኢፌዴሪ የ2015 በጀት ዓመት የተደገፈ በጀት ሰነድ ላይ የተመላከተው።
ግንቦት 2015 ዓ.ም በሚኒስትሮች ምክር ቤት 21ኛ መደበኛ ስብሰባ ላይ ቀርቦ 801 ነጥብ 65 ቢሊዮን ብር እንዲሆን ውሳኔ ያገኘው እና ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርቦ ለዝርዝር እይታ ወደ ቋሚ ኮሚቴ ተመርቶ ያለው የ2016 በጀት ዓመት የፌዴራል መንግሥት ረቂቅ በጀት፤ በጀቱ የፌዴራሉን መንግሥት በአስር ዓመቱ መሪ የልማት ዕቅድ ያስቀመጣቸውን ታላሚ ግቦች ታሳቢ ያደረገ ስለመሆኑ ነው የተነገረው።
በዚህም ለፌደራል መንግሥት መደበኛ ወጪዎች 369 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር፣ ለካፒታል ወጪዎች 203 ነጥብ 9 ቢሊዮን ብር፣ ለክልሎች የሚሰጥ ድጋፍ 214 ነጥብ 07 ቢሊዮን ብር፣ ለዘላቂ የልማት ግቦች ማስፈጸሚያ ድጋፍ 14 ቢሊዮን ብር እንዲውል የታሰበ ነው።
በጀቱ ከዓምናው በጀት አንጻር መጠነኛ ጭማሪ ያለው ቢሆንም፤ እንደ 2015ቱ ሁሉ ከፍ ያለ የበጀት ጉድለት የታየበት ስለመሆኑም ነው የተመላከተው። በዚህም የ281 ቢሊዮን ብር ጉድለት የታየበት ሲሆን፤ ይሄ ደግሞ መንግስት የበጀት ጉድለቱን ለመሙላት ከአገር ውስጥ እና ከውጪ ብድር ለመውሰድ እንደሚገደድ አመላካች ነው።
ረቂቅ በጀቱ ለምክር ቤት በቀረበበት ወቅት ወጪውን ለመሸፈን ይችል ዘንድ ከአገር ውስጥ ገቢ እና ከውጪ አገር ርዳታ ምንጮች 520 ቢሊዮን ብር ለመሰብሰብ ያቀደ ሲሆን፤ የበጀት ጉድለቱ 242 ቢሊዮን ብር ከአገር ውስጥ ብድር፣ ቀሪው 39 ቢሊዮን ብር ከውጭ ብድር እንደሚሸፈን መገለጹም ይሄንኑ የሚያረጋግጥ ነው።
በዚህ መልኩ የሚገለጸው አገራዊ የበጀት ወጪ እና የገቢ ሁኔታ የሚያስረዳው፤ ከግብር እና ታክስ የሚሰበሰበው ገንዘብ ከጊዜ ወደ ጊዜ የቁጥር መሻሻል ያሳያ ቢሆንም፤ ከመንግስት የወጪ እድገት እና የገቢ ፍላጎት አንጻር ሲታይ የሚፈለገውን ያህል አለመሆኑን ነው። ከዚህም በላይ ከአገር ውስጥ ምርት ጥምርታ አኳያ ሲታይ እያሽቆለቆለ ያለ እና ይሄንን ለማሻሻል ትልቅ ትኩረት ሰጥቶ መስራት እንደሚገባ ያረጋገጠ እውነት መሆኑን ለመረዳት ያስችላል።
እንደ መውጫ
በ2016 በጀት ዓመት ሊኖር የሚችለው የሃብት ፍላጎት እንዲሁም የታየው የበጀት ጉድለት መንግስት ለሚያከናውናቸው ተግባራት ከፍ ያለ ገቢ እንደሚፈልግ አመላካቾች ናቸው። በተለይ መንግስት የፋይናንስ ፍላጎቱን ለማሟላት ሲል ወደ ብድር አልያም ወደ ገንዘብ ሕትመት የሚገባ ከሆነ እንደ አገር ሊፈጥር የሚችለውን የዋጋ ንረት እና የኑሮ ውድነት ሁሉም ሊገነዘበው የሚችለው ሃቅ ነው። በመሆኑም ይሄ እንዳይሆን የአገር ውስጥ ገቢን ማሳደግ የቅድሚያ ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባ ታላቅ የቤት ስራ ነው።
ይሄን የአገር ውስጥ ገቢ ማሳደግ እና ውጤታማ የግብር ስርዓት እውን እንዲሆን ደግሞ የአንድ ተቋም ወይም አካል ተግባር ብቻ ሊሆን አይገባም። ምክንያቱም ግብር ሰብሳቢው ተቋም እሰበስባለሁ ብሎ ስለተነሳ ብቻ የሚፈልገውን ሃብት/ገቢ መሰብሰብ አይችልም። በመሆኑም ግብር ሰብሳቢው ተቋም እና አጋር የመንግስት ኃይሎች (በፌዴራልም ሆነ በክልል ደረጃ)፤ ግብር ከፋዩ ማህበረሰብ እንዲሁም ሁሉም ዜጋ፤ በበጀት ዓመቱ ሊሰበሰብ የሚገባው ግብር ለእሱም ሆነ ለአገሩ ምን ማለት እንደሆነ ተገንዝቦ የበኩሉን ሚና ሊወጣ ይገባል።
እያሽቆለቆለ የመጣው የግብር እና የአገር ውስጥ አጠቃላይ ምርት (ጂ.ዲ.ፒ) ጥምርታ ገጽታም መቀየር ያስፈልጋል። ምክንያቱም ሁነቱ ህብረተሰቡ የግብር ግዴታውን እየተወጣ፤ መንግስትም ኢኮኖሚው ከሚያመነጨው ሃብት ገቢ እየሰበሰበ እንዳልሆነ እማኝ ነው። ይህ ደግሞ መንግስት ለሕዝቡ ማድረስ የሚገባውን አገልግሎት እንዳያዳርስ፤ የመሰረተ ልማት ስራዎቹም እንዲቀንሱ ያስገድደዋል።
በመሆኑም የግብር አሰባሰብ ሂደቱን ውጤታማ ለማድረግ መስራት እንደተጠበቀ ሆኖ፤ መንግስት (እንደ አጠቃላይ ተቋማት እና መዋቅሩ) የተያዘውን በጀት እና የሚሰበሰበውን ሃብት በአግባቡ (በቁጠባ እና ለታለመለት ዓላማ ብቻ እንዲውል በማድረግ) መጠቀም ይኖርባቸዋል። ምክንያቱም ሃብቱም የሚፈለገውን ውጤት የሚያመጣው ለታለመለት ዓላማ ሲውል፤ ሕብረተሰቡም ለመክፈልም፣ እንዲከፈል ድርሻ ወስዶ ለመስራትም ተነሳሽነትና ቁርጠኝነቱ የሚኖረው የተሰበሰበው ግብር የሚታይ ስራ ተሰርቶበት ሲመለከትና ከልማቱም ተጠቃሚነቱን ሲያረጋግጥ ስለሆነ ነው።
በመሆኑም መንግስትም፣ ህብረተሰቡም የየድርሻውን ከተወጣ ታክሱ ተሰብስቦ የአገራችንን ልማት ወደፊት ማራመድ ይችላል። ለዚህ ደግሞ ሁሉም ዜጋ “ይሄንን የማደርገው ለማንም ብዬ ሳይሆን፤ ለራሴ፣ ለልጆቼ፣ ለወገኖቼ፣ ለአገሬና እንደ አጠቃላይ ለሕዝቤ ነው” የሚል መንፈስን ሊላበስ ይገባል። መንግስትም በጀቱንም አሰራሩንም ግልጽ ማድረግ አለበት።
በመሆኑም የ2016 በጀት ዓመት የገቢ አሰባሰብ ሂደቱ አገራዊ የሃብት ፍላጎቱንና የበጀት ጉድለቱን ያገናዘበ ሊሆን ይገባዋል። “በ2022 ዘመናዊ የታክስ አስተዳደር ተገንብቶ አገራዊ ወጪ በታክስ ገቢ ተሸፍኖ ማየት” የሚለው የገቢዎች ሚኒስቴር ርዕይ ሊሳካ የሚችለውም፤ ቃልን በጽሑፍ ከማኖር ያለፈ ዘመናዊ የታክስ አሰባሰብ ሥርዓትን እውን በማድረግ እና ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን የታክስ ገቢ በመሰብሰብ ሲገለጽ ነው። ይህ ሲሆን ነው አገራዊ የወጪ ፍላጎቱ በራስ አቅም ሊፈጸም የሚችለው።
ማሙሻ ከአቡርሻ
አዲስ ዘመን ሰኔ 16/2015