አበው «የበላ እና የተማረ ወድቆ አይወድቅም» ይሉት ብሂል፤ አንድም የበላ ጉልበቱ በቀላሉ ለዳገትም፣ ለድካምም እጅ አይሰጥም፤ አንድም የተማረ ለችግርና ፈተና መሻገሪያ መላ ከአዕምሮው ጓዳ እንደማይጠፋ ለማመልከት ነው። አንጋፋው ሙዚቀኛ አለማየሁ እሸቴም፣ በዜማው «ተማር ልጄ፣ ዘመድ አዝማድ የለኝ ሀብት የለኝም በእጄ፤» ሲል ለልጁ ብርቱ ምክር አዘል ማስጠንቀቂያ በግጥም ስንኞቹ ውስጥ ማኖሩ ይሄንኑ የትምህርትን ችግር አሻጋሪነት፤ ሀብትና ፀጋ አጎናጻፊነት የሚያስገነዝብ ነው።
እነዚህ እና ሌሎችም በብሂልም፣ በስንኝም የምናገኛቸው የመማርን ከፍ ያለ ዋጋ የሚያስረዱ አገራዊ ታሪኮች ታዲያ፤ ትምህርት በሰው ልጅ ሕይወት ውስጥ ምን ያህል ከፍ ያለ ቦታም፣ አቅምም እንዳለው የሚያረጋግጡ ናቸው። እርግጥ ነው ዓለምም በተማሩና በተመራመሩ ሕዝቦቿ ነው ዛሬ ላይ ከረቀቁት እስከ ገዘፉት የፈጠራ ቴክኖሎጂዎች ታግዛ የተወሳሰቡ ችግሮቿን መፍታት የምትችልበትን አቅም የተጎናጸፈችው።
በአገራችን ኢትዮጵያም ይሄው ዘመናትን ያስቆጠረው የቀለም አውድ (ቀድሞ በቤተ እምነቶች፣ ኋላም በዘመናዊው አስኳላ) ዜጎች ፊደል ከመቁጠር እስከ መመራመርና ፈጠራ የሚያዘልቃቸውን አቅም እንዲሰንቁ ሲያደርግ ቆይቷል። እያደረገም ይገኛል። ይሁን እንጂ ይሄ የተመራማሪነት እና የፈጠራ አቅምን የሚያጎናጽፈው ትምህርት፤ የሚፈለገውን አቅምና ክህሎት ለተማሪዎች ማጎናጸፍ አልቻለም። ከዚህ የተነሳም በትውልዶች ሆነ ከዚህ በሚመነጭው የአገር ግንባታ ላይ ትልቅ ተግዳሮት ሆኗል።
በዚህ ረገድ በአገራችን ኢትዮጵያ አፍ ሞልቶ «ትምህርት ድሮ ቀረ» ሊያስብል የሚያስችል በሁሉም መልክ የተደራጁ ትምህርት ቤቶች አሉ ባይባልም፤ አሁንም «ትምህርትስ ድሮ ቀረ» የሚሉ ቀደምቶች አልታጡም። ለዚህ እንደ ምክንያት የሚያቀርቡትን የቀደመው ትምህርት ከግብዓቱም ይሁን ከትምህርት ሥርዓቱ ይሄ ነው ብለው ባይለዩትም፤ ተማሪዎቹ ግን በእውቀትም፣ በአስተሳሰብ ብስለትም ከአሁኑ ቀለሜ ሻል ያሉ ስለመሆናቸው ይሞግታሉ።
ይሄ የቀደምቶች ብሂል እንደተጠበቀ ሆኖ፤ ዛሬ ላይ ሊካድ የማይገባው ሃቅ ግን ትምህርት ቤቶች የቁጥራቸውን ያህል በሚፈለገው መጠን የተደራጁ እና ለመማር ማስተማር ብቁ መሆን አለመቻላቸው ነው። ይሄንኑ እውነት መንግሥት በተለይም ዘርፉን የሚመራው ትምህርት ሚኒስቴር ደጋግሞ እወቁልኝ ያለ ሲሆን፤ ዛሬ ላይ የኢትዮጵያ ትምህርት ቤቶች ዘመኑን በሚመጥኑ እና የተማሪዎችን ሁለንተናዊ አቅም ከሚገነቡ ትምህርት ቤቶች ይልቅ፤ በጭቃ ቤት፣ በዳስ እና በዛፍ ጥላ ስር ተማሪዎችን አስጠልለው «እውቀት ቅሰሙ» የሚሉ ስለመሆናቸው በመረጃም፣ በማስረጃም አስደግፎ ገልጿል።
በእንዲህ ዓይነት ትምህርት ቤቶች ውስጥ የሚከናወን የመማር ማስተማር ሂደት ደግሞ ተማሪዎችን ትምህርት ቤት ውለን መጣን ከሚል እሳቤ የዘለለ፤ በትምህርት ቤት ቆይታቸው ይሄንን እውቀት ቀሰምኩ፣ ይሄንን አዲስ ክህሎት አዳበርኩ ብለው የሚጠቅሱት ተደማሪ አቅም ማግኘት አይችሉም። ይሄንኑ ሃቅ የሚያረጋግጥልን ደግሞ፣ የትምህርትና ሥልጠና ፍኖተ-ካርታ ጥናት እንዲሁም ሌሎች በዘርፉ የተደረጉ ጥናቶች የትምህርት ጥራት አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱን ማሳየታቸው ነው።
ለምሳሌ፣ በርካታ ትምህርት ቤቶቹ ከደረጃ በታች ብቻ ሳይሆን የዳስ እንደሆኑ የሚነገርለት የአማራ ክልል፤ ከሁለትና ሦስት ዓመታት በፊት የወጡ መረጃዎች እንደሚያሳዩት በክልሉ ከሚገኙ ዘጠኝ ሺ የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ውስጥ ሰባት ሺህ ያህሉ ከደረጃ በታች ናቸው። እነዚህ ትምህርት ቤቶች ደግሞ ከደረጃ በታች ከመሆናቸው ባሻገር ቀላል የማይባል ቁጥር ያላቸው የዳስ ትምህርት ቤቶች ናቸው። መደበኛ የሚባሉት ትምህርት ቤቶችም ቢሆኑም የወንበር፣ በር፣ መስኮትና ጥቁር ሰሌዳ ሳይቀር በተሟላ መንገድ የሌላቸውና ለመማር ማስተማሩ ሥራ ምቹ ያልሆኑ ናቸው።
በመሆኑም እነዚህን ትምህርት ቤቶች ከዳስ ትምህርት ቤትነት ከፍ ለማድረግ እንዲሁም አስፈላጊው ግብዓት እንዲሟላላቸው ለማድረግ የተወሰነ እንቅስቃሴ ተደርጎ ነበር። በዚህ እንቅስቃሴም በክልሉ አንድ ሺህ የሚደርሱ የዳስ ትምህርት ቤቶችን በጊዜያዊነት ወደ ቆርቆሮ መቀየር የተቻለ ሲሆን፤ በዚህ ሂደት የመንግሥት አቅም ውስን እንደመሆኑ ባለሀብቱ የራሱ አበርክቶ ነበረው። በዚህ ረገድ ሻለቃ አትሌት ኃይሌ ገብረሥላሴ አንድ የዳስ ትምህርት ቤትን ዘመናዊና ግብዓት ወደተሟላለት ትምህርት ቤት ቀይሮ ለተማሪዎችም ለወላጆችም እፎይታን መፍጠር፤ በትውልድ ግንባታ ሂደትም ተደማሪ አሻራውን ማኖር የቻለበት ሃቅ ተጠቃሽ ነው።
በአማራ ክልል በዚህ መልኩ የተነሳው መረጃና ተግባር ከሰሜኑ ጦርነት በፊት የነበረ ሲሆን፤ ጦርነቱ በትምህርት ተቋማትና ሌሎችም ላይ ከፍ ያለ ጉዳት ያሳደረ እንደመሆኑ ከዚያ በኋላ የትምህርት ቤቶቹ ሁኔታ ወዴት ሊያሽቆለቁል እንደሚችል መገመት አያዳግትም። ሻለቃ አትሌት ኃይሌ ገብረሥላሴ ከዳስነት ወደ ዘመናዊ ትምህርት ቤትነት የለወጠው ትምህርት ቤት ላይ የደረሰው ጉዳት ደግሞ ለዚህ አንዱ ማሳያ ነው።
ለሁለት ዓመታት የዘለቀው የሰሜኑ ጦርነት አማራ ክልልን ብቻ ሳይሆን ትግራይ እና አፋር ክልሎች ላይም ከፍ ያለ ጉዳትን ያስከተለ ነው። ከዚህ ባለፈም በኦሮሚያ፣ ደቡብ እና ቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልሎችን ጨምሮ በበርካታ የኢትዮጵያ ክፍሎች በነበሩ ግጭቶች ትምህርት ቤቶች የጥፋቱ ሰለባ ሆነዋል። በዚህም በሺዎች የሚቆጠሩ ትምህርት ቤቶች ለከፋ ጉዳት የተዳረጉ ሲሆን፤ እነዚህን መልሶ ለማደራጀትና ወደሥራ ለማስገባት ዘርፈ ብዙ ተግባራት እየተከናወነ ስለመሆኑም መገለጹ ይታወቃል።
ለምሳሌ፣ የትምህርት ሚኒስቴር የ2015 ዓ.ም በጀት ዓመት የመጀመሪያው ግማሽ ዓመት ሪፖርት እንደሚያመለክተው፤ በጦርነት ምክንያት የወደሙ ትምህርት ቤቶችን መልሶ ለመገንባት «አዲስ የኢትዮጵያ ትምህርት ቤት» የሚል የትምህርት ቤት ዲዛይን ተዘጋጅቶ እየተሠራ ነው፡፡ በዚህም በጦርነት ከወደሙት 1 ሺህ 335 ትምህርት ቤቶች ውስጥ የተወሰኑትን ሥራ ለማስጀመር ጥረት ተደርጓል፡፡ ሌሎች ትምህርት ቤቶችንም መልሶ ለማደራጀት እና ወደ መማር ማስተማር ሥራው ለማስገባት ከውስጥም ከውጪም ካሉ ባለድርሻዎች ጋር በትብብር እየተሠራ ነው፡፡
ለዚህ አንድ ማሳያ የሚሆነው፣ ትምህርት ሚኒስቴር በጦርነት የወደሙ ትምህርት ቤቶችን መልሶ በመገንባት እና ወደ ሥራ በማስገባት ሂደት ላይ ከየክልል ትምህርት ቢሮዎች ጋር ጥር 2014 ዓ.ም ላይ ባደረገው ውይይት ለመልሶ ግንባታ ሥራው ከ1 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር በላይ መመደቡን ገልጿል፤ ይሄም በተለይ በጦርነቱ ከፍተኛ ጉዳት በደረሰባቸውና ሙሉ በሙሉ የወደሙ በአማራ እና አፋር ክልሎች የሚገኙ 1 ሺህ 93 ትምህርት ቤቶች ግንባታ እንደሚያውለውም አስታውቋል፡፡
ይሁን እንጂ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት በአፋር ክልል ብቻ ከ700 በላይ ትምህርት ቤቶች ተጎድተዋል፤ በአማራ ክልልም ከአራት ሺህ በላይ ትምህርት ቤቶች በጦርነት ቀጣና ውስጥ ነበሩ፡፡ ይሄ ደግሞ ትምህርት ቤቶቹ ጣራና ግድግዳቸው ብቻ ሳይሆን፤ መሠረተ ልማታቸው እና የመማር ማስተማር ቁሳቁሳቸው (ቤተ ሙከራዎች፣ ቤተ መጽሐፍቶች፣ የአይ.ሲ.ቲ ቁሳቁሶች፣ ፕላዝማዎች እና ሌሎችም ቁሳቁሶች) አብረው ለጉዳት ተጋልጠዋል፤ ወድመዋልም፡፡
በትግራይ ክልል ያለውም ጉዳት በተመሳሳይ ደረጃ የሚገለጽ ነው፡፡ በዚህ መልኩ የደረሰው ጉዳት ሲሰላ ደግሞ ለአብነት፣ በአማራ ክልል ብቻ በጦርነቱ የወደሙ ትምህርት ቤቶችን መልሶ ለመገንባት እና ለማደራጀት ከ20 ቢሊዮን ብር በላይ የሚያስፈልግ ስለመሆኑ ነው የተለያዩ መረጃዎች የሚያመለክቱት፡፡
ይሄን መሰል እውነት ለማሳየት በሚል ሦስቱ ክልሎች በተለይም የአማራ ክልል እንደ ዋና ማሳያ ይነሳ እንጂ፤ በአንድም በሌላም ምክንያት በኢትዮጵያ በሁሉም ክልሎችና አካባቢዎች የትምህርት ቤቶች ደረጃ ጉዳይ እጅጉን አሳሳቢ ሁኔታ ላይ ይገኛል፡፡ ከዚህ አኳያ የትምህርት ጥራት ችግሮች መንስኤዎች ዘርፈ ብዙ ቢሆኑም፤ ትምህርት ቤቶች ለመማር ማስተማር ምቹ አለመሆናቸው ከመሠረታዊ ችግሮች አንዱና ዋነኛው ነው። ምክንያቱም ደረጃቸውን ያልጠበቁ ብቻ ሳይሆን ከደረጃ በታች ያሉ ትምህርት ቤቶች በኢትዮጵያ እጅጉን የበዙ ናቸውና ነው፡፡
ለአብነት፣ የትምህርት ሚኒስቴርም ሆነ ሌሎች መንግሥታዊ መረጃዎች እንደሚያመላክቱት፤ በአገራችን ከ49 ሺ በላይ የሚሆኑ ትምህርት ቤቶች ያሉ ሲሆን፤ ከእነዚህ ውስጥ ከ86 በመቶ በላይ የአንደኛና የመካከለኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች እንዲሁም ከ71 በመቶ በላይ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ለመማር ማስተማር አስፈላጊ የሆኑ መሠረተ-ልማቶች በተሟላ ደረጃ ስለሌላቸው ተማሪዎች በተጓደለ የትምህርት ከባቢ ውስጥ እንዲማሩ ተገድደዋል።
ይሄ ደግሞ በእነዚህ ደረጃቸውን ባልጠበቁ ትምህርት ቤቶች ውስጥ የሚማሩ በየደረጃው ያሉ ተማሪዎች የሚጠበቅባቸውን እውቀት፣ ክህሎትና የባህሪ ለውጥ ማምጣት እንዳይችሉ አድርጓቸዋል፡፡ ምክንያቱም እነዚህ ትምህርት ቤቶች መሠረታዊ ለሚባሉት የትምህርት ቤት መሠረተ ልማቶች (ንጹሕ ውሃ፣ መፀዳጃ ክፍሎች፣ በቂ መማሪያ ክፍሎች፣ ወንበር፣ ጠረጴዛ፤ የስፖርት ሜዳ፣ መጻሕፍት፣ የኤሌክትሪክ አገልግሎት፣ ቤተ-መጻሕፍት፣ ቤተ-ሙከራ፣ ወዘተ.) እንኳን ባዕድ የሆኑ ናቸው፡፡
ለምሳሌ፣ በአገሪቱ ካሉት ትምህርት ቤቶች 33 ነጥብ ሁለት በመቶ አንደኛ እና መካከለኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች፤ እንዲሁም 55 ነጥብ 67 በመቶ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ብቻ ናቸው የንጹህ መጠጥ ውሃ አገልግሎት ያላቸው። ከዚህ ውስጥም 21 ነጥብ ሦስት በመቶ በአንደኛ እና መካከለኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች እንዲሁም 49 ነጥብ አንድ በመቶ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች በቀጥታ የቧንቧ ውሃ ተጠቃሚ መሆናቸውን መረጃው ያመላክታል። የተቀሩት ትምህርት ቤቶች ምንም ዓይነት የውሃ አቅርቦት የላቸውም፡፡
በተመሳሳይ መልኩ፣ 37 በመቶ አንደኛ እና መካከለኛ ደረጃ እንዲሁም 43 በመቶ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ብቻ የመፀዳጃ አገልግሎት የሚሰጡ መሆኑን መረጃው ያሳያል። ከኤሌክትሪክ መሠረተ ልማት አቅርቦት ጋር በተያያዘም፤ 29ነጥብ አራት በመቶ አንደኛ እና መካከለኛና 74 ነጥብ አምስት በመቶ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ብቻ ናቸው የኤሌክትሪክ ኃይል ተጠቃሚ የሆኑት። ይህም ትምህርት ቤቶች በቴክኖሎጂ የተደገፈ የ21ኛው ክፍለ ዘመን የትምህርት ክህሎትን እንዲያዳብሩ ለማድረግ የሚሠራውን ሥራ ፈታኝ ያደርገዋል።
ሌላው የትምህርት ቤቶቻችን ችግር የትምህርት ፋሲሊቲና ግብዓቶችን የሚመለከት ሲሆን፤ ከዚህ ቀደም የትምህርት ቤቶችን ቁጥር ከማሳደግ አንፃር የሚያበረታታ ሥራ ተሠርቷል፡፡ ይሁን እንጂ የትምህርት ቤት ቁጥር መጨመር በራሱ የትምህርት ጥራትን ለማሻሻል ያለው አስተዋጽኦ እንደተጠበቀ ሆኖ ትምህርት ቤቶቹ ስታንዳርዱን ጠብቀው እንዲመሠረቱ ከማድረግ አንፃር ሰፊ ክፍተት ያለ በመሆኑ ከግብዓት አንፃር መሠረታዊ የሚባል ክፍተት አለባቸው።
እነዚህ እና መሰል የትምህርት ቤቶች የደረጃ በታች መገለጫ እና የተማሪዎችን እውቀትና ክህሎት ከመገንባት አውድነት የመነጠል ችግር በዚህ መልኩ ከቀጠለ ትውልዱ ላይ ምን ሊፈጠር እንደሚችል መገመት ቀላል አይሆንም። ለዚህ አንዱ ማሳያ ደግሞ በባለፈው ዓመት የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ ፈተና የወሰዱ ተማሪዎች ያስመዘገቡት ውጤት የሚጠቀስ ነው፡፡ በመሆኑም ይሄንን ችግር ለመፍታት እና የትምህርት ቤቶችን ደረጃ ለማሻሻል በመንግሥት አቅጣጫ ተይዞ እየተሠራ ነው፡፡
ይሁን እንጂ ይህን ሥር የሰደደ ችግር በመንግሥት አቅም ብቻ ለመፍታት ቢታሰብ ከሦስት አስርት አመታት ያላነሰ ጊዜ ሊወስድ ይችላል። ይሄንንም መንግሥት የተቀበለው እና በሂደቱ የሕዝብን ተሳትፎ ማረጋገጥ ወሳኝ ሚና እንዳለው ግንዛቤ ተይዟል፡፡ ስለዚህ ይህን ሰፊ ችግር መፍታት የሚቻለው ሥርዓት ዘርግቶ በዘላቂነት የማኅበረሰብና የልዩ ልዩ የትምህርት ባለድርሻ አካላት ቀጥተኛ ተሣትፎን ያማከለ ንቅናቄ በማድረግ እንደሆነም ታምኖበታል።
ከዚህ አንፃር የትምህርት ሚኒስቴር ባቀደው አገር አቀፍ ንቅናቄ መሠረት በየደረጃው ያሉ አመራሮች፣ የአካባቢው ማኅበረሰብ፣ የቀድሞ ተማሪዎች፤ ታዋቂ ግለሰቦች፣ በውጭ አገር የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን፣ ባለሀብቶች፣ ወዘተ. በትውልድ ቦታቸው፣ በተማሩበት ቦታ፣ በሚሠሩባቸውና በሚኖሩባቸው አካባቢ የሚገኙ ትምህርት ቤቶች መሠረተ ልማቶችን ለማሟላት በሚችሉት መንገድና መጠን አስተዋጽኦ በማድረግ አሻራቸውን የሚያሳርፉበት ሁኔታ ስለመመቻቸቱም ነው መረጃዎች የሚጠቁሙት።
የንቅናቄው ዓላማም በየደረጃው ባለው ማኅበረሰብ እና ልዩ ልዩ አካላት ተሳትፎ የትምህርት ቤቶችን መሠረተ-ልማት ለማሻሻል የአሠራር ሥርዓት ተዘርግቶ ሥራው በዘላቂነት እንዲቀጥል፤ እና ማኅበረሰቡ በትምህርት ሥርዓት ውስጥ በመሠረተ-ልማት መሻሻል ሳይወሰን የመማር ማስተማሩን ሂደት በባለቤትነት እንዲደግፍ ማስቻል ነው፡፡ ከዚህ ከፍ ሲልም በየትምህርት ቤቶቹ ያሉ ችግሮችን በመገምገም እና ችግሮችን በቅደም ተከተል በማስቀመጥ ትምህርት ቤቶች ያለባቸውን ክፍተቶች በመፍታት የተማሪዎችን ውጤትና ሥነምግባር ማሻሻል ነው።
ይሄ እውን ይሆን ዘንድ ደግሞ፣ ሁሉም አካል የትምህርት ቤት መሠረተ ልማት ለትምህርት ያለውን ፋይዳ ሊገነዘበው ይገባል፡፡ በዚህ መልኩ ችግሩን መገንዘብ እና ሁሉንም የትምህርት ባለድርሻ አካላት በማስተባበር ችግሮቹን መፍታት ካልተቻለ፤ ትምህርት ቤቶች የተማሪዎች መማሪያ ማዕከል ከመሆን ይልቅ መዋያ ብቻ መሆናቸው አይቀሬ ይሆናሉ። ይህ ደግሞ የትምህርት ሥርዓቱን ምን ያህል እንደጎዳ ቀደም ብሎ እንደተጠቀሰው የ2014 ዓ.ም የተማሪዎችን የ12ኛ ክፍል ፈተና ውጤት ማየት ብቻ በቂ ነው። ስለሆነም የተለያዩ አማራጮችን በመፈተሽ የትምህርት ቤት መሠረተ ልማቶችን በስታንዳርዱ መሠረት ማሟላት ከሁሉም ዜጋ የሚጠበቅ ኃላፊነት ይሆናል።
በዚህ መልኩ የትምህርት ቤቶችን ደረጃ በማሻሻል ረገድ መሠረታዊ ከሚባሉት ከውሃ፣ መብራት፣ መጸዳጃ ቤቶች፣ የኤሌክትሪክ እና ሌሎችም መሠረተ ልማቶች ባሻገር፤ ሦስት መሠረታዊ ጉዳዮችን ማዕከል አድርጎ መስራት ከባለድርሻዎች ከሚጠበቁ ተግባራት አሉ፡፡ ከእነዚህ ሦስት ነጥቦች መካከል አንደኛው፣ ትምህርት ቤቶች በስታንዳርድ መሠረት የተሟላ ቤተ መጻሕፍት እንዲኖራቸው ማድረግ ነው፡፡
ምክንያቱም አብዛኞቹ ትምህርት ቤቶች ደግሞ በግብዓት የተሟላና ስታንዳርዱን የጠበቀ የቤተ መጻሕፍት አገልግሎት የላቸውም። ያላቸውም ቢሆኑ በስታንዳርዱ መሠረት በግብዓት የተሟሉ አይደሉም። ተማሪዎች ደግሞ በክፍል ውስጥ ከሚሰጣቸው ትምህርት በተጨማሪ የተማሩትን ትምህርት በተሻለ ደረጃ እንዲገነዘቡና እንዲመራመሩ በስታንዳርድ መሠረት የተሟላ ቤተ መጻሕፍት ያስፈልጋቸዋልና ይሄንን ማድረግ ከሁሉም ይጠበቃል፡፡
ሁለተኛው ጉዳይ የቤተ-ሙከራ አገልግሎት ሲሆን፤ ይሄም ተማሪዎች በንድፈ ሀሳብ የተማሩትን ትምህርት በተሻለ መልኩ እንዲረዱት ከማገዙም በተጨማሪ የተማሪዎችን የፈጠራ ችሎታ የማገዝ፣ ንድፈ ሀሳቦችን የመገምገምና የመተንተን ችሎታቸውን የሚያበለጽግ ነው፡፡ በትምህርት ቤቶች የቤተ ሙከራ አገልግሎት መኖር ለቀጣይ የትምህርት እርከኖች የተዘጋጁ ተማሪዎች እንዲኖሩ ከማድረግ አንጻር ፋይዳው ከፍተኛ ነው፡፡
በመሆኑም በአንደኛ ደረጃ ትምህርትም ሆነ በሌሎች የትምህርት እርከኖች ስታንዳርድ ውስጥ ለትምህርት እርከኑ አስፈላጊ የሆኑ ቁሳቁሶችን ያሟሉ ቤተ-ሙከራዎች እንዲኖሩ የሚጠበቅ ነው፡፡ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት ግን አስፈላጊውን አገልግሎት ሊሰጡ የሚያስላቸውን ቁሳቁሶች አሟልተው የተገኙ ቤተ-ሙከራዎች ያሏቸው 59 በመቶ አንደኛ እና መካከለኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች፤ እንዲሁም 79 በመቶ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ብቻ እንደመሆናቸው፤ ይሄንን ገጽታ መቀየር የሁሉም ዜጋ ቀጣይ ትኩረት ሊሆን ይገባል፡፡
ሦስተኛው ነጥብ የትምህርት ማበልፀጊያ ማዕከላትን የሚመለከት ሲሆን፤ እነዚህ ማዕከላት መምህራን በሚያስምሩት የትምህርት ዓይነት የትምህርት መርጃ መሣሪያ የሚያዘጋጁበትና ትምህርት ቤቱም ከአካባቢ ቁሳቁስ ከሚሠሩ አጋዥ የመማሪያና ማስተማሪያ ቁሳቁሶች በተጨማሪ የፋብሪካ ምርቶችን በመግዛት የሚያደራጁበት ማዕከል ናቸው፡፡ በመሆኑም መምህራን ከማዕከሉ የትምህርት መርጃ መሣሪያዎችን እየተዋሱ የሚያስተምሩትን ትምህርት ይበልጥ ተጨባጭ በማድረግ የተማሪዎችን የትምህርት አቀባበል ለማሳደግ የሚገለገሉበትን ዕድል መፍጠር ቀጣይ የትውልዱን ዕጣ ፈንታ መወሰን መሆኑን ተገንዝቦ መሥራት ይገባል፡፡
እንደ አጠቃላይ ዛሬ ላይ በአገራችን ያሉ ትምህርት ቤቶች ተማሪዎች ውለው የሚገቡባቸው ስፍራዎች ሳይሆን፤ ተምረው፣ እውቀትና ክህሎት አግኝተው የሚመለሱባቸው ቦታዎች እንዲሆኑ ማድረግ የዛሬ ተግባር መሆኑን መገንዘብ ይገባል፡፡ ይሄ ሲሆን በማኅበረሰብና በልዩ ልዩ አካላት አስተዋጽኦና ጥረት እያደጉ የመጡ መሠረተ ልማታቸውን (ንጹሕ ውሃ፣ መፀዳጃ ክፍሎች፣ በቂ መማሪያ ክፍሎች፣ ወንበር፣ ጠረጴዛ፤ የስፖርት ሜዳ፣ መጻሕፍት፣ የኤሌክትሪክ አገልግሎት፣ ቤተ-መጻሕፍት፣ ቤተ-ሙከራ፣ ወዘተ.) ያሻሻሉ ትምህርት ቤቶች በብዛት እንዲኖሩ ማድረግ ይቻላል፡፡ ይሄ ሲሆን ደግሞ ልጆቻችን ከትምህርት ቤቶች ማግኘት የሚገባቸውን የእውቀት፣ ክህሎት፣ አመለካከትና ሥነምግባራዊ ሰብዕናን ማግኘት ያስችላቸዋል፡፡
በመሆኑም ዛሬ ላይ ከደረጃ በታች ያሉ ትምህርት ቤቶችን ደረጃ በማሻሻል ሂደት የምናስቀምጣት አንዲት ጡብ፤ በነገ የልጆቻችን ዕጣ ፈንታ ላይ የራሳችንን አሻራ የማኖር ኃላፊነታችን መሆኑን አምኖ መቀበል ይኖርብናል። ስለሆነም የትምህርት ቤቶችን ደረጃ በማሻሻል ሂደት የራሳችንን አበርክቶ በማድረግ በነገ የልጆቻችን ዕጣ ፈንታ ላይ የምንወስንበትን አሻራ እናኑር፤ የዕለቱ መልዕክቴ ነው፡፡ አበቃሁ፣ ሰላም፤ ቸር እንሰንብት!::
ማሙሻ ከአቡርሻ
አዲስ ዘመን ሰኔ 13/2015