እንደ አገር ትልቅ ህልም አለን፡፡ ኢትዮጵያ ሙሉ ሆና ለማየት፣ ሕዝባችን ከድህነት ተላቆ ከተረጂነት እንዲወጣ የተመኘነውን ያክል ምንም ነገር ተመኝተን አናውቅም፡፡ ምኞታችን ግን ሆኖ አገራችንን ከኋላቀርነት፣ ሕዝባችንን ከድህነት ሲታደገው አላየንም፡፡ ለምን? ይሄ የለምን ጥያቄ ሁላችንንም የሚመለከት የጋራ ጥያቄ ነው፡፡
አብዛኞቹ የአገራችን ችግሮች በጠያቂ ትውልድ በኩል የሚመለሱ ናቸው፡፡ ጠያቂ ትውልድ በጥያቄው ፖለቲከኞችን የሚሞግት እና ለሕዝብ ጥያቄ መልስ የሚፈልግ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ችግሮች ከዛሬ ወደነገ እንዳይሄዱ ያለን አማራጭ እንደብሔራዊ ምክክር በመሰሉ ሕዝባዊ መድረኮች ላይ መወያየት ነው፡፡
ስንወያይ ግን ለመግባባትና አንድነታችንን ለማጠንከር መሆን አለበት፡፡ እንዳለፈው ጊዜ ለውጥ ባላመጣ ውይይትና ምክክር ውስጥ ህልሞቻችንን መውለድ አንችልም፡፡ በእያንዳንዳችን አእምሮ ውስጥ ኢትዮጵያ ክበድ ናት፡፡ ጸንሰናት ግን ልንወልዳት አልቻልንም፡፡ ለክብሯ የሚመጥን ኢትዮጵያዊ አንድነትና ፍቅር ያሻታል። በዛ ካልታረሰች በምንም ብናርሳት ልክ አንሆንም፡፡
ኢትዮጵያን እስካሁን ያልወለድናት ለክብሯ የሚመጥን የፍቅርና የአንድነት ግርግም ስላላዘጋጀንላት ነው፡፡ ህልሞቻችን ከምኞት ባለፈ መሬት ያልወረዱት ቂምና ብሔርተኝነትን ባነገቡ አእምሮና ልቦቻችን ስለተጸነሱ ነው፡፡ ትግላችን አገር መፍጠር ከሆነ፣ እንደ ፖለቲከኛ ተቧድነን የምረጡኝ ቅስቀሳ የምናካሂደው አገር ለማሻገር ከሆነ ልቦቻችንን ከእኔነት፣ አእምሯችንን ከራስ ወዳድነት ልንጸዳ ይገባል፡፡
የተሻለች – የበለጸገች አገር መፍጠር ለምን አቃተን? ወጣት የበዙባት፣ በየአመቱ ከሁለት መቶ ሃምሳ ሺ በላይ ተማሪዎችን አስተምራ የምታስመርቅ አገር፣ ስልጣኔና ፊተኝነት መጠሪያዋ የሆነች ምድር፣ ዓድዋን የፈጠረች፣ የዚህኛውና የዛኛው ትውልድ የነጻነት በር፣ የጥቁሮች የትንሳኤ በትር፣ የትኛውም ቃልና ፍልስፍና የማይገልጻት አገር ለራሷ የሚሆን ሰላም፣ ለሕዝቦቿ የሚሆን ዘመናዊነት፣ ለትውልድሱ የሚሆን የሀቅ መረማመጃ እንዴት አጣች?
ኢትዮጵያን ያቆሸሻት ፖለቲካው ነው፡፡ ፖለቲካው እስካልጸዳ ድረስ ኢትዮጵያ የምትባለው አገር ከመቆሸሽ አትድንም፡፡ ፖለቲከኞቻችን ለሚሆነው ነገር ኃላፊነት የሚወስዱ ሳይሆኑ ክርስቶስን ሰቅሎ በርባንን እንደፈታው ጲላጦስ እጃቸውን ታጥበው ከደሙ ንጹህ ነኝ የሚሉ ናቸው፡፡
ሥርዓት ሰርተው፣ ፓርቲ አቋቁመው አገር እየመሩ ከደሙ ንጹህ ነኝ ማለት ጥሩ ያለማወቅ ማሳያ ነው። ትላንታችን እንዲህ ባለው ራስን ነጻ በማድረግና ሌላውን ተጠያቂ በማድረግ እሳቤ ውስጥ ነበር፡፡ ይሄ ፖለቲካዊ አስተሳሰብ ከምኞት ባለፈ የምንፈልጋትን አገር፣ የምንፈልገውን ሕዝብ፣ የምንፈልገውን ትውልድ፣ የምንፈልገውን ስልጣኔ አልሰጠንም፡፡
እናም ለዘመናት ሳትወለድ የጸነስናት ኢትዮጵያ እውን እንድትሆን ከምኞታችን ጋር መሳለመሳ የቆመ ፖለቲካና ተግባር ያስፈልገናል፡፡ ከትላንት እስከዛሬ በተራመድነው የፖለቲካ ዳና ላይ ከህልማችን እኩል የሆነ ተግባርና ቅንጅት አልነበረንም፡፡ ለዛም ነው ህልመኞች ብቻ ሆነን የቀረነው፡፡
በህልሞቻችን ውስጥ ፍቅርና ወንድማማችነት ከሌለ ሩቅ መራመድ አንችልም፡፡ ፍቅርና አንድነት የሌላት አገር ማር የሌለው ቀፎ ናት፡፡ አገራችንን በራስ ወዳድነት ለማንም እንዳትበጅ አበባ ከሌለው፣ ንቦች ከማያጠዘጥዙበት ስፍራ የሰቀልናት እኛው ነን፡፡ ቀፏችን ማር እንዲይዝ ስፍራ መቀየር አለብን፡፡ አገራችን ለሁላችን እንድትበቃ በሁላችን የተዋቀረች የሁላችን ሀሳብ ውጤት ልትሆን ይገባል፡፡
እንደ አገር ትልቁ ህልማችን ሰላም ነው፡፡ እንደ አገር ትልቁ ህልማችን በአንድነቱ የሚደነቅ ማህበረሰብ መፍጠር ነው፡፡ እኚህ የጋራ ህልሞቻችን እውነትነት እንዲለብሱ በፖለቲካ እድፍ የቆሸሹ አንዳንድ የእኔነት እሳቤዎች መጽዳት አለባቸው፡፡
በፍልስፍናው ዘርፍ አንድ እውነት አለ..‹ዓለምን ለመቀየር መጀመሪያ ራስን መቀየር› የሚል፡፡ አገራችንን ለመቀየር መጀመሪያ ራሳችንን መቀየር አለብን፡፡ የእኔና የሌላው ሰው የአስተሳሰብና የተግባር ነጸብራቅ ነው አገር የሚሰራው፡፡ አገራችን ወደፊት መራመድ አቅቷት ባለችበት እየረገጠች ያለችው በእኔና በእናንተ ዘመኑን ያልዋጀ የብሔር ኣስተሳሰብ ነው፡፡
ይሄ አስተሳሰብ አገር አይሰራም፡፡ የእኔ የአንተ ከማለትና ትላንትን እያስታወሰ ቁርሾ በመፍጠር ባለፈ የጋራ እውነት አይሰጠንም፡፡ እንደ ህልመኛ የኢትዮጵያን ነባርና ወቅታዊ የፖለቲካ ትኩሳት አስታውሰን ብዙ ነገር ልንመኝ እንችላለን፡፡ እንደ አገርና እንደማህበረሰብ ተመኝተናቸው ያጣናቸው በርካታ የጋራ ፍላጎቶች አሉን። እነዚህ የጋራ ፍላጎቶች ነፍስ ዘርተው አገር እንዲጠቅሙ በህልሞቻችን በኩል የተዋወቅንው የጋራ እሴትና አንድነት ያስፈልገናል፡፡
አገራችን ኢትዮጵያ ላለፉት ሁለት አመታት ጦርነት ውስጥ እንደነበረች ይታወቃል፡፡ የቅርብ ጊዜ ትውስታችንን አነሳሁ እንጂ ያለፉት ሃምሳና ስድሳ አመታትም እንደ ቅርብ ጊዜ ትውስታችን መከራንና እንግልትን የሚያስታውሱን ናቸው፡፡ በፖለቲካው ረገድ በበጎ የሚጠቀስ ታሪክ አልጻፍንም፡፡
አፄ ኃይለሥላሴ በኃይል ነው ከስልጣን የተገረሰሱት። አፄውን ጥሎ ወደ ስልጣን የመጣው ደርግም በኢህአዴግ ከስልጣን ተወግዷል፡፡ ኢህአዴግም ከብልጽግና ጋር የነበረውን ትንቅንቅ ሁላችንም የምናስታውሰው ነው። ፖለቲካችን እንደዚህ ነው..በጦርነት ጀምሮ በጦርነት የሚያበቃ፡፡
ስልጣን የምንይዘው በጦርነት፣ ከስልጣን የምንወርደው በጦርነት፡፡ ላለፉት ብዙ አመት በሰላም የተያዘ ስልጣን፣ በሰላም የተለቀቀ ስልጣን የለንም። አይገርምም? የኢትዮጵያ የኋላቀርነት ነቀርሳ ከዚህ የስልጣን ጥም ውስጥ የሚመዘዝ ነው፡፡ በጦርነት ተጀምሮ በጦርነት ያበቃ ፖለቲካ ውስጥ እንዴት ነው አገር ልዕልና የሚኖራት? እንዴት ነው ሕዝብ ከድህነት የሚወጣው? እንዴት ነው ህልሞቻችን መሆንን የሚወርሱት?
ይሄን የጦርነት ታሪክ መቀየር አለብን፡፡ የመጣንበትን የኃይል ርምጃ በሰላም ሀሳቦች አሟሽተን ሌላዋን ኢትዮጵያ ደግሞ እንያት፡፡ ሰላም ባልገባበት የጠብ ፖለቲካ ለሃምሳና ለስልሳ አመታት አንድ አይነት ሆነን ሰንብተናል፡፡ ራስ ተኮር በሆነ ፖለቲካዊ አስተሳሰብ፣ የአንድ ቡድን የበላይነት በሚመስል እሳቤ ሩቅ በማይወስድ የቅርብ ርምጃ ስንፍገመገም ነበር፡፡
እነዛ ነውረኛ ኮቴዎች ናቸው ዛሬ ላይ ከጦርነት አጀንዳ ሌላ ምንም የሌላትን አገር የሰጡን፡፡ እነዛ ነውረኛ የእኔነት እሳቤዎች ናቸው ዛሬ ላይ ፖለቲካችንን በብሔር እድፍ ያጨማለቁት፡፡ አገር የምትቀየርበትን የሰላም አጀንዳ መፍጠር አለብን፡፡ በተዋጣ ሃሳብ፣ ባስታራቂ እውነት አገራችን ከፍ የምትልበትን መላ መዘየድ ከእያንዳንዳችን ይጠበቃል፡፡
በጦርነት ውስጥ የሚሞት ሰው የለም፡፡ በጦርነት ውስጥ አገር ነው የምትሞተው፡፡ ስንገልና ስንሞት አገራችንን እየገደልናት ነው፡፡ በጥላቻ ስንገፋፋ አገራችንን እየገፋናት ነው፡፡ በጦርነት ውስጥ ሰው ሲሞት አገር ነው የምትሞተው፡፡ ሰው ሲደማ አገር ነው የምትደማው፣ ሰው ሲሰደድ አገር ነው የምትሰደደው፡፡
ጦርነትን በተመለከተ ከዚህ የራቀ እውነት አልተገለጠልኝም፡፡ አንድ ሰው በሞተ ቁጥር አገር እየሞተች እንደሆነ ነው የገባኝ፡፡ እስከዛሬ ድረስ ባለመግባባት ኢትዮጵያን ገለናታል፡፡ ክብሯን ዝቅ አድርገንዋል፡፡ እስከዛሬ አገራችንን ነው የገደልናት፡፡ እስከዛሬ አገራችንን ነው ከሙላት ያጎደልናት፡፡
ዛሬ ላይ አልሞላ ያለን የሕይወት ኮሮጆ እኮ ያ ትላንት ላይ በጦርነት ያጎደልነው ጸጋችን ነው፡፡ ዛሬ ላይ አልደፈን ያለን የድህነት ቀዳዳ፣ የኋላቀርነት ሽንቁር ትላንት ላይ በጦርነት የሸነቆርነው የእምዬ ጓዳ ነው፡፡ ዛሬ ላይ አልጠራ ያለን የፖለቲካ እድፍ ትላንት ላይ ያበላሸነው የእምዬ መልክ ነው፡፡ መልካችን እንዲጸዳ ጦርነትን እርም ማለት አለብን፡፡ ኢትዮጵያዊነት እንዲመለስ ሰላም አጀንዳዎችን መፍጠር አለብን፡፡
ፍቅር የሚወራበት አንድነት የሚነገርበት የእርቅ መድረኮች ያስፈልጉናል፡፡ የምንመራረቅበት፣ የምንመሰጋገንበት፣ የምንተቃቀፍበት የእርቅ አጀንዳዎች ያስፈልጉናል፡፡ እየገደሉ መሞት ጀግንነት አይደለም.. እየኖሩ ማኖር ነው ጀግንነት፡፡ በዚህ ዘመን በጦርነት ውስጥ ጀግንነት የማይታሰብ ነው፡፡
ጀግና ማለት በሰላም ሀሳብ ውስጥ የቆመ ነው፡፡ ጀግና ማለት ጥልን ገሎ ፍቅርን የሚሰብክ ነው፡፡ ጀግና ማለት እንደ እየሱስ ለሌሎች ስለፍቅር መሞት ነው፡፡ ለዘመናት በጦርነት ውስጥ ጀግና ሆነን ኖረናል፡፡ እስኪ አሁን ደግሞ በሰላም ውስጥ ያለውን ጀግንነት እንተዋወቀው፡፡ እስኪ አሁን ደግሞ ገሎ በመሞት ሳይሆን ኖሮ በማኖር ጀግና እንሁን፡፡
ባለፈው ጊዜ ለጦርነት የሚሆን ብዙ አጀንዳ ሲኖረን ለሰላም ግን ምንም አልነበረንም፡፡ አጀንዳዎቻችን ሁሉ ፍቅርን የሚሽሩ፣ አንድነትን የሚሸረሽሩ ሆነው ዘልቀዋል። የጠራና የነጣ ፖለቲካ ቸግሮን ውሃ ቢወቅጡት እንቦጭ በሆነ ቁመና ውስጥ ነበርን፡፡ የእርቅና የሰላም አጀንዳ አጥተን የጦርነት ነጋሪት እየጎሰምን በብዙሃኑ መከራ ጥቂቶች ስናተርፍ ነበር፡፡
እናም አጀንዳዎቻችንን መቀየር ይኖርብናል። የመጣው ሰላም የደረቀ ተስፋችንን አለምልሞ ስብራታችንን እስኪጠግን ድረስ ከሰላም ውጭ ዜማ አይኑረን፡፡ ማንም የመውደቂያ ጉድጓዳችንን አልቆፈረም። የመውደቂያ ጉድጓዳችንን ስንቆፍር የነበረው እኛው ነን፡፡ ከጦርነት የመውጪያ አጀንዳዎች እንጂ ወደ ጦርነት የሚወስዱ አጀንዳዎች አይጠቅሙንም፡፡ ወደ ሰላም የሚያመጡ የእርቅ ስልቶች እንጂ ወደ መለያየት የሚወስዱ የጥላቻ ስልቶች አይጠቅሙንም፡፡
ስለውጊያ ስልት ስናወጣ፣ ስለ ጦርነት ስልት ስንነድፍ ግማሽ ምዕተ አመት አስቆጠርን፡፡ እስኪ አሁን ደግሞ አንደበታችን ስለሰላም ያውራ፡፡ እስኪ አሁን ደግሞ ከመግደልና ከመሞት ስልት ወጥተን ስለ ሰላም ስልት እንደፍ፡፡ ፖለቲካችን ሰንኮፉን ጥሎ በታደሰ ሥርዓት አገር እንዲሰራ ሀሳብ እናዋጣ፡፡
የሚያዋጣን በጋራ እርምጃ አልደረስ ያሉን ህልሞቻችን ላይ መድረስ ነው፡፡ አጀንዳ መፍጠር የፖለቲካ ጥንካሬን ወይም ደግሞ የአንድን ፖለቲከኛ ወይም ደግሞ የአንድን ፓርቲ የበላይነት አያሳይም፡፡ እንደ አገር ጥንካሬየችን ያለው ልዩነቶቻችንን በንግግር መፍታታችን ላይ ነው፡፡ በሚያግባቡን ነገሮች ላይ መስማማታችን ላይ ነው፡፡
ጦርነት ላደቀቃት፣ የፖለቲካ ትኩሳት ላነደዳት አገር ከአንድነት ሌላ ሽረት የላትም፡፡ በብሔር ደዌ ለምትሰቃይ፣ በእኔነት ካባ ለምትንፏቀቅ አገር የሰላም እና የእርቅ ከፍ ሲልም የወንድማማችነት አጀንዳ ነው የሚያስፈልጋት። ድህነትና ኋላቀርነት አልፎም የኑሮ ውድነት ላሰቃየው ማህበረሰብ የሚበጀው ከችግር የሚወጣበትን መላ መስጠት እንጂ አጀንዳ እየፈጠሩ በቁስሉ ላይ ጥዝጣዜ መፍጠር አይደለም፡፡
እንደአገር ትልቁ ህልማችን ምንድነው? በሚል የመነሻ ጽሁፍ ይሄን መሰሉን ወግ አውግተናል፡፡ የአገራችን ጉድ ብዙ ነው፡፡ በአንድ ጊዜ ተወርቶ የሚያልቅ አይደለም፡፡ መሻታችን አገር መስራት፣ ትውልድ ማሻገር ከሆነ ለማንም ከማይበጅ ከትንሹ የፉክክር እሳቤ ወጥተን ትልቁ ህልማችን ላይ ማተኮር አለብን፡፡
ትልቁ ህልማችን እኔ፣ አንተና አንቺ ሁላችን ያለንበት የጋራ ታሪካችን ነው፡፡ ትልቁ ህልማችን በፍቅርና በአብሮነት፣ በይቅርታና በወንድማማችነት የምንራመደው የብዙሃነት ጎዳና ነው፡፡ ትልቁ ህልማችን ኢትዮጵያን አስቀድመን የምናስበው ሀሳብ፣ የምንኖረው ሕይወት እሱ ነው፡፡
እንደአገር ተመኝተን ያጣነው ብዙ ነው፡፡ ዛሬም በዛ አልደረስ ባለን ምኞታችን ውስጥ በአምሮት የምንሰቃይ ነን፡፡ የአገራችን ፊተኝነት በእኛ እጅ ውስጥ ነው፡፡ ወደፊት እንዳንሄድ፣ ወደፊት እንዳናይ ያደረገንን የጥላቻ ጽንስ ስናስወርድ ብቻ ነው አልደረስ ካለን የስኬት ምኩራባችን የምንደርሰው፡፡
ትልቁ ህልማችን በትልቁ ሀሳባችን ውስጥ ነው፡፡ ትልቁ ሀሳባችን ደግሞ ሰላም ያለበት፣ ወንድማማችነት የቀደመበት የእርቅና የአብሮነት ሀሳብ ነው፡፡ በዚህ እውነት ውስጥ ርቀን ስንጓዝ ብቻ ነው አልደረስ ካለን የስልጣኔ ደጅ የምንደርሰው፡፡ ይሄን እውነት አምነን ስንቀበል ብቻ ነው ስማችን የሚታደሰው፡፡
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ሰኔ 14/2015